የኢየሱስ ትንሣኤና ዕርገት (ሉቃስ 24፡1-53)

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) የኢየሱስ ትንሣኤ ወሳኝ እንደሆነ የምታስበው ለምንድን ነው? ለ) 1ኛ ቆሮ. 5፡12-32 አንብብ። ጳውሎስ ትንሣኤ አስፈላጊ ነው የሚለው ለምንድን ነው? ሠ) በትንሣኤው ላይ ብዙ ትኩረት እየሰጠን ትንሣኤውን እምብዛም የማናነሣው ለምንድን ነው?

ከታሪክ ምሑሩ አመለካከት አንጻር፣ የኢየሱስ ትንሣኤ በታሪክ እጅግ በጣም አስፈላጊ ነገር ነው። ቀደም ሲል ሰዎች በመስቀል ላይ ሲሞቱ ኖረዋል። ከእነዚህም አንዳንዶቹ የእግዚአብሔር ሕዝብ መሪዎች ናችሁ ተብለው ነበር የተሰቀሉት። ነገር ግን ከኢየሱስ በስተቀር ያለ ሌላ አካል እገዛ ከሞት የተነሣ ማንም ሰው በታሪክ ውስጥ የለም።

በእግዚአብሔር ዕቅድ ውስጥ የኢየሱስ ስቅለትና ትንሣኤ ሁለቱም አስፈላጊዎች ነበሩ። በስቅለቱ ኢየሱስ የኃጢአት ዋጋችንን ከፍሏል። ትንሣኤው ደግሞ ለአያሌ ምክንያቶች አስፈላጊ ነበር። አንደኛው፥ እግዚአብሔር ኢየሱስ ያቀረበውን የኃጢአት መሥዋዕት እንደ ተቀበለ ያረጋግጣል። እግዚአብሔር በኢየሱስና በመሥዋዕቱ ደስ ባይሰኝና የኃጢአት መሥዋዕቱ በቂ ባይሆን ኖሮ፣ ኢየሱስን ከሞት አያስነሣውም ነበር። ሁለተኛው፣ ትንሣኤው የእግዚአብሔር ልጆች ሁሉ ትንሣኤ በኩር ነው። የክርስቶስ ትንሣኤ እግዚአብሔር እኛንም ከሞት እንደሚያስነሳን የሰጠን የተስፋ ቃል ነው። የኢየሱስ ትንሣኤ እጅግ አስፈላጊ በመሆኑ የክርስትና አስተምህሮ ሁሉ በዚህ እውነት ላይ ይመሠረታል። ለዚህ ነው ጳውሎስ ኢየሱስ ከሞት ካልተነሣ እምነታችን ከንቱ ነው ያለው (1ኛ ቆሮ. 5፡12-19)።

ከሌሎቹ የወንጌላት ጸሐፊዎች በላይ ሉቃስ በኢየሱስ ትንሣኤ ላይ አትኩሯል። ሌሎች የወንጌል ጸሐፊዎች በትንሣኤው እሑድ ጠዋት ምን እንደ ተፈጸመ አልገለጹም። ሉቃስ ስለ ኢየሱስ ትንሣኤ ያቀረባቸው ታሪኮች ሁሉ የትንሣኤውን እርግጠኝነት የሚያስገነዝቡ ናቸው። ትንሣኤው እውነተኛ ታሪካዊ ክስተት እንጂ አፈ ታሪክ አይደለም። ከሞት የተነሣውን ጌታ የተመለከቱ የዐይን ምስክሮች ገና አልሞቱም። ስለሆነም አንዳንድ ከአሕዛብ ወገን የሆኑ ሰዎች ቢሳለቁም (የሐዋ. 17፡32)፣ ኢየሱስ በእርግጥ ከሞት ተነሥቷል!

ሀ. ኢየሱስ ከሞት እንደ ተነሣ መላእክት ለሴቶቹ ነገሯቸው (ሉቃስ 24፡1-12)። ሉቃስ ሴቶች በኢየሱስ አገልግሎት ውስጥ ስለነበራቸው ትልቅ ድርሻ፥ ትኩረት ሰጥቶ መዘገቡን ቀደም ብለን ተመልክተናል። እሑድ ማለዳ ለኢየሱስ አካል ልዩ ቅመሞች ይዘው የሄዱት ሴቶቹ ነበሩ። ነገር ግን መቃብሩ ባዶ ሆኖ ሲያገኙት ደነገጡ። ሁለት መላእክት ከሞቱና ከትንሣኤው በፊት የነገራቸውን አስታወሷቸው። ሴቶቹ ከመላእክት የሰሙትን ለደቀ መዛሙርቱ ሲናገሩ ሊያምኗቸው አልቻሉም። በዚህ ጊዜ ጴጥሮስ ራሱ አይቶ ሊያረጋግጥ ፈለገ። ወደ ባዶው መቃብር ውስጥ ሮጦ ቢገባም፣ የተከሰተውን ነገር ሊገነዘብ አልቻለም።

በታሪክ ሁሉ የማያምኑ ሰዎች የትንሣኤውን እውነት ለመካድ የሚያቀርቡት ምክንያት ደቀ መዛሙርቱ ኢየሱስን ለማግኘት ከመጠን በላይ ስለ ተመኙ እርሱን ሳይሆን ራእይ ነው ያዩት የሚል ነው። ኢየሱስ እንዲሞት ስላልፈለጉ የትንሣኤውን ሕልም እንዳዩ ይናገራሉ። ሕልሙ በጣም ጠንካራ ስለነበር ደቀ መዛሙርቱ ኢየሱስ ከሞት ተነሥቷል ብለው አሰቡ። ነገር ግን ሉቃስና ሌሎች ጸሐፊዎች ያቀረቡት አሳብ ከዚህ ፍጹም የሚቃረን ነው። ከደቀ መዛሙርቱ መካከል ኢየሱስ ከሞት ይነሣል ብሎ የጠበቀ አልነበረም። መላእክትና የዐይን ምስክሮች ቢነግሯቸውም እንኳ ለእነርሱ ተገልጦ አሳባቸውን ከመለወጡ በፊት ተነሥቷል ብለው አላመኑም ነበር። የደቀ መዛሙርቱን የአመለካከት መለወጥና ኢየሱስ ከሞት የተሣ ጌታ ነው እንዲሉና ራሳቸውን አሳልፈው እንዲሰጡ ያደረጋቸውን ነገር ሊያብራራ የሚችለው ትንሣኤው ብቻ ነው።

ለ. ኢየሱስ በኤማሁስ መንገድ ለሁለት ደቀ መዛሙርት ታየ (ሉቃስ 24፡13-35)። በዚያን እሑድ ዕለት ሁለት ደቀ መዛሙርቱ ከኢየሩሳሌም 11 ኪሎ ሜትር ያህል ርቃ ወደምትገኘው ወደ ኤማሁስ በመጓዝ ላይ ነበሩ። ስለ ኢየሱስ ስቀለትና ስለ ትንሣኤው የሰሙት ነገር አእምሯቸውን እያናወጠው ነበር። በዚህ ጊዜ ኢየሱስ በመካከላቸው ተገኘ። ኢየሱስን ለመለየት ያልቻሉት በሁለት ምክንያት ሊሆን ይችላል። አንደኛው፣ ኢየሱስ እንደ ሞተ እርግጠኞች በመሆናቸው በመካከላቸው እንደሚገኝ አልጠረጠሩም ነበር። አእምሯቸው ከእነርሱ ጋር የሚነጋገረው ኢየሱስ እንደሆነ እንዳይቀበሉ አድርጓቸዋል። ሁለተኛው፣ ምናልባትም የኢየሱስ የትንሣኤ አካል በብዙ መንገዶች ቀደም ሲል ከሚያውቁት ተለይቶባቸው ይሆናል። የቀድሞውን የሚመስሉና የተለዩም ነገሮች ነበሩ።

በዚህ ታሪክ ሉቃስ ኢየሱስ ሞቱና ትንሣኤው የእግዚአብሔር ዕቅድ መሆኑን እንዴት እንዳረጋጋጠ ገልጾአል። መላእክቱ ኢየሱስ ከመሞቱ በፊት ስለተነበየው ጉዳይ ለሴቶቹ እንደተናገሩት ሁሉ፣ ኢየሱስ እነዚህንም ሰዎች ወደ ብሉይ ኪዳን ታሪኮች በመውሰድ ሁሉም ነገር እንዴት እርሱን፣ ሞቱንና ትንሣኤውን እንደሚያመለክት አስነዘባቸው። ኢየሱስ የብሉይ ኪዳን መልእክት ማዕከላዊ ነው። እነዚህ ደቀ መዛሙርት ኢየሱስን ያወቁት ለምግቡ እግዚአብሔርን በማመስገን ከጸለየ በኋላ ነበር።

ሐ. ኢየሱስ ለሁሉም ደቀ መዛሙርት ታየ (ሉቃስ 24፡36-49)። የማያምኑ ሰዎች ለኢየሱስ ትንሣኤ የሚያቀርቡት ሌላው ማብራሪያ ደቀ መዛሙርቱ መንፈስን እንዳዩ የሚያስረዳ ነው። የኢየሱስ መንፈስ ለደቀ መዛሙርቱ የታየበትን ሁኔታ ልክ የሳኦል መንፈስ ለሳሙኤል ከታየበት ጋር ያዛምዳሉ (1ኛ ሳሙ. 28)። ነገር ግን ኢየሱስ ክርስቶስ መንፈስ እንዳልሆነ በዚህ ታሪክ ውስጥ እንመለከታለን። በመጀመሪያ ደቀ መዛሙርቱ ድንገት በመካከላቸው ቆሞ ሲያዩት መንፈስን እንዳዩ ነበር ያሰቡት። ኢየሱስ ግን የትንሣኤ አካሉን ዳስሰው መንፈስ እንዳልሆነ እንዲያረጋግጡ ነገራቸው። ይህ አንዳንዶችን ሊያሳምን ባለመቻሉ ምግብ ለመብላት ማንነቱን ሊያሳያቸው ሞከረ። መስቀሉና የኢየሱስ ትንሣኤ ቀደም ብለው የተተነበዩ መሆናቸውን ለደቀ መዛሙርቱ ለማሳየት ሉቃስ ኢየሱስ ብሉይ ኪዳንን የጠቀሰበትን ሁኔታ ለሁለተኛ ጊዜ አመልክቷል።

ከዚያ በኋላ ኢየሱስ ለደቀ መዛሙርቱ የመጨረሻውን ትእዛዝ ሰጣቸው። አገልግሎታቸውን በአገራቸው ወይም በነገዳቸው ሳይወስኑ ወደ ዓለም ሁሉ እንዲሄዱ አዘዛቸው። ሰዎች ንስሐ ገብተው በኢየሱስ በማመን የኃጢአት ይቅርታ እንዲያገኙ ደቀ መዛሙርቱ ከኢየሩሳሌም ጀምሮ መስበክ ነበረባቸው። ነገር ግን ታላቁን ትእዛዝ ተግባራዊ የሚያደርጉበትን ኃይል ከየት ያገኛሉ? ኢየሱስ መንፈስ ቅዱስ እንደሚወርድላቸው ቃል ገብቷል። ይኸው መንፈስ ቅዱስ እስኪመጣ ድረስ አገልግሎታቸውን እንዳይጀምሩ ተነግሯቸዋል። የሐዋርያት ሥራ የሚጀምረው የሉቃስ ወንጌል ካቆመበት ነው። የመንፈስ ቅዱስ መሰጠት፣ ደቀ መዛሙርቱ የኢየሱስን ትእዛዝ ተቀብለው ወንጌሉን ወደ ሮም ግዛቶች ሁሉ መውሰዳቸው በሐዋርያት ሥራ ውስጥ ተብራርቷል።

የኢየሱስ ክርስቶስ ተከታዮች ለሆንን ሰዎች ይህ ትእዛዝ ዛሬም ተግባራዊ ሊሆን ይገባዋል። ዛሬ ከ2000 ዓመታት በኋላ፣ የኢየሱስን ወንጌል ወደ ሁሉም ሕዝቦችና ብሔሮች ዘንድ አላዳረስንም። ራስ ወዳድነት የአብዛኞቹን ክርስቲያኖችና አብያተ ክርስቲያናት ሕይወት ማበላሸቱን እንደቀጠለ ነው። ከቤተሰቦቻችንና ከቤተ ክርስቲያናችን፣ ሳንነጠል በአገራችን ተደላድለን ለመኖር እንፈልጋለን። ይህ ግን የኢየሱስን ልብ ያስጨንቃል። እርሱ ወደ ሰማይ የሄደው እኛ የምሥራቹን ቃል ሰምተን የእግዚአብሔር ልጆች እንሆን ዘንድ ነው። እኛ ግን ከአገራችን ወጥተን ለሌሎች ወንጌልን ለመናገር አንሻም። ቤተ ክርስቲያን በወንጌሉ ብርሃን ደስ ብትሰኝም፣ ብዙውን ጊዜ ወንጌሉን ለሌሎች ለማዳረስ የሚያስፈልገውን ዋጋ ለመክፈል አንፈልግም።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ክርስቲያኖችና አብያተ ክርስቲያናት ራስ ወዳድ በመሆን መልካሙን የምሥራች ወደ ዓለም ሁሉ እንዳናዳርስ የሚጠይቀውን የኢየሱስን ትእዛዝ ችላ ሊሉ የሚችሉባቸውን መንገዶች ዘርዝር። ለ) ስለ ቤተ ክርስቲያንህ አስብ። ቤተ ክርስቲያንህ ራስ ወዳድነትን ለመቆጣጠርና ወንጌሉን ወዳልሰሙት ለማድረስ ምን እያደረገች ነው? ሐ) ይህንን ለተከታዮቹ ሁሉ የተሰጠውን የኢየሱስን ትእዛዝ ለመጠበቅ ምን እያደረግህ ነው?

መ. ኢየሱስ ወደ ሰማይ ዐረገ (ሉቃስ 24፡50-53)። ቀጥሉ የተከሰተውን ነገር በዚህ ወንጌልና በሐዋርያት ሥራ ውስጥ የሚተርክልን ሉቃስ ብቻ ነው። ኢየሱስ ለ40 ቀናት ያህል ለደቀ መዛሙርቱ ከታየ በኋላ ሁሉም እያዩ ወደ ሰማይ ወጣ። የኢየሱስ ምድራዊ ታሪክ በዚሁ ይጠናቀቃል። ነገር ግን በሰማይ ሆኖ በደቀ መዛሙርቱ ሕይወት ውስጥ መሥራቱን እንደሚቀጥል የሐዋርያት ሥራ መጽሐፍ ያስረዳል። ይሁንና ኢየሱስ አንድ ቀን ወደ ምድር ተመልሶ ይመጣል። ምጽአቱ ምንኛ የተለየ ነው! ያን ጊዜ የሚመለሰው እንደ ሕጻን ልጅ ወይም አምላክነቱን ደብቆ አይደለም። ኢየሱስ እንደ ድል እድራጊና ገዥ ንጉሥ በክብር አሸብርቆ ይመለሳል። አሁን እየተጨነቅንና እየተጨቆንን እንገኝ ይሆናል። ነገር ግን ኢየሱስ በሚመጣበት በዚያን ታላቅ ቀን የዓለም ክፋትና መከራ ሁሉ ያበቃል። እነሆ ተስፋችን ይህ ነው። በደስታ እንድንኖር የሚያደርገንም ይኸው ነው። ነገር ግን አሁን ከሞት የተነሣው ኢየሱስ ምን እየሠራ ነው? ለድሀውና ለተጨነቀው ርኅራኄን እያሳየ በምድር ላይ የተመላለሰው ኢየሱስ አሁን በሰማይ በሊቀ ካህንነት እንደሚያገለግል የዕብራውያን መልእክት ይነግረናል። አሁንም ርኅራኄው አልተለየውም። ምንም እንኳን የሚያደርገውን ነገር ባናይና ባንግዘብ እንኳ፥ ይህም ደግሞ ለደስታችን ምክንያት ይሆንልናል።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ኢየሱስ በእኛ ፈንታ በሰማይ መሥራቱ የሚያበረታታትን ለምንድን ነው? ለ) በሕይወትህ፣ በአገርህ ወይም በቤተ ክርስቲያንህ ውስጥ የሚከሰቱ ነገሮች እየተፈታተኑህ ሳለ፥ ኢየሱስ የዘላለም መንግሥት ይዞ በክብር የመመለሱ ነገር በተስፋ እንድትጓዝ የሚያደርግህ እንዴት ነው?

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

1 thought on “የኢየሱስ ትንሣኤና ዕርገት (ሉቃስ 24፡1-53)”

Leave a Reply

%d bloggers like this: