የ1ኛ ጢሞቴዎስ በማን ተጻፈ፣ ለማን ተጻፈ፣ መቼና የት ተጻፈ

የ1ኛ ጢሞቴዎስ ጸሐፊ

የውይይት ጥያቄ፡- 1ኛ ጢሞቴዎስ 1፡1-2 አንብብ። ሀ) የመልእክቱ ጸሐፊ ማን ነው? ራሱን እንዴት ይገልጻል? ይህ ገለጻ ከሌሎች መግቢያዎች ጋር ምን ዓይነት ተመሳሳይነት ወይም ልዩነት እንዳለው ግለጽ (ለምሳሌ፥ ሮሜ 1፡1፤ ገላ. 1፡1፥ 1ኛ ቆሮ. 1፡1) ለ) የመልእክቱ ተቀባይ ማን ነበር? የተገለጸውስ እንዴት ነው?

ጳውሎስ እንደ ሌሎቹ መልእክቶቹ ሁሉ የዚህ መልእክት ጸሐፊ መሆኑን ሲገልጽ፥ «መድኃኒታችን እግዚአብሔር ተስፋችንም ኢየሱስ ክርስቶስ እንዳዘዘው ትእዛዝ የኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያ የሆነው ጳውሎስ» በማለት ገልጾአል። ምንም እንኳ ጳውሎስ የሚጽፈው በኤፌሶን ቤተ ክርስቲያን ውስጥ እንዲያገለግል ለላከው የቅርብ ጓደኛው ቢሆንም፥ ለጢሞቴዎስ ሐዋርያነቱን ለማስገንዘብ ፈልጓል። ምናልባትም ጳውሎስ ይህንን ያደረገው የጢሞቴዎስ አገልግሎት በቤተ ክርስቲያን አሠራር ላይ ተጽዕኖ እንደሚያስከትል ስለተገነዘበ ሳይሆን አይቀርም። የኤፌሶን ቤተ ክርስቲያን ጢሞቴዎስ የራሱን ሕግጋት እየፈጠረ ሳይሆን ነገር ግን የኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያ ከሆነውና በሥልጣን ቃል ከሚናገረው ጳውሎስ እንደተቀበለ ለማስገንዘብ ይፈልጋል።

የጳውሎስ መግቢያ በኢየሱስ ክርስቶስ ላይም ያተኩራል። ጳውሎስ የኢየሱስ ክርስቶስ ተወካይ ወይም ሐዋርያ መሆኑ ብቻ ሳይሆን፥ ሥልጣኑም የሚመጣው ተስፋችን ከሆነው ከኢየሱስ ክርስቶስ ነው። ጳውሎስ በዚህ ጊዜ ወደ ሕይወቱ ፍጻሜ እየተቃረበ ነበር። በመሆኑም አሳቡ ይበልጥ በሰማያዊ መንግሥት ላይ ያተኮረ ይመስላል። የዘላለም ሕይወት ተስፋ በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ እንደ ተመሠረተ ተረድቶ ነበር። ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ካለው ግንኙነት የተነሣ እንዲሁም እግዚአብሔር አብ አዳኙ በመሆኑ ጳውሎስ ኢየሱስ ክርስቶስ በሰማይ የሚያዘጋጅለትን በረከት ለማግኘት ሙሉ ዋስትና ወይም ተስፋ ነበረው።

ጳውሎስ መልእክቱን የጻፈው ለማን ነበር።

ይህ መልእክት የተጻፈው የጳውሎስ የእምነት ልጁ ለነበረው ለጢሞቴዎስ ነበር። ከ15 ዓመታት ለሚልቁ ጊዜያት ጢሞቴዎስ ከጳውሎስ ጋር የቅርብ ጓደኛ ሆነው አገልግለዋል። ምናልባትም ግንኙነታቸው የተጀመረው በጳውሎስ የመጀመሪያው የወንጌል መልእክተኝነት ጉዞ ወቅት ሳይሆን አይቀርም። ከሁለተኛው የወንጌል መልእክተኝነት ጉዞ በኋላ ግን ጢሞቴዎስ በአብዛኛው በጳውሎስ አገልግሎት ላይ ተካፋይ ሆኖ ሠርቷል።

ጢምቴዎስ ያደገው ልስጥራ በምትባል ከተማ ነበር። አባቱ የግሪክ ሰው ነበር። በልጅነቱ ግን አይሁዳዊያን የሆኑት እናቱ ኤውንቄ እና አያቱ ሎይድ ብሉይ ኪዳንን በጥንቃቄ ያስተማሩት ይመስላል (የሐዋ. 16፡1)፡፡ ግሪኮች ግርዘት ያልሠለጠኑ ሰዎች ልማድ ነው ብለው ያስቡ ስለነበር፥ ግሪካዊ አባቱ ምናልባትም ጢሞቴዎስ በአይሁዳውያን ልማድ እንዳይገረዝ ሳይከለክለው አልቀረም። ጳውሎስ ወደ ልስጥራ በመጣ ጊዜ ጢሞቴዎስን ወደ ክርስቶስ የመራው ይመስላል። ይህም የሆነው በጳውሎስ የመጀመሪያው የወንጌል መልእክተኝነት ጉዞ መጨረሻ አካባቢ ነበር። ጳውሎስ ባልነበረበት አንድ ወይም ሁለት ዓመታት ውስጥ ጢሞቴዎስ ከክርስቶስ ጋር ባለው ግንኙነት አድጎ በአካባቢው ክርስቲያኖች ዘንድ የታወቀ ሆነ። ጳውሎስ በሁለተኛው የወንጌል መልእክተኝነት ጉዞው አካባቢ ወደ ልስጥራ ሲመጣ (50 ዓ.ም)፥ በዚህ ወጣት ልጅ ሁኔታ ተማረከ። በመሆኑም ጢሞቴዎስ የሁለተኛው የወንጌል መልእክተኝነት ጉዞው አጋዥ ሆኖ ከእርሱ ጋር እንዲሠራና እንዲሠለጥን ጋበዘው። ጳውሎስ ጢሞቴዎስን የመረጠው እግዚአብሔር ከሰጠው ትንቢት የተነሣ ሳይሆን አይቀርም (1ኛ ጢሞ. 1፡18፤ 4፡14)።

ጳውሎስ ልስጥራን ለቅቆ ከመሄዱ በፊት ሁለት ነገሮችን አከናውኗል። በመጀመሪያ፥ ጢሞቴዎስን አስገረዘው። ለምን ነበር ይህን ያደረገው? ጳውሎስ ጢሞቴዎስን የገረዘው ግርዘት በጢሞቴዎስ ደኅንነት ላይ የሚያበረክተው አስተዋጽኦ እንዳለ በማመኑ ምክንያት አልነበረም። ቀደም ሲል ጳውሎስ በእናቱም በአባቱም ግሪክ የነበረው ቲቶ እንዳይገረዝ መከልከሉንና ግርዘት ለደኅንነት አስፈላጊ አለመሆኑን የሚገልጽ መልእክት ለገላትያ ሰዎች መላኩን ተመልክተናል። ነገር ግን ጳውሎስ የወንጌሉን እውነተኝነት በማይነካ መልኩ ቃሉን ሰምተው የሚድኑ ሰዎች እንዳይሰናከሉ መርዳት አስፈላጊ መሆኑን ያምን ነበር። በከተማይቱ ውስጥ ጳውሎስ በዋናነት የሚያገለግለው አይሁዶችን ስለሆነና ጢሞቴዎስም ከፊል አይሁድ ስለነበረ፥ አይሁዶችን ለመድረስ እንቅፋት ሊሆን የሚችለውን ነገር ለማስወገድ ሲል ጢሞቴዎስን ገረዘው። ሁለተኛ፥ ጳውሎስ እጆቹን በመጫንና በመጸለይ ጢሞቴዎስን ለአገልግሎት ላከው። እግዚአብሔር ለጢሞቴዎስ ልዩ መንፈሳዊ ስጦታ የሰጠው በዚህ ጊዜ ነበር (1ኛ ጢሞ. 4፡14፤ 2ኛ ጢሞ. 1፡6)።

ጢሞቴዎስ ለቀጣይ 15 ዓመታት የጳውሎስ የአገልግሎት ባልደረባ ሆኖ ሠርቷል። ይህንንም ያደረገው በሁለተኛና በሦስተኛ የወንጌል መልእክተኝነት አገልግሎት ላይ፥ እንዲሁም ጳውሎስ በሮም ታሥሮ በነበረበት ወቅት ነበር። ጢሞቴዎስ ከጳውሎስ ጋር የነበረ ቢሆንም፥ ጳውሎስ ወደ ተለያዩ አብያተ ክርስቲያናት እየላከው ክርስቲያኖችን ያበረታታና ያነቃቃቸው ነበር። በዓመታት ውስጥ በጳውሎስና በጢሞቴዎስ መካከል ጠንካራ ግንኙነት ተመሥርቷል። ይህም በጳውሎስና በሌሎች አገልጋዮች መካከል ከነበረው ግንኙነት ሁሉ የጠነከረ ነበር። ጳውሎስ ከአብራኩ የወጡ ሥጋዊ ልጆች ስላልነበሩት፥ ጢሞቴዎስ ልክ እንደ ልጁ ሆነለት።

ጢሞቴዎስ እንደ ሐዋርያ የተቆጠረ አገልጋይ አልነበረም። ወይም ደግሞ የአጥቢያ ቤተ ክርስቲያን መጋቢ አልነበረም። ይልቁንም ጢሞቴዎስ የጳውሎስ አጋዥ ነበር። ብዙውን ጊዜ የጳውሎስ ልዩ ተወካይ በመሆን ወደ ተለያዩ አብያተ ክርስቲያናት እየሄደ ችግሮችን ይፈታ ነበር። ስለሆነም አብያተ ክርስቲያናት ጳውሎስን እንደሚቀበሉት ሁሉ ጢሞቴዎስንም መቀበልና ማክበር ነበረባቸው (1ኛ ቆሮ. 16፡10-11)። ይህ መልእክት በተጻፈበት ወቅት ጢሞቴዎስ በኤፌሶን ከተማ ውስጥ ነበር። ምክንያቱም ጳውሎስ ጢሞቴዎስ በዚያ ያለችውን ቤተ ክርስቲያን እንዲያደራጅና የተወሰኑ አመራሮችን እንዲሰጥ ልኮት ነበር።

ጳውሎስ 1ኛ ጢሞቴዎስን በጻፈበት ወቅት ምናልባትም 60 ዓመታት ያለፉት አዛውንት ሳይሆን አልቀረም። ጢሞቴዎስ ደግሞ በ30ዎቹ የዕድሜ ክልል ውስጥ ነበር። በጥንታዊ ማኅበረሰቦች ዘንድ እንደ ወጣት መቆጠሩ የማይቀር ነበር። ምንም እንኳን ጢሞቴዎስ መንፈሳዊና እግዚአብሔር በስጦታ ያበለፀገው አገልጋይ ቢሆንም፥ ዝምተኛና ዓይናፋር የነበረ ይመስላል። ስለሆነ ጳውሎስ እንዳይፈራ ወይም እንዳያፍር ያበረታታዋል (1ኛ ቆሮ. 16፡10፤ 1ኛ ጢሞ. 4፡12፤ 2ኛ ጢሞ. 1፡7-8)። ጳውሎስ በሕይወቱ መጨረሻ አካባቢ ጢሞቴዎስ በወንጌሉና በጳውሎስ መታሠር ስላፈረ ገሥጾታል (2ኛ ጢሞ. 1፡8)።

ጳውሎስ ከመሠዋቱ ጥቂት ቀደም ብሎ፥ ሁለት የቅርብ ጓደኞቹ ማለትም ጢሞቴዎስና ዮሐንስ ማርቆስ ወደ እርሱ እንዲመጡ ጠይቋቸዋል (2ኛ ጢሞ. 4፡9)። ጢሞቴዎስ የጳውሎስ አንገት በሮማ ወታደሮች ከመቀላቱ በፊት መድረስ አለመድረሱን በመጽሐፍ ቅዱስ አልጠቀሰም። አንዳንድ ምሁራን እንደሚያስቡት ጢሞቴዎስ ሮም ከተማ በደረሰ ጊዜ ለእሥራት የተዳረገ ሲሆን በኋላ ግን ተፈትቷል (ዕብ. 13፡23)። የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ከጳውሎስ ሞት በኋላ ስለነበረው የጢሞቴዎስ ሁኔታ ብዙም የሚያስረዳው ነገር የለውም። አንደኛው ታሪክ እንደሚለው ጢሞቴዎስ በመጀመሪያው ምእተ ዓመት መጨረሻ አካባቢ በመሥዋዕትነት ተገድሏል።

1ኛ ጢሞቴዎስ የተጻበፈት ዘመንና ቦታ

የውይይት ጥያቄ፡- የሐዋ. 28፡30-31 እንብብ። የሐዋርያት ሥራ መጽሐፍ ታሪክ በሚጠናቀቅበት ጊዜ ጳውሎስ የት ነበር?

የሐዋርያት ሥራ በሚጠናቀቅበት ጊዜ ጳውሎስ በሮም ከተማ ታሥሮ ነበር። ሉቃስ እንደሚነግረን ጳውሎስ በዚያ ከተማ ውስጥ ለሁለት ዓመታት ያህል ታስሮ ቆይቷል። ሉቃስ ጳውሎስ በቅርብ ጊዜ ይፈታል የሚል ግምት የነበረው ይመስላል። የጥንታዊቷ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ የሚጠናቀቀው በዚሁ ስፍራ ነው። ለመሆኑ ጳውሎስ ከእሥራቱ ተፈትቶ ነበር? ወይስ በዚሁ ጊዜ ነበር የተገደለው? በጥንታዊ የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ውስጥ እርስ በርሳቸው የሚጋጩ ዘገባዎች በመገኘታቸው ምክንያት ምሁራን በእነዚህ ጥያቄዎች ላይ ይከራከራሉ። ምናልባትም ጳውሎስ በዚህ ጊዜ ተፈትቶ ሊሆን ይችላል? እንደዚያ ከሆነ ደግሞ እራተኛው የወንጌል መልእክተኝነት አገልግሎት ወደሚባለው ሌላ የወንጌል መልእክተኝነት ጉዞ ሳይሄድ አይቀርም። አንዳንድ ምሁራን ጳውሎስ ከመጀመሪያው እሥራቱ በ62 ዓመተ ምሕረት እንደ ተፈታ ይናገራሉ። ጳውሎስ ወደ ስፔን ለመሄድ እንደሚፈልግ በመግለጽ ለሮሜ ከጻፈው መልእክት ለመረዳት እንደሚቻለው፥ ምናልባትም ጳውሎስ ወደ ስፔን ሄዶ ሊሆን ይችላል። ከዚያም ወደ ኋላ ወደ ምሥራቅ ተጓዘ። በ65 ዓ.ም አካባቢ ወደ ቀርጤስ ሄደ (ቲቶ 1፡5)። እዚያ ነበር ቲቶን ለአገልግሎት ትቶት የተመለሰው። ከዚያም ወደ ኤፌሶን ተጓዘ (1ኛ ጢሞ. 1፡3)። ይህ የሆነው በ66 ዓ.ም አካባቢ ሲሆን፥ ጢሞቴዎስን በዚያ ቤተ ክርስቲያን እንዲመሠርት መድቦታል። ከዚያም ጳውሎስ በ66 ዓ.ም አካባቢ ወደ ፊልጵስዩስ ሄደ (1ኛ ጢሞ. 1፡3)። ቀጥሎም ከ66-67 ባለው ጊዜ ኒቃፖሊስ ወደምትባል ከተማ ሄደ (ቲቶ 3፡12)። ከዚያ በኋላ ታስሮ ወደ ሮም ተመለሰ። በእሥር ቤት ውስጥ ከቆየ በኋላ ጥፋተኛ ሆኖ በመገኘቱ የሞት ቅጣት ተፈረደበት። ለሮም ዜጋ በሚፈጽመው የሞት ቅጣት መሠረት፥ አንገቱ በሰይፍ ተቀላ።

ጳውሎስ ወደ ኤፌሶን በደረሰ ጊዜ ጢሞቴዎስን የቤተ ክርስቲያኒቱ ኃላፊ አድርጎ ከሾመው በኋላ ወደ መቄዶኒያ ተጓዘ (1ኛ ጢሞ. 1፡3)። ምናልባትም የጢሞቴዎስ አገልግሎት ከቤተ ክርስቲያን ወደ ቤተ ክርስቲያን እየተጓዘ የሚያከናውነው የመጋቢነት ኃላፊነት ሳይሆን አይቀርም። ጳውሎስ ምናልባትም በፍጥነት ወደ ኤፌሶን እንደሚመላስ ሳያስብ አልቀረም። ነገር ግን ቶሎ ለመመለስ ባለመቻሉ ከመቄዶኒያ ሆኖ 1ኛ ጢሞቴዎስን ጻፈ። ይህም የ1ኛ ጢሞቴዎስ መልእክት ጢሞቴዎስ ሽማግሌዎችን ስለሚመርጥበትና ሌሎች የቤተ ክርስቲያኒቱን ጉዳዮች ስለሚያከናውንበት መንገድ መመሪያ የሚሰጥ መልእክት ነበር። ምናልባትም ይህ መልእክት የተጻፈው ከ66-67 ዓ.ም ባለው ጊዜ ውስጥ ሳይሆን አይቀርም። (ማስታወሻ፡ ጳውሎስ በ64 ዓ.ም እንደ ሞተ የሚያስቡ ሌሎች ምሁራን 1ኛ ጢሞቴዎስ በ63 ዓ.ም ሳይጻፍ አይቀርም ይላሉ።)

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

2 thoughts on “የ1ኛ ጢሞቴዎስ በማን ተጻፈ፣ ለማን ተጻፈ፣ መቼና የት ተጻፈ”

  1. Tesfaye, Tesgera

    I have so much pleased with the new knowledge I got from your program. I urge you to continue

  2. ክብር ለጌታችንና ለመድሃኒታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ ይሁን። ጸጋ ይብዛልን

Leave a Reply to Tesfaye, TesgeraCancel reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading