የአዲስ ኪዳን አከፋፈል

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ኢየሱስ ስንት የአዲስ ኪዳን መጻሕፍትን ጻፈ? ለ) የአዲስ ኪዳን መጻሕፍትን የጻፉ የክርስቶስ ተከታዮችን ስም ዝርዝር።

ኢየሱስ ክርስቶስ አዲስ ኪዳንን አልጻፈም። አዲስ ኪዳን የተጻፈው እርሱ ከዐረገ ከረዥም ጊዜ በኋላ ነበር። ስለዚህ አዲስ ኪዳን የተጻፈው ክርስቶስ ካረገ ከ20 ዓመት በኋላ ነበር። ምናልባትም በ49 ዓም አካባቢ የተጻፈው የመጀመሪያው መጽሐፍ የገላትያ መልእክት ሳይሆን አይቀርም ተብሎ ይገመታል። የመጨረሻው የአዲስ ኪዳን መጽሐፍ የሆነው የዮሐንስ ራእይ የተጻፈው በ95 ዓ.ም. አካባቢ ነበር። ክርስቲያኖች በየስፍራው ተበትነው ይኖሩ ስለ ነበር፥ የእግዚአብሔር እስትንፋሰ የሆኑትን የአዲስ ኪዳን መጻሕፍት ለመለየት ተጨማሪ 200 ዓመት ወስዷል።

የውይይት ጥያቄ፡– ኤር. 31፡31-34፤ ኢዩ. 2፡28-29፣ ሕዝ. 37፡24-28 አንብብ። እግዚአብሔር ስለሚመጣው ለውጥ ለአይሁዶች የገባው ቃል ኪዳን ምን ነበር?

የጥንት ክርስቲያኖች አሁን አዲስ ኪዳን ብለን በምንጠራው ጥራዝ ውስጥ የሚገኙትን መጻሕፍት ካሰባሰቡ በኋላ፥ መጽሐፍ ቅዱስን ለሁለት ከፈሉ። አይሁዶች እንደ እግዚአብሔር ቃል የተቀበሏቸውን የመጀመሪያዎቹን 39 መጻሕፍት ብሉይ ኪዳን ብለው ሰየሟቸው። (በክርስቶስ ዘመን የነበሩ አብዛኛዎቹ አይሁዶች 39ኙም የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት የእግዚአብሔር ቃል መሆናቸውን ያምኑ ነበር። የዚህ ስብስብ ስምምነት ተግባራዊ የሆነው በ100 ዓ.ም. አካባቢ በተደረገው የአይሁድ ሸንጎ ነበር።) ክርስቲያኖች ከአይሁዶች ጋር በመስማማት እነዚህ መጻሕፍት የእግዚአብሔር ቃል መሆናቸውን ተቀበሉ። ይህም ሆኖ፥ የክርስቶስ መምጣት ለውጥ እንዳስከተለ ያውቁ ነበር። ኤርምያስ፥ ኢሳይያስና ሌሎችም ነቢያት የተነበዩለት አዲስ ኪዳን፥ በክርስቶስ ሞት ተጀመረ። ስለሆነም ክርስቲያኖች ከክርስቶስ በፊት የተጻፉትን መጻሕፍት «ብሉይ ኪዳን» ብለው ጠሯቸው። ይህም እነዚህ መጻሕፍት ከክርስቶስ በፊት እግዚአብሔር ይሠራ የነበረበትን ሁኔታ የሚገልጹ መሆናቸውን እንዳመኑ ያሳያል። ነገር ግን ክርስቶስ በመምጣቱና በመስቀል ላይ በመሞቱ አዲስ የታሪክ ምዕራፍ ተከፍቷል። ክርስቶስ ደሙ አዲስ ኪዳን» እንደሆነ ገልጾላቸው ነበር (ሉቃስ 22፡20)። በዚህ ጊዜ እግዚአብሔር በአይሁዶች ላይ ብቻ ማተኮሩን ትቶ ለአሕዛብ ሁሉ ዕቅዱን በመፈጸም ላይ ነበር። በመሆኑም የጥንት ክርስቲያኖች 27 መጻሕፍት የሚገኙበትን ሁለተኛውን የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል አዲስ ኪዳን ብለው ጠሩት።

የውይይት ጥያቄ፡- የአዲስ ኪዳን መጻሕፍትን በቅደም ተከተል ዘርዝራቸው።

የጥንት ቤተ ክርስቲያን መሪዎች የአዲስ ኪዳን መጻሕፍትን ሲያሰባስቡ፥ ዝርዝራቸውን በጊዜ ቅደም ተከተል አላዘጋጁም ነበር። ነገር ግን በአምስት ዐበይት ምድቦች ከፍለዋቸው ነበር።

የመጀመሪያው ምድብ ወንጌላትን ያካትታል። እነዚህ በተለያዩ ደራሲያን የተጻፉ አራት መጻሕፍት፥ ስለ ክርስቶስ ሕይወትና ሞት ይተርካሉ።

ሁለተኛው ምድብ የሐዋርያት ሥራ ነው። ይህ ታሪካዊ ዘገባ፥ የጥንቷ ቤተ ክርስቲያን ከኢየሩሳሌም ወደ ሮም መስፋፋቷን ያብራራል (ከ30 እስከ 40 ዓ.ም.)።

አብዛኛዎቹ መጻሕፍት የሚገኙት በሦስተኛው ምድብ ውስጥ ነው። እነዚህም በሐዋርያው ጳውሎስ የተጻፉ መልእክቶች ናቸው። እነዚህ በጊዜ ቅደም ተከተል የተዘረዘሩ ሳይሆኑ፥ ከረዥሙና በጣም አስፈላጊ (ሮሜ፥ 1ኛ ቆሮንቶስ) ከሆነው ወደ አጭሩ የፊልሞና መልእክት የሚያመሩ ናቸው። እነዚህም የጳውሎስ መልእክቶች በመባል የሚታወቁ ሲሆኑ፥ ለተወሰኑ አብያተ ክርስቲያናት ወይም ግለሰቦች የተላኩ ናቸው። እነዚህ መልእክቶች ሐዋርያው ጳውሎስ ስለተወሰኑ ጉዳዮች የሰጣቸውን ምክሮችና ትምህርቶች የሚያካትቱ ናቸው።

(ማስታወሻ፡- በቀድሞይቱ ቤተ ክርስቲያን የዕብራውያን መልእክት ጸሐፊ ማንነት ለረዥም ጊዜ ሲያከራክር ቆይቷል። አንዳንዶች ጸሐፊው ጳውሎስ እንደሆነ ያምናሉ። ይህም በአማርኛው የመጽሐፍ ቅዱስ ርእስ ላይ ተንጸባርቋል። ሌሎች ምሑራን ደግሞ ሌላ ሰው እንደ ጻፈው ይገምታሉ። በግሪኩ ቅጂ ላይ መልእክቱ ስለ ደራሲው ማንነት አይናገርም። የዕብራውያን መልእክት በጳውሎስ መጻፉ ስላልተረጋገጠ በቀጣይ የአዲስ ኪዳን ምድብ ውስጥ እንዲገባ ተደርጓል።)

አራተኛው ምድብ እንደ ጴጥሮስ፥ ያዕቆብ (የክርስቶስ ወንድምና) ሐዋርያው ዮሐንስ በመሳሰሉት የተለያዩ ደራሲያን የተጻፉትን መልእክቶች ያጠቃልላል። እነዚህ መልእክቶች ለአንድ ግለሰብ ወይም ቤተ ክርስቲያን ሳይሆን፥ ለሁሉም ክርስቲያኖች የተጻፉ በመሆናቸው ምሑራን አጠቃላይ መልእክቶች በማለት ይጠሯቸዋል። በዚህ ክፍል ውስጥ ስምንት መጻሕፍት ሲኖሩ፥ እነርሱም ከዕብራውያን እስከ ይሁዳ ያሉት ናቸው። እነዚህ መልእክቶች የተጻፉት ጠለቅ ያሉ ትምህርታዊ ትንታኔዎችን ለመስጠት ሳይሆን፥ ብዙ አብያተ ክርስቲያናት የሚያጋጥሟቸውን ችግሮች ለማመልከት ነው።

በአምስተኛው ምድብ ውስጥ የሚገኘው የዮሐንስ ራእይ ነው። ክርስቲያኖች ይህ መጽሐፍ እግዚአብሔር የዘላለምን መንግሥት ለመመሥረት የወጠነውን አጠቃላይ ዕቅድ የሚያመለክት የመጨረሻው የእስትንፋሰ-እግዚአብሔራዊ ጽሑፍ እንደሆነ ስለ ተንዘቡ፥ በመጨረሻ ላይ አስገብተውታል፡፡ ሐዋርያው ዮሐንስ ይህ የመጨረሻ የእስትንፋሰ እግዚአብሔር መጽሐፍ መሆኑን ስለተገነዘበ የሚከተለውን ጽፎአል። «በዚህ መጽሐፍ የተጻፈውን የትንቢት ቃል ለሚሰማ ሁሉ እኔ እመሰክራለሁ፤ ማንም በዚህ ላይ አንዳች ቢጨምር እግዚአብሔር በዚህ መጽሐፍ የተጻፉትን መቅሠፍቶች ይጨምርበታል፤ ማንምም በዚህ በትንቢት መጽሐፍ ከተጻፉት ቃሎች አንዳች ቢያጎድል፥ በዚህ መጽሐፍ ከተጻፉት ከሕይወት ዛፍና ከቅድስቲቱ ከተማ እግዚአብሔር ዕድሉን ያጎድልበታል» (ራእይ 22፡18-19)፡ ምንም እንኳ ዮሐንስ ይህንን ማስጠንቀቂያ የሰጠው ስለ ራሱ መጽሐፍ ቢሆንም፥ የጥንት ክርስቲያኖች ማስጠንቀቂያው ለአዲስ ኪዳን በሙሉ የሚሠራ መሆኑን ተገንዝበው ነበር። በዚህ መጽሐፍ እግዚአብሔር እንዲጻፍ የፈለገው ሁሉ ተጽፎአል።

በ66ቱ መጻሕፍት ውስጥ እግዚአብሔር ይበልጥ እንዲያብራራልን የምንፈልጋቸው ብዙ ነገሮች ቢኖሩም፥ እግዚአብሔር ሰዎች ከእርሱ ጋር ለመዛመድ የሚፈልጓቸውን ነገርች ሁሉ አመልክቷል። ለዚህም ነው ሌሎች መጻሕፍትንና የመጽሐፍ ቅዱስ ማብራሪያዎችን ከመጽሐፍ ቅዱስ እኩል መቁጠር አደገኛ የሚሆነው። እስትንፋሰ እግዚአብሔር የሆነ መጽሐፍ፥ መጽሐፍ ቅዱስ ብቻ ነው። ለጥያቄዎቻችን ሁሉ መልስ መፈለግ የሚገባንም ከመጽሐፍ ቅዱስ ብቻ ነው።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) 2ኛ ጢሞ. 3፡16–17፤ 2ኛ ጴጥ. 1፡20-21 እንብብ። እነዚህ ጥቅሶች በእስትንፋሰ-እግዚአብሔር ስለተጻፈው ቃል ምን ያስተምራሉ? ለ) ብዙ ክርስቲያኖች እውነትን ለማወቅ ሌሎች መጻሕፍትን ወይም ሕልሞችን ዋና ምንጭ አድርገው ለመጠቀም የሚፈተኑባቸውን መንገዶች ግለጽ። ሐ) ይህ አደገኛ የሚሆነው ለምንድን ነው?

አዲስ ኪዳን እንደ ብሉይ ኪዳን በአንድ ሰው የተጻፈ አይደለም። ነገር ግን መንፈስ ቅዱስ፥ በሁሉም ዘመን የምትኖረው ቤተ ክርስቲያን የምትፈልገውን መልእክት ለመጻፍ የተለያዩ ሰዎችን መርጦ በልባቸውና በአእምሯቸው ውስጥ ተግባሩን አከናውኗል። አዲስ ኪዳንን የጻፉት ማቴዎስ፥ ማርቆስ፥ ሉቃስ፥ ዮሐንስ፥ ጴጥሮስ፥ ያዕቆብ፥ ይሁዳ፥ ጳውሎስና ያልታወቀው የዕብራውያን ጻሐፊ ናቸው። አዲስ ኪዳን የተጻፈበት ዘመን ቅደም ተከተል

ብሉይ ኪዳን የተጻፈው በ1000 ዓመታት ጊዜ ውስጥ (1400-400 ዓ.ዓ) ሲሆን፥ አዲስ ኪዳን የተጻፈው ደግሞ በ50 ዓመታት ጊዜ ውስጥ ነው (48– 100 ዓም)። ምንም እንኳ ምሑራን አንዳንድ መጻሕፍት የተጻፉባቸውን ትክክለኛ ጊዜ ባያውቁም፥ በሐዋርያት ሥራ ውስጥ ከተፈጸሙት ድርጊቶች ጋር በማነጻጸር መሠረታዊ ግምቶችን ለመስጠት ችለዋል። እነዚህ በሐዋርያት ሥራ ውስጥ የሚገኙ ድርጊቶች ደግሞ በዓለም ታሪክ ከተፈጸሙት ድርጊቶች ጋር ይነጻጸራሉ። ከዚህ በታች ስለ አዲስ ኪዳን መጻሕፍት የጊዜ ቅደም ተከተል የተሰጠውን ሠንጠረዥ አጥና። መጻሕፍቱ የተጻፉባቸውን ዓመታትና የተፈጸሙትን ክስተቶች አስተውለህ አጥና።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) የአዲስ ኪዳን መጻሕፍትን አሁን ባሉበት ቅደም ተከተል ዘርዝር። የመጻሕፍቱን ሙሉ መጠሪያ ጻፍ።

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ ስለዚህ አስደናቂ አገልግሎታቸው እግዚአብሔር ይባርካቸው፡፡)

1 thought on “የአዲስ ኪዳን አከፋፈል”

  1. መፅሐፍ ቅዱስን በአግባቡ ለማጥናት ጠቃሚ ማብራሪያ ስለሚሰጥ ወድጄዋለሁ ተባረኩ

Leave a Reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading