አማኞች ከንቱ ሰብአዊ ትምህርቶችን ከመከተል ይልቅ በክርስቶስ ላይ ማተኮር ይኖርባቸዋል (ቆላ. 2፡6-23)

አሁን ደግሞ ጳውሎስ በሐሰተኛ ትምህርቶች ላይ ያተኩራል። እነዚህንም ትምህርቶች ጳውሎስ፥ እንደ ክርስቶስ ትምህርት ሳይሆን እንደ ሰው ወግና እንደ ዓለማዊ እንደ መጀመሪያ ትምህርት ያለ ፍልስፍናን ከንቱ መታለል» ሲል ይገልጻል። አማኞች በመንፈሳዊ ሕይወታቸው እንዲያድጉ ያበረታታቸዋል። ሥር እንደሌላቸውና ማዕበል በተነሣ ጊዜ እንደሚወድቁ ዛፎች ከመሆን ይልቅ ከክርስቶስ ጋር ጥልቅ የእውቀትና የግንኙነት ሥሮች ልንይዝ ይገባል። መጀመሪያ ባመንን ጊዜ ባገኘነው እውነት ላይ እየጨመርን መሄድ አለብን።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) በቅርቡ የተማርሃቸውና መንፈሳዊ ሥሮችህ ወደ ክርስቶስ ጠልቀው እንዲሄዱ ያደረጉህ እውነቶች ምን ምንድን ናቸው? ለ) ብዙ ክርስቲያኖች በመንፈሳዊ ሕይወታቸው የሚያድጉትና ባላቸው እውቀት የሚረኩት ለምንድን ነው? ሐ) ሰዎች ከክርስቶስ ጋር የጠለቀ ግንኙነት እንዲመሠርቱና ስለ እርሱም የበለጠ እንዲያውቁ ቤተ ክርስቲያንህ ምን ልታደርግ ትችላላች?

ጳውሎስ አጽንኦት የሰጠባቸው አንዳንድ እውነቶች፡-

ሀ. ኖስቲኮች ክፉ ሰብአዊ ሰውነት ሊለብስ እንደማይችል ያስተምሩ ነበር። ይህም ክፉ ያደርገዋል ብለው ያስቡ ነበር። ጳውሎስ ግን ክርስቶስ ሙሉ በሙሉ አምላክና ሰው እንደሆነ ያስረዳል።

ለ. ኖስቲኮች የቆላስይስ አማኞች ከክፉ ቁሳዊ ተፈጥሮ ነፃ የሚያደርጋቸውን ምሥጢራዊ ነገሮች ስለማያውቁ ምሉዓን እንዳልሆኑ ገልጸው ነበር። ጳውሎስ ግን በክርስቶስ ምልዓት እንደተሰጣቸው ያስረዳል። የሚያስፈልጋቸው ክርስቶስ ብቻ እንጂ ሌላ ልዩ ነገር አልነበረም። እርሱ በቂ የሆነው ለምንድን ነው?

  1. ክርስቶስ አማኞች ለኃጢአት ተፈጥሮ የታሠሩበትን ሁኔታ በማስወገድ ልባቸውን ገርዟል። ከክርስቶስ ጋር በሞቱ፥ በቀብሩና በትንሣኤው ስለተባበርን፥ በሕይወታችን ላይ የነበረው የኃጢአት ቁጥጥር ተወግዷል። በመሆኑም ኖስቲኮች የሚፈልጉትን አዲስ ሕይወት አግኝተናል።
  2. የአማኞች ኃጢአቶች በሙሉ ይቅርታን አግኝተዋል። «በእኛ ላይ የነበረውን የሚቃወመንንም በትእዛዛት የተጻፈውን የዕዳ ጽሕፈት ደመሰሰው።» በጥንት ጊዜ አንድ ሰው ገንዘብ በሚበደርበት ጊዜ መበደሩን የሚያመለክት ፊርማ ያሰፍር ነበር። የተበደረውን ገንዘብ ባይከፍል አበዳሪው ፊርማው ያረፈበትን ማስታወሻ ከዳኛ ዘንድ በመውሰድ በፍርድ ቤት ገንዘቡን ያስከፍል ነበር። ገንዘቡን በሚከፍልበት ጊዜ ሕዝብ በሚያልፍበት ስፍራ «በሙሉ ተከፍሏል» የሚል ማስታወቂያ ይለጠፋል። ጳውሎስ ስለ ኃጢአታችንም ተመሳሳይ ማብራሪያ ይሰጣል። እግዚአብሔር በብሉይ ኪዳን ውስጥ የሰጣቸውን ትእዛዛት ስላልጠበቅን፥ በደለኛነታችንን የሚያመለክት የዕዳ ጽሕፈት ነበረብን። ክርስቶስ ስለ እኛ በሞተ ጊዜ ግን ኃጢአታችን ወይም የዕዳ ጽሕፈታችን በሙሉ በመስቀል ላይ ተጠረቁ። ሰይጣን የሚከስሰን ስለ እነዚሁ ኃጢአቶቻችን ነበር። ክርስቶስ በሞተ ጊዜ ለእነዚህ ዕዳዎቻችን ተገቢውን ዋጋ ከፈለ። ስለሆነም፥ በእግዚአብሔር ዐይኖች ፊት በዚያው የዕዳ ጽሕፈት ላይ «በሙሉ ተከፍሏል» ተብሎ ይጻፋል። ስለሆነም ሰይጣን ከእንግዲህ ወዲህ ሊከስሰን አይችልም። እግዚአብሔር ራሱ ስለከፈለልን ዕዳችንን መክፈል አያስፈልገንም።
  3. ክርስቶስ ክፉ ኃይላት (ሰይጣንና አጋንንቱ) በእኛ ላይ የነበራቸውን ይዞታ አስወግዷል። አንድ ድል አድራጊ ጄኔራል በጦርነት የማረካቸውን እሥረኞች በሰንሰለት አሥሮ እንደሚነዳ ሁሉ፥ ክርስቶስ ሰይጣንና አጋንንትን በመስቀል ላይ አሸንፎ በሰንሰለት ጠፍሯቸዋል። ሰይጣን ዛሬም በዓለማችን ውስጥ ኃይል ስላለው ኃጢአትን እንድንሠራ ሊፈትነን ይችላል። ነገር ግን ሕይወታችንን የመቆጣጠር አቅም ስለሌለው፥ እግዚአብሔር እንዲቀጣን የማዘዝ ችሎታ የለውም። በክርስቶስ ደም የኃጢአታችን ዋጋ ተከፍሏል።

እግዚአብሔር ሙሉ በሙሉ ስለተቀበለን የሐሰት አስተማሪዎችን ትምህርት የምንከታተልበት ምክንያት አይኖርም። ክርስቲያኖች የተወሰኑ ምግቦችን እንዲመገቡ፥ የብሉይ ኪዳን ሃይማኖታዊ በዓላትን እንዲከተሉ ወይም በሰንበት ቀን እንዲያመልኩ የሚጠይቀውን የአይሁዶች ትምህርት የሚከተሉበት ምክንያት አይኖርም። በተጨማሪም ክርስቲያኖች በምሥጢራዊ ዕውቀት ወይም ሰውነትን በመቅጣት የኃጢአትን ቁጥጥር ለማሳነስ በሚሞከሩ ሕጎች ላይ ማተኮር የለባቸውም። በእነዚህ ሰው ሠራሽ ደንቦች ላይ ብዙ አጽንኦት መስጠቱ ጠቃሚ የማይሆንባቸው አያሌ ምክንያቶች አሉ።

በእነዚህ ነገሮች ላይ ማተኮሩ ክርስቶስ ለኃጢአቶቻችን መሞቱን ሙሉ በሙሉ እንደማናምን ያሳያል። እምነታችን ለጋ መሆኑን ያሳያል። ይህም በአብዛኛው ወደ ትዕቢት ይመራል። በውጫዊ ሕጎችና ልምምዶች ላይ ማተኮራችን ዓይናችንን በክርስቶስ ላይ ተክለን ከእርሱ ጋር ኅብረት እያደረግን እንደማንመላለስ ያሳያል። እነዚህ ነገሮች ዘለቄታዊ እሴት የሌላቸውና በመንግሥተ ሰማይ የማናገኛቸው ናቸው። ሕግጋቱ እውነተኛ አምልኮን አያስከትሉም። እግዚአብሔር እንዲኖረን የሚፈልገውን ጥበብ አያሳዩም። ራሳችንን እንድንጎዳ የሚያዙንን እነዚህን ሕግጋት መጠበቁ የመንፈሳዊነት ምልክት ቢመስልም ግን አይደለም። ዋናው ክርስቶስ እንጂ ሕግጋት አይደሉም።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) አንዳንድ ክርስቲያኖች ከክርስቶስ ጋር የተሟሟቀ ግንኙነት ከመመሥረት ይልቅ ቤተ ክርስቲያናቸው በፈጠረቻቸው ውጫዊ ደንቦችና ሕግጋት ላይ እንዴት አጽንኦት እንደሚሰጡ ግለጽ። ለ) ከመንፈሳዊነት ጋር ቀጥተኛ ግንኙነት ሳይኖራቸው ብዙውን ጊዜ ክርስቲያኖች የሚጠብቋቸውን ነገሮች፥ ሕጎችና ደንቦች ዘርዝር። (ለምሳሌ፥ ክርስቲያኖች ሊከተሉ የሚገባቸው አለባበስ፥ ወዘተ) እነዚህ ነገሮች የሚመጡት ከየት ነው? እነዚህ ሕጎች ለጋዎችና መንፈሳዊ ብስለትን የማያሳዩ የሆኑበትን ምክንያት አብራራ።

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading