ክርስቶስ የእግዚአብሔር መንጋ መልካም እረኛ ነው (ዮሐ. 10፡1-21)

የውይይት ጥያቄ፡- መዝሙር 23 እና ሕዝቅኤል 34ን አንብብ። ሀ) ከእነዚህ ምንባቦች ስለ እግዚአብሔር ምን እንማራለን? ለ) ከእነዚህ ምንባቦች እግዚአብሔር ፍጹም እረኛን ስለመላኩ ምን እንማራለን? ሐ) ስለ እረኛ አንዳንድ አሳቦችን ለማግኘት የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት እንብብ። የአይሁድ እረኞች ምን እንደሚመስሉና በኢትዮጵያ ከሚገኙ እረኞቹ እንዴት እንደሚለዩ ጠቅለል ያለ ማብራሪያ ጻፍ።

ውብ ከሆኑት ምሳሌዎች መካከል አንዱ፥ እግዚአብሔር እንደ እረኛ መመሰሉ ነው። ይህን ምሳሌ በትክክል ለመረዳት፥ የአይሁድ እረኞች ዛሬ በኢትዮጵያ ውስጥ ከምናያቸው እረኛች በጣም የተለዩ መሆናቸውን መገንዘብ ይኖርብናል። አብዛኞቹ በኢትዮጵያ የምናያቸው እረኛች ከደሀ ቤተሰብ የተወለዱና ያልተማሩ ሲሆኑ፥ ለበጎቻቸውም እምብዛም አይጨነቁም። በጎቻቸውን በድንጋይ ይወግራሉ፥ በበትር ይመታሉ፥ ወደ ቤታቸውም ሊወስዱ እያቻኮሉ ይወስዳሉ። አይሁዶች ግን ለእረኞቹ ከፍተኛ ግምት ይሰጣሉ፤ እረኞቻቸውም ለበጎቻቸው የላቀ ስፍራ ይሰጣሉ። የኢትዮጵያ እረኞች ቀኑ ሲመሽ በጎቻቸውን ይዘው ወደ ቤት ይመለሳሉ። የአይሁድ እረኞች ግን ቀኑ ከመሸ በዚያው ባሉበት ከበጎቻቸው ጋር ያድራሉ። ይህም ብዙ የከብት መንጋ ካላቸው የቦረናና ሌሎች የደቡብ ኢትዮጵያ ጎሳዎች ሁኔታ ጋር የሚመሳሰል ነው። የአይሁድ እረኞች ለበጎቻቸው ምርጥ ሣርና ውኃ ለማግኘት ከቦታ ቦታ ይዘዋወራሉ። አንዳንድ ጊዜ ሌሊት በጎቻቸውን ለመጠበቅ ሲሉ በረት ይሠራሉ። በረቱ መዝጊያ ስለማይኖረው እረኞቹ በበሩ ላይ ይተኛሉ። ይህም በጎቹ ከበረቱ ወጥተው በአራዊት እንዳይበሉ ይከላከላል። እረኛው ከቦታ ቦታ ሲዘዋወር በጎቹን ከኋላ ሆኖ እየነዳ ሳይሆን ከፊት ሆኖ እየመራ ነው የሚሄደው። በስማቸው እየጠራ ወደ ለምለም ስፍራ ይመራቸዋል። ትናንሽ የበግ ግልገሎች በሚወለዱበት ጊዜ እረኛው በክንዶቹ አቅፎ ከቦታ ቦታ ያጓጉዛቸዋል። ይህም የአይሁድ እረኞች ከበጎቻቸው ጋር ያላቸው ግንኙነት የጠበቀ መሆኑን ያሳየናል።

በብሉይ ኪዳን እግዚአብሔር ለአይሁድ የእረኞች አለቃ መሆኑን ነግሮአቸው ነበር። ሕዝቡን የሚንከባከብ፥ የሚመራና የሚያስፈልጋቸውንም ሁሉ የሚያዘጋጅ እርሱ ነው። ሕዝቡን ለሚንከባከቡ ለሌሎች እረኞች ማለትም መሪዎች (ነገሥታት፥ ካህናትና ነቢያት) እንደሚሰጥ ተናግሯል። ነገር ግን እነዚህ እረኞች የእግዚአብሔርን መንጋ ስለበተኑ በሌላ እረኛ ማለትም በመሢሑ ተተኩ።

እንግዲህ ኢየሱስ መልካም እረኛ ነኝ ሲል አምላክ ነኝ ማለቱ ነበር። በተጨማሪም፥ የሕዝቅኤል ትንቢት በእኔ ተፈጸመ ማለቱ ነበር። ኢየሱስ ራሱን በእረኛ መስሎ ባቀረበው ተምሳሌት ውስጥ እያሌ እውነቶች ተካትተዋል።

ሀ. ክርስቶስ ወደ እግዚአብሔር መንጋ የሚወስድ በር ነው። ይህም ከርስቶስ «እኔ ነኝ» በማለት የተናገረው ሦስተኛው ዓረፍተ ነገር ነው። እርሱ መንገድ ነው። በክርስቶስ በኩል ሳይመጡ ከእግዚአብሔር መንጋ ጋር ለመቀላቀል የሚሞክሩ ሰዎች ምንም ያህል ቢጥሩ አይሳካላቸውም፤ መጨረሻቸውም የእግዚአብሔርን መንጋ መስረቅ ይሆናል።

ለ. የእግዚአብሔር መንጋ አካል መሆን አለመሆናችንን እንዴት እናውቃለን? የኢየሱስን ድምፅ ስለምናውቅ እንከተለዋለን። ከኢየሱስ ወገን የሆኑ በጎች ድምፁን ስለሚያውቁ በታዛዥነት ይከተሉታል።

ሐ. ሐሰተኛ እረኞች ከበጎቹ ጥቅም ለማግኘት ሲሉ ይመጣሉ። ክርስቶስ ግን ለበጎቹ ጥቅም ይሠራል። በደስታ የተሞላ ሕይወት ይሰጠናል ፍላጎታችንንም ይሞላል።

መ. ኢየሱስ መልካም እረኛ ነው። ይህ ኢየሱስ የተናገረው «እኔ ነኝ» የሚለው አራተኛው ዓረፍተ ነገር ነው። ክርስቶስ ሕይወቱን አሳልፎ በመስጠት በጎቹን የሚንከባከብ ፍጹም መሪ ነው። ከአራዊት በጎቹን ለመታደግ ከበሩ ላይ እንደሚተኛ የአይሁድ እረኛ፥ ክርስቶስ ለእግዚአብሔር በጎች ራሱን አሳልፎ ከመስጠቱም በላይ፥ ለዓለም ሁሉ ኃጢአት በመስቀል ላይ ሕይወቱን አሳልፎ ሰጥቷል።

ሠ. ኢየሱስ በሕይወቱ ላይ ሙሉ ሥልጣን አለው። የአይሁድ መሪዎችም ሆኑ የሮም መንግሥት በክርስቶስ ሕይወት ላይ ሥልጣን የላቸውም። ሕይወቱ በራሱ እጅ በመሆኑ፥ በመስቀል ላይ ለመሞትና በትንሣኤ ሕይወት ለመነሣት ሥልጣን አለው።

ረ. ኢየሱስ ሌሎች በጎች አሉት። ክርስቶስ ይህን ሲል ምናልባትም ወደ ፊት በእርሱ ስለሚያምኑት አሕዛብ ሊሆን ይችላል። እነርሱም የክርስቶስን ድምፅ ለይተው ይከተሉታል። አንድ ቀን የአሕዛብና የአይሁድ አማኞች ቤተ ክርስቲያን ከተባለች አንዲት መንጋ ሥር ይተባበራሉ።

የውይይት ጥያቄ፡- የቤተ ክርስቲያን መሪዎች (ሽማግሌዎች) የእግዚአብሔር መንጋ እረኞች ናቸው። (1ኛ ጴጥ. 5፡1-4 አንብብ።) ከርስቶስ ስለ እረኝነቱ ሚና | ከተናገረው ነገር የእግዚአብሔርን መንጋ ስለመምራት እንማራለን።

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

%d bloggers like this: