የ1ኛ ጢሞቴዎስ ዓላማ

1) በኤፌሶን ጳውሎስ የሰጠውን ኃላፊነት ለማሟላት ደፋ ቀና ይል ለነበረው ጢሞቴዎስ ሥልጣንን ለመስጠት። ጢሞቴዎስ ሐዋርያ ባለመሆኑ የጳውሎስ ዓይነት ሥልጣን አልነበረውም። ስለሆነም ትምህርቱን ተቀባይነት ያለው ለማድረግ ጳውሎስ የጻፈለትን ደብዳቤ ለአብያተ ክርስቲያናቱ ማሳየት ይችል ነበር።

2) በኤፌሶን ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የሐሰት ትምህርት በመስፋፋት ላይ ነበር። በመሆኑም ጳውሎስ ጢሞቴዎስ እነዚህን የሐሰት ትምህርቶች እንዲከላከል አዞታል (1ኛ ጢሞ. 1፡3-20)። እነዚህ የሐሰት አስተማሪዎች እነማን እንደሆኑ በግልጽ አልተጠቀሰም። ምናልባትም እነዚህ ሰዎች ክርስቲያኖች ሊጠብቋቸው ይገባል የሚሏቸውን አንዳንድ የብሉይ ኪዳን ትምህርቶች የሚያስተምሩ አይሁዶች ሳይሆኑ አይቀሩም። ምናልባትም ደግሞ እነዚህ የሐሰት አስተማሪዎች የቀድሞዎቹ የኖስቲሲዝም ገጽታዎችን የሚያንጸባርቁ ሊሆኑ ይችላሉ። እነዚህ የኖስቲሲዝም እስተማሪዎች ከክፉ ሥጋቸው ለመገላገል የሚፈልጉ ክርስቲያኖች ሥጋቸውን እንዲጨቁኑና ከተወሰኑ ነገሮች እንዲርቁ ያስተምሩ ነበር (1ኛ ጢሞ. 4፡1-8፥ 6፡3-5፥ 20-21)። እነዚህ ሐሰተኛ አስተማሪዎች ብሉይ ኪዳንን በተሳሳተ መንገድ ይተረጉሙ ስለነበር ጳውሎስ ጢሞቴዎስ ሕጉን ማለትም ብሉይ ኪዳንን በጥንቃቄ እንዲያጠናና እንዲገነዘብ አስጠንቅቆታል (1ኛ ጢሞ. 1፡8-11)።

3) ጳውሎስ 1ኛ ጢሞቴዎስን የጻፈው ጢሞቴዎስ ቤተ ክርስቲያንን ስለሚያስተዳድርበት መንገድ መመሪያዎችን ለመስጠት ነበር። በመሆኑም የሚከተሉትን ጉዳዮች ሲዳስስ እንመለከታለን። ሀ) የጉባዔ አምልኮ (1ኛ ጢሞ. 2፡1-8)፥ ለ) ብዙ ሕዝብ በተሰበሰበበት የአምልኮ ቦታ የሴቶች ሚና ምን መሆን እንዳለበት (1ኛ ጢሞ. 2፡9-15)፤ ሐ) ለመበለቶችና ላላገቡ ሴቶች ሊደረግ ስለሚገባው እንክብካቤ (1ኛ ጢሞ. 5)፥ እና መ) ለሽምግልናና ለዲቁና የሚመረጡ ሰዎች ሊያሟሉ ስለሚገባቸው ብቃቶች ጳውሎስ ሰፊ ማብራሪያ ሰጥቷል (1ኛ ጢሞ. 3፡1-13)።

4) ጢሞቴዎስ ሀ) ስደትን የማይፈራ፥ ለ) ንጹሕ ሥነ ምግባራዊ ሕይወት የሚመራና፥ ሐ) ጥንቃቄ የተሞላበትን የገንዘብ አያያዝ የሚከተል ታማኝ የወንጌል አገልጋይ እንዲሆን ለማበረታታት።

የውይይት ጥያቄ፡- እነዚህ ዕበይት ትምህርቶች ለቤተ ክርስቲያንህ ለምን እንደሚያስፈልጉ አብራራ። የ1ኛ ጢሞቴዎስ መጽሐፍ ለዲያቆናትና ለሽማግሌዎች ዛሬ ጠቃሚ የሚሆንበትን መንገድ ግለጽ?

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading