በመንፈስ መመላለስ የሚገኝ የመንፈስ ቅዱስ ፍሬ (ገላ. 5፡16-6፡18)።

ከብሉይና አዲስ ኪዳን አስደናቂ ልዩነቶች አንዱ መንፈስ ቅዱስ በአማኞች ሕይወት ውስጥ የሚጫወተው ሚና ነው። በብሉይ ኪዳን፥ የመንፈስ ቅዱስ አገልግሎት የተወሰኑ መሪዎች የመሪነትና ጠላቶቻቸውን የማሸነፍ ተግባር እንዲያከናውኑ የሚያስችላቸው የእግዚአብሔር ኃይል ነበር። ስለሆነም፥ መንፈስ ቅዱስ ለጥቂት ሰዎች የሚሰጥ ሲሆን፥ አንዳንድ ጊዜ ከኃጢአት ወይም ከአገልግሎታቸው ፍጻሜ በኋላ መንፈስ ቅዱስ ይለያቸው ነበር።

በአዲስ ኪዳን ግን እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስን ለልጆቹ በሙሉ ለመስጠት ቃል ገብቷል። ስለ መንፈስ ቅዱስ በምናስብበት ጊዜ በአብዛኛው አልፎ አልፎ ስለሚያከናውናቸው እንደ ልሳን ወይም ለአንዳንድ ሰዎች በሚሰጣቸው የተአምራት ስጦታዎች ስላመሳሰሉት አስደናቂ ነገሮች እናስባለን። አብዛኛው የአዲስ ኪዳን አስተምህሮ የሚያተኩረው ግን በመንፈስ ቅዱስ ሌሎች አገልግሎቶቹ ላይ ነው። ከመንፈስ ቅዱስ እጅግ ጠቃሚ አገልግሎቶች አንዱ ክርስቲያኖች የኃጢአት ባሕርያቸውን እንዲያሸንፉና እግዚአብሔርን በሚያስደስት መንገድ እንዲመላለሱ ማስቻል ነው።

ጳውሎስ በመንፈስ ቅዱስ ኃይል የሚመራ የነጻነት ሕይወት በአኗኗራችን ላይ ለውጥን እንደሚያስከትል አስተምሯል። እንደ መንፈስ ቅዱስ ኃይል በምንኖርበት ጊዜ የኃጢአት ባሕርያችንን ሳይሆን እግዚአብሔርን ደስ እናሰኛለን። ጳውሎስ በእያንዳንዱ ክርስቲያን ውስጥ ሁለት ተጻራሪ ኃይላት እንዳሉ ገልጾአል። የኃጢአት ተፈጥሮና መንፈስ ቅዱስ አሉ። ድነትን (ደኅንነትን) ባገኘን ጊዜ እግዚአብሔር የኃጢአት ተፈጥሯችንን አላስወገደም። የኃጢአት ፍላጎት አሁንም አብሮን አለ። ነገር ግን ከሕይወታችን የኃጢአት ተፈጥሮ የመቆጣጠር ኃይልን ሰብሮ ከእርሱ የበለጠ ኃይል ተሰጥቶናል። ይህም ኃይል በእያንዳንዱ ክርስቲያን ውስጥ የሚኖረው መንፈስ ቅዱስ ነው። እነዚህ ሁለት ኃይላት እኛን ለመቆጣጠርና በሕይወታችን ፍሬያቸውን ለማፍራት ይታገላሉ። [ማስታወሻ፡- ክርስቲያኖች ሰይጣን ወደ ኃጢአት እንደሚመራን በመግለጽ ወቀሳ መሰንዘራችን የተለመደ ነው። ምንም እንኳ ሰይጣን ኃጢአት እንድንፈጽም ሊፈትነንና የኃጢአት ተፈጥሯችንን ቢጠቀምም፥ ኃጢአትን የምንፈጽመው ሁልጊዜም በምርጫችን ነው። መውቀስ ያለብንም ራሳችንን ነው ያዕ. 1፡13-15 አንብብ]።

የኃጢአት ባሕርይ የእግዚአብሔርን ፈቃድ ሳይከተል የግል እርካታንና ጥቅምን የሚያስገኙ ተግባራትን ለመፈጸምና የራስን ሕይወት ለመቆጣጠር የሚደረግ የእያንዳንዱ ሰው ኩሩ የማንነት ክፍል ነው። ይህ እግዚአብሔር ከሕዝቡ የሚፈልገው አመለካከትና ተግባር ተቃራኒ ነው። ጳውሎስ ከእነዚህ የኃጢአት ባሕርያት «ተግባራት» ወይም «ፍሬዎች» አንዳንዶቹን ጠቃቅሷል። እነዚህም በሦስት የተለያዩ ምድቦች ሊቀርቡ ይችላሉ።

ሀ. ወሲባዊ ኃጢአቶች። ዝሙት (ከጋብቻ ውጭ የሚፈጸም የትኛውም ዓይነት ወሲባዊ ግንኙነት)፥ ርኩሰት፥ መዳራትና ዘፋኝነት። (ማስታወሻ፡- ዘፋኝነት የሚለው የአማርኛው ቃል ሙዚቃንና የሰውነት እንቅስቃሴን ያመለክታል። ነገር ግን ጳውሎስ ይህን ሲል ዘፋኝነት ሁሉ ኃጢአት ነው ማለቱ ሳይሆን፥ ሰዎችን ለወሲብ ለማነሣሣት የሚካሄድ ዳንስና ጭፈራ ኃጢአት እንደሆነ ማመልከቱ ነው።)

ለ. እንደ ጣዖት አምልኮና ጥንቆላ ያሉ ሐሰተኛ አምልኮዎችም አሉ።

ሐ. ራሳችንንና ሌሎችን ወደ ተሳሳቱ ተግባራት የሚመሩ የሚጎዱ የተሳሳቱ አመለካከቶች አሉ። እነዚህም ጥላቻ፥ መከፋፈል፥ ቅንዓት፥ ቁጣ፥ አድመኛነት፥ መለያየት፥ መናፍቅነት፥ ምቀኝነትና ስካር ናቸው።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) እነዚህ ኃጢአቶች በቤተ ክርስቲያንህ ችግር የሚፈጥሩባቸውን መንገዶች ግለጽ። ለ) እነዚህ ኃጢአቶች በሕይወትህ ችግር የሚፈጥሩባቸውን መንገዶች ግለጽ።

መንፈስ ቅዱስ ግን ከዚህ የሚቃረን ፍሬ ይሰጣል። ሰዎች እንዲለውጡ በሚፈልጋቸው ብዙ ውጫዊ ተግባራት (ብዙም ሳይቆይ እነዚህ ነገሮች ወደ ሕግጋት ተመልሰው ሰዎችን በባርነት ይገዛሉ) ላይ ከማተኮር ይልቅ፥ መንፈስ ቅዱስ ልባችንና አመለካከቶቻችንን ለመለወጥ ይፈልጋል። የአማኙ ልብና አመለካከቶች ከተስተካከሉ በኋላ፥ ተግባራቱም ይለወጣሉ። የመንፈስ ቅዱስ ፍሬ በቀዳሚነት የኃጢአት ባሕርይ አመለካከቶች ተቃራኒ የሆኑ አመለካከቶች ናቸው። እነዚህም ፍቅር፥ ደስታ፥ ሰላም፥ ትዕግሥት፥ ቸርነት፥ በጎነት፥ ታማኝነት፥ የውኃትና ራስን መግዛት ናቸው። ጳውሎስ እንዲኖሩን የሚፈልጋቸውን አመለካከቶች ሁሉ ለመዘርዘር እየሞከረ አልነበረም። ነገር ግን በግንኙነት ዓይኖች የመንፈስ ቅዱስን ሥራዎች እየተመለከተ ነው። እምነታችንን የምንገልጽበት ዋነኛው መንገድ ፍቅር ከሆነ ለማፍቀር እንችል ዘንድ እነዚህ ባሕርያት በሕይወታችን ውስጥ ሊኖሩ ይገባል።

በኃጢአት ባሕሪያችንና በአዲሱ ባሕርያችን መካከል የሚካሄደው ጦርነት የተጧጧፈ ነው። ይህም ወደ መንግሥተ ሰማይ እስክንሄድ ድረስ የሚቀጥል ይሆናል። ይህ ጦርነት ሳይካሄድ የሚውልበት ቀን ሊኖር አይችልም። እንግዲህ፥ እግዚአብሔር በሚፈልገው መንገድ እንኖር ዘንድ ድልን የምንቀዳጀው እንዴት ነው? ጳውሎስ ማድረግ የሚገባንን ሁለት ዋና ዋና ነገሮች ሰጥቶናል።

በመጀመሪያ፥ የኃጢአትን ተፈጥሮ መስቀል አለብን። በገላትያ 2፡20 ጳውሎስ ከክርስቶስ ሞት ጋር ስለመተባበራችንና በዚህ ውስጥ ስለተገለጠው የእግዚአብሔር ሥራ ገልጾአል። ይህ የክርስቶስ ስቅለት የኃጢአት ባሕርያችንን ቁጥጥር በማጥፋት ለእግዚአብሔር እንድንኖር አስችሎናል።

ጳውሎስ በዚህ ስፍራ ልናደርገው ስለሚገባን ነገር ገልጾአል። ወደ ኃጢአት ለመምራት የሚያቀርበውን ፈተና ለመስማት ባለመፈለግ በየቀኑ የኃጢአት ተፈጥሯችንን መስቀል አለብን። ይህንን እንዴት ልናደርግ እንችላለን? አሮጌውን የኃጢአት ባሕርይ ላለመስማትና ፍላጎቶቹን ላለመፈጸም ከምንወስዳቸው እርምጃዎች መካከል የሚከተሉት ይገኙባቸዋል፡- ሀ) እንደ መንፈስ ቅዱስ ምሪት መመላለሳችንን ለማረጋገጥ በየጊዜው ራሳችንን መመርመር። ይህም መጽሐፍ ቅዱስን ማንበብ እንዳለብን ያሳያል። መንፈስ ቅዱስ የትኞቹ አሳቦችና አመለካከቶች ከክፉ ባሕርይ፥ የትኞቹ ደግሞ ከእግዚአብሔር እንደሆኑ የሚያሳየን በዚህ መንገድ ነው። ለ) የኃጢአት ተፈጥሮ መንገድ ትክክል እንዳልሆነና ኃጢአትን እንደፈጸምን በመገንዘብ አስፈላጊ በሆነ ጊዜ ሁሉ ንስሐ መግባት። ሐ) ወደ ኃጢአት ለመምራት የሚሞክረውን የአሮጌውን ባሕርይ ድምፅ ላለመስማት መምረጥና መንፈስ ቅዱስ እግዚአብሔርን በሚያስከብር መንገድ እንዴት መኖር እንዳለብን ሲናገረን መስማት። መ) የኃጢአት ባሕርያችን ስበት ጠንካራ በሚሆንበት ጊዜ ይረዳን ዘንድ ወደ እግዚአብሔር መጸለይ አለብን።

ሁለተኛ፥ በመንፈስ እንድንመላለስ ታዘናል። መንፈስ ቅዱስ የማያቋርጥ ወዳጃችን፥ መሪያችንና አጽናኛችን ነው። እርሱን መስማት መማር አለብን። በቃሉ ውስጥ የጻፈውን በማንበብ ድምፁን እንለያለን። መንፈስ ቅዱስ ወደ ንጹሕ ግንኙነት፥ የከበረ አምልኮ፥ የቤተ ክርስቲያን አገልግሎትና ወንጌሉን ወደ ማካፈል፥ ወደ የትኛውም ስፍራ በሚመራን ጊዜ በታዛዥነት እንከተለዋለን።

ጳውሎስ ለድነት (ደኅንነት) በክርስቶስ ስናምን አዲስ ፍጥረት እንደምንሆን አስረድቷል (ገላ. 6፡15)። ይህም እግዚአብሔር ሁለንተናችንን ለመለወጥ እንደሚፈልግ ያሳያል። ጳውሎስ የእግዚአብሔር ልጆች ከሆንን በኋላ በመንፈስ ቅዱስ በምንመላለስበት ጊዜ የሚከሰቱትን የተወሰኑ ለውጦች ዘርዝሯል (ሮሜ 8፡9)።

ሀ. በመንፈስ መመላለስ፣ በኃጢአት የሚመላለሱ ሰዎች እግዚአብሔር ወደሚፈልገው መንገድ እንዲመለሱ መርዳትን ያካትታል። ፍቅር ለመርዳት ይሞክራል እንጂ ለኃጢአተኛ «በመጸለይ» ብቻ አያበቃም። ፍቅር ወደ ኃጢአተኛው በመሄድ ወደ እግዚአብሔር እንዲመለስ ይማጸነዋል። ጳውሎስ ክርስቲያኑ ከኃጢአት መንገድ እንዲመለስ ለማድረግ በምንጥርበት ጊዜ እኛ ራሳችን እንዳንፈተን ያስጠነቅቀናል።

ለ. በመንፈስ መመላለስ የሌሎችን ሰዎች ሸክም ማገዝን ይጠይቃል። ይህ ግን በራስ ወዳድነት ሰዎች እንዲንከባከቡን መጠበቅ አይደለም። ስንችል የራሳችንን ሸክም መሸከም አለብን።

ሐ. በመንፈስ መመላለስ በትዕቢት ከሌሎች እንደምንበልጥ ማሰብ ወይም ራሳችንን እንደማንረባ መቁጠር አይደለም። ነገር ግን እግዚአብሔር የሰጠንን ስጦታዎች በመመርመር በተቻለን አቅም ለእግዚአብሔር ክብር ለመጠቀም መጣር አለብን።

መ. በመንፈስ መመላለስ የኃጢአት ባሕርያችንን የሚያጠናክር ተግባር አለመፍቀድም ነው። ጳውሎስ በሕይወታችን ውስጥ የሚሆነውን ሁኔታ ለማሳየት የመዝራትንና የማጨድን ምሳሌ ተጠቅሟል። መልካምና መንፈሳዊ ነገር (ጸሎት፥ አምልኮ፥ መጽሐፍ ቅዱስን ማንበብ፥ መልካም ጓደኝነትን የሚያንጽ ንግግር፥ የሚያንጽ ቪዲዮ ማየትን) ከዘራን፥ በመንፈስ ቅዱስ ኃይል መንፈሳዊ ዕድገትንና ዘላለማዊ ሽልማቶችን እናጭዳለን። ነገር ግን የኃጢአት ባሕርያችንን የሚያጠናክሩትን ነገሮች (መጥፎ ጓደኝነት፥ ሐሜት፥ መጥፎ መጻሕፍት ወይም መጥፎ ቪዲዮዎችን ማየት) ከዘራን፥ የኃጢአት ባሕርያችን ዘላለማዊ ጉዳት የሚያስከትሉትን ፍሬዎች እንድናጭድ ያደርገናል።

ሠ. በመንፈስ መመላለስ አሁን ጥቅም እያገኘንበት ባይመስልም እንኳን ለሰዎች መልካም ማድረግን ይጠይቃል።

እነዚህ ነገሮች ሙሉ በሙሉ ማለት ይቻላል ከሰዎች ጋር ያለንን ግንኙነትና ለእነርሱ የምናሳያቸውን ፍቅር የሚመለከቱ መሆናቸውን አጢን። ፍቅር መንፈስ ቅዱስ በሕይወታችን ውስጥ ለማፍራት የሚፈልገው ዐቢይ ቁም ነገር ነው።

የውይይት ጥያቄ፡– ሕይወትህን መርምር። ሀ) በመንፈስ መመላለስህን የምታሳይባቸውን መንገዶች ዘርዝር። ለ) ለመንፈሳዊ ሕይወትህ የሚያግዙ ነገሮችን የምትዘራባቸውን መንገዶች ዘርዝር። ሐ) ለኃጢአት ተፈጥሮህ የሚያግዙ ነገሮችን የምትዘራባቸውን መንገዶች ዘርዝር።

መደምደሚያ (ገላ. 6፡11-18)

ጳውሎስ መልእክቱን ሲደመድም የሚከተሉትን ነገሮች ገልጾአል።

  1. በትላልቅ ፊደላት ጽፎአል። ይህን ያደረገበትን ምክንያት ባናውቅም፥ የመልእክቱን አስፈላጊነት ለማጉላት የፈለገ ይመስላል። ከዚህ በበለጠ ግን ሌላ ሰው ሳይሆን ራሱ እንደ ጻፈና ከዓይኑ ሕመም የተነሣ ትላልቅ ፊደላትን እንደ ተጠቀመ የሚያሳይ ይሆናል።
  2. አማኞች በትክክለኛ ነገሮች መመካታቸውን እንዲያረጋግጡ መከሯቸዋል። ስለ መገረዝ ጥቅም የሚሰብኩ ሰዎች በመገረዛቸው ይመኩ ነበር። እነዚህ ሰዎች ለክርስቶስ መስቀል ክብርን ሳይሰጡ መንፈሳዊነታችንን ያጎላሉ በሚሏቸውና ባከናወኗቸው ውጫዊ ተግባራት ይመኩ ነበር። ጳውሎስ በግርዛት ላይ የሚያተኩሩበት ብቸኛው ምክንያት አይሁዶች እንዳያሳድዷቸው በመፍራታቸው እንደሆነ ገልጾአል።

በአንጻሩ፥ ከክርስቶስ መስቀል በቀር ጳውሎስ በየትኛውም ውጫዊ ነገር ላለመመካት ይወስናል። ከክርስቶስ በስተቀር አይሁዳዊ ባሕሉ፥ ነገዱ፥ ወንድነቱ፥ ወይም ትምህርቱ እርባና-ቢስ እንደሆነ ገልጾአል። ጳውሎስ ዓለም እንደ ብርቅ ለምታያቸው ነገሮች ሞቷል። ጳውሎስ እንደ ትልቅ ነገር የሚቆጥረው አዲስ ፍጥረትነቱን ነበር። በሰውነቱ ላይ የሚታዩት የስደት ምልክቶች ጳውሎስ እግዚአብሔርን በሚያስከብር መንገድ እንደሚመላለስ ያሳያሉ። ስለሆነም፥ ሌሎች አማኞች ሊንቁት አይገባም።

  1. ጳውሎስ እርሱንና የእግዚአብሔርን ቃል በእውነተኛ ሰላምና ምሕረት የሰሙትን የገላትያ ክርስቲያኖች ባረከ።

የውይይት ጥያቄ፡– ከገላትያ መልእክት ሁሉም ክርስቲያኖች ሊያውቋቸው ይገባል የምትላቸውን እውነቶች ዘርዝር።

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

%d bloggers like this: