Site icon

ሮሜ 9፡30-10፡21

  1. ብዙ አይሁዶች እግዚአብሔር የማይቀበለውን የድነት (ደኅንነት) መንገድ በመከተላቸው ምክንያት አልዳኑም (ሮሜ 9፡30-33)።

«አይሁዶች በኢየሱስ የማያምኑት ለምንድን ነው? ይህ ክርስቶስ መሢሕ አለመሆኑን አያሳይምን?» በማለት ሰዎች ጳውሎስን ይጠይቁት ነበር። ጳውሎስ ላለማመናቸው ምክንያቱ የክርስቶስ መሢሕ አለመሆን ሳይሆን አይሁዶች ድነትን (ደኅንነትን) ወይም ጽድቅን በተሳሳተ መንገድ መፈለጋቸው እንደሆነ አብራርቷል። አይሁዶች ከእግዚአብሔር ዘንድ ድነት እና ማረጋገጫ ለመቀበል የፈለጉት በውርላሳቸው፥ በግርዛታቸውና በመልካም ሥራቸው አማካኝነት ነበር። እግዚአብሔር ያዘጋጀው የድነት መንገድ ግን ይሄ አልነበረም። በድንጋዩ በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ በመሰናከላቸው ምክንያት ድነት ሊያገኙ አልቻሉም። ታሪካዊ የእግዚአብሔር ሕዝብ እንዳልሆኑና የእግዚአብሔርን ምሕረት ለመቀበል በክርስቶስ ሞት ማመን እንደሚያስፈልጋቸው የተገነዘቡት አሕዛብ ግን ድነትን አግኝተዋል። አሕዛብ የራሳቸውን ጽድቅ ከመመልከት ይልቅ የእግዚአብሔርን ጽድቅ ተቀበሉ።

የውይይት ጥያቄ፡- አማኞች ነን የሚሉትን ጨምሮ ሃይማኖተኛ ሰዎች እግዚአብሔር ከሚሰጠው ጽድቅ በላይ በራሳቸው ጽድቅ ላይ በማተኮራቸው ምክንያት ዛሬ የድነትን መንገድ ለማግኘት የሚቸገሩት እንዴት ነው?

ጳውሎስ አይሁዶች ስላልዳኑበት ሁኔታ ማብራራቱን ይቀጥላል። በዚህ ጊዜ ጳውሎስ በድነት ውስጥ እግዚአብሔር ከሚያበረክተው ድርሻ ይልቅ በሰዎች ድርሻ ላይ ያተኩራል።

  1. አይሁዶች የእግዚአብሔርን የድነት (የደኅንነት) ዕቅድ አልተገነዘቡም (ሮሜ 10፡1-4)። አይሁዶች የብሉይ ኪዳን ሕግጋትን በቅንዓት ቢጠብቁም፥ ቅንዓታቸው ድነትን ሊያስገኝላቸው አልቻለም። ብዙ ጊዜ አንድ ሰው ቀናተኛና ሃይማኖተኛ ሆኖ እምነቱን የሚከተል ከሆነ እግዚአብሔር ይቀበለዋል ብለን እናስባለን። ነገር ግን ቡድሂስቶች፥ ሙስሊሞችም ሆኑ ሌሎች ሕዝቦች ለሃይማኖታቸው ቀናተኞች እንደሆኑ መገንዘብ ይኖርብናል። ቅንዓት አንድን ነገር ትክክል ሊያደርግ አይችልም። አንድ ሰው ስለ አንድ ነገር ቀናተኛ ሊሆንና የተሳሳተ ሊሆን ይችላል። ቅንዓት ከትክክለኛ እውቀት ጋር መዋሃድ አለበት። አይሁዶች ያላገኙትም የድነትን መንገድ ትክክለኛ ግንዛቤ ነበር። የእግዚአብሔር አቀባበሉ፥ ጽድቁ፥ «ጥፋተኛ አይደለህም። የሚለው እወጃው እንዴት በስጦታ መልክ እንደሚመጡ አላውቁም ነበር። ይህ በራሳቸው ጥረት የሚያገኙት ነገር አይደለም። መሢሐቸው ክርስቶስ በፖለቲካዊ ጠላቶቻቸው ላይ ድልን እንደሚነሣ ንጉሥ ላይሆን እንደ የኃጢአት መሥዋዕት መምጣቱን ሊገነዘቡ አልቻሉም።
  2. ድነት (ደኅንነት) ወይም «ጻድቅ ነህ» የሚል እወጃ የሚያምኑ ሰዎች ሁሉ የሚቀበሉት እንጂ የማይቻል ነገር አይደለም (ሮሜ 10፡5-13)። ጳውሎስ ሁለት የድነት (ደኅንነት) መንገዶችን ለማነጻጸር ሲል ብሉይ ኪዳንን ይጠቀማል። የመጀመሪያው፥ አይሁዶች ድነትን (ደኅንነትን) ለማግኘት የሚያስችል በጎነት ለመቀዳጀት ያደረጉት ጥረት ነው። ዘሌዋውያን 18፡5 እንደሚለው፥ እግዚአብሔርን ለማስደሰት ሕግጋቱን ሙሉ በሙሉ መፈጸም ያስፈልጋቸው ነበር። ነገር ግን ይህ ለሁሉም ኃጢአት የሚሠራ አለመሆኑን ጳውሎስ ቀደም ብሎ አመልክቷል። ስለሆነም፥ መንፈሳዊ ሕይወት ሕግጋትን ከመከተል ሊገኝ አይችልም።

የእግዚአብሔር የሆነው ሁለተኛው የድነት መንገድ ግን ከፍተኛ ብርታትንና ተአምራትን አይጠይቅም። ወደ ቅዱስ ስፍራዎች የሚደረጉ ረዣዥም ጉዞዎች ለድነት ሚያበረከቱት አስተዋጽኦ አይኖርም። የእግዚአብሔር ድነት ሰዎች ሁሉ ይቀበሉት ዘንድ በአጠገባቸው አለ። ድነትን ለማግኘት ከፍተኛ ጥረት ከማድረግ ይልቅ ማመን እንደሚያስፈልግ ጳውሎስ አብራርቷል። ክርስቶስ የኃጢአታችንን ቅጣት የከፈለ የግል መሥዋዕታችን እንደሆነ ከልባችን ማመን አለብን። እንዲሁም ክርስቶስን እንደ ጌታችን ለመከተል ቆራጥ ውሳኔ ማድረግ አለብን። ይህ ውስጣዊ ተግባር በኃፍረት ተሸማቅቀን ከሰዎች የምንደብቀው ዓይነት ሳይሆን፥ በይፋ የሚታወጅ ነው። አንድ አይሁዳዊ ወይም አሕዛብ ይህን ቀላልና ነገር ግን ሕይወት ለዋጭ ውሳኔ በሚያደርግበት ጊዜ የእግዚአብሔር ጽድቅና በረከት ሕይወቱን ይሞላዋል።

የውይይት ጥያቄ፡- ብዙውን ጊዜ ወንጌላውያን ክርስቲያኖች አንድ ሰው ክርስቶስን እንደ ግል አዳኙ አድርጎ መቀበል እንዳለበት በሚያስረዳው እውነት ላይ ቢያተኩሩም፥ ግለሰቡ ክርስቶስን እንደ ጌታውም አድርጎ መቀበል እንዳለበት አያብራሩም። ሀ) ይህ ሚዛናዊ አስተምህሮ ይመስልሃል? ለ) አንድ ሰው ክርስቶስን እንደ ግል አዳኙ አድርጎ ለመቀበልና በጌትነቱ ሥር ለመኖር ቃል መግባት ያለበት ለምን እንደሆነ አብራራ? ሐ) ሮሜ 10፡9-10ን በቃልህ አጥና።

  1. ሰዎች ለማመን ወንጌሉን መስማት አለባቸው (ሮሜ 10፡14-15)። እግዚአብሔር ስለ ክርስቶስ ባልሰሙት ሰዎች ላይ አይፈርድም የሚሉ አንዳንድ ምዕራባውያን ክርስቲያኖች አሉ። ምንም እንኳ ጳውሎስ በዚህ ጉዳይ ላይ ባያተኩርም፥ ቀደም ሲል ወንጌልን ያልሰሙትን ጨምሮ አሕዛብ ሁሉ እግዚአብሔር በልባቸው ውስጥ ያስቀመጠውንና በተፈጥሮ የገለጣቸውን እውነቶች ሆነ ብለው ስላላከበሩ ኃጢአተኞች መሆናቸውን ገልጾአል። በክርስቶስ ላይ ያለ እምነት ሊፈጠር የሚችለው እንደ ጳውሎስ ብርቱ ትምህርት ሲሰማና ሊያምን ብቻ ነው። ለዚህም ነበር ምንም ወንጌል ወዳልተሰበከበት የስፔይን አገር ለመሄድ የፈለገው። እግዚአብሔር ሰዎችን ወደ ድነት (ደኅንነት) የሚያመጣበት መንገድ የእግዚአብሔር ልጆች የማመን ዕድል ያገኙ ዘንድ ወንጌሉን ላልሰሙት ሰዎች በሚሰብኩበት ጊዜ ነው። ጳውሎስ ይህ የሐዋርያ፥ የወንጌላዊ ወይም የሚሲዮናዊ ኃላፊነት ብቻ እንዳልሆነ አመልክቷል። ነገር ግን ጠቅላላይቱ ቤተ ክርስቲያን እግዚአብሔር መልእክተኞቹ እንዲሆኑ የመረጣቸውን ሰዎች የመላክ ኃላፊነት አለባት። ጳውሎስ የሮም ክርስቲያኖች በስፔይን ወንጌልን በመሰብክ ሥራው ላይ እንዲተባበሩት አበረታቷቸዋል።

ይህ በጣም አስፈላጊ አገልግሎት በመሆኑ፥ ጳውሎስ የእግዚአብሔርን ጥሪ ሰምተው ወንጌሉን ወዳልሰሙት ወገኖች የሚያደርሱ ሰዎች ያማረ እግር እንዳላቸው አመልክቷል። ብዙ ጊዜ ክርስቲያኖች ለመማርና ጥሩ ሥራ ለመያዝ ወይም የራሳቸውን «ቢዝነስ» ለመክፈት ይፈልጋሉ። ጳውሎስ ግን ሥራቸውን በእግዚአብሔር እይታ እንዲመለከቱ ያበረታታቸዋል። ሰዎች ወንጌልን መስበክ ጊዜ ማጥፋትና ላልተማሩትና ሌላ ሥራ ሊያገኙ ለማይችሉ ሰዎች ሥራ መፍጠሪያ ነው ብለው ሊያስቡ ይችላሉ። በእግዚአብሔር ዓይኖች ግን ይህ እጅግ ውብ የሆነ ሥራ ነው።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) በኢትዮጵያ ብዙ አማኞች የሌሉባቸውን ጎሳዎች ዘርዝር። ለ) አምነው ይድኑ ዘንድ ወንጌልን በማድረሱ በኩል እግዚአብሔር ከአንተና ከቤተ ከርስቲያንህ ምን የሚፈልግ ይመስልሃል? ሐ) ጥቂት ወጣቶች ለጠፉት ወንጌል መስበክን እንደተከበረ ሙያ የሚያዩት ለምን ይመስልሃል? በሕይወት ጠቃሚ ስለሆነው ነገር የእግዚአብሔርን እይታ በተሳሳተ መንገድ የተገነዘቡት እንዴት ነው?

  1. ጳውሎስ አይሁዶች የእግዚአብሔርን የድነት (የደኅንነት) ጥሪ እንዴት እንደተቃወሙ ያብራራል (ሮሜ 10፡ 16-21)። በጳውሎስ ዘመን፥ በቀድሞዪቱ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ለውጦች ተካሂደዋል። እስከዚህ ጊዜ ድረስ፥ ቤተ ክርስቲያን በኢየሩሳሌም የተማከለች ስትሆን፥ ብዙ አይሁዶች ክርስቶስን እንደ መሢሐቸው ተቀብለውት ነበር። አሁን ግን ቤተ ክርስቲያን በአሕዛብ መካከል በፍጥነት በመስፋፋቷና በኢየሩሳሌም ብሔርተኝነት እያደገ በመምጣቱ፥ ብዙ አይሁዶች በክርስቶስ ላለማመን ወሰኑ። በዚህ ጊዜ በፍልስጥኤም በአሕዛብ ላይ ፖለቲካዊ ጠላትነት እያደገ ከመምጣቱም በላይ፥ የሮምም ጭቆና ተጠናክሮ ነበር። ከዚህም የተነሣ በክርስቶስ የሚያምኑ አይሁዶች በቁጥር እየቀነሱ ሄዱ። ቀደም ሲል ያመኑትም በክርስቶስ ላይ የነበራቸውን እምነት ትተው ወደ ቀደመው የብሉይ ኪዳን የአምልኮ ሥርዓት እንዲመለሱ ግፊት ተደረገባቸው። የዕብራውያን መጽሐፍ እምነታቸውን ለመተው በተፈተኑት በእነዚህ አይሁዶች ላይ ትኩረት ያደርጋል።

ጳውሎስ በክርስቶስ ያመኑ ብዙ አይሁዶች እንዳሉ ቢያምንም፥ አንዳንዶች በክርስቶስ ላይ የተቃዋሚነት አቋም ይዘው ነበር። ይህ ግን ጳውሎስን አላስደነቀውም። በብሉይ ኪዳን ውስጥ አይሁዶች የእግዚአብሔርን መልእክት እንደማይቀበሉ የሚገልጸውን ሰፊ ጭብጥ ተመለከተ። ኢሳይያስ ምንም እንኳ እግዚአብሔር እጆቹን ዘርግቶ ወደ እርሱ እንዲመለሱ ቢጠይቃቸውም፥ አይሁዶች በእግዚአብሔር መልእክት ለማመን አለመፈለጋቸውን መስክሯል። ነገር ግን ታሪካዊ የእግዚአብሔር ሕዝብ ያልነበሩት አሕዛብ ወደ እግዚአብሔር በመመለስ ድነትን ያገኙ ነበር። ይህም ሙሴ እግዚአብሔር አንድ ቀን አይሁዶችን ለማስቆጣት ሲል አይሁዶች ባልሆኑት ሰዎች መካከል እንደሚሠራ የተነበየው ትንቢት ነበር።

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Exit mobile version