ሮሜ 8፡1-39

፩. እግዚአብሔር ልጆቹ የኃጢአትን ኃይል ያሸንፉ ዘንድ መንፈስ ቅዱስን ሰጥቷቸዋል (ሮሜ 8፡1-17)

የውይይት ጥያቄ፡- ሮሜ 8ን አንብብ። ) ክርስቲያን ሕግን ከመጠበቅ፥ በእግዚአብሔር ጻድቅ ከመደረግና ከኃጢአት ተፈጥሮ ኃይል ጋር ያለውን ግንኙነት ጠቅለል አድርገህ ግለጽ። 2) መንፈስ ቅዱስ ለአማኙ የሚያደርጋቸውን ነገሮች ዘርዝር። 3) ጳውሎስ የክርስቲያኑን የወደፊት ተስፋ እንዴት ይገልጸዋል? 4) ጳውሎስ እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር ያለንን ግንኙነት አስተማማኝ ለማድረግ እንዳከናወናቸው የሚገልጻቸውን ነገሮች ዘርዝር።

ሮሜ 6፡1-8፡17 በክርስትና አኗኗራችን እንዴት ቅዱሳን ልንሆን እንደምንችል የሚያስረዳ መሆኑን ማስታወሱ ጠቃሚ ነው። ጳውሎስ የሚያብራራው እንዴት ክርስቲያን መሆን እንደሚቻል ሳይሆን ክርስቲያን ከሆንሁ በኋላ፥ የእግዚአብሔርን ሕግጋት ለመፈጸም እየፈለግሁ የኃጢአት ባሕርይ ሲያሸንፈኝ ምን ተስፋ ይኖረኛል? የሚለውን ነው።

ጳውሎስ የሚከተሉትን ነጥቦች በማሳየት ለዚህ ጥያቄ ምላሽ ይሰጣል።

  1. በክርስቶስ ካመንን በኋላ ምንም እንኳ ከኃጢአት ጋር ብንታገልና ለመታዘዝ የምንፈልጋቸውን የእግዚአብሔርን ሕግጋት ብንተላለፍም፥ የእግዚአብሔር ውሳኔ «ጥፋተኛ አይደላችሁም» የሚል ነው (ሮሜ 8፡1-4)። ከእግዚአብሔር ዘንድ ዘላለማዊ ኩነኔ እይጠብቀንም። የክርስቶስ ሞት ከመዳናችን በፊት፥ አሁንም በየዕለቱ፥ እንዲሁም እስክንሞት ድረስ የምንፈጽማቸውን ኃጢአቶች ሁሉ ቅጣት ከፍሏል። ስለሆነም፥ ኃጢአትን በምንፈጽምበት ጊዜ ወደ ሲዖል እንድንወርድ አይፈርድብንም። ጳውሎስ ሕይወታችን ሁሉ በክርስቶስ ውስጥ እንደተሰወረ ለማመልከት ክርስቲያን «በኢየሱስ ክርስቶስ ውስጥ» መሆኑን አመልክቷል። ይህ ከክርስቶስ ጋር እስከተዛመድን ድረስ የክርስቶስን በረከቶች ሁሉ እንደምንቀበል ለማሳየት የሚጠቀምበት ተወዳጅ አገለላጽ ነው።

እንግዲህ፥ ኃጢአታችንን መናዘዝ የሚያስፈልገን ለምንድን ነው? ኃጢአትን ስንፈጽም ምን ይከሰታል? ኃጢአት ኑዛዜና ዕርቅ እስክንፈጥር ድረስ ከሰማያዊ አባታችን ጋር ያለንን ግንኙነት ያደናቅፋል። ይህ ልጃችን ለመታዘዝ በማይፈልጉበት ጊዜ ከሚሆነው ሁኔታ ጋር ተመሳሳይ ነው። ልጅነቱ ባይፋቅም በተግባሩ ማዘናችን ግንኙነቱን ያበላሸዋል።

ጳውሎስ በዳንን ጊዜ መንፈስ ቅዱስ መንፈሳዊ ሕይወት እንደሰጠን አብራርቷል። ይህም ሕይወት ከኃጢአት ኃይልና ይጠብቀን ከነበረው የሞት ፍርድ (ሲዖል) አድኖናል። ክርስቶስ «የኃጢአት መሥዋዕታችን» (ለፈጸምናቸው ኃጢአቶች የተከመረብንን ዕዳ የከፈለው) ሆኖ በእግዚአብሔር ፊት ጻድቃን አድርጎናል። ይህም በፍጹም ኃጢአት ሠርተን እንደማናውቅና የብሉይ ኪዳን ሕግጋትን ሙሉ በሙሉ እንደጠበቅን ያህል በእግዚአብሔር ፊት የምንስተናገድበት መንገድ ነው።

  1. አማኞች በመሆናችን፥ የምንመላለሰው በኃጢአት ባሕርይ ሳይሆን በመንፈስ ቅዱስ ኃይል ነው። በኃጢአት ተፈጥሮና በመንፈስ ቅዱስ በመመላለስ መካከል ያለው ልዩነት ምንድን ነው? በሮሜ 8፡5-8 ጳውሎስ እነዚህን ሁለት ሁኔታዎች ያነጻጽራል።

ሀ. የኃጢአት ተፈጥሮ ቁጥጥር የሚጀምረው ከአእምሮ ነው። ይህም የራስወዳድነት አሳባችን፥ ራስን ለማስደሰት መፈለግንና ክፉ ባሕሪያችንን ያረካል ብለን የምናስበውን እርምጃ መውሰድን ያጠቃልላል። በአንጻሩ፥ በመንፈስ ቅዱስ ቁጥጥር ሥር የሚኖር ሰው ስለ መንፈሳዊ ነገሮች ያስባል። ይህም እግዚአብሔርን ማስደሰትን፥ ማክበርን፥ ለእርሱ መገዛትን፥ ማምለክን፥ ሌሎችን ማገልገልን፥ ወዘተ…. ያጠቃልላል። ጳውሎስ እንደሚለው፥ እግዚአብሔርን ወይም የኃጢአት ባሕሪያችንን የማስደሰቱ ጦርነት የሚጀምረው ከአሳባችን ነው። ክርስቲያኖች ለሚያነቡት፥ በቴሌቪዥን ወይም በቪዲዮ ለሚመለከቱት ወይም ከሰዎች ለሚሰሟቸው ነገሮች ጥንቃቄ ማድረግ ያለባቸው ለዚህ ነው። ክፉ አሳቦች አእምሯችንን ሲሞሉት ተግባራችንም ክፉ ይሆናል።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) አስተሳሰብህ በባሕሪህ፥ እግዚአብሔርን ወይም የኃጢአት ባሕሪህን በመታዘዝህ ላይ እንዴት ተጽዕኖ እንደሚያሳድር ግለጽ። ለ) እግዚአብሔርን ስለሚያስከብሩ ነገሮች ታስብ ዘንድ የምትመለከተውንና የምትስማውን እንዴት እንደምትመርጥ ምሳሌዎችን በመስጠት አብራራ (ፊልጵ. 4፡8ን አንብብ።)

ለ. ባለማቋረጥ ስለ ክፉ ነገሮች የሚያስበው ሰው ሞትን ሲያጭድ፥ በመንፈስ ቅዱስ ቁጥጥር ሥር የሚኖር አእምሮ ሕይወትን ያጭዳል። ሥጋውን ስለማስደሰት፥ የሚፈልገውን ብቻ ስለማድረግ የሚያስብ ሰው በመንፈሳዊ ሕይወቱ የሞተ ሲሆን፥ በሥጋ ከሞተ በኋላ የዘላለምን ሞት ይጋፈጣል። የኃጢአት ባሕሪያችንን ለማስደሰት ስንል የምንኖረው ሕይወት በቤተሰባችን፥ በቤተ ክርስቲያናችንና በማኅበረሰባችን ውስጥ የሚኖረንን ግንኙነት ያበላሻል። ነገር ግን በሚያስበው አሳብ መንፈስ ቅዱስን ለማክበር የሚፈልግ ሰው መንፈሳዊ ሕይወት ያለው ሲሆን፥ በሥጋ በሚሞትበት ጊዜ የዘላለም ሕይወትን ይቀበላል። እንዲህ ዓይነቱ አኗኗር ለሚኖሩን ለግንኙነቶቻችን ሁሉ ሕይወትን ይሰጣል።

ሐ. በኃጢአት የተበላሸ አእምሮ ማረጋገጫው ግለሰቡ እግዚአብሔርን ለማስደሰት የማይኖር መሆኑ ነው። ለእግዚአብሔር ስፍራ የለውም ወይም ይጠላዋል። ለእግዚአብሔር ሕግጋት የመገዛት ፍላጎት የሌለው ሲሆን፥ ትእዛዛቱን ለመታዘዝ የሚያስችል ኃይል የለውም። ግለሰቡ መልካምና ግብረገባዊ ቢመስልም፥ እግዚአብሔርን ሊያስከብር ወይም ሊያስደስት አይችልም። እግዚአብሔርን ልናስደስትና እርሱ የሚፈልገውን ተግባር ልናከናውን የምንችለው አእምሯችን፥ ሕይወታችንና ልባችን በመንፈስ ቅዱስ ቁጥጥር ሥር ሲውል ብቻ ነው።

  1. እግዚአብሔር የኃጢአትን ባሕርይ እንቋቋም ዘንድ ለእያንዳንዱ አማኝ መንፈስ ቅዱስን ሰጥቷል (ሮሜ 8፡9-17)። ክርስቲያኖች በምንሆንበት ጊዜ አዲስ ባሕርይ ከመቀበላችን በላይ፥ እግዚአብሔር ራሱ በመንፈስ ቅዱስ አማካኝነት በሕይወታችን ውስጥ ይኖራል። ምንም እንኳ አንዳንድ ሰዎች ክርስቲያኖች መንፈስ ቅዱስን የሚቀበሉት ከዳኑ በኋላ በመንፈሳዊ ሕይወታቸው ሲያድጉ ነው ብለው ቢያስተምሩም፥ መጽሐፍ ቅዱስ ይህን አስተምህሮ አይደግፍም። ጳውሎስ መንፈስ ቅዱስ በክርስቲያኑ ውስጥ ከሌለ፥ ያ ሰው ከክርስቶስ ጋር ኅብረት እንደ ሌለው ገልጾአል (ሮሜ 8፡9)። መንፈስ ቅዱስ በእያንዳንዱ አማኝ ውስጥ በመኖሩ ምክንያት የሚፈጸሙ አያሌ ነገሮች አሉ።

ሀ. ከእንግዲህ የሚቆጣጠረን የኃጢአት ባሕርይ ሳይሆን በውስጣችን የሚኖረው መንፈስ ቅዱስ ነው። ጳውሎስ፥ «ክርስቶስ በእናንተ ዘንድ ቢሆን ሰውነታችሁ በኃጢአት ምክንያት የሞተ ነው። መንፈሳችሁ በጽድቅ ምክንያት ሕያው ነው» (ሮሜ 8፡10)። ሊል ምን ለማለት እንደፈለገ ለማወቅ አስቸጋሪ ነው። ምናልባትም ጳውሎስ ይህን ሲል የወደቀው ሰብአዊ አካል በመሆናችን በሥጋ እንደምንሞትና፥ መንፈሳዊ ሕይወት ስለተሰጠንና እግዚአብሔርም ጻድቃን ብሎ ስለጠራን፥ ከሞት ተነሥተን ለዘላለም ሕያዋን እንደምንሆን መግለጹ ይሆናል። ወይም ደግሞ ለኃጢአት ባሕሪያችን ቁጥጥር እንደሞትንና እግዚአብሔር የሚፈልገውን መንገድ ለመከተል ሕያዋን እንደሆንን መግለጹ ይሆናል።

ለ. መንፈስ ቅዱስ በሚፈልገው መንገድ ለመኖር መምረጥ አለብን። አንዳንድ ክርስቲያኖች ምንም መልካም ነገር ልንፈጽም እንችልም ብለው ያስተምራሉ። ስለሆነም፥ ዝም ብለን መንፈስ ቅዱስ ሁሉንም ነገር እንዲያደርግልን መጠበቅ አለብን ይላሉ። ነገር ግን ጳውሎስና ሌሎችም አገልጋዮች እግዚአብሔርን ስለሚያስከብሩት ነገሮች ለማሰብ መምረጥ እንዳለብን ያሳስባሉ። የእግዚአብሔርን ትእዛዛት ለመጠበቅና መንፈስ ቅዱስ በሕይወታችን ውስጥ እንዲሠራ ልንፈቅድለትና ራሳችንን ልንሰጠው ይገባል። ኃይል የሚመጣው ከመንፈስ ቅዱስ ነው፥ ያለ እርሱ ኃይል እግዚአብሔርን ልናስደስት አንችልም። መንፈስ ቅዱስ በአእምሯችንና በፈቃዳችን ውስጥ ስለሚሠራ፥ እርሱን ለመከተል ወይም ላለመከተል መምረጥ አለብን። እግዚአብሔር ከሕይወታችን የሚፈልገውን በመቃወም ፀረ-እግዚአብሔር የሆኑትን ነገሮች ብንመርጥ፥ በኃጢአት ተፈጥሯችን ቁጥጥር ሥር እንኖራለን ማለት ነው። እነዚህ ምርጫዎች የልባችንን ሁኔታ በማሳየት ክርስቲያኖች መሆን አለመሆናችንን ያሳያሉ። ምንም እንኳ ክርስቲያኖች በኃጢአት ቢወድቁም፥ መንፈስ ቅዱስ በውስጣቸው ስለሚኖር ባለማቋረጥ የኃጢአት ተፈጥሯቸውን ለመከተል አይመርጡም። የኃጢአት ባሕርያችንን የመግደል ወይም ያለመከተል ልማድ ልናዳብር ይገባል።

ሐ. መንፈስ ቅዱስ የእግዚአብሔር ልጆች እንድንሆን ያደርገናል። የግሪኩ ቃል የሚያመለክተው ትንሽን ልጅ ሳይሆን በእግዚአብሔር ቤተሰብ ውስጥ ኃላፊነት ሊቀበል የሚችለውን የበሰለ ልጅ ነው። መንፈስ ቅዱስ የእግዚአብሔር መንግሥት ሕጋዊ ወራሾች ያደርገናል። እንዲያውም ከክርስቶስ ጋር አብረን እንደምንወርስ ተገልጾአል። በሌላ አገላለጽ፥ ክርስቶስ ያለ እኛ መንግሥቱን ከእግዚአብሔር ዘንድ አይቀበልም ማለት ነው። መንግሥቱን አብረን ተቀብለን ከክርስቶስ ጋር እንነግሣለን። ባይታዘዝ ጌታው ምን ዓይነት ቅጣት እንደሚያደርስበት በማሰብ ከሚፈራው ባሪያ በተቃራኒ ከእግዚአብሔር ዘንድ ዕርዳታ ለመጠየቅ የልጅነት ነጻነት አለን። በተለይም የኃጢአትን ተፈጥሮ ስበት ለመቋቋም የእርሱን እገዛ ልንጠይቅ እንችላለን። «አባ» የሚለው ቃል አንድ ትንሽ አይሁዳዊ ልጅ በፍቅር አባቱን የሚጠራበት ነው። ኃጢአት በምንሠራበት ጊዜ ሳይቀር መንፈስ ቅዱስ ባለማቋረጥ ስለሚያሳስበን በእግዚአብሔር የተወደድን ልዩ ልጆቹ እንጂ ከኩነኔው ሥር የወደቅን አይደለንም።

የውይይት ጥያቄ፡– በኃጢአት፥ በኃጢአት ባሕርይና እነዚህን ማሸነፍ በሚቻልበት መንገድ መካከል ስላለው ግንኙነት በራስህ አገላለጽ ጠቅለል አድርገህ ጻፍ።

፪. የእግዚአብሔር ልጅ የኋላ ኋላ እንደሚከበርና የእግዚአብሔርን የማያቋርጥ ፍቅር እንደሚያገኝ ማረጋገጫ ተሰጥቶታል (ሮሜ 8፡18-39)።

በምድር ላይ በሚያጋጥመን መከራ ምክንያት ክርስቲያኖች ለክርስቶስ ለመኖር እንደክማለን። በሽታ አጥቅቶን ሳለ እግዚአብሔር ጸሎታችንን የማይመልስ የሚመስልበት ጊዜ አለ። ክርስቲያንነታችንን ባለመደበቃችን ሥራ ወይም የትምህርት ዕድል የምንነፈግባቸው ጊዜያት አሉ ወይም ትምህርታችንን ለመቀጠል እንቸገራለን፥ ነገር ግን ብናጭበረብር ወይም እምነታችንን ብንደብቅ ይህንን ሁሉ የማግኘት ዕድላችን ሰፊ ይሆን ነበር። ባል ሚስቱንና ልጆቹን ትቶ በሞት ያልፋል። ከኃጢአት ባሕርይ ጋር የማያቋርጥ ትግል ይካሄዳል። ከዚህ ሁሉ በላይ፥ የክርስቶስ ተከታዮች በመሆናችን የማያቋርጥ ጥቃትና ስደት ይደርስብናል። እስከ መጨረሻው ድረስ በታማኝነት እንድንጸና የሚያደርገን ምንድን ነው? ጳውሎስ ሁኔታዎች አመቺ በማይሆኑባቸው ጊዜያት ሳይቀር በእምነታችን እንድንጸና የሚያደርጉትን የድነት (ደኅንነት) ሂደትና ፍጻሜ እውነቶች ገልጾአል።

ሀ. የእግዚአብሔር ልጆች ከክርስቶስ ጋር ይከብራሉ (ሮሜ 8፡18-25)። የሥነ መለኮት ምሁራን ድነትን (ደኅንነትን) በሦስት የጊዜ አስተሳሰቦች (frames) ይከፍላሉ። በክርስቶስ አምነን ከኃጢአታችን የዳንንበት «የአንድ ጊዜ» ኃላፊ የድነት ገጠመኝ አለ። ይህም ጳውሎስ በሮሜ 1-5 እንዳብራራው፥ መጽደቅ ይባላል። ከዚያም ከኃጢአት ኃይል እየተላቀቅን በቅድስና የምናድግበት «ቀጣይ» የድነት ልምምድ አለ። ይህም መቀደስ ይበላል። ጳውሎስ ስለ መቀደሱ በሮሜ 6፡1-8፡17 አስተምሯል። አሁን ጳውሎስ ወደ መንግሥተ ሰማይ ደርሰን ከምድራዊ ትግሎቻችን ሁሉ ስለምናርፍበት ጊዜ ማብራራት ይጀምራል፡፡ እግዚአብሔር በሚፈልገው መንገድ ኢየሱስ ክርስቶስን የምንመስል ቅዱሳን ልጆች እንሆናለን (1ኛ ዮሐ 3፡2 አንብብ።) ይህም «መከበር» ይባላል።

ጳውሎስ ይህን ክፍል የሚጀምረው፥ «አብረን መከራ ብንቀበል ከክርስቶስ ጋር አብረን ወራሾችን ነን» በሚል ማስጠንቀቂያ ነው (ሮሜ 8፡17)። ብዙ ክርስቲያኖች ክርስቶስን በመከተላችን ችግሮቻችን ሁሉ ይወገዳሉ ብለው ያስተምራሉ። በሽታም ሆነ ድህነት እንደማያጠቃን ያስባሉ። ሀብትን እንደምናካብትና ከስደት እንደምንተርፍ ያምናሉ። ጳውሎስ ግን ከክርስቶስ ጋር አብረን የምንወርስ ከሆነ፣ አሁን የመከራው ተካፋዮች መሆን እንዳለብን ያስጠነቅቀናል። ጳውሎስ ሁኔታዎችን በተስፋ መቁረጥ ወይም እንደ ዕድል ቆጥሮ በመቀበል ፈንታ እነዚህ ጊዜያት እንዴት ትርፋማ እንደሆኑ ይናገራል።

አዲስ ኪዳን ክርስቲያን በማንኛውም ጊዜ መከራን ሊቀበል እንደሚችል ያስተምራል። በተለይም ለእምነቱ መከራ በሚቀበልበት ጊዜ እውነተኛው የመከራ ተቀባይ ክርስቶስ እንደሆነ ያስተምራል። ቤተ ክርስቲያን የክርስቶስ አካል ስለሆነች፥ ቤተ ክርስቲያን ስትሠቃይ እርሱም ይሠቃያል። የተፈጥሮ ዝንባሌያችን ግን ከስደት ለመሸሽ ይጥራል። ጳውሎስ ግን ክርስቶስ በሚከብርበት ጊዜ እኛም የተዘጋጀልንን ክብር የምናገኘው ወደ ሕይወታችን የሚመጣውን መከራ (ሥጋዊ ችግሮችና ስደት) ከተቀበልን ብቻ መሆኑን ያስረዳል።

ጳውሎስን ጨምሮ መከራን የሚወድ ማንም ሰው የለም። (ጳውሎስ ለወንጌል ሲል የተዘረዘሩትን መከራዎች ሁሉ ተቀብሏል። ከ2ኛ ቆሮንቶስ 11፡16-33 አንብብ።) ነገር ግን ጳውሎስ ጊዜያዊውን ምድራዊ መከራ ክርስቶስን በታማኝነት ለሚከተሉ ሰዎች ከተዘጋጀው ዘላለማዊ ክብርና ሽልማት ጋር ያነጻጽራል። በ2ኛ ቆሮንቶስ 4፡16-18 ጳውሎስ መከራዎቹ «ቀላል» እና «ጊዜያዊ» መሆናቸውን ገልጾአል። በአዳም ኃጢአት ምክንያት የተጎዱትን ጨምሮ ፍጥረት ሁሉ ክርስቶስ በክብሩ የሚመለስበትን ጊዜ አብሮን ይጠብቃል። ብዙ ዓይነት መከራዎች በሚያጋጥሙን ጊዜ ሥቃይ፥ መከራ፥ መለየትና ሞት የማይኖርበትን የነጻነት ጊዜ እንናፍቃለን። እንዲሁም፥ ሙሉ ለሙሉ ከኃጢአት ባሕሪያችን የምንገላገልበትንና ክርስቶስን እንደሚገባ የምናከብርበትን ጊዜ እንናፍቃለን። ዛሬ ተስፋ ቆርጠን ለኃጢአት ባሕሪያችን እንዳንገዛ የሚያደርገን አንድ ቀን የእግዚአብሔር የተስፋ ቃሎች በሙሉ በዓይኖቻችን ፊት ይፈጸማሉ የሚል እምነት ነው። ግለኝነታችንን ለማሸነፍና የኃጢአት ተፈጥሯችንን ላለመስማት ከፈለግን ዓይኖቻችንን ወደፊት በሚሆነው ሰማያዊ ክብር ላይ ማነጣጠር አለብን።

ለ. ከኃጢአት ጋር በምናደርገው ትግልና በመከራችን ወቅት መንፈስ ቅዱስ በቅርባችን ሆኖ ይማልድልናል (ሮሜ 8፡26-27)። አንዳንድ ሰዎች በሚጸልዩበት ጊዜ የሚያሰሙት የመቃተት ድምፅ መንፈስ ቅዱስ ለእነርሱ መጸለዩን እንደሚያሳይ ይናገራሉ። የጳውሎስ ትኩረት ግን ይሄ አልነበረም። እርሱ የሚናገረው ስለ መከራ፥ በተለይም ከኃጢአት ጋር ስንታገል ስለሚገጥመን መከራ ነው። በእነዚህ ጊዜያት ተስፋ ልንቆርጥ አይገባም። በውስጣችን የሚኖረው መንፈስ ቅዱስ እኛን ከማወቁም በላይ፥ እግዚአብሔር ለእኛ ያለውን ፈቃድም ያውቃል። አንዳንድ ጊዜ የራቀን ቢመስልም እንኳ እርሱ ከእኛ የራቀ አይደለም። ይልቁንም በጸሎታችን አብሮን ይቃትታል። ራስ ወዳድነት ከሚታይባቸው ጸሎቶቻችን በተቃራኒ፥ የመንፈስ ቅዱስ ጸሎት እንደ እግዚአብሔር ፍቃድ የሚካሄድ በመሆኑ ምላሽን ያገኛል። ይህም ታላቅ ተስፋ ሊያስጨብጠን ይገባል።

ሐ. እግዚአብሔርን ብንወድደው ሁሉንም ነገር ወደ በጎ እንደሚለውጠው ተስፋ ሰጥቶናል (ሮሜ 8፡28)። አንዳንድ ክርስቲያኖች ይህን ጥቅስ በተሳሳተ መንገድ ይገነዘባሉ። ይህ ጥቅስ እግዚአብሔር በክርስቲያን ላይ ምንም ዓይነት ክፉ ነገር እንደማይደርስበት የሚገልጽ መሆኑን ይናገራሉ። ጳውሎስ ክርስቲያን በስደት ሊሞት እንደሚችል ስለሚናገር፥ እግዚአብሔር ከየትኛውም ዓይነት ክፉ ነገር ይጠብቀናል ማለቱ አይደለም። ነገር ግን እግዚአብሔር በሕይወታችን ውስጥ እንዳለና ሁሉንም ነገር እንደሚቆጣጠር ማወቅ ይኖርብናል። በታማኝነት ካከብርነው እግዚአብሔር አስቸጋሪ ሁኔታዎችን ለበጎነት ሊጠቀም ይችላል። ያም በጎነት መንፈሳዊ ዕድገት ወይም የሌላ ሰው ድነትን (ደኅንነትን) ማግኘት ሊሆን ይችላል። ብዙውን ጊዜ ግን በጎነቱን ምን እንደሆነ አናውቅም። ነገር ግን እግዚአብሔር በልጆቹ ሕይወት ውስጥ በቅርብ እንደሚሠራና የሚከሰተውን ነገር ሁሉ እንደሚቆጣጠር ማወቅ እንችላለን።

መ. እግዚአብሔር ከአንድ ሰው ጋር ግንኙነት የሚያደርገው በአጋጣሚ ወይም በግለሰቡ ምርጫ ብቻ ሳይሆን በራሱ አሠራር ነው (ሮሜ 8፡28-30)። ብዙውን ጊዜ ድነትን (ደኅንነትን) ከሰው አንጻር በመመልከት፥ እንዴት በእግዚአብሔር እንዳመንን እናስባለን። ጳውሎስ ግን በመከራ ውስጥ ለነበሩት ክርስቲያኖች ድነትን ከእግዚአብሔር አንጻር ለማሳየት ፈለገ። በሕይወታቸው ውስጥ ችግሮች መከሰታቸው በእግዚአብሔር መተዋቸውን አያመለክትም። ጳውሎስ እግዚአብሔር በክርስቲያኖች ሕይወት ውስጥ የሚያስደንቅ ተግባር እንደሚያከናውን አስረድቷል። ጳውሎስ እግዚአብሔር ለእያንዳንዱ አማኝ እንዳከናወነ የዘረዘራቸውን የድነት (ደኅንነት) ደረጃዎች ከዚህ በታች ተመልከት።

  1. እግዚአብሔር በዓላማው መሠረት ጠርቶናል። በዓለም ውስጥ ከሚገኙ በቢሊዮኖች ከሚቆጠሩ ሰዎች እግዚአብሔር አንተን መርጦሃል። ለምን? ከሌሎች ስለምትሻል ነው? አይደለም። ነገር ግን እግዚአብሔር በፍቅሩ ስለመረጠህ ነው።
  2. እግዚአብሔር አስቀድሞ አውቆሃል። ከመወለድህ በፊት ጀምሮ እግዚአብሔር ከአንተ ጋር የቃል ኪዳን ግንኙነት አድርጓል። በዕብራይስጥ የዚህ ቃል ትርጉም እግዚአብሔር በእርሱ እንደምታምን ያውቃል ከማለት ያለፈ ነው። እግዚአብሔር ከአንተ ጋር ለማድረግ የወሰነውን ግንኙነት ያመለክታል።
  3. የልጁን መልክ እንድትመስል አስቀድሞ ወስኗል። በክርስቶስ ከማመንህ በፊት፥ እግዚአብሔር ከአንተ ጋር ግንኙነት እንደሚያደርግ አስቀድሞ ወስኗል። መንግሥተ ሰማይ በደረስህ ጊዜ ልጁ ኢየሱስ ክርስቶስን ትመስል ዘንድ በሕይወትህ ውስጥ ለመሥራት ቃል ገብቷል። አመለካከቶችህ፥ ባሕርይህና ተግባራትህ የክርስቶስን ይመስሉ ዘንድ ይለወጣሉ።
  4. እግዚአብሔር በጊዜው ጠርቶሃል። እግዚአብሔር ጥሪውን እንኳ ለመስማት የማትችል ሙት ኃጢአተኛ ሆነህ ሳለ፥ መንፈሳዊ ዓይኖችህንና ጆሮዎችህን በመክፈት፥ ጠራህና በእርሱ እንድታምን አድርጎሃል።
  5. እግዚአብሔር ለፈጸምሃቸው ኃጢአቶች ሁሉ ተጠያቂ እንዳልሆንህ በማወጅ አጽድቆሃል።
  6. እግዚአብሔር አክብሮሃል። ድነትህ (ደኅንነትህ) በእግዚአብሔር ዓይኖች ፊት አስተማማኝ ነው። እርሱ በሕይወትህ መልካሙን ሥራ ከጀመረ ወዲያ እንደሚፈጽመው ቃል ገብቷል (ፊልጵ. 1፡6)። ማንም ከእጁ ሊነጥቅህ እንደማይችል ተናግሮሃል (ዮሐ. 10፡28-29)። በተጨማሪም፥ እግዚአብሔር ወደ መንግሥተ ሰማይ እስክትደርስና ለእግዚአብሔር ልጅ የተዘጋጀውን ክብር እስክትቀበል ድረስ የድነት (ደኅንነት) ሂደቱ እንደማይቋረጥ የተስፋ ቃሉን ሰጥቷል።

ይህ ምናልባት እንግዳ ነገር ሊመስልህ ይችላል። በኢትዮጵያ ውስጥ ብዙዎቻችን ትኩረት የምንሰጠው በሰዎች የማመን ኃላፊነት ላይ ነው። ጳውሎስ ግን ድነትን (ደኅንነትን) ከመለኮታዊ እይታ አንጻር ይመለከታል። ይህም እግዚአብሔር ሰዎች ከማመናቸው በፊት ጀምሮ ወደ መንግሥተ ሰማይ እስከሚደርሱበት ጊዜ ሙሉ በሙሉ ተግቶ የሚሠራ መሆኑን የሚያሳይ ነው። ምናልባትም የድነት ሥራ እንዴት እንደሚካሄድ፥ በድነት ሥራ ውስጥ ምን ድርሻ እንዳለንና (እንድናምንና ፍቃዱን እንድንፈጽም ታዘናል)፥ የእግዚአብሔርም ድርሻ ምን እንደሆነ በትክክል አናውቅም ይሆናል። ጳውሎስ ግን በእግዚአብሔር ፍቅርና ወደ ቤተሰቡ ከመጣን ወደ ሰማይ እስክንደርስ ድረስ እንደሚጠብቀን እርግጠኞች ልንሆን እንደምንችል ገልጾአል።

ሠ. ከእግዚአብሔር ፍቅር ምንም ነገር ሊለየን አይችልም (ሮሜ 8፡31-39)። ይህ መጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ከሚገኙ እጅግ አጽናኝ ከሆኑ ክፍሎች አንዱ ነው። ሁላችንም በቃል ልናጠናቸውና እግዚአብሔር የማይጠነቀቅልን በሚመስለን ጊዜ ሁሉ ልንናገራቸው ይገባል። ጳውሎስ እግዚአብሔር በሰማይ ውስጥ ተቀምጦ ስለ እኛ ከማስብ የሚቆጠብ የሚመስልባቸው ጊዜያት እንዳሉ ያውቅ ነበር። ምንም ያህል ተግተን ብንጸልይ የምንፈልገውን ምላሽ አናገኝም። ጳውሎስ እግዚአብሔርን ከመጠራጠር ወይም በዚህ ሁኔታ ውስጥ የእግዚአብሔር ዓላማ ምን እንደሆነ ለማወቅ ከመሞከር ይልቅ እግዚአብሔር ለእኛ ስላለው አስደናቂ ፍቅሩ እንድናስብ ያበረታታናል። ጳውሎስ ከዚህ አስደናቂ የእግዚአብሔር ፍቅር ይመነጫሉ ያላቸውን ነገሮች ቀጥለን እንመልከት።

  1. እግዚአብሔር ለኃጢአታችን የመጨረሻውን መሥዋዕትነት ከፍሏል። እግዚአብሔር ከፍቅሩ የተነሣ ልጁ ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ እኛ እንዲሞት ልኮታል። የሚያጋጥሙን ሌሎች ችግሮች ሁሉ ለእግዚአብሔር ከእኛ ኃጢአት ያነሰና ዝቅ ያለ ዋጋ የሚያስከፍሉ ናቸው። ስለሆነም፥ በአንድ ሁኔታ ውስጥ የእግዚአብሔር ፍቅር እንዴት እንደሚንጸባረቅ በማናውቅበት ጊዜ እንኳ አባታችን እጅግ የተወደደውን የትኛውንም ነገር እንደማይነፍገን ልናስታውስ ይገባል። ወላጆች ልጆቻቸውን ቢወዱም እንኳ የሚጠይቋቸው ነገሮች ሁሉ እንደማይጠቅሟቸው ስለሚያውቁ ይነፍጓቸዋል። በተመሳሳይ ሁኔታ፥ እግዚአብሔርም ለእኛ ከሁሉም የሚሻለውን ያውቃል። በፍቅሩ ለእኛ ከሁሉም የሚሻለንን እንጂ የጠየቅነውን ሁሉ አይሰጠንም።
  2. እግዚአብሔር ያለፈውን፥ የአሁኑንና የወደፊቱን ኃጢአታችንን ሁሉ ሙሉ በሙሉ ይቅር ብሎናል። እግዚአብሔር የመጨረሻው ይግባኝ የማይጠየቅበት ዳኛ ስለሆነና ኃጢአታችንን ሙሉ በሙሉ ይቅር ስላለ፥ በእነዚያ ኃጢአቶች ምክንያት ማንም ወደ ሲኦል ሊሰድደን አይችልም።
  3. ክርስቶስ ለኃጢአታችን ከመሞቱ በተጨማሪ፥ በእኛ ፈንታ ተግባሩን ይቀጥላል። እንደ መንፈስ ቅዱስ እንደሚማልድልን ሁሉ፥ ክርስቶስም በሰማይ ሆኖ ይማልድልናል። ክርስቶስና መንፈስ ቅዱስ ባለማቋረጥ በሕይወታችን ውስጥ የሚሠሩ ከሆነ፥ እግዚአብሔር ሁሉንም አሸንፈን ወደ መንግሥተ ሰማይ እንድንደርስ እንደሚረዳን እርግጠኞች ልንሆን እንችላለን።
  4. በምድርም ሆነ በሰማያዊ ስፍራ ያለው መንግሥት ወይም ገዥ (ሰይጣን)፥ እንዲሁም ምድራዊ ችግር (መገደል እንኳ ቢሆን)፥ እግዚአብሔር ለልጆቹ ካለው ፍቅር ሊለየን አይችልም። በበሽታ ወይም በስደት ምክንያት ልንሞት ብንችልም፥ እነዚህ እግዚአብሔር ወደ ዘላለማዊ ቤታችን እኛን ለመውሰድ የሚጠቀምባቸው መሣሪያዎች እንደሆኑ ልንገነዘብ ይገባል። እንደ ሰይጣን፥ የማያምኑ ሰዎች ወይም ክፉ መንግሥታት ባሉ ጠላቶች እየተጠቃን ቢመስለንም፥ አሸናፊዎቹ እኛው ነን። ፍጻሜያችን የተረጋገጠ ነው።

ምክንያቱም እኛ የዘላለማዊው ንጉሥ መንፈሳዊ ልጆች ነን።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) አንድ ጓደኛህ በአደጋ ምክንያት ሚስቱንና ልጁን አጥቷል እንበል። ከዚህ ክፍል፥ እምነቱ በክርስቶስ እንዲጸና ምን ብለህ ታበረታታዋለ? ለ) በግልህ ተስፋ ቆርጠህ እግዚአብሔር እንደማያስብልህ ያሰብክበትን ጊዜ አስታውስ። በእግዚአብሔር ፍቅር ላይ የጠበቀ እምነት መያዝ እነዚህን የተስፋ መቁረጥ ጊዜያት እንድናሸንፍ የሚረዳን እንዴት ነው? ሮሜ 8፡31-39ን በቃልህ አጥና።

የውይይት ጥያቄ፡- እስካሁን በሮሜ ውስጥ የተመለከትናቸውን ጠቃሚ ቃላት አብራራ። ሀ) መጽደቅ፥ ለ) መቀደስ፥ ሐ) መክበር፥ መ) ቁጣውን ማብረድ፥ ሠ) እምነት፥ ረ) ስርየት። የቃላቱን ፍቺ ካላወቅህ የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት ተጠቀም።

የውይይት ጥያቄ፡- ጳውሎስ በሮሜ 1-8 ያስተማረውን በራስህ አገላለጽ ጻፍ። ሰው ከኃጢአት የሚድነው እንዴት ነው? ኃጢአትን ሊያሸንፍ የሚችለውስ እንዴት ነው? በመከራ ውስጥ በልበ-ሙሉነት ሊኖር የሚችለው እንዴት ነው?

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

2 thoughts on “ሮሜ 8፡1-39”

  1. Pingback: የሮሜ መልእክት ጥናት – ወንጌል በድረ-ገፅ አገልግሎት

Leave a Reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading