አማኝ ከሞተ በኋላ ሥጋው ምን ይሆናል? (1ኛ ቆሮ. 15፡1-58)

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ሞት የሰዎችን እምነት ጭምር የሚያናጋ አስፈሪ ነገር መሆኑን በተለያዩ መንገዶች አብራራ። ለ) ለክርስቲያኖች ከሞቱ በኋላ ስለሚደርስባቸው ነገር ግልጽ ግንዛቤ ማግኘት አስፈላጊ የሚሆነው ለምንድን ነው?

በዓለም ውስጥ የሚገኙ ሰዎች ሁሉ ሞትን ይፈራሉ። ከሞት ለማምለጥ ያላቸውን ሀብት ሁሉ ለመሠዋት ፈቃደኞች ናቸው። ከሞት በኋላ የሚሆነውን ነገር በፍጹም አያውቁትም። አንድ መልካም ነገር ይመጣል ብለው ተስፋ ቢያደርጉም አያውቁትም። ስለሆነም፥ ሞት በተስፋ ቢስ ለቅሶና ፍርሃት የተሞላ ነው። መጽሐፍ ቅዱስ ግን ከሞት በኋላ በክርስቲያን ላይ ስለሚሆነው ነገር በግልጽ ያብራራል። ይህም እውቀት በሽታንና ሞትን ሳንፈራ በእርጋታ ክርስቶስን እንድንከተል ያደርገናል። ለክርስቲያን ሞት ሥቃይ፥ መከራ ወይም ሞት ወደሌለበት ስፍራ የሚመራን በር ማለት ነው። በዚያ ከክርስቶስ ጋር ለዘላለም እንኖራለን።

የውይይት ጥያቄ፡- 1ኛ ቆሮ. 15ን አንብብ። ሀ) ጳውሎስ ስለ ሙታን ትንሣኤ የገለጻቸውን እውነቶች ዘርዝር። ለ) እነዚህን እውነቶች ክርስቲያኖች ሁሉ በግልጽ ማወቃቸውና ማመናቸው ለምን ይጠቅማል?

ችግሩ፡- ብዙ የቆሮንቶስ ክርስቲያኖች የሙታን ትንሣኤ መኖሩን የተጠራጠሩ ይመስላል። ግሪኮች በሥጋ ትንሣኤ አያምኑም ነበር። ለዚህ ነበር የአቴና ሰዎች ጳውሎስ ወንጌሉን ሲመሰክርላቸው የቀለዱበት። (የሐዋ. 17፡32 አንብብ።) እንደ ሰውነት ያሉ የተፈጠሩ ነገሮች ተራና በራሳቸው ክፉ ናቸው የሚል እምነት ነበር። ስለሆነም፥ እግዚአብሔር ተራ የሆነውን ነገር ወደ መንግሥቱ እንዲገባ ስለማይፈቅድ መንፈስ እንጂ ሥጋ ከሞት እንዲነሣ አያደርግም የሚል አሳብ ነበራቸው። የቆሮንቶስ ክርስቲያኖችም ከሞት መነሣትን በተመለከተ ጳውሎስ ማብራሪያ እንዲሰጣቸው ደብዳቤ ጽፈው ጠየቁት። የጳውሎስ መልስ፡

፩. የክርስቶስ ትንሣኤ እኛም ከሞት እንደምንነሣ ያረጋግጣል (1ኛ ቆሮ. 15፡1-34)

ሀ. ወንጌሉ ክርስቶስ ለኃጢአት መሞቱን ብቻ ሳይሆን በሥጋ ከሞት መነሣቱንም ያስተምራል። የእርሱ ትንሣኤ መንፈሳዊ ብቻ አልነበረም። የክርስቶስ መነሣት በብዙ ሰዎች ተረጋግጧል። ራሱ ጳውሎስም ከሞት የተነሣውን ክርስቶስን አይቶታል። ጳውሎስ ከዕርገት በኋላ ከሞት የተነሣውን ጌታ ማየቱ ክርስቶስ ወደ ሰማይ ከሄደ በኋላም ቢሆን የትንሣኤ አካሉን ይዞ እንደሚገኝ ያመለክታል። ስለሆነም፥ የምናመልከው ክርስቶስ እንደ መንፈስ ብቻ ሳይሆን በትንሣኤ አካልም ይኖራል።

ለ. አካላዊ ትንሣኤን መካድ ማለት ክርስቶስ ራሱ ከሞት አልተነሣም እንደ ማለት ነበር። ይህ ማለት ደግሞ ጳውሎስ ስለ ክርስቶስ ትንሣኤ የሚያስተምረው ትምህርት ብቻ ሳይሆን ጠቅላላው ክርስትና ውሸት ነው እንደ ማለት ነበር። ቀደም ሲል የሞቱት ክርስቲያኖችም እንደ ዓለማውያን ሁሉ ያለ ተስፋ ጠፍተዋል እንደ ማለት ይሆናል። ለወደፊቱ የትንሣኤ ተስፋ ከሌላቸው ደግሞ ክርስቲያኖችም እንደ ዓለማውያን ሁሉ ያለ ተስፋ ጠፍተዋል ማለት ነበር። ለወደፊቱ የትንሣኤ ተስፋ ከሌላቸው ደግሞ ክርስቲያኖች ለእግዚአብሔር መኖራቸውን አቁመው ለራሳቸው መኖር ይኖርባቸዋል። ምቾትን በመከተል በሕይወት መደሰት አለብን። እንዲሁም፥ ከሞት በኋላ ሕይወት ከሌለ ፋይዳ ሊሰጥ ከማይችል ስደት መሽሽ አለብን ማለት ነው።

ሐ. ክርስቶስ ከሞት የተነሣ ሲሆን፥ ለተከታዮቹ የትንሣኤ ምሳሌ ነው። ጳውሎስ የክርስቶስ ትንሣኤ የሁሉም ክርስቲያኖች ትንሣኤ ምሳሌ መሆኑን ለማሳየት ሁለት ማብራሪያዎችን ተጠቅሟል። በመጀመሪያ፥ ክርስቶስ የሚሞቱት ክርስቲያኖች ሁሉ «በኩር» መሆኑን ገልጾአል። በብሉይ ኪዳን አዝመራ በሚደርስበት ጊዜ አይሁዶች ከእህል አነስተኛውን ክፍል ወደ ቤተ መቅደስ ወስደው ለእግዚአብሔር ያቀርቡ ነበር (ዘሌ. 23፡10-11፥ 17፥20)። ይህንንም የሚያደርጉት እግዚአብሔር አዝመራውን እንደሰጣቸው ለመግለጽና ለስጦታውም ምስጋናቸውን ለማቅረብ ነበር። አንድ ሰው ከእህሉ የተወሰነውን ለእግዚአብሔር በሚሰጥበት ጊዜ የቀረውን ለእግዚአብሔር ክብር እንደሚያውል መግለጹ ነበር። ክርስቶስም እንዲሁ ከሞት የተነሡት ሰዎች ታላቅ አዝመራ በኩራት ነው። የክርስቶስ ተከታዮች እንደ ክርስቶስ ሁሉ ከሞት ይነሣሉ። ሁለተኛ፥ ኢየሱስ ሁለተኛው «አዳም» ነው። የመጀመሪያው አዳም በኃጢአቱ ምክንያት በሰዎች ሁሉ ላይ ሥጋዊና መንፈሳዊ ሞት አስከትሏል። ሁለተኛው አዳም ግን ከሞት በመነሣቱ ለክርስቲያኖች መንፈሳዊና ሥጋዊ ትንሣኤ ሕይወት አስገኝቶላቸዋል።

መ. የክርስቶስ ትንሣኤ በዘላለማዊነት የሚፈጸም የታላቅ ሂደት ጅማሬ ነው። ክርስቶስ «የትንሣኤዎች መከር» መጀመሪያ በመሆኑ፥ የትንሣኤን ሂደት በአዲስ አካል ጀምሯል። ሁለተኛ፥ የብሉይም ሆነ የአዲስ ኪዳን ቅዱሳን ትንሣኤ ይከተላል። ሦስተኛ፥ ክርስቶስ አገዛዙን በሰዎች ሁሉ ላይ ከመሠረተና ክፋትን ሁሉ ካወደመ በኋላ፥ መንግሥቱን ለእግዚአብሔር አብ አሳልፎ ይሰጣል። ከሚጠፉት የመጨረሻ ክፋቶች አንዱ ሞት ነው።

፪. የትንሣኤው አካል አሁን ካለን አካል ጋር ቢመሳሰልም የተለየ ይሆናል (1ኛ ቆሮ. 15፡35-58)።

አሁን ያለን አካል በኃጢአት የተበላሸ ስለሆነ፥ የቆሮንቶስ ክርስቲያኖች ምን ዓይነት የትንሣኤ አካል እንደሚኖራቸው እያሰቡ ነበር። ጳውሎስ ከትንሣኤ በኋላ ስለሚኖረው ሁኔታ የተለያዩ ገለጻዎችን ያቀርባል።

ሀ. ጳውሎስ የሰው ካልሆኑት ሦስት የተለያዩ አካላት ጋር በማነጻጸር ማብራሪያውን ይጀምራል። በመጀመሪያ፥ የትንሣኤ ሕይወት የተክልን ሕይወት ይመስላል። የስንዴ ዘር መሬት ውስጥ ተቀብሮ ከበሰበሰ በኋላ በእግዚአብሔር ኃይል አዲስ ተመሳሳይ ተክል ያስገኛል። ሁለተኛ፣ እግዚአብሔር ለተለያዩ እንስሳትና ዓሦች የተለያዩ አካላትን ይሰጣል። ሦስተኛ፥ ፀሐይ ከጨረቃ የበለጠ ክብር እንዳላት ሁሉ እግዚአብሔር የተለያዩ የክብር ደረጃ ዎችን ይሰጣል።

ጳውሎስ ከእነዚህ ማብራሪያዎች በመነሣት የሚከተለውን አስተምሯል።

  1. እንደ ተክል ሁሉ የትንሣኤ አካላችን ከቀድሞው አካላችን ጋር የሚመሳሰል ቢሆንም አዲስና የተለየ ይሆናል። ከእንግዲህ ሞትና መበስበስ የማይነካን ዘላለማውያን እንሆናለን። የትንሣኤው አካል ተፈጥሯዊ ብቻ ሳይሆን ለዘላለም ከእግዚአብሔር ጋር ለመኖር የሚያስችል መንፈሳዊ ብቃት ያለው አዲስ አካል ነው።
  2. እንደ ተለያዩ አካላት ሁሉ፥ የትንሣኤ ተጨባጭ ትንሣኤ ይሆናል። ነገር ግን የተለየ ዓይነት አካል ይኖረናል።
  3. የፀሐይና የጨረቃ ክብር የተለያየ እንደሆነ ሁሉ፥ አሁን ያሉን አካላት ብዙ ክብር የላቸውም። ከትንሣኤ በኋላ ግን አካላችን አዲስ ክብርና ኃይል ይኖረዋል።

ለ. ጳውሎስ አዳምንና ክርስቶስን (ሁለተኛ አዳም) ያነጻጽራል። አዳም የተፈጠረው ከምድር አፈር ነበር። የእኛም ቁሳዊና ኃጢአተኛ አካላት የእርሱን ይመስላሉ። ክርስቶስ ግን ከሰማይ ስለመጣ ከመጀመሪያው አዳም ይበልጣል። ክርስቶስ ከሞት ከተነሣ በኋላ አዲሱን «መንፈሳዊ» አካል መሥርቷል። ይህም ከሞት በተነሣን ጊዜ የምናገኘው ነው። ጳውሎስ መንፈሳዊ አካል የሚለው እንደ መላእክት ያለውን ዓይነት አይደለም። ነገር ግን በመንፈሳዊ ስፍራ ለመኖር የሚያስችል አካል ማለቱ ነው፡፡ የክርስቶስ ተከታዮች ከትንሣኤው በኋላ ሊዳስሱትና ሊያዩት እንደቻሉት ዓይነት ተጨባጭ ይሆናል። ነገር ግን የትንሣኤ አካላችን የማይጠፋ፣ ኃጢአት እልባና ለዘላለም ከእግዚአብሔር ጋር ለመኖር የሚችል በመሆኑ ከምድራዊ አካል የተለየ ነው። ሰውነታችን የክርስቶስን የትንሣኤ አካል ይመስላል።

ሐ. የጳውሎስ ድምዳሜ፡- የትንሣኤ አካላችን ምን እንደሚመስል ሙሉ በሙሉ ግልጽ ባይሆንም፥ የክርስቶስን የትንሣኤ አካል እንደሚመስል አያጠራጥርም። ልናውቅ የምንችላቸው አንዳንድ ነገሮች አሉ። በመጀመሪያ፥ ሥጋና ደም የሆነው የአሁኑ አካላችን በዘላለማዊ የእግዚአብሔር መንግሥት ውስጥ ለመኖር ስለማይስማማ፥ የግድ ለውጥ መደረግ አለበት። የአሁኑ ሰውነታችን በሆነ መንገድ ተለውጦ የማይበሰብስ ይሆናል፡፡ ሁለተኛ፥ እግዚአብሔር ለጳውሎስ በብሉይ ኪዳን ያልታወቀውን «ምሥጢር» ገልጦለታል። ያም ምሥጢር በመጨረሻው ዘመን የእግዚአብሔር ልጆች ምን እንደሚሆኑ የሚያሳይ ነው። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሚመለስበት ጊዜ ነገሮች ከመቅጽበት ይለወጣሉ። ለውጡ የሚጀምረው «በክርስቶስ በሞቱት » ይሆናል። ይህም በሥጋ የሞቱትን ክርስቲያኖች የሚያሳይ ነው። ሥጋዊ ሰውነታቸው በትል ተበልቶ ቢጠፋም፥ የማይጠፋና የማይሞት የትንሣኤ አካል ከመቅጽበት ይቀበላሉ። ከዚያም በምድር ላይ በሕይወት ያሉት ሰዎች ሟች አካል በማይሞት፥ በማይጠፋና በትንሣኤ አካል ይተካል። ከዚያ በኋላ በእምነት ስንጠባበቅ በቆየነው በእግዚአብሔር ዘላለማዊ መንግሥት ውስጥ ለመኖር ዝግጁዎች እንሆናለን።

ስለሆነም፥ ክርስቲያኖች ሞትን ወይም ከመቃብር በኋላ የሚመጣውን ያልታወቀ ክስተት መፍራት የለባቸውም። ምንም እንኳ የምንወዳቸው ሰዎች በሞት በሚለዩን ጊዜ ማዘናችን ባይቀርም፥ እንደ ሌሎች ሰዎች ተስፋ-ቢሶች አይደለንም። ምክንያቱም እያንዳንዱ የእግዚአብሔር ልጅ አዲስን አካል እንደሚቀበል እናውቃለን። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሲመለስና እኛም ዘላለማዊ አካላችንን ተቀብለን ከሌሎች አማኞች ጋር ለዘላለም በምንኖርበት ጊዜ የመለያየቱ ሥቃይ ሳይቀር ይወገዳል። ይህ እውነት ክርስቲያኖችን ሁልጊዜም ሊያጽናናቸው ይገባል። ከመቃብር በኋላ ለዘላለም ከክርስቶስ ጋር እንደምንኖር በመረዳት በልበሙሉነት እየተመላለስን እግዚአብሔርን ልናገለግል እንችላለን። ይህ ለማያምኑ ወይም እምነታቸውን ለተዉትም ማስጠንቀቂያ ነው። ሞተው በሚነሡበት ጊዜ ከሌሎች አማኞች ጋር አብሮ የመኖር ዕድል ሳያገኙ ወደ ዘላለማዊ ሲዖል ይወርዳሉ።

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

1 thought on “አማኝ ከሞተ በኋላ ሥጋው ምን ይሆናል? (1ኛ ቆሮ. 15፡1-58)”

Leave a Reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading