የውይይት ጥያቄ፡– ሮሜ 11ን አንብብ። ሀ) ጳውሎስ እግዚአብሔር ከአይሁዶች ጋር ስለሚያደርገው የአሁንና የወደፊት ግንኙነት ምን አለ? ለ) ጳውሎስ ለአሕዛብ ክርስቲያኖች የሰጣቸው ማስጠንቀቂያ ምን ነበር?
አይሁዶች እንደ ሕዝብ የእግዚአብሔርን የድነት (ደኅንነት) መንገድ ለመቀበል ስላለመፈለጋቸው ጳውሎስ የሚሰጠውን ትንታኔ የሚሰማ አይሁዳዊ ክርስቲያን፥ «ይህ ማለት እግዚአብሔር ከእንግዲህ ለአይሁዶች ልዩ ዕቅድ የለውም ማለት ነው?» የሚል ጥያቄ ማንሣቱ የማይቀር ነው። ጳውሎስ ለዚህ ጉዳይ በሦስት መንገዶች ምላሽ ሰጥቷል።
- በታሪክ ሁሉ እግዚአብሔር በእርሱ የሚያምኑ ቅሬታዎች አሉት (ሮሜ 1፡1-10)። ራሱ ጳውሎስና የአይሁድ ክርስቲያኖች እግዚአብሔር አይሁዶችን ሙሉ ለሙሉ ላለመተዉ ማረጋገጫዎች ናቸው። እግዚአብሔር በጨለማው የእስራኤል ታሪክ እንዳሳየው፥ ኤልያስ ታማኝ የእግዚአብሔር ተከታይ እኔ ብቻ ነኝ በሚልበት ወቅት ሌሎች 7,000 ታማኝ ተከታዮች ነበሩት (1ኛ ነገ 19)። አብዛኞቹ አይሁዶች «የመንፈስ ድንዛዜ» ቢደርስባቸውም፥ ታማኝ ቅሬታዎች የእግዚአብሔርን የድነት (ደኅንነት) መንገድ ተከትለው በክርስቶስ አምነዋል። በአሁኑ ጊዜ አይሁዶች ክርስቲያኖች ወገኖቻቸውን በወንጌል ለመድረስ ከፍተኛ ጥረት በማድረግ ላይ ናቸው። ብዙ አይሁዶችም ክርስቶስን ለማመን እንደ መሲሐቸው አድርገው ለመከተል እየወሰኑ ነው።
- እግዚአብሔር «የአሕዛብን ዘመን» ዐቅዷል። ይህም ብዙ አሕዛብ በክርስቶስ የሚያምኑበትና ቀደም ሲል አይሁዶች ያገኙ የነበረውን በረከት የሚቀበሉበት ነው (ሮሜ 11፡11-24)። ጳውሎስ የአሕዛብ ክርስቲያኖች አሁን ከአይሁዶች ይልቅ እነርሱ የእግዚአብሔርን ሞገስ እንዳገኙ በማሰብ እንዳይታበዩ ሰግቶ ነበር። ስለሆነም፥ የእግዚአብሔርን ረዥም የድነት (ደኅንነት) ዕቅድ በሰፊው ያብራራል። ይህ ለአሕዛብ የተሰጠው ጸጋ ጊዜያዊ ይሆናል። ይህም እግዚአብሔር አይሁዶችን አስቆጥቶ ወደ ራሱ የሚመልስበት መንገድ ነበር። በእግዚአብሔር ዕቅድ፥ አይሁዶች የእግዚአብሔርን የድነት (ደኅንነት) መንገድ አለመቀበላቸው በአንድ ወቅት ከእግዚአብሔር ሕዝብ ተገልለው ለነበሩት አይሁዶች የድነትን መንገድ ከፍቷል። ጳውሎስ አንድ ቀን አይሁዶች እንደ ሕዝብ በክርስቶስ የሚያምኑ ሲሆን፥ ደኅንነታቸውም ለዓለም የበለጠ በረከትን ያመጣል በማለት ተስፋውን ተናግሯል።
ጳውሎስ እግዚአብሔር እያደረገ የነበረውን ተግባር ለማብራራት አያሌ ምሳሌዎችን ተጠቅሟል።
ሀ. አይሁዶች ከመጀመሪያው የመከር እህል ያዘጋጁትን ሊጥ ለእግዚአብሔር ስለሚሠዉበት ሁኔታ ይገልጻል። ይህም ለእግዚአብሔር የተሠዋውን እርሾ ብቻ ሳይሆን የተቀረውንም ሊጥ በመቀደስ (ስመለየት)፥ እግዚአብሔር የሚያስፈልጋቸውን ሁሉ እንደሚያሟላላቸው ያመለክታል። በተመሳሳይ ሁኔታ፥ እግዚአብሔር የእምነት አባቶችን ልዩ ሕዝቡ አድርጎ ስለመረጣቸው፥ የተቀሩትም አይሁዶች ለእግዚአብሔር ልዩ ይሆናሉ። (በዚህ ክፍል «ቅዱስ» የሚለው ቃል ኃጢአት አልባነትን ሳይሆን «መለየት»ን ያሳያል።)
ለ. ጳውሎስ በተጨማሪም የአይሁዶችንና የአሕዛብን ግንኙነት ከወይራ ዛፍ ጋር ያነጻጽረዋል፡፡ አይሁዳውያን ካሏቸው ዋና ዋና ተክሎች መካከል አንዱ የወይራ ዛፍ ነው። ጳውሎስ የእግዚአብሔርን ልጆች በወይራ ዛፍ መስሏቸው ነበር። ዋነኞቹ የወይራ ዛፍ በልዩ ሁኔታ የተመረጡት የብሉይ ኪዳን ሕዝቦች አይሁዶች ነበሩ። አሕዛብ ክርስቲያኖች በዚያው የወይራ ዛፍ ላይ የተተከሉ የበረሃ ቅርንጫፎች ናቸው። (ብዙውን ጊዜ ሰው ጥሩ ቅርንጫፎችን በበረሃ ዛፍ ላይ ለማዳቀል ያጣብቃል እንጂ የማይጠቅም የሚመስለውን የበረሃ ቅርንጫፍ በጥሩ ዛፍ ላይ አያጣብቅም። የእግዚአብሔር ጸጋ ግን ኃጢአተኛ አሕዛብን ወደ ትውፊታዊ የእግዚአብሔር ቤተሰብ በማምጣት በዚህ መንገድ ይሠራል።) ክርስቶስን የተዉት የአይሁድ ሕዝብ ፍሬያማ ባለመሆናቸው ምክንያት ከዛፍ እንደተቆረጡ ቅርንጫፎች ናቸው። ነገር ግን የአሕዛብ ክርስቲያኖች መመካት እንደሌለባቸው ማስጠንቀቂያ ተሰጥቷቸዋል። ወደ እግዚአብሔር የበረከት ዛፍ ለመግባት የሚያበቃ ምንም ዓይነት ተግባር አላከናወኑም። ይህ የእግዚአብሔር ምሕረት ያስገኘላቸው በረከት ነበር። ጳውሎስ አሕዛብ እንዲጠነቀቁ ያሳስባል። ካልታዘዙ እነርሱም ከእግዚአብሔር በረከት ሊቆረጡና ሊወገዱ ይችላሉ። ጳውሎስ እግዚአብሔር አንድ ቀን ተፈጥሯዊ ቅርንጫፎቹ የሆኑትን አይሁዶች ወደ በረከት ዛፍ መልሶ እንደሚተክላቸው ገልጾአል።
- አንድ ቀን እግዚአብሔር አይሁዶችን እንደ አንድ ሕዝብ ያድናቸዋል (ሮሜ 11፡25-32)። በዚህ ጊዜ አይሁዶች የአሕዛብ ክርስቲያኖችን ቢያሳድዱም፥ ይህ ማለት እግዚአብሔር አይሁዶችን ሙሉ ለሙሉ ከዕቅዶቹ ሠርዟቸዋል ማለት አልነበረም። «የአሕዛብ ሙላት ከተፈጸመ በኋላ» እግዚአብሔር አይሁዶችን እንደገና በመጎብኘት ብዙዎቹን ያድናቸዋል።
ጳውሎስ ይህን እውነት «ምሥጢር» ብሎ ይጠራዋል። በአዲስ ኪዳን ውስጥ ምሥጢር ለሌላ ሰው የማይነገር አሳብ ማለት ሳይሆን፥ በብሉይ ኪዳን ተሰውሮ የነበረና በአዲስ ኪዳን ግን እግዚአብሔር ለሕዝቡ የገለጠው እውነት ነው።
የአሕዛብ ሙላት ማለት ምን ማለት ነው? «እስራኤል ሁሉ» በሚለው ውስጥ የተካተቱትስ እነማን ናቸው? በዚህ ጉዳይ ላይ የሚቀርቡ የተለያዩ አተረጓጎሞች ቢኖሩም፥ ጳውሎስ በዚህ የአሕዛብ ወይም የቤተ ክርስቲያን ዘመን እግዚአብሔር በአሕዛብ ድነት (ደኅንነት) ላይ ማተኮሩን ለማሳየት ይፈልጋል።
በቤተ ክርስቲያን ዘመን የተወሰነ ቁጥር ያላቸው አሕዛብና የተወሰነ የድነት (ደኅንነት) ጊዜ ስላለ፥ በዋናነት አሕዛብ ይድናሉ። የተመረጡት አሕዛብ በሙሉ ከዳኑ በኋላ፥ ታሪኩ አቅጣጫውን ይቀይራል። ከዚያ በኋላ እግዚአብሔር በአይሁዶች መካከል በመሥራት በክርስቶስ እንዲያምኑ ያደርጋል። ይህ ማለት ግን እያንዳንዱ አይሁዳዊ ድነት ያገኛል ማለት አይደለም። ነገር ግን እንደ አንድ ሕዝብ ብዙ አይሁዶች በክርስቶስ አምነው ይድናሉ። ከእንግዲህ አይሁዶች በጥረታቸው ድነትን ለማግኘት መሞከራቸውን አቁመው እንደ አሕዛብ ሁሉ ወደ እግዚአብሔር ምሕረት ፊታቸውን ያዞራሉ። ጳውሎስ እግዚአብሔር በስጦታዎቹና በመጥራቱ አይጸጸትም ብሏል። በሌላ አገላለጽ፥ እግዚአብሔር ሊዋሽ ስለማይችል በብሉይ ኪዳን ለአብርሃምና ለአይሁዶች የሰጣቸው የተስፋ ቃሎች ይፈጸማሉ።
- ለእግዚአብሔር ታላቅ ጥበብ የቀረበ የምስጋና መዝሙር (ሮሜ 11፡33-36)። እግዚአብሔር የአይሁዶችን አለመታዘዝ ተጠቅሞ አሕዛብን ማዳኑና በኋላም አይሁዶች በአሕዛብ ድነት (ደኅንነት) ቀንተው ወደ እርሱ እንዲመለሱ ማድረጉ አስደናቂ ነገር አይደለምን? ጳውሎስ የእግዚአብሔር መንገድ ከሰዎች ማስተዋል ይልቅ ምሥጢራዊ መሆኑን የሚገልጽ መዝሙር ተቀኝቷል። የድነትና የበረከቶች ሁሉ ምንጭ እግዚአብሔር ነው። በረከቱን የሚያመጣልን እርሱ ሲሆን፥ ይህንንም ለክብሩ ይጠቀምበታል። ልናደርግ የምንችለው ነገር ቢኖር እርሱን ለዘላለም ማክበር ነው (ሮሜ 11፡33–36)።
ይህ የጳውሎስ መዝሙር እግዚአብሔር በአንድ ሁኔታ ውስጥ የሚያደርገውን ሁሉ እንገነዘባለን እንዳንል ሊያስጠነቅቀን ይገባል። «ኃጢአትን ስለሠራህ እግዚአብሔር እየፈረደብህ ነው። እግዚአብሔር ልጅ ያልሰጠህ የበለጠ እንድታምነው ነው። እግዚአብሔር በአገሪቱ ላይ ረሃብን ያመጣው ኃጢአተኞች ስለሆኑ ነው።» እነዚህ ሁሉ አሳቦች እግዚአብሔር በአንድ ሁኔታ ውስጥ ምን ዓላማ እንዳለው እናውቃለን ባይነታችንን ያሳያሉ። ነገር ግን እግዚአብሔር የሚያደርገው ነገር በአብዛኛው ከእኛ የተሰወረ ምሥጢር ነው። ብዙውን ጊዜ እግዚአብሔር የሚሠራው እኛ ከምንጠብቀው መንገድ ውጭ ነው። እግዚአብሔር ክፉውን የኮሚዩኒዝም ዘመን ተጠቅሞ ቤተ ክርስቲያንን እንዲህ በፍጥነት ያሳድጋታል ብሎ ማን ያሰበ ነበር? ጳውሎስ እንደሚለው፥ የእግዚአብሔር መንገድ ከማስተዋል ያለፈ መሥጢራዊ መሆኑን ልንገነዘብ ይገባል። የእርሱ መንገዶች ሁልጊዜም አስደናቂዎች በመሆናቸው፥ ሁሉም ነገር ከእርሱ እንጂ ከአመክኒዮአችን (Logic)፥ ከትምህርታችን፥ ከዘዴያችን፥ ከመዋቅራችን፥ ወዘተ… እንደማይመጡ ልንገንዘብ ይገባል።
የውይይት ጥያቄ፡- እግዚአብሔር ያደረገውና ምሥጢር የሆነብህን ነገር ዘርዝር? ለ) እግዚአብሔር ሰዎች ከሚያደርጉት መንገድ ፍጹም በተለየ ሁኔታ ያከናወነውንና ለእግዚአብሔር ታላቅ ክብር ያስገኘውን አንድ ነገር ጥቀስ። ሐ) አሁን ጊዜ ውሰድና እግዚአብሔርን ስለ ታላቅ ጥበቡና እውቀቱ፥ በማትገነዘብበት ጊዜ እንኳ ነገሮችን ሁሉ ስለ መቆጣጠሩ አመስግነው።
(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)
Pingback: የሮሜ መልእክት ጥናት – ወንጌል በድረ-ገፅ አገልግሎት