ሉቃስ 18፡1-43

ሙላቱ የአንዲት ፍሬያማ ቤተ ክርስቲያን መሪ ነበር። ለብዙ ዓመታት ክርስቲያን ሆኖ ስለኖረ ከመዳኑ በፊት፡ ኃጢአት በሕይወቱ ውስጥ የነበረውን ኃይል ዘንግቷል። ስለሆነም ክርስቲያኖች በኃጢአት በሚወድቁበት ጊዜ ትዕግሥት በማጣት በብርቱ ቃላት ይገሥጻቸዋል። ገና ከኃጢአት እስራት ላልወጡት ዓለማውያንም ትዕግሥት የለውም። «ሁሉም ሰው ለምን እንደ እኔ አይሆንም? የጽድቅ ኑሮን የማይኖሩት ለምንድን ነው? እኔ በቤተ ክርስቲያኔ ውስጥ ካሉት አብዛኞቹ ሰዎች እሻላለሁ። እርግጠኛ ነኝ እግዚአብሔር በእኔ ሕይወት ኩራት ይሰማዋል» እያለ ያስባል።

የውይይት ጥያቄ፡- ለክርስቲያኖች በሕይወታቸው ትዕቢት የሚሰማቸውና እንደ እነርሱ ያልሆኑትን ሌሎች ሰዎች መናቅ የሚቀናቸው ለምንድን ነው?

በክርስትና ሕይወታችን ረዥም ዘመን ያስቆጠርነውን ሰዎች ሰይጣን ሊያሸንፍ ከሚችልባቸው አደገኛ መንገዶች አንዱ፥ በጽድቃችን እንድንመካ በማድረግ ነው። ራሳችንን በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ከሚገኙት ሌሎች ሰዎች ጋር ማነጻጸር እንጀምርና የተሻልን ነን ብለን እናስባለን። ከዚያም መታበይ እንጀምራለን። ፈሪሳውያን እንደዚህ ዐይነት አመለካከት ነበራቸው። ራሳቸውን ኃጢአተኞች ናቸው ብለው ከሚቆጥሯቸው እንደ ቀራጮች ካሉት ሰዎች ጋር ያነጻጽሩና፣ «እግዚአብሔር በእኔ ሕይወት ኩራት ሳይሰማው አይቀርም። ብለው ያስባሉ። ነገር ግን ራሳችንን ማነጻጸር ያለብን ከእግዚአብሔር የጽድቅ መመዘኛ እንጂ፥ ከሌሎች ሰዎች ጋር ሊሆን አይገባም። ይህንን በምናደርግበት ጊዜ ምን ያህል ኃጢአተኞች እንደሆንን ይገባናል። አሁንም የኃጢአት ! ተፈጥሮ ስላለን፣ አስተሳሰባችን የራስ ወዳድነት፣ ለሌሎች ሰዎች ያለን አመለካከት ኢየሱስ እንዲኖረን የሚፈልገው ዐይነት ፍቅር አይደለም። ስለሆነም ራሳችንን ከእግዚአብሔር ጋር በምናነጻጽርበት ጊዜ፣ ከእግዚአብሔር ሳይሆን ከምንንቃቸው ጋለሞታዎች ጋር የሚቀራረብ ሕይወት እንዳለን እንገነዘባለን። ሁላችንም የእግዚአብሔር ምሕረት ያስፈልገናል። ልባችን በኃጢአታችን ሊሰበርና የእግዚአብሔርን ምሕረት ልንለምን ይገባል። ገና ከኃጢአት ጋር በመታገል ላይ ላሉትም ምሕረትን ልናደርግላቸው ይገባል። ለ40 ዓመት ክርስቲያን ሆኖ የኖረውና በቤተ ክርስቲያን መሪነት የሚያገለግለው የ60 ዓመቱ ሙላቱም እንደ ሌሎች ማንኛውም ሰዎች አሁንም ከኃጢአት ጋር እየታገለ ነው። ሁላችንም በመስቀሉ ፊት እኩል ነን። ሁላችንም የእግዚአብሔር ምሕረት የሚያስፈልገን ኃጢአተኞች ነን።

ኢየሱስ በይሁዳና በጴሪያ ሲያገለግል ቆይቷል፤ አሁን የምድር አገልግሎቱ በመጠናቀቅ ላይ ነው። ወደ ኢየሩሳሌም ሲቃረብ በቅርብ ቀን እንደሚሞት ያውቅ ነበር። በመጨረሻዎቹ ጥቂት ቀናት ኢየሱስ ለደቀ መዛሙርቱ እርሱን መከተል ምን እንደሆነ በማስተማር፣ ስለሚገጥማቸውም ፈተና አስጠንቅቋቸዋል።

  1. ኢየሱስ በጸሎት ስለ መትጋት አስተማረ (ሉቃስ 18፡1-8)

እግዚአብሔር ሁልጊዜ ጸሎትን ይመልሳል? አዎን። ነገር ግን አንዳንድ ጊዜ የሚመልሰው እኛ በምንጠብቀው መንገድ ላይሆን ይችላል። አንዳንድ ጊዜ በፍጥነት አዎንታዊ ምላሽ ሲሰጥ፣ ሌላ ጊዜ ግን «ጠብቅ» ይለናል። «የለም፣ እኔ ለአንተ የምፈልገው እንደዚህ ዐይነት ነገር አይደለም» የሚልበትም ጊዜ አለ። እኛ ግን ከእግዚአብሔር አፍ ለመስማት የምንፈልገው «እሺ፣ አደርግልሃለሁ» የሚለውን እንጂ፥ «አይሆንም» የሚለውን አይደለም። ነገር ግን ጳውሎስም እንኳ «መውጊያው» ከሥጋው እንዲነሣላት በጠየቀ ጊዜ የ«አይሆንም» መልስ ተሰጥቶታል (2ኛ ቆሮ. 12፡7-10)። አንዳንድ ጊዜ እግዚአብሔር «ጠብቅ» የሚል መልስ ይሰጠናል። ወይም ዝም ይላል። በዚህ ጊዜ ምን ማድረግ ይኖርብናል? ኢየሱስ ደቀ መዛሙርቱ ሳያቋርጡ ተግተው እንዲጸልዩ ነግሯቸዋል። ፍትሕ የማያውቀው ዳኛ በሴቲቱ ንዝነዛ ምክንያት ትክክል ከፈረደ፣ የሚወደንና ፍትሕን የሚወደው አምላካችን እግዚአብሔር ጸሎታችንን ምንኛ በጊዜ አሳምሮ ይመልስልን ይሆን? (ማስታወሻ፡ ኢየሱስ እግዚአብሔር አብ እንደ ዐመፀኛው ዳኛ ደጋግመን በጸሎት ልንጠይቀው የሚገባን መሆኑን እየተናገረ አይደለም። ይልቁንም በአፍቃሪ አባትና በዐመፀኛ ዳኛ መካከል ያለውን ልዩነት እያሳየ ነበር።)

የትምህርቱ አውድ የፍትሕ አስፈላጊነት ነው። ብዙውን ጊዜ የኢየሱስ ተከታዮች በኢ-ፍትሐዊ ዳኞች ይበደላሉ። እንዲያውም በዚህ ክፍለ ዘመን ብቻ ካለፉት ሌሎች ክፍለ ዘመናት ሁሉ በላይ ብዙ ክርስቲያኖች ለእምነታቸው ሞተዋል። በዚህ ዓይነት ሁኔታ ውስጥ ክርስቲያኖች ምን ማድረግ ይኖርባቸዋል? መበቀልና መዋጋት ያስፈልገናል? አያስፈልግም። እምነታችንን መተው አለብን? የለብንም። ልባችንን በእግዚአብሔር ፊት አፍስሰን ልንጸልይና ፍትሕን እንደሚያመጣ ልንተማመንበት ይገባል። አንድ ጊዜ ብቻ ሳይሆን እግዚአብሔር በራሱ ጊዜ መልስ እስኪሰጠን ድረስ ደጋግመን መጸለይ አለብን። እግዚአብሔር በምንፈልገው መንገድ መልስ ሳይሰጠን ሲቀር እምነታችንን ለመተው ልንፈተን እንችላለን። ኢየሱስ ዳግም ሊመለስ ሲል ከበፊቱ የከፋ ስደት ይነሣል። ያን ጊዜ ብዙዎች ኢየሱስን በመከተል የሚከፈለውን ዋጋ ለመክፈል ፈቃደኛች አይሆኑም። ኢየሱስ በሚመለስበት ጊዜ እምነትን በምድር ላይ አገኝ ይሆን? በማለት የጠየቀው ለዚህ ነው። ጌታ በሚመለስበት ጊዜ በእምነት የሚመላለሱትን ሰዎች እንደሚያገኝ ባያጠራጥርም፣ በዚያን ጊዜ የኢየሱስ ተከታዮች በእርሱ ለመጽናት ከፍተኛ ዋጋ ይከፍላሉ።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ኢየሱስ ጸሎትህን ወዲያውኑ የመለሰበትን ጊዜ አስታውሰህ ጻፍ። ለ) «አይሆንም» የሚል መልስ የሰጠህን ጊዜ ጻፍ። ሐ) «ጠብቅ» ካለህ በኋላ በራሱ ጊዜ የሚያስፈልግህን ነገር ስላደረገልህ ጊዜ ምሳሌ ስጥ። መ) ይህ ሳያቋርጡ ስለ መጸለይና ስለ ትሕትና ምን ያስተምረናል?

  1. ኢየሱስ እግዚአብሔር ምሕረትን ለሚፈልጉ ሰዎች እንደሚሰጣቸው አስተማረ (ሉቃስ 18፡9-14)

የሃይማኖት መሪዎች ራሳቸውን ከሌሎች ሰዎች ጋር በሚያነጻጽሩበት ጊዜ መንፈሳዊ ኩራት ይሰማቸዋል። ይህ በፈሪሳውያን ሕይወት የታየ ሲሆን፣ በዚህም ዘመን የምንመለከተው ነው። ኢየሱስ በኃጢአቱ ተጸጽቶ በእግዚአብሔር ምሕረት ላይ ስለ ተደገፈ አንድ ቀራጭ እና እንደ ቀራጩ ባለመሆኑ በጽድቁ ስለተመካ ፈሪሳዊ የሚያስረዳ ታሪክ ተናግሯል። በዚህም ኢየሱስ ትሑትና የሚጸጸት ልብ ያላቸው ሰዎች ብቻ ኃጢአታቸውን እንደሚያውቁና በእግዚአብሔር ዘንድ ተቀባይነት እንደሚያገኙ አመልክቷል (መዝሙር 50፡16-17 አንብብ።] ከሌሎች የተሻልን በመሆናችን በእግዚአብሔር ፊት ተቀባይነት እናገኛለን ከሚል አሳብ ልባችንን መጠበቅ አለብን። ባለማቋረጥ ኃጢአተኞች መሆናችንን በማስታወስ የእግዚአብሔርን ምሕረትና ጸጋ መማጸን አለብን!

  1. ልጆች እግዚአብሔርን የመከተል ምሳሌዎች ናቸው (ሉቃስ 18፡15-17)

ኢየሱስ ለደቀ መዛሙርቱ በእግዚአብሔር ፊት ተቀባይነት ሊያገኙ የሚችሉበትን መንገድ ለማስተማር ወደ ልጆች ማመልከቱ የሚደነቅ ነው። በምድር ላይ ልጆች ቸል ተደርገው የተተዉት ሰዎች አካል ናቸው። ለመብታቸው ለመከራከር የሚያስችል አካላዊ ብቃት ስለሌላቸው፣ ሰዎች በቀላሉ ይሰድቧቸዋል፤ ይጎዷቸዋል። ልጆች በወላጆቻቸው ላይ ተጠግተው የሚኖሩ እንጂ፥ ለሌሎች ሰዎች ቁሳዊ በረከት የሚያስገኙ አይደሉም። ይሁንና ባይገባቸውም እንኳ በቶሎ የሚቀበሉና ከፍተኛ ፍቅር ያላቸው ናቸው። ኢየሱስ ለደቀ መዛሙርቱ የልጆች ጉዳይ እንደሚያሳስበው ገልጾላቸዋል። እኛም እንደ ልጆች ሁሉንም ነገር ባንረዳም እንኳ በፍጹም እምነትና ፍቅር ከእግዚአብሔር ጋር መዛመድ አለብን። ልጆች ያለ ብዙ ችግር ወንጌልን የሚቀበሉ የበሰሉ የመከር አዝመራዎች ናቸው።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ለልጆች ወንጌልን ለማካፈል ቤተ ክርስቲያንህ ምን እያደረገች ነው? ለ) የቤተ ክርስቲያንህ አገልጋዮች ልጆችን ከመናቅ ይልቅ እንደ ኢየሱስ የሚያከብሯቸው እንዴት ነው?

  1. ኢየሱስ ተከታዮቹ ከምንም ነገር በላይ እንዲወዱት ጠየቀ (ሉቃስ 18፡18-30)

ኢየሱስን በምንከተልበት ጊዜ ከሚያጋጥሙን ችግሮች አንዱ በልባችን ውስጥ የፍቅር ግጭት መኖሩና ኢየሱስ ደግሞ በሕይወታችን ውስጥ ከሁሉም የላቀ ስፍራ መጠየቁ ነው። ለአንዳንዶች ፍቅር ማለት ቤተሰብ ነው። ለሌሎች ደግሞ ትምህርት ነው። እንደ ሀብታሙ ባለሥልጣን ላሉት ደግሞ ገንዘብና ሥልጣን፣ ብሎም ሥልጣን የሚያመጣው ምቾት ነው። ምንም እንኳ ሰውዬው በጣም ሃይማኖተኛና የብሉይ ኪዳንን ሕግ የሚጠብቅ ቢሆንም፣ ኢየሱስ በዚህ አልረካም። ወደ ወጣቱ ገዥ ሕይወት ዘልቆ በማየት መዋዕለ ንዋይ የልቡን ማዕከል እንደተቆጣጠረ ተገነዘበ። ለዚህ ወጣት ገዥ መድኃኒቱ በባርነት ከገዛውና የመጀመሪያውን ፍቅር ከወሰደበት ገንዘብ መራቅ ነበር። ስለሆነም ኢየሱስ የዘላለምን ሕይወት ከፈለገ ገንዘቡን ትቶ እንዲከተለው ጠየቀው። የሚያሳዝነው ወጣቱ ጊዜያዊ ጥቅም የሚያስገኝለትን ገንዘብ ትቶ የዘላለምን ሕይወት ለመቀበል አልፈለገም።

ኢየሱስ እርሱን ለመከተል ጥሪውን ቀላል እንዳልሆነ ገልጾአል። ገንዘብ ለማግኘት የተጠየቁትን ከማድረግ የማይመለሱትን ድሆችና ባላቸው የማይረኩትን ሀብታሞች ጨምሮ፣ ብዙ ሰዎች የገንዘብ ባሮች ናቸው። የኢየሱስ ተከታዮች ነን ከማለታችን በፊት ይህ መዳሰስ ያለበት አካባቢ ነው። ነገር ግን እግዚአብሔር የምንወዳቸውን ነገሮች እንድንተው ካላስቻለን፣ ይህ የሚሞከር አይሆንም። ይህንን የሚያስችለው በሰውዬው ልብ ውስጥ ያለው የመንፈስ ቅዱስ ኃይል ብቻ ነው። ነገር ግን ልባችንን የሚቆጣጠሩትን ነገሮች አስወግደን ኢየሱስን ከሁሉም በበለጠ ስንወድ፣ ሕይወታችን ይለወጣል። በዚህ ጊዜ የዘላለምን ሕይወትና የወደፊት በረከቶችን ከማግኘታችንም በላይ፣ በዚህም ሕይወት ሽልማትን እናገኛለን። ያ ሽልማት ቁሳዊ ሀብት ሊሆን ወይም ላይሆን ይችላል፣ ኢየሱስ ከእኛ ጋር እንዳለና ሁሉም ነገር እንደሚበልጥ መገንዘቡ ከምንም ነገር የበለጠ ሀብት ነው።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ልብህን፡ ፍቅርህንና ሕይወትህን ለመቆጣጠር የሚፈልጉ ነገሮች የትኞቹ ናቸው? ለ) እነዚህን ነገሮች ከኢየሱስ በላይ የምትወድ መሆን አለመሆንህን እንዲያሳይህ እግዚአብሔርን ለመጠየቅ ጊዜ ውሰድ። ከዚያም ኢየሱስ በሕይወትህ ከሁሉም የሚበልጥ ፍቅር መሆኑን ለማረጋገጥ ምን ማድረግ እንዳለብህ ይገልጽልህ ዘንድ እግዚአብሔርን ጠይቀው።

  1. ኢየሱስ ሞቱንና ትንሣኤውን ተነበየ (ሉቃስ 18፡31-34) .

ጴጥሮስ ኢየሱስ መሢሕ መሆኑን ከመሰከረ በኋላ፣ ለደቀ መዛሙርቱ የመስቀል ላይ ሞት እንደሚጠብቀው ይነግራቸው ጀመር። ወደ መስቀሉ ይበልጥ በቀረበ ቁጥር፥ ደቀ መዛሙርቱን ስለ ሞቱ አብልጦ ያስጠነቅቃቸው ነበር። አሁን በኢየሩሳሌም አቅራቢያ ሊሆን ስላለው ነገር በግልጽ ነግሯቸዋል። በአይሁዶች እጅ ለአሕዛብ አልፎ እንደሚሰጥ ነገራቸው። አሕዛብና አይሁዶች በእርሱ ላይ ከተሳለቁ፣ ሰደቡት፣ ከተፉበትና ከገረፉት በኋላ ገድለውታል። በዚህም ኢየሱስ እርሱን በመከተላቸው ምክንያት የመሳለቅ፣ የመሰደብ፣ የመገረፍ፣ የመተፋትና የሞት ስደት ለሚደርስባቸው ክርስቲያኖች ምሳሌ ሆኗል።) ከዚያም በሦስተኛው ቀን እንደሚነሣ በግልጽ ነገራቸው። በኢየሱስ ላይ ከደረሰው ነገር በድንገት የተከሰተ ምንም አልነበረም፡፡ ኢየሱስ የሚደርስበትን ሁኔታ እንዴት አወቀ? ይህንን ያወቀው አምላክ ስለሆነና ሁሉንም ነገር ስለሚንዘብ ብቻ ነውን? አይደለም። ሉቃስና ሌሎችም የወንጌል ጸሐፊዎች ካደረጓቸው ነገሮች አንዱ፥ የብሉይ ኪዳን ክፍል ሁሉ ወደ ኢየሱስ እንደሚያመለክት መግለጽ ነበር። ኢየሱስ ከመወለዱ በመቶዎች ከሚቆጠሩ ዓመታት በፊት የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት ስለ ሞቱና ስለ ትንሣኤው ተንብየዋል።

  1. ኢየሱስ ዐይነ ስውሩን ለማኝ ፈወሰው (ሉቃስ 18፡35-43)

ሉቃስ ኢየስሱ ከመሞቱ በፊት እንዳደረገው በመግለጽ ያቀረበው የመጨረሻው ተአምር ወደ ኢየሩሳሌም በመሄድ ላይ ሳለ ከኢያሪኮ ውጭ ተቀምጦ የነበረውን ለማኝ ዐይን መፈወሱ ነው። ምንም እንኳ አብዛኞቹ አይሁዶች በመንፈሳዊ ሕይወታቸው ዕውራን ቢሆኑም፣ ለማኙ ዐይነ ስውር ኢየሱስ መሢሕ መሆኑን ለመገንዘብ ችሎ ነበር። ስለሆነም ሥጋዊ ብርሃኑ በርቶለታል።

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

%d bloggers like this: