በዚህ ክፍል ስለ መንፈስ ቅዱስ ዓላማና አገልግሎት ግልጽ አሳብ የሚያስተላልፉ ትምህርቶች ይገኛሉ። ምንም እንኳ አንዳንድ ክርስቲያኖች በልሳን መናገርን በመሳሰሉት አንዳንድ የመንፈስ ቅዱስ ስጦታዎች ብቻ ደስ ቢሰኙም፥ የመንፈስ ቅዱስ መሠረታዊ ዓላማና አገልግሎት ምን እንደ ሆነ ለማወቅ ከፈለግን፥ እነዚህን በክርስቶስ የተነገሩትን እውነቶች መረዳት ይኖርብናል።
ሀ. መንፈስ ቅዱስ ከእግዚአብሔር አብ በክርስቶስ በኩል ይመጣል።
ለ. መንፈስ ቅዱስ «ሌላው» አጽናኝ ነው። በግሪክ ቋንቋ «ሌላ» የሚለውን ቃል ለመግለጽ የገቡ ሁለት ቃላት አሉ። እነዚህም «በዐይነቱ የተለየ»፤ ሌላው ደግሞ «በዐይነቱ ያው የሆነ» የሚሉ ናቸው። ዮሐንስ የመረጠው «በዐይነቱ ያው የሆነ» የሚለውን ነው። ይህም ክርስቶስ መንፈስ ቅዱስ በአካልና በአገልግሎት ከእርሱ ጋር ተመሳሳይ እንደሚሆን ያመለከተበት ነው።
ሐ. መንፈስ ቅዱስ «አጽናኝ» ነው። «አጽናኝ» የሚለውን ለመግለጽ የገባው የግሪኩ ቃል ብዙ ፍችዎችን ይዟል። በግሪክ፥ ቃሉ ችሎትን የሚያመለክት ሕጋዊ ጽንሰ-አሳብን የያዘ ነው። «አጽናኝ» እንደ ጠበቃ በችሎት ፊት ከተከሳሹ ጎን ቆሞ በአግባቡ እንዲከራከር የሚረዳው ሰው ነው። ስለሆነም፥ የመንፈስ ቅዱስ መሠረታዊ አገልግሎት በችግራችን ጊዜ መጽናናትን መስጠት ብቻ ሳይሆን፥ በእግዚአብሔር ፊት ባለን አገልግሎት ጸንተን እንድንቆም ማገዝ ነው።
መ. መንፈስ ቅዱስ «የእውነት መንፈስ» ነው። ከዚህ ስያሜ እንደምንረዳው፥ የመንፈስ ቅዱስ ዐቢይ አገልግሎት ተአምራትን ለማድረግ ኃይልን መስጠት ሳይሆን፥ ሰዎች እውነተኛውን ነገር ተረድተው እንዲኖሩበት መርዳት ነው።
ሠ. መንፈስ ቅዱስ «ለዘላለም» ከእነርሱ ጋር ይኖራል። የመጀመሪያው አጽናኝ የሆነው ክርስቶስ ወደ ምድር ሲመጣ፥ በፍልስጥኤም አገር ብቻ ኖሮ ወደ ሰማይ ተመልሶአል። መንፈስ ቅዱስ ግን መንፈስ በመሆኑ፥ በአንድ ጊዜ በሁሉም ስፍራ ይገኛል። ስለሆነም፥ አንድ የክርስቶስ ተከታይ በዓለም ውስጥ በየትኛውም ስፍራ ቢገኝ መንፈስ ቅዱስ አብሮት ይሆናል። በተጨማሪም፥ መንፈስ ቅዱስ ከዳንንበት ጊዜ ጀምሮ ወደ ሰማይ እስከምንሄድበት ጊዜ ድረስ ሁልጊዜም አብሮን ይሆናል። መንፈስ ቅዱስ እንደ ክርስቶስ መጥቶ ተመልሶ የሚሄድ ላይሆን፥ ሁልጊዜም አብሮን ይኖራል።
ረ. መንፈስ ቅዱስ ለዓለም አይታይም። የክርስቶስ ተከታዮች ግን በውስጣቸው ስለሚኖር ያውቁታል። ክርስቶስ በመንፈስ ቅዱስ አገልግሎት ውስጥ በቅርቡ ለውጥ እንዲሚኖር ገልጾአል። ክርስቶስን በሚከተሉባት ወቅት መንፈስ ቅዱስ ከደቀ መዛሙርቱ «ጋር» ነበር። ከበዓለ ኀምሳ በኋላ ግን በደቀ መዛሙርቱ «ውስጥ» ይኖራል።
ሰ. መንፈስ ቅዱስ ያስተምራል። ክርስቶስን በሚያከብር መንገድ እንዴት መመላለስ እንዳለብን ያስተምረናል። ክርስቶስ ለተከታዮቹ ያስተማረውን እውነት ያሳስባቸዋል።
የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) በመንፈስ ቅዱስ ከተነገሩት እውነታዎች በቤተ ክርስቲያንህ ትኩረት ያልተሰጠባቸው የትኞቹ ናቸው? ለ) በቤተ ክርስቲያንህ ስለ መንፈስ ቅዱስ ትኩረት የተሰጠው ምንድን ነው? ከዚህ እንዴት ይለያል?
ክርስቶስ ደቀ መዛሙርቱን በሌሎች መንገዶችም አበረታቷል። አንደኛው፥ ምንም እንኳ ለጊዜው በሥጋዊ ዓይኖቻቸው ባያዩትም፥ በመንግሥተ ሰማይ እንደሚያገኙት ገልጾላቸዋል። ክርስቶስ ከእነርሱ የተለየው ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ አልነበረም።
ሁለተኛው፥ ክርስቶስ ስለ ሰጣቸው ዐቢይ ትእዛዝ እንደገና አስታውሷቸው ነበር። ለእርሱ በመታዘዝ ፍቅራቸውን እንዲያሳዩም አሳስቧቸዋል። እርስ በርሳቸው እንዲዋደዱ የጠየቀበትንና ክርስቶስ የሰጣቸውን ሌሎች ትእዛዛት መጠበቅ ያስፈልጋቸው ነበር። ክርስቶስን እንደምንወደው ከምናሳይባቸው መንገዶች አንዱ፥ ቃሉን መታዘዛችን ነው። ክርስቶስን የምንታዘዘው እንዲወደን ሳይሆን፥ ስለምንወደው ነው። እምነትና ፍቅር በሚኖረን ጊዜ፥ ክርስቶስ ብቻ ሳይሆን እግዚአብሔር አብም ይወደናል።
ሦስተኛው፥ ክርስቶስ በሁኔታዎች የማይወሰን ሰላም እንደሚሰጣቸው ተናገረ። ለዓለም ሰላም ማለት ጦርነትን፥ በሽታን ወይም ሁከትን የመሳሰሉ ችግሮች አለመኖራቸው ማለት ነው። ስለሆነም መንፈስ ቅዱስ የሌለው ወይም በመንፈስ ቅዱስ ኃይል የማይመላለስ ሰው እነዚህ ችግሮች በሚከሰቱበት ጊዜ ሰላም ያጣል። ክርስቶስ ግን ሰላምን የኅብረትና የአንድነት መኖር አድርጎ ያየዋል። መንፈስ ቅዱስ በችግሮቻችን ጊዜ ሁል ጊዜም ከእኛ ጋር ስለሚኖርና እግዚአብሔርም ችግሮቻችንን ሁሉ ስለሚከታተል፥ የእግዚአብሔር ተከታዮች በመከራ ውስጥ እንኳ የሰላምና የዋስትና ስሜት ይኖራቸዋል።
አራተኛው፥ ምንም እንኳ «የዓለም ገዥ » የሆነው ሰይጣን ሰዎች ክርስቶስን ወደ መስቀል እንዲወስዱት ለማነሣሣት በመዘጋጀት ላይ ቢሆንም፥ ክርስቶስ በነገሮች ላይ የነበረውን ሥልጣን አጥቷል ማለት አይደለም። የክርስቶስን ሕይወት የሚቆጣጠረው እግዚአብሔር እንጂ ሰይጣን አይደለም። እግዚአብሔር ክርስቶስ በመስቀል ላይ እንዲሞት ስለነገረው ከፍቅር የተነሣ ይህንኑ ተግባራዊ ማድረጉ የማይቀር ነው። በተመሳሳይ ሁኔታ፥ ሰይጣን ዛሬም እኛን ይተናኮለናል። ነገር ግን በሕይወታችን ላይ የሚፈጸሙትን ነገሮች ለመቋቋም የሚያስችል ሥልጣን፥ በእኛ ላይ እንደሌለው መገንዘብ አለብን። ኃይል የክርስቶስ ነው። ሰይጣን ሊሠራ የሚችለው እግዚአብሔር እስከ ፈቀደለት ገደብ ድረስ ብቻ ነው።
የውይይት ጥያቄ፡- ክርስቲያኖች እነዚህን ትምህርቶች ከሕይወታቸው ጋር ማዛመድ ያለባቸውን ምክንያቶች ዘርዝር።
(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)