- የአሥሩ ምናን (ብር) ምሳሌ (ሉቃስ 19፡11-27)
የውይይት ጥያቄ፡- 2ኛ ተሰሎ. 2፡1-12 አንብብ። ሰዎች ኢየሱስ ስለሚመለስበት ጊዜ ምን ያስባሉ?
አይሁዶችና የቀድሞ ክርስቲያኖች ከሚጠብቋቸው ነገሮች መካከል አንዱ፥ ኢየሱስ በፍጥነት ተመልሶ መሢሑ በዓለም ሁሉ የሚገዛበትን ምድራዊ መንግሥት መመሥረቱ ነበር። ምናልባትም ወደ ኢየሩሳሌም እየቀረበ ሲመጣ፣ አይሁዶች አሁን የመሢሑን አገዛዝ በጳለስቲና እንደሚጀምር በማሰብ ሳይደሰቱ አልቀሩም። ስለሆነም ኢየሱስ ለአይሁዶች ምድራዊ መንግሥቱን ገና ወደፊት እንደሚመሠርት ለማሳየት ፈለገ። ይህ ደግሞ ለክርስቲያኖችም የሚያስፈልግ ትምህርት ነው። ጳውሎስ በተሰሎንቄ ቤተ ክርስቲያን ከመሠረተ ብዙም ሳይቆይ አብዛኞቹ ክርስቲያኖች ኢየሱስ ዳግም መጥቶ ሳናውቅ ሄዶ ይሆናል በሚል አሳብ ተሸብረው ነበር። ኢየሱስ በምሳሌው ለማስተማር የፈለገው ዋንኛ ትምህርት የሚመለስበት ጊዜ ገና ወደፊት እንደሆነና ዋናው ነገር እርሱ እስኪመለስ ድረስ በታማኝነት እያገለገሉ መኖር መሆኑን ነው።
ከንጉሣዊ ቤተሰብ የተወለደ ሰው ኢየሱስን ይወክላል፤ እርሱም ወደ ሰማይ በመሄድ የንጉሥነትን ሹመት ተቀብሎ ወደ ምድር ይመለሳል። ደቀ መዛሙርቱ ደግሞ ኢየሱስ ለክብሩ ይጠቀሙበት ዘንድ ገንዘብ ሰጥቶ የሾማቸው አሥር አገልጋዮች ነበሩ። ገንዘቡ ደግሞ የኢየሱስ ተከታዮች ንብረት የሆነው አካላቸው፣ ትምህርታቸው፣ ጊዜያቸው፣ ገንዘባቸው ነበር። ያን ጊዜ አንድ ብር የሦስት ወር ደመወዝ ያህል ገንዘብ ስለ ነበር፣ እሥር ብር የሁለት ዓመት ተኩል ደመወዝ ያህል ነበር። (ማስታወሻ፡ በማቴ. 25፡14-30 በተጠቀሰው ምሳሌ ውስጥ ሦስት ባሪያዎች ብቻ ሲጠቀሱና ለእያንዳንዱ ባሪያ የተለያየ መጠን ያለው ገንዘብ ሲሰጥ፣ እዚህ ላይ ግን እኩል ገንዘብ የተሰጣቸው አሥር ባሪያዎች ተጠቅሰዋል። ማቴዎስ ያተኮረው የተለያዩ ስጦታዎችንና ችሎታዎችን በታማኝነት በመጠቀሙ ጉዳይ ላይ ሲሆን፣ በዚህ ስፍራ ሉቃስ እግዚአብሔር ሕይወታችንን ሁሉ ለእርሱ ክብር እንድንጠቀምበት አጽንኦት ሰጥቶ ያስተምራል። የሁለቱም ትኩረት ታማኝነት የታከለበትን አገልግሎት ማበርከት እንደሚገባ መግለጽ ነው።) ከዚህ ምሳሌ የሚቀስሙ በርካታ ጠቃሚ እውነቶች አሉ።
ሀ. ኢየሱስ፥ አይሁዶች ንጉሥ እንዲሆን ባይፈልጉም፣ እርሱ መሢሕ ነበር። የንግሥና አክሊል እንዳይደፋና አንድ ቀን ወደ ምድር ተመልሶ እንዳይገዛ ሊከለክሉት አይችሉም። (አንዳንድ ምሑራን ከዚህ ክፍል አርከሉስ በተባለ የሄርድስ ልጅ ላይ የደረሰውን ሁኔታ የሚመስል ነገር ይመለከታሉ። አባቱ ታላቁ ሄሮድስ አርኬላውስን ንጉሥ አድርጎ ሲሾመው፣ አይሁዶች ወደ ሮም የልዑካን ቡድን በመላክ ከዙፋኑ አስወርደውት ነበር። በኢየሱስ ላይ ግን ይህንን ሊያደርጉ አልቻሉም። እግዚአብሔር ኢየሱስን ወይም ሌላ ንጉሥ የመምረጥ ዕድል አልሰጠንም። ስለዚህ ኢየሱስ ብቸኛው ንጉሥ ስለሆነ፣ አማራጫችን እርሱ ንጉሥ መሆኑን አምነን ግንኙነታችንን ከእርሱ ጋር ማድረግ ብቻ ነው።
ለ. አሥሩ ሰዎች እኩል መጠን ያለው ገንዘብ እንደተሰጣቸው ሁሉ እኛም የተለያዩ ስጦታዎችና ችሎታዎች አሉን የሁላችንም ሕይወት የእግዚአብሔር ነው። ስለሆነም እግዚአብሔርን የማገልገል ብቃታችን እኩል ነው።
ሐ. እግዚአብሔር ለሰዎች የተለያየ ስጦታ እንዳላቸው ያውቃል፤ ስጦታዎቹን የሰጣቸው እርሱ ነው። ስለሆነም እያንዳንዱ ባሪያ እግዚአብሔር ከሰጠው ውስጥ የተወሰነውን እንደሚመልስ ያውቃል።
መ. ዋናው ነገር ራሳችንን ከሌሎች ጋር ማወዳደር ሳይሆን፣ በሰጠን ነገር ኢየሱስን በታማኝነት ማገልገል ነው። ኢየሱስን የሚያገለግሉ ሁሉ ዋጋቸውን ሲቀበሉ፣ ስጦታዎቻቸውንና ችሎታዎቻቸውን ያባከኑት ሰዎች ግን ከፍተኛ ቅጣት ይጠብቃቸዋል።
ሠ. እግዚአብሔር እርሱን ለሚያገለግሉ ሰዎች ያለው መርሕ ትጋትን ላሳዩ ሰዎች የበለጠ ኃላፊነት መስጠት ነው። የሥልጣን ደረጃ የሚወሰነው በሁለት ነገሮች ነው። አንደኛው፥ ያለንን በታማኝነት በመያዛችን ላይ ይመሠረታል። ሁለተኛው፣ እግዚአብሔር በሰጠን ችሎታ ላይ ይመሠረታል። አንድ ባሪያ አሥሩን ብር ወደ ሃያ ብር ለማድረስ በታማኝነት የሚሠራ ከሆነ፡ ከዚያ የበለጠ ኃላፊነት ይስጠዋል። ነገር ግን ታማኝነት ባይጎድልበትም እንኳ የባሪያው ችሎታ አምስት ብር ብቻ እንዲያተርፍ ካደረገ፣ የሚሰጠውም ኃላፊነት እንደዚያው ይቀንሳል።
ረ. እግዚአብሔር የሰጣቸውን ነገር ለመጠቀም በማይፈልጉ ሰዎች ላይ የሚፈርድ ሲሆን፣ ያላቸውም እንኳ ይወሰድባቸዋል። በቤተ ክርስቲያን ውስጥ እግዚአብሔር የሰጣቸውን ችሎታ ለእርሱ ክብር የማይጠቀሙ ሰዎች አሉ። እነዚህ ሰዎች እግዚአብሔር የሰጠውን ብር እንደ ደበቀው ሰው ናቸው። እነዚህ ሰዎች እሑድ እሑድ ወደ ቤተ ክርስቲያን መጥተው ከምእመናኑ ጋር ይዘምራሉ እንጂ፣ በሥራ ቦታ አይመሰክሩም፤ በልግስና አይሰጡም፤ ድሆችን አይረዱም፣ ወይም በሆነ መንገድ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ አያገለግሉም። እግዚአብሔር የሰጣቸውን መክሊት ይደብቁታል። ኢየሱስ በእነዚህ ሰዎች እጅ ያለውን ነገር ወስዶ ለክብሩ ለሚጠቀሙት እንደሚሰጥ ተናግሯል። ብዙ ሰዎች የመሪነትን አገልግሎት ቢመኙም፣ እግዚአብሔር የሰጣቸውን ተጠቅመው ሊያገለግሉትና በፈቀደም ጊዜ ከፍ ለማለት አይሹም። እግዚአብሔር በታማኝነት ያላገለገለውን ሰው ከፍ አያደርግም፣ እነዚህ ሰዎች ረዥም ጊዜ መጠበቅ አይሆንላቸውም፤ እንዲያውም የበለጠ ዝቅ ያደርጋቸዋል።
የውይይት ጥያቄ- ሀ) እግዚአብሔር የሰጠህ አንዳንድ ስጦታዎችና ችሎታዎች ምንድን ናቸው? ለ) የትኞቹን ለእግዚአብሔር እየተጠቀምህ ነው? እንዴት? ሐ) ያልተጠቀምህባቸው የትኞቹ ናቸው? ለምን? መ) ብዙ ሰዎች ያላቸውን ስጦታና ችሎታ እግዚአብሔርን ለማገልገል የማይጠቀሙት ለምን ይመስልሃል? ሠ) በቤተ ክርስቲያን ውስጥ እያንዳንዱ ሰው ለጦታውን በሥራ ላይ የሚያውልበትን መንገድ በማሳየቱ ረገድ የመሪዎች ኃላፊነት ምንድን ነው? ይህ መሪዎች ሌሎችን በአገልግሎት ማሳተፍ እንዳለባቸው የሚያመለክተው እንዴት ነው?
- ኢየሱስ ወደ ኢየሩሳሌም በድል ገባ (ሉቃስ 19፡28-44)
አምልኮን የምንገመግመው እንዴት ነው? በስሜቶች፣ በእንቅስቃሴዎች፣ በጭብጨባዎችና በዕልልታዎች ነውን? ወይስ በሆነ መንገድ በምስጋናና በውዳሴ ራሱን የሚገልጽ ሕይወት ከእግዚአብሔር ጋር በመምራት ነው? ብዙውን ጊዜ ሰዎች በአምልኮ ጊዜ ስሜታውያን ሆነው ሊታዩና በእግዚአብሔር ላይ ጽኑ እምነት ላይኖራቸው ይችላል። ኢየሱስ በአህያ ውርንጫ ላይ ተቀምጦ ወደ ኢየሩሳሌም በተጓዘበት ጊዜ እንዲህ ዐይነት ሁኔታ ተከስቷል። ብዙ ሰዎች ደስታቸውን በጩኸት፣ በጭፈራና በዝማሬ ከመግለጻቸውም በላይ፣ እግዚአብሔርንም አመስግነዋል። ነገር ግን ከስድስት ቀናት በኋላ እነዚሁ ሰዎች «ስቀለው!» እያሉ ጮኸዋል። ስሜታዊ አምልኳችን ከእግዚአብሔር ጋር ካለን ትክክለኛ ዓላማ መመንጨቱን ማረጋገጥ አለብን።
ኢየሱስ የሕዝቡን ውዳሴ አዳመጠ። ነገር ግን ኢየሩሳሌምን ሲመለከትና ቀጥሎ የሚሆነውን ሁኔታ ሲያስብ ልቡ በኀዘን ተመታ። መሢሑ ንጉሣቸው መጥቷል። ነገር ግን አይሁዶች ኢየሱስን ለመቀበል ስላልፈለጉ፣ የእግዚአብሔር ፍርድ እየመጣባቸው ነበር። ብዙም ሳይቆይ ከተማይቱ ትደመሰሳለች። በ70 ዓ.ም. የሮም ወታደሮች የኢየሩሳሌምን ከተማ በወረሩ ጊዜ እስከ አንድ ሚሊዮን የሚደርሱ ሰዎች እንደ ተገደሉ ይገመታል።
- ኢየሱስ ቤተ መቅደሱን አጸዳ (ሉቃስ 19፡45-48)
የኢየሱስ ደስታ ወደ እንባ፣ ከዚያም ወደ ቁጣ ተቀየረ። ይህ ሁሉ የሆነው በጥቂት ሰዓታት ውስጥ ነበር። ኢየሱስ የቤተ መቅደስ ውስጥ ነጋዴዎች የሚያደርጉትን የሙስና ተግባር በመመልከቱ እጅግ ተቆጥቶ አባረራቸው። የስግብግብነት ባሕርይ በፍጥነት ሰዎቹን በመቆጣጠሩ አምልኳቸውን ለሚያቀርቡ ሰዎች (እንስሳትን ለመሥዋዕትነት፣ ገንዘብን ደግሞ ለቤተ መቅደስ ቀረጥ ማቅረብ) እንዲያገለግል የታሰበው ነገር የመበዝበዣ መሣሪያ ሆነ። ይኸው ተመሳሳይ ዝንባሌ ሰዎች የውጭ አገር ዜጎችን ወይም አቅመ ደካሞችን በማታለል ለአንድ ነገር ከሚገባው በላይ ዋጋ ሲወስዱ የሚከሰት ነው። ይህ ልናደርግ የሚገባን ነገር ተገላቢጦሽ ነው። ምክንያቱም እንደ ኢየሱስ ክርስቶስ ተከታዮች ልናገለግል እንጂ በሰዎች ጉዳት ልንጠቀም አይገባም።
(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)