ሉቃስ 17፡1-37

  1. እንደ ኢየሱስ ተከታዮች እንዴት መኖርና ማሰብ እንደሚገባ የሚያሳዩ ትምህርቶች (ሉቃስ 17፡1-10)

ሀ. ደቀ መዛሙርት የማሰናከያ ዓለት ሆነው ሰዎችን ለኃጢአት እንዳይዳርጉ መጠንቀቅ አለባቸው። የኢየሱስ ተከታዮች ኃጢአት መሥራታቸው የማይቀር ጉዳይ ነው። ኃጢአትን እንድናደርግ የሚፈትኑን ብዙ ፈተናዎች አሉ። ይህ ግን አንድ ሰው በተለይም የቤተ ክርስቲያን መሪ በግድየለሽነት እንዲኖርና ሌላውን ሰው ወደ ኃጢአት እንዲመራ ወይም ሌላውን ሰው በኃጢአት እንዲፈትን ማመኻኛ አይሆነውም። ኢየሱስ የዚህን ድርጊት ስሕተት ለማሳየት ሲል ደቀ መዛሙርቱ ፈሪሃ እግዚአብሔር እንዲያድርባቸውና ሰዎች ሁሉ በእግዚአብሔር ፊት ንጹሓን ይሆኑ ዘንድ እንዲያግዙ በብርቱ ቃል ያስጠነቅቃቸዋል።

ለ. ደቀ መዛሙርት ስለ ሌሎች አማኞች ግድ ሊላቸውና ኃጢአት በሚሠሩበት ጊዜ፥ ወቅሰው እግዚአብሔርን ወደ መታዘዝ ሊመልሷቸው ይገባል።

ሐ. ደቀ መዛሙርት ሁልጊዜ ፈጥነው ይቅር ማለት አለባቸው። ቂም መያዝ የለባቸውም። አንድ ሰው ደጋግሞ ቢበድላቸው ይቅር ከማለት ወደ ኋላ ማለት የለባቸውም።

መ. ዋናው ጉዳይ የኢየሱስ ተከታዮች ተጨማሪ እምነት ማግኘታቸው ሳይሆን፣ እምነታቸውን በሥራ ላይ ማዋላቸው ነው። ታላቁ አምላካችን ትንሹን እምነታችንን በመጠቀም ለእርሱ ክብር እንድናውለው መጠየቅ ይገባል። ኢየሱስ የሚፈልገው ዐይነት ደቀ መዝሙር ሆኖ ለመኖር ከባድ ነው። ነገር ግን የእምነት ዐይናችንን በእርሱ ላይ ካኖርን፣ ታላላቅ ነገሮችን እንድናደርግ ያስችለናል።

ሠ. ኢየሱስ ጌታ ሲሆን፣ ደቀ መዛሙርቱ ደግሞ ባሪያዎቹ ናቸው። ይህ ወደ ሁለት የተሳሳቱ አመለካከቶች ሊመራን ይችላል። አንደኛው፥ አንዳንድ ሰዎች በትዕቢት፣ «እኔ የኢየሱስ ተከታይ ነኝ። እናም ከአንተ እሻላለሁ። ለኢየሱስ ያደረግኋቸውን ነገሮች ተመልከት ሊሉ ይችላሉ። ሁለተኛው፣ ጥቅምን ለማግኘት ሆን ብሎ የመሥራት አደጋ ሊያጋጥም ይችላል። «ኢየሱስ የበለጠ ስለሚሰጠኝ ለድሆች መስጠት አለብኝ። ሽልማት ስለማገኝበት ኢየሱስን አገለግለዋለሁ።» ኢየሱስ ላደረግንለት አገልግሎት እንደሚሸልመን ጥርጥር የለውም። ይህ ማለት ግን ዋጋ ለማግኘት ስንል መሥራት አለብን ማለት አይደለም። በሥራ ሲጣደፍ የደከመ ባሪያ ጌታው ከመብላቱ በፊት ምግብ አይቀርብለትም። አንድ ጌታም ባሪያው ኃላፊነቱን ስለተወጣ ለማመስገን ኃላፊነት የለበትም። ልክ እንዲሁ፣ እኛም ለክርስቶስ ባደረግንለት ነገር ከመመካት ይልቅ፥ የባሪያን ትሕትና ልንላበስ ይገባል። የድርሻችንን ብቻ እንደተወጣን በትሕትና ልንገነዘብ ይገባል። እግዚአብሔርን የምናገለግለው ምስጋናውን ወይም ጥቅም በመፈለግ መሆን የለበትም።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) አንዳንድ ጊዜ፣ «ለእግዚአብሔር ብትሰጥ እርሱ ብዙ ይሰጥሃል። እግዚአብሔር ያንተ ባለ ዕዳ አይደለም» የሚሉ አሳቦችን እንሰማለን። ሉቃስ 17፡1-10 ካነበብክ በኋላ ለዚህ አባባል ምን ዐይነት መልስ ትሰጣለህ? ለ) ኢየሱስን በምናገለግልበት ጊዜ ምን ዐይነት አመለካከት ሊኖረን ይገባል? የራስ ወዳድነት አሳቦች የትኞቹ ናቸው? ኢየሱስን ለማክበር የልባችንን ምስጋና የሚያሳዩትስ የትኞቹ ናቸው?

  1. ኢየሱስን ያመሰገነው ለምጻም (ሉቃስ 17፡11-19)

ራስ ወዳድነት በሁላችንም ዘንድ የሚገኝ ችግር ነው። እግዚአብሔር አንድ መልካም ነገር ካደረገልን በኋላ እንኳ ለማመስገን ይከብደናል። ይህንን ለማረጋገጥ ጸሎታችን ምን እንደሚመስል ማጤኑ በቂ ነው። የተለያዩ ነገሮችን ለመጠየቅና ምስጋና ለማቅረብ ከምንጠቀምባቸው ቃላት የትኞቹ ይበዛሉ? ሉቃስ የኢየሱስ ተከታዮች የምስጋና ልብ ሊኖራቸው እንደሚገባ ያስተምራል። ይህንን አሳብ ለማስተማር ኢየሱስ 9 አይሁዶችና 1 ሳምራዊ ያለበትን የለምጻሞች ቡድን ስለፈወሰበት አጋጣሚ ተርኳል። የሚገርመው ከተፈወሰ በኋላ ወደ ኢየሱስ ተመልሶ ምስጋናውን ያቀረበው ሳምራዊው ብቻ ነበር። በእግዚአብሔር ቤት ረዥም ጊዜ የኖርን ሰዎች የአመስጋኝነት ልብ ሊኖረን እንደሚገባ መገንዘብ አለብን። ብዙውን ጊዜ እግዚአብሔር እንደሚባርከን እያሰብን ለማመስገን ግን አንፈልግም። እንደ ጥንቶቹ እስራኤላውያን ነገሮች እንደጠበቅናቸው ሳይሆኑ ሲቀሩ፥ ፈጥነን እናጉረመርማለን።

የውይይት ጥያቄ፡- ኢየሱስን እንድታመሰግን የሚያደርጉህን አሥር ነገሮች ዝርዝር። በጸሎትህ የተለያዩ ነገሮችን እንዲያደርግልህ ከመጠየቅ ይልቅ ያደረገልህን ነገር እየዘረዘርህ ማመስገንን ተለማመድ።

  1. ኢየሱስ ስለ መጭው የእግዚአብሔር መንግሥት ያቀረበው ትምህርት (ሉቃስ 17፡20-37)

አዲስ ኪዳን «የእግዚአብሔር መንግሥት» የሚለውን ሐረግ የሚጠቀመው በሁለት ዐበይት መንገዶች ነው። አንደኛው፥ ኢየሱስ ክርስቶስ የጀመረው መንፈሳዊ መንግሥት አለ። ኢየሱስ እንደ ንጉሥ በሰዎች ሕይወት ወይም በቤተ ክርስቲያን ውስጥ በሚነግሥበት ጊዜ ሁሉ፥ የእግዚአብሔር መንግሥት በዚያ ይገኛል። ሁለተኛው፣ ይበልጥ ሙሉ የሆነና የሚታይ የእግዚአብሔር መንግሥት እንድ ቀን ይመጣል። ይህ የሚታይ መንግሥት የሚመጣው የኢየሱስ አገዛዝ በዓለም ሁሉና በሰዎች ሁሉ ላይ በሚገለጽበት ጊዜ ይሆናል።

ፈሪሳውያን ስለዚያ የሚታይ መንግሥት ኢየሱስን ጠይቀውታል። ኢየሱስ ግን ትኩረታቸውን በእርሱ መምጣት በተጀመረው መንፈሳዊ መንግሥት ላይ አድርጓል። ኢየሱስ በመካከላቸው ያለው መንግሥት በመጨረሻው ዘመን ስለሚመጣው መንግሥት ከማሰብ እንደሚበልጥ በመግለጽ አስጠንቅቋቸዋል። ንጉሡ ኢየሱስ በዚያ ነበር። እርሱን ምን ማድረግ ነበረባቸው? ፈሪሳውያን ታላቅና የሚታይ መንግሥት ከመጠባበቅ ይልቅ ኢየሱስ ላመጣው ስውር መንፈሳዊ መንግሥት ትኩረት መስጠት ነበረባቸው። ይሁንና ኢየሱስ ለደቀ መዛሙርቱ ዘላለማዊና የሚታይ የእግዚአብሔር መንግሥት መቼ እንደሚመጣ የሚለዩባቸውን አንዳንድ ምልክቶች ሰጥቷል።

ሀ. ደቀ መዛሙርቱ ኢየሱስን እንደ ድል አድራጊ ንጉሥ ተመልሶ ሲመጣ ለመመልከት ፈልገው ነበር። ነገር ግን ይህ እነርሱ በፈለጉበት ጊዜ የሚሆን አልነበረም። ይህ ከመሆኑ በፊት ኢየሱስ መከራ መቀበልና መሞት ነበረበት።

ለ. የመብረቅ መምጫ እንደማይታወቅ ሁሉ የኢየሱስም መምጫ ቅጽበታዊና የማይጠበቅ ይሆናል። የኢየሱስ ተከታዮች መሢሕ ነን የሚሉትን ለመቀበል መጣደፍ አልነበረባቸውም።

ሐ. ኢየሱስ ክርስቶስ ዳግም ተመልሶ በሚመጣበት ጊዜ ሰዎች በመብላት፣ በመጠጣትና በመጋባት የተለመደ የሕይወት ዘይቤ ይከተላሉ። የመምጫው ጊዜ በኖኅ ዘመን እንደተከሰተው ጎርፍ ወይም በሎጥ ዘመን በሰዶምና በገሞራ ላይ እንደተከሰተው አደጋ ቅጽበታው ይሆናል።

መ. የኢየሱስ መምጫ በጣም ቅጽበታዊ ስለሚሆን፣ ደቀ መዛሙርቱ ስለ ቁሳዊ ሀብት መጨነቅ የለባቸውም። ሁሉንም ትተው መሸሽ ነበረባቸው። የኢየሱስ ተከታዮች ቁሳዊ ሀብቷን ለመመልከት ወደ ኋላ እንደተመለሰችው የሎጥ ሚስት መሆን የለባቸውም። (ማስታወሻ፡ የጥንት ቤቶች ጣሪያቸው ዝርግ ነበር፤ በሙቀት ጊዜ ሰዎች አየር ለማግኘት ወደዚያ ይወጡ ነበር። የመውጫ ደረጃዎቹ ከቤቱ ውጭ ስለነባር ኢየሱስ ንብረቶቻቸውን ለመውሰድ ወደ ቤቱ መግባት እንደሌለባቸው ይናገራል።) በምድራዊ ነገሮች ላይ የሙጥኝ የሚሉ ደቀ መዛሙርት ሕይወታቸውን ያጣሉ።

ሠ. የመጨረሻው ዘመን መከፋፈልን ያመጣል። የቅርብ ጓደኛሞች ወይም የአንድ ቤተሰብ አባላት መሆን ብቻ በቂ አይደለም። እግዚአብሔርን የሚወዱ ሰዎች ወደ ዘላለማዊ ስፍራቸው ሲወሰዱ፣ የቀሩት – ግን የእግዚአብሔርን ቁጣ ይቀበላሉ።

ረ. ኢየሱስ የሚመለስበትን ስፍራ «አሞራዎች» ያመለክታሉ። ይህ ለመረዳት የሚያስቸግረን የኢየሱስ አባባል ምናልባትም አይሁዶች ሲጠቀሙበት የነበረ ምሳሌያዊ አነጋገር ሳይሆን አይቀርም። የአንድ አሞራ ማንዣበብ አንድ ነገር እንደ ሞተ ለማመልከት በቂ እንዳልሆነና በተመሳሳይ ሁኔታ፣ ስለመመለሱ ከተነገሩት ምልክቶች አንዱ ብቻ መታየቱ በቂ እንዳልሆነ ለማመልከት የፈለገ ይመስላል። ነገር ግን ኢየሱስ የሰጣቸው ምልክቶች ሁሉ በሚፈጸሙበት ጊዜ የመምጫው ጊዜ እንደ ደረሰ እንገነዘባለን።

የውይይት ጥያቄ፡- ብዙ ክርስቲያኖች ኢየሱስ በቶሎ ይመለሳል ብለው ያስባሉ። ሀ) በዘመናችን ኢየሱስ ከሰጣቸው ምልክቶች የትኞቹ በመፈጸም ላይ ናቸው? ለ) እስካሁን ያልታዩት ምልክቶች የትኞቹ ናቸው?

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

2 thoughts on “ሉቃስ 17፡1-37”

    1. ትምሕርቶቻችንን በግልህ ማግኘትን በተመለከተ የተሻለውና ፈጣኑ መንገድ የሚከተለው እንደሆነ እናምናለን፡፡ ትምሕርቶቻችን ሁሉ በሚከተለው ዌብ ሳይታችን ላይ ይገኛሉ (https://ethiopiansite.com/)፡፡ እነዚህን ትምሕርቶች ሁሉ ፕሪንት ማድረግም ሆነ ኮፒ አድርጎ መጠቀም ይቻለል፡፡ ፕሪንት ለማድረግ የምትሻ ከሆነ የትምሕርቱ መጨረሻ ወይም ግርጌ ላይ በመሄድ “More” የሚለውን ስትጫን፣ ፕሪንት የሚለውን አማራጭ ማግኘት ትችላለህ፡፡ እግዚአብሔር ይባርክህ፡፡

Leave a Reply to dingetegnaCancel reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading