የ1ኛ ጢሞቴዎስ ልዩ ባሕርያት

1) የ1ኛ ጢሞቴዎስ መልእክት ለጢሞቴዎስ የግል ምክሮችን የሚለግስና ለቤተ ክርስቲያንም የሚያገለግል መልእክት ነው። ይህ ቀደም ሲል ከተመለከትናቸውና ጳውሎስ ለአብያተ ክርስቲያናት ወይም ለተወሰኑ እማኞች ቡድን ከላካቸው መልእክቶች የተለየ ነው። ለምሳሌ ያህል፥ ጳውሎስ ከሰጣቸው ምክሮች አንዳንዶቹ የጢሞቴዎስን ግላዊ ሁኔታ ያገናዘቡ ነበሩ። ጳውሎስ ጢሞቴዎስን ልጄ እያለ በመጥራት (1ኛ ጢሞ. 1፡18)፥ በልጅነቱ የበታችነት ስሜት እንዳይሰማው (1ኛ ጢሞ. 4፡12)፥ እንዲሁም ላለበት በሽታ ጥቂት የወይን ጠጅ እንዲጠጣ ይመክረዋል (1ኛ ጢሞ. 4፡23)። ነገር ግን በዚህ መልእክት ውስጥ የሚገኙ አብዛኞቹ ጉዳዮች ጢሞቴዎስ በኤፌሶን ከተማ ቤተ ክርስቲያንን በሚገባ እንዲያደራጅ የሚያሳስቡ ነበሩ። ይህ መልእክት ምናልባትም ጢሞቴዎስ እንደ መመሪያ ሊከተለውና ከእርሱ በኋላ የሚመጡ የቤተ ክርስቲያን መሪዎችም በዚሁ መንገድ ቤተ ክርስቲያንን እንዲመሠርቱ የሚያመለክት ሳይሆን አይቀርም።

2) የ1ኛ ጢሞቴዎስና የቲቶ መልእክቶች የቀድሞዎቹ አብያተ ክርስቲያናት እንዴት ይደራጁ እንደነበር ያስገነዝቡናል። ምንም እንኳን በሐዋርያት ሥራ ውስጥ ዲያቆናትና ሽማግሌዎች የተጠቀሱ ቢሆንም፥ ሽማግሌዎች በተወሰኑ አብያተ ክርስቲያናት ውስጥ ማገልገላቸውን ወይም ዲያቆናት በተወሰኑ ቦታዎች ብቻ መገኘታቸውን በዝርዝር እንመለከትም። የጢሞቴዎስ መልእክት በአዲስ ኪዳን ዘመን የተለመደው የቤተ ክርስቲያን አመራር ዲያቆናትንና ሽማግሌዎችን እንደሚያካትት ያብራራል። እነዚህ መሪዎች እንዴት እንደሚመረጡ ግን የተገለጸ ነገር የለም። በሐዋርያት ይሆን የሚሾሙት? ወይስ በምእመናን ይመረጡ ነበር? ይህም አንድ ዓይነት የአመራር መዋቅር መርጠን በአዲስ ኪዳን ልናስደግፈው እንደማንችል ያስገነዝባል። ጳውሎስ ለአገልግሎቱ ስለሚያስፈልግ ውጫዊ የብቃት መለኪያም የገለጸው ነገር የለም። የቀድሞይቱ ቤተ ክርስቲያን ትኩረት የምትሰጠው በውስጣዊ ብቃቶች ላይ ነበር። ከዚህም የተነሣ በባሪያና ጨዋ፥ ማንበብ በሚችልና በማይችል፥ ወይም በሀብታምና ድሃ መካከል ልዩነት አይደረግም ነበር። ሁለቱም ውስጣዊ ብቃቶችን ካሟሉ በመሪነት ሊያገለግሉ ይችሉ ነበር። ሌላው በጳውሎስ መልእክቶች ውስጥ የሽማግሌ አገልግሎት ከዲያቆን የሚለይባቸው ነጥቦች ሰፍረው አንመለከትም።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) በቤተ ክርስቲያንህ ሽማግሌዎችን ወይም ዲያቆናትን ለመምረጥ በዋናነት የሚወሰዱ ብቃቶች ምን ምንድን ናቸው? ትኩረት የሚሰጠው እንደ ታዋቂነት፥ ትምህርት፥ ሀብት፥ መልካም ቤተሰባዊ ሥረ መሠረት ላሉት ውጫዊ ብቃቶች ነው ወይስ እንደ የጸሎት ሕይወት፥ የማስተማር ችሎታ፥ መንፈሳዊነት፥ ላሉ መንፈሳዊ ብቃቶች ነው? ለ) ብዙ መሪዎች ከመንፈሳዊ ብስለታቸው ይልቅ በጎሳቸው፥ በቤተሰባቸው ወይም በትምህርት ደረጃቸው ምክንያት የሚመረጡት ለምንድን ነው? ሐ) ይህ ቅድሚያ ስለምንሰጣቸው ነገሮች ምን ያሳያል?

3) ጳውሎስ ሰዎች ሊያምኑት፥ ሊጠብቁትና ለሌሎች ሊያስተላልፉ ስለሚገባው ወንጌል አጽንኦት ሰጥቶ ይናገራል። ጳውሎስ ጢሞቴዎስ አዲሱን ትውልድ ለማስደሰት አዳዲስ መረጃዎችን እንዲፈጥር አይጠብቅበትም ነበር። ይልቁንም ጢሞቴዎስ ብዙ ጊዜ ጳውሎስ ወንጌል ሲሰብክ ስለሰማ ይህንኑ እውነት በጥንቃቄ ለሌሎች እንዲያስተላልፍ ይፈልጋል (1ኛ ጢሞ. 1፡3-11)። ምንም እንኳን ወንጌሉን የምንሰብክበት መንገድ ከባህል ባህል ወይም ከትውልድ ትውልድ ሊለያይ ቢችልም፥ የወንጌሉ አስኳል ይዘት መለወጥ የለበትም። ሁልጊዜም ወንጌሉ ክርስቶስ ብቸኛው የመዳን መንገድ መሆኑን፥ ለኃጢአታችን መሞቱንና ሰው ድነትን (ደኅንነትን) የሚያገኘው በክርስቶስ በማመን መሆኑን አጽንቶ መናገር አለበት። ሰባኪው ጢሞቴዎስ፥ ጳውሎስ ወይም ዛሬ ያለነው እኛ ብንሆን ወይም ሰውዬው በቻይና፥ ዩናይትድ ስቴትስ፥ ወይም በኢትዮጵያ ውስጥ ቢኖር ይህ የመልእክት አስኳል መለወጥ የለበትም። ኃይማኖቶች ሁሉ ወደ እግዚአብሔር ይመራሉ የሚለው ዓይነት የትኛውም የወንጌሉን አስኳል የሚለውጥ ትምህርት ወንጌሉን በመለወጥ ከእግዚአብሔር ስለሚያርቀን ሐሰተኛነቱ ሊገለጥ ይገባል።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) እያንዳንዱ ክርስቲያን የወንጌልን ምንነት በግልጽ መገንዘቡ አስፈላጊ የሚሆነው ለምንድን ነው? ለ) ሐሰተኛ አስተማሪዎች በኢትዮጵያ ውስጥ የወንጌሉን አስኳል እንዴት እንደሚለውጡ ምሳሌዎችን ዘርዝር።

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

%d bloggers like this: