ጴጥሮስ በአንጾኪያ የወንጌሉን ግንዛቤ የሚያዛባ ተግባር በመፈጸሙ ጳውሎስ ተጋፈጠው (ገላ. 2፡11-21)።

ጳውሎስ ወደ ሶርያ አንጾኪያ ከተመለሰ በኋላ፥ ጴጥሮስ በዚያ የሚገኙትን አብያተ ክርስቲያናት ለመጎብኘት ወደዚያው ሄደ። በመጀመሪያ ካልተገረዙና «ከረከሱ» አሕዛብ ጋር መብላትን የሚከለክለውን የአይሁዶች ልማድ ጥሶ ጴጥሮስ በብሉይ ኪዳን ያልተፈቀደውን ምግብ በላ። ከዚያ በኋላ ግን አንዳንድ አጥባቂ የአይሁድ ክርስቲያኖች ከኢየሩሳሌም መጥተው አይሁዳውያን ክርስቲያኖች እንዳይረክሱ ከአሕዛብ ጋር ኅብረት እንዳያደርጉ አስተማሩ። ጴጥሮስም ጠቃሚ ሚና ከነበራቸው የኢየሩሳሌም ቤተ ክርስቲያን መሪዎች ጋር ለመጋጨት ባለመፈለጉ ከአሕዛብ ጋር የሚያደርገውን ኅብረት አቆመ። አይሁዳዊ ልማዳቸውን ትተው ከአሕዛብ ጋር በግልጽ ኅብረት ማድረግ የጀመሩት እንደ በርናባስ ያሉ አንዳንድ አይሁዶችም ከአሕዛብ ክርስቲያኖች ፈቀቅ ማለት ጀመሩ። ወዲያውም የአይሁድና የአሕዛብ ክርስቲያኖች በኅብረት ያመልኩባት በነበረችው የአንጾኪያ ቤተ ክርስቲያን አይሁዶችና አሕዛብ ክርስቲያኖች ኅብረት የማያደርጉባት ሆነች። የክርስቶስ ቤተ ክርስቲያን በዘር ሐረጎች ተከፋፈለች።

ጳውሎስ ይህ ለአንጾኪያ ቤተ ክርስቲያን ብቻ ሳይሆን ለክርስትና የወደፊት ግሥጋዌ አደገኛ መሆኑን ተገነዘበ። አብያተ ክርስቲያናት አይሁዶችን በሚደግፉና አሕዛብን በሚደግፉ ወገኖች መከፋፈል ነበረባቸው? ወንጌሉ እነዚህን የመለያየት ግድግዳዎች አላፈረሰም? ይህ እግዚአብሔር አሕዛብን የሚቀበለው ባሕላቸውን ከለወጡ፥ ከተገረዙና የብሉይ ኪዳንን ሕግጋት ለመከተል ከፈለጉ ብቻ ነው ማለት ይሆን? እግዚአብሔርና የእግዚአብሔር ሕዝብ ሰዎችን የሚቀበሉት ክርስቶስን በማመን ላይ በተመሠረተ አንድነት ሳይሆን በሥራ መመዘኛነት ነውን?

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) የተሳሳተ የወንጌል፥ የቤተ እምነቶች ወይም የዓለም አስተሳሰብ በማራመድ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ያልሆኑ ክፍፍሎች ወደ አብያተ ክርስቲያኖቻችን እንዲገቡ የምናደርግባቸውን መንገዶች አብራራ። ለ) የተለያዩ ቤተ እምነቶች እርስ በርሳቸው ኅብረት ላለማድረግ ሲወስኑ ወይም የእነርሱ እምነት ከሌሉች እንደሚሻል ሲናገሩ ስለ ወንጌሉ ለዓለም የሚያስተላልፉት የተሳሳተ መልእክት ምንድን ነው? ሐ) አብያተ ክርስቲያናት በክርስቶስ የሚገኘውን አንድነት በማያሳዩበት ጊዜ የአማኞች ምስክርነት እንዴት እንደሚጠፋ ግለጽ።

ጳውሎስ በጠቅላላይቱ ቤተ ክርስቲያን ፊት ጴጥሮስን በመጋፈጥ ምላሽ ሰጥቷል። በርናባስን ወይም ሌሎች አይሁዶችን ሳይሆን ጴጥሮስን የተጋፈጠው ለምን ነበር? ጴጥሮስ ታላቅ መሪ በመሆኑ የእርሱ ግብዝነት (አጥባቂ አይሁዶች የሚሰነዝሩበትን ወቀሳ በመፍራት ተግባሩን መለወጡ) ሌሎች አይሁዶች እንዲሳሳቱ አድርጎ ነበር። ጴጥሮስ መሪ በመሆኑ በወንጌሉ እውነት የመመላለስ ኃላፊነት ነበረበት።

ጳውሎስ ከጴጥሮስ ጋር በአደባባይ ለምን ተፋጠጠ? የጴጥሮስ ተግባር ከጠቃሚ ሥነ መለኮታዊ ችግር የመነጨ ነበር። አሕዛብ በአይሁዶች ዘንድ ተቀባይነትን ለማግኘት ምን ማድረግ ያስፈልጋቸው ነበር? ይህ ጉዳይ ግልጽ መፍትሔ ካላገኘ የወንጌሉ ግንዛቤ መለወጥና ሰዎች አሕዛብ በእግዚአብሔር ዘንድ ተቀባይነትንና ድነትን (ደኅንነትን) ከማግኘታቸው በፊት ወደ አይሁድነት መለውጥ አለባቸው ብለው ማሰባቸው አይቀርም ነበር። የጴጥሮስ ተግባር የአይሁድ አማኞች ከአሕዛብ አማኞች እንዲለዩና የአሕዛብ አማኞች እምነት ድነትን ለማስገኘት ብቁ አይደለም ብለው በተግባራቸው እንዲናገሩ አድርጓቸዋል።

አንድ ኃጢአት የተፈጸመው በግለሰብ ደረጃ ከሆነ ማቴዎስ 18፡15-17ን በመጠቀም ንስሐንና ዕርቅን ለማምጣት መትጋት አለብን። ነገር ግን ኃጢአቱ በአጠቃላይ ቤተ ክርስቲያኒቱን የሚያካትት ከሆነ በአደባባይ መፍትሔ መሻት አለብን። ኃጢአቱ ይፋ ሊመጣ፥ ኑዛዜው በሰዎች ሁሉ ፊት ሊቀርብ፥ ሰዎች ሁሉ የሚመለከቱትና የሚረዱት ለውጥ ሊደረግ ይገባል። ጳውሎስ የተጋፈጠው ጴጥርስን ብቻ ቢሆን ኖር የመለየት ችግርና ድነት (ደኅንነት) በእምነት ብቻ የመገኘቱ ጉዳይ ለሌሎች ክርስቲያኖች ግልጽ አይሆንላቸውም ነበር።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ከጠቅላላው ቤተ ክርስቲያን ይልቅ በግል ልናስተካክላቸው የሚገቡ የኃጢአት ምሳሌዎችን ዘርዝር። ለ) በቤተ ክርስቲያን ፊት በይፋ ሊጋለጡና ሊወገዙ የሚገባቸው የኃጢአት ምሳሌዎችን ዘርዝር። ሐ) ኃጢአቶች በተለይም የመሪዎች ኃጢአቶች በይፋ ከመውጣት ይልቅ ከመእመናን በሚደበቁበት ጊዜ ሊከሰቱ የተመለከትሃቸውን አሉታዊ ነገሮች ግለጽ።

ጳውሎስ ጴጥሮስን የወቀሰው በሁለት ዐበይት ጉዳዮች ነበር። በመጀመሪያ፥ ጳውሎስ ጴጥሮስን ስለ ግብዝነቱ ወቀሰው። ግብዝነት ሰዎችን ለማስደሰት ለንል ያልሆንነውን መስለን የምንቀርብበት ሁኔታ ነው። ጴጥሮስ ከአሕዛብ ጋር እንዳይበላ የሚከለክለው ምንም ሥነ መለኮታዊ ምክንያት አልነበረውም። ቀደም ሲል ከአሕዛብ ጋር ይበላ ነበርና። ከአሕዛብ ጋር ኅብረት ማድረጉን ያቆመው ከኢየሩሳሌም የመጡትን የአይሁዳውያን ክርስቲያኖች ትችት በመፍራቱ ምክንያት ነበር። ሌሎችን በመፍራት ትክክለኛ የሆነውን ተግባር ከመፈጸም በምንቆጠብበት ጊዜ ሁሉ ግብዝነትን እናስተናግዳለን። እንዲሁም በሰዎች ፊት መንፈሳውያን መስለን ለመታየት ስንል አተገባበራችንን (ለምሳሌ፥ አዘማመራችንን፥ አጸለየያችንን፥ ሃሌ ሉያ ማለታችንን) የምንቀይር ከሆነ የግብዝነት ኃጢአት ነው።

የውይይት ጥያቄ፡- ክርስቲያኖች ሌሎችን በመፍራት ወይም ለማስደነቅ የሚፈጽሟቸውንና በእግዚአብሔር ፊት የግብዝነት ኃጢአቶች የሚሆኑትን ነገሮች ዘርዝር።

ሁለተኛ፥ ጳውሎስ አሕዛብ የአይሁድን ልማዶች ይክተሉ ዘንድ ለማስገደድ ወንጌሉን ስለለወጠ ጴጥሮስን ወቀሰው። ጳውሎስ፥ «አንድ ሰው ድነትን (ደኅንነትን) ለማግኘት ምን ማድረግ አለበት?» ብሎ ቢጠይቅ ኖሮ፥ ጴጥሮስ በክርስቶስ ማመን አለበት ብሎ ይመልስ እንደነበረ አይጠረጠርም፤ የሐዋ. 3፡19 አንብብ)። ነገር ግን ጴጥሮስ ከአሕዛብ ክርስቲያኖች ጋር ኅብረት ለማድረግ በመፍቀዱ በተግባሩ የተለየ ስብከት እየሰበከ ነበር። ጴጥሮስ ለአሕዛብ፥ «እውነተኛ ክርስቲያኖች ከሆንን ከእኛ ጋር ኅብረት ለማድረግ ከፈለጋችሁ እንደኛ መሆን አለባችሁ። ልትገረዙና የሙሴን ሕግጋት ልትከተሉ ይገባል። ከእናንተ ጋር ኅብረት የምናደርገውና በእኩል ደረጃ የምንመለከታችሁ ያን ጊዜ ብቻ ይሆናል። ይህ ካልሆነ ግን ድነትን ልታገኙ ብትችሉም ከእኛ ከአይሁዶቹ ዝቅ ያላችሁ “የሁለተኛ ደረጃ ክርስቲያኖች ናችሁ” እያለ ነበር። ይህም አሕዛብ እግዚአብሔርንና ሌሎች ክርስቲያኖችን ለማስደሰት ብለው ወደ አይሁድነት እንዲለወጡ ያደርግ ነበር። ይህ ደግሞ የሐሰት ወንጌል ነበር።

የውይይት ጥያቄ ዛሬ በተግባራችን የሐሰትን ወንጌል ልንሰብክ የምንችልባቸውን መንገዶች ግለጽ። ለምሳሌ፥ በልሳንና ብልጽግናና ፈውስ፥ በመሳሰሉት ላይ የተጋነነ ትኩረት በመስጠት።)

ከገላትያ 2፡15-21 ውስጥ ጳውሎስ ለጴጥሮስና ለአንጾኪያ ቤተ ክርስቲያን ምን ያህሉን እንደተናገረና ምን ያህሉ ደግሞ የትምህርቱ ማጠቃለያ እንደሆነ ማወቅ አስቸጋሪ ይሆናል። ነገር ግን ጳውሎስ ይህንን ከጴጥሮስ ጋር ያደረገውን የአደባባይ ፍጥጫ የተጠቀመው የወንጌሉን መሠረታዊ ምንነት ለመግለጽና ሰው በሥራ ሳይሆን በእምነት ብቻ እንደሚድን ለማሳየት ሳይሆን አይቀርም። የተቀረው የገላትያ መልእክት ክፍል ይህንኑ እውነት ያብራራል። የጳውሎስ አስተምህሮ የሚከተሉትን ነገሮች ያጠቃልላል።

ሀ. የአይሁድ ክርስቲያኖች ሕግጋትን በመጠበቅ ሊድኑ እንደማይችሉ ያውቃሉ። አለበለዚያ በክርስቶስ ማመን ለምን አስፈለጋቸው? ሌሎች አይሁዶች «የጸደቁት» በኢየሱስ ክርስቶስ በማመናቸው እንጂ የብሉይ ኪዳንን ሕግጋት በመጠበቃቸው አልነበረም። ይህ «ጽድቅ» የሚለው በጳውሎስ ጽሑፎች ውስጥ ዋነኛ ቁልፍ ቃል ነው። ይህም ዳኛው ተከሳሹን “ጥጥፋተኛ አይደለህም” ብሎ የሚያውጅበት የሕግ ቃል ነው። ስለሆነም፥ ጳውሎስ በክርስቶስ የሚያምኑ አይሁዶች ዋናው ነገር በክርስቶስ ማመን እንጂ ሕግጋትን መጠበቅ እንዳልሆነ የሚያሳዩ መሆናቸውን ገልጾአል። እግዚአብሔርም ኃጢአተኛ አይደላችሁም በማለት የተቀበላቸውና ድነት ያጎናጸፋቸው በክርስቶስ ባመኑ ጊዜ ነበር። አንድ ሰው ሕግጋትን መጠበቅ ወይም መገረዝ በእግዚአብሔር ዘንድ ተቀባይነትን ያስገኝልኛል ብሎ ካሰበ በክርስቶስ ማመን አያስፈልገውም። ለዚህ ሰው ክርስቶስ የሞተው በከንቱ ነው ማለት ነው። (ገላትያ 3-4 ዝርዝር ማብራሪያ ይሰጣል።)

ለ. ድነትን (ደኅንነትን) የሚያስገኘው በክርስቶስ ማመን እንጂ ሕግጋትን መጠበቅ ካልሆነ፥ ሰዎች በኃጢአታቸው በመቀጠል የእግዚአብሔርን ጸጋ አላግባብ አይጠቀሙም? ጳውሎስ ድነት (ደኅንነት) በእምነት ብቻ እንጂ በሥራ እንደማይገኝ ባስተማረ ጊዜ ሰዎችን ያሳሰባቸው ይሄ ነበር። ምንም እንኳን ሕግጋትን በመጠበቅ እግዚአብሔርን ለማስደሰት መሞከሩ ድነት (ደኅንነትን) ሊያስገኝ እንደማይችል ቢታወቅም፥ በክርስቶስ ባመንን ጊዜ ከክርስቶስ ጋር ሕያዋን ሆነናል። አሁን የክርስቶስ የትንሣኤ ሕይወት የእኛ ነው። አሁን ክርስቶስ በመንፈስ ቅዱስ አማካኝነት በውስጣችን ይኖራል። አመለካከታችን ሊለወጥና ባለማቋረጥ በክርስቶስ ታምነንና ተደግፈን ልንመላለስ ይገባል። እምነታችንን ተግባራዊ ስናደርግና በክርስቶስ ስናምን ክርስቶስ የአብን ፈቃድ ለመፈጸም አሁን በእኛ ውስጥ እንደሚኖር ሁሉ የተለየ ሕይወት እንኖራለን።

ጳውሎስ ከሚወዳቸው አገላለጾች አንዱ «በክርስቶስ ውስጥ» የሚል ነው። ጳውሎስ የክርስቲያኑን ሕይወትና ድነት (ደኅንነት) በሚያብራራበት ጊዜ፥ በድነት ግዜ ክርስቲያኑ በምሥጢራዊ መንገድ ከክርስቶስ ጋር ስለሚዋሃድ በክርስቶስ ላይ የደረሰው ሁሉ በክርስቲያኑም ላይ እንደሚደርስ ተዓነዘበ። (ለምሳሌ፥ ከእናቱ ጀርባ ላይ በአንቀልባ የታዘለ ሕጻን እርሷ ወደሄደችበት ስፍራ ሁሉ ይሄዳል።) ስለሆነም አዲስ ኪዳንን በምንመለከትበት ጊዜ ከክርስቶስ የመስቀል ሞት ጋር መተባበራችንን እንመለከታለን። ጳውሎስ ከክርስቶስ ጋር መሰቀሉንና መሞቱን ገልጾአል። (አሮጌ ተፈጥሮው ሞቷል ሕግን በመጠበቅ ከእግዚአብሔር ድጋፍ ለማግኘት የሚያደርገው ሙከራ ከስሟል። በሕይወቱ ላይ ይነሣ የነበረው የኃጢአት ኃይል ሞቷል) ክርስቶስ ከሞት ሲነሣ ክርስቲያኑም አብሮት ይነሣል። የክርስቶስ ትንሣኤ ለአካላዊ ትንሣኤያችን ዋስትና ይሰጣል። እንዲሁም እንደ አዲስ ፍጥረት የምንመላለስበትን ዘላለማዊ ትንሣኤ ያስገኛል። ክርስቶስ ወደ ሰማይ ባረገ ጊዜ እኛም ወደ ሰማይ ዐርገን በመንፈሳዊ ሁኔታ ከክርስቶስ ጋር በሰማያዊ ስፍራ ተቀምጠናል (ኤፌ. 26)።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ድነትን የምናገኘው በክርስቶስ በማመናችን እንጂ በምናከናውነው ተግባር አይደለም የሚለው ትምህርት ምን ያህል የቤተ ክርስቲያን መሪዎችን እንደሚያስፈራ ግለጽ፡፡ የሚፈሩት ለምንድን ነው? ለ) ከክርስቶስ ጋር በመንፈስ ከተነሣን ምን ዓይነት ለውጥ ይጠበቅብናል?

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading