የቤተ ክርስቲያን መሪ ቤተ ክርስቲያን ሽማግሌዎችና ዲያቆናትን በጥንቃቄ እንደሚመርጡ ሊረዳቸው ይገባል (1ኛ ጢሞ. 3፡1-16)

የአንድ መሪ መንፈሳዊ ሕይወት ለቤተ ክርስቲያን በጣም አስፈላጊ መሆኑን ቀደም ብለን ተመልከተናል። ትክክለኛ ያልሆኑ መሪዎች በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሥልጣን መያዛቸው ወይም አንድ መሪ በኃጢአት መውደቁ፥ ቤተ ክርስቲያንንና ምስክርነቷን እጅግ ይጎዳል። ስለሆነም ጳውሎስ በ1ኛ ጢሞቴዎስ ውስጥ ስለ መሪዎችና የብቃት መመዘኛዎቻቸው በሰፊው ጽፎአል።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) በአንድ ወረቀት ላይ ሦስት አምዶችን አዘጋጅ። የመጀመሪያውን አምድ ‹ሽማግሌዎችን፥ ሁለተኛውን ‹ዲያቆናትን፥ ሦስተኛውን ‹ቤተ ክርስቲያናችን› ብለህ ሰይም። በእነዚሁ አምዶች ውስጥ በ1ኛ ጢሞቴዎስ 3 እና ቲቶ 1 ለሽማግሌዎችና ዲያቆናት የተሰጡትን የብቃት መለኪያዎች ዘርዝር። የመጨረሻው እምድ የምትሞላውን አሳብ ለማግኘት በቅርቡ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሽማግሌዎች የተመረጡበትን ሁኔታ አስብ። እነዚህ መሪዎች የተመረጡበት ምክንያት ምን እንደሆነ የምታስበውን በዚህ አምድ ውስጥ አስፍር። ለ) ጳውሎስ በዘረዘራቸው የብቃት መመዘኛዎች መካከል የምትመለከታቸው አንድነቶችና ልዩነቶች ምን ምንድን ናቸው?

በአዲስ ኪዳን ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሁለት ዓይነት ዐበይት የመሪነት ዓይነቶች ነበሩ። ከእነዚህም መካከል የመጀመሪያዎቹ በቀዳሚነት የቤተ ክርስቲያን መሪዎች ሲሆኑ፥ ሽማግሌዎች (የሐዋ. 20፡17) መጋቢዎች ወይም ኤጲስ ቆጶሳት (1ኛ ጢሞ. 3፡1) ወይም እረኞች (1ኛ ጴጥ. 5፡1-4) ተብለው ይጠራሉ። በአዲስ ኪዳን ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ስንት ሽማግሌዎች በአንድ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ እንደሚያገለግሉ ወይም እንዴት እንደሚመረጡ አልተጠቀሰም። አገልግሎቱ የሕይወት ዘመን ወይም በተወሰነ ጊዜ ውስጥ የሚቀያየሩበት መሆኑም አልተጠቀሰም። ጳጳስ ወይም ኤጲስ ቆጶስ የሚለው ቃል ከግሪክ ቋንቋ የተገኘ ሲሆን፥ የአንድ ቤተ ክርስቲያን ወይም የመንግሥታዊ ድርጅት መሪ የሆነን ሰው ያመለክታል። ይህም ፕሬዚዳንት ወይም ዋና ጸሐፊ ከሚለው የዘመናችን አገላለጽ ጋር ተቀራራቢ ነው። ሽማግሌ የሚለው ቃል ከአይሁዳውያን ባህል የተወሰደ ሲሆን፥ የማኅበረሰብ ወይም እንደ ምኩራብ ያለ ድርጅት መሪዎችን ያመለክታል (የሐዋ. 20፡17፤ 28፤ ቲቶ 1፡5-7፤ 1ኛ ጴጥ. 5፡1-2) ሽማግሌዎች፥ ዲያቆናትና እረኞች የሚሉ ቃላት ተመሳሳይነታቸውን በሚያመለክት ሁኔታ ቦታ ተቀያይረው ማገልገላቸውን ያሳያሉ።) ሽማግሌዎች ቤተ ክርስቲያኒቱን በማስተዳደር አጠቃላይ ተግባር ላይ ላቅ ያለ ኃላፊነት ነበራቸው። በመሆኑም የጸሎትና የትምህርት መንፈሳዊ አገልግሎቶችን፥ ብሎም ለምእመናን የመጋቢነት አገልግሎት በመስጠቱ ተግባራት ላይ ያተኩራሉ።

ሁለተኛው የመሪዎች ዓይነት ‘ዲያቆናት’ በመባል ይታወቅ ነበር። ዲያቆን የሚለው ቃል ከግሪክ ቋንቋ የተወሰደ ሲሆን፥ አገልጋይ ወይም አስተናጋጅ የሚል ፍቺ ይሰጣል። ይህ የአገልግሎት ዘርፍ መጀመሪያ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ የተመሠረተው በሐዋርያት ሥራ 6፡1-6 በቀድሞይቱ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ዲያቆናት ሐዋርያትን ለማገልገል በተመረጡበት ወቅት ነበር። ዲያቆናት በሁሉም አብያተ ክርስቲያናት ውስጥ መመረጥ እለመመረጣቸውን ባናውቅም፥ ቤተ ክርስቲያን የተወሰነ ዕድገት በምታሳይበት ጊዜ ዲያቆናት ሽማግሌዎችን ለማገዝ ይመረጡ የነበረ ይመስላል። ሽማግሌዎች መንፈሳዊ አገልግሎቶችን ሲወጡ፥ ዲያቆናት ደግሞ ድሆችን እንደ መንከባከብ ያሉትን ተግባራዊ አገልግሎቶች ያከናውኑ ነበር።

ብዙ ሰዎች በመሪነት ለማገልገል አይፈልጉም። ምንም ዓይነት ኃላፊነት ሳይሸከሙ ተራ የቤተ ክርስቲያን አባል ሆነው ማምለኩ ቀላል መስሎ ይታያቸዋል። የቤተ ክርስቲያን መሪነት ትንሽ ደመወዝ እያገኙ ብዙ ጊዜ ማጥፋትንና ለልብ ስብራት መዳረግን የሚያካትት ተግባር ነው። መሪዎች ለመሆን የሚፈልጉ ሰዎች ደግሞ ይህን ስፍራ የሚፈልጉት ትክክለኛ ላልሆኑ ምክንያቶች ነው። ጥሩ ደመወዝ የሚያገኙበት ከሆነ ብሩን ወይም ደግሞ ከመሪነት የሚመጣውን ክብር ይፈልጋሉ። ጳውሎስ ግን የመሪነት ጥሪ ወይም ፍላጎት በአንድ ሰው ልብ ውስጥ ማደሩ መልካም እንደሆነ ይናገራል። በተለይም ደግሞ ግለሰቡ ይህ አገልግሎት በእርሱና በቤተሰቡ ላይ የሚያስከትለውን ችግር የሚገነዘብ ከሆነ ለመሪነት አገልግሎት መጠራቱ ነው። የቤተ ክርስቲያን መሪ መሆን በእግዚአብሔር ዓይኖች ፊት ክቡር ተግባር ነው። እግዚአብሔር በስጦታዎች ያበለጸገውና የጠራው ሰው በአመራር አላገለግልም ማለቱ ተገቢ አይሆንም።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) አንድ ሰው በመሪነት አገልግሎት ላይ ለመሠማራት የሚፈልግባቸው የተሳሳቱ ምክንያቶች ምንድን ናቸው? ለ) አንድ ሰው መሪነትን ሊፈልግ የሚገባቸው ትክክለኛ ምከንያቶች ምን ምንድን ናቸው? ሐ) ብዙ ክርስቲያኖች በመሪነት ለማገልገል የማይፈልጉበት ምክንያቶች ምን ምንድን ናቸው?

ለሽምግልና ወይም ለድቁና አገልግሎት የሚያስፈልጉትን የብቃት መመዘኛዎች ጠለቅ ብለን ስንመረምር የሚከተሉትን እውነቶች እንመለከታለን።

  1. ለሽምግልናና ለድቁና የሚያስፈልጉ አብዛኞቹ መመዘኛዎች ተመሳሳይ ናቸው። ከዋነኛ ልዩነቶች አንዱ ሽማግሌ የማስተማርና መጽሐፍ ቅዱሳዊ እውነትን ለማኅበረ ምእመናን የማስተላለፍ ችሎታ ሊኖረው የሚገባ መሆኑ ነው።
  2. አብዛኞቹ የመሪነት ብቃቶች ከባህሪ ጋር የተያያዙ ናቸው። ጳውሎስ በመሪነት የሚያገለግሉ ሰዎች እንደ ራስን መግዛት፥ የዋህነት፥ ቅድስና፥ ከነቀፋ ነፃ መሆንና የመሳሰሉትን ውስጣዊ ብቃቶች ሊያሟሉ እንደሚገባ ያስተምራል። ይህ ዛሬ ትኩረት ከምንሰጥባቸው እንደ ትምህርት፥ ሀብት፥ ጥሩ ሥራ፥ ከጥሩ ጎሳ መወለድ፥ እና ከመሳሰሉት ውጫዊ ብቃቶች የተለየ ነው።
  3. ሌላው ብዙ ጊዜ ተደጋግሞ የሚጠቀሰው ከሌሎች ሰዎች ጋር የሚደረገውን ግንኙነት የሚመለከት ነው። አንድ መሪ እንግዳ ተቀባይ፥ በውጪ ባሉት ዘንድ መልካም ስም ያለው፥ የአንዲት ሚስት ባልና ቤተሰቡን በአግባቡ የሚያስተዳድር መሆን ይኖርበታል። በዚህ ክፍል ውስጥ የተጠቀሱት አብዛኞቹ ባህሪዎች አንድ ሰው ከሌሎች ጋር መልካም ግንኙነት ማድረግ መቻሉን የሚያመለክቱ ናቸው።
  4. ከመሪ የሚጠበቀው ዋናው ብቃት ለማስተማር መቻሉ ነው።
  5. ዋንኛው የአመራር ብቃት መለኪያ አንድ ሰው የራሱን ቤተሰብ ማስተዳደር መቻሉ ነው።
  6. የመሪዎች ሚስቶች ባህሪም እንዲሁ አስፈላጊ መሆኑ ተጠቅሷል። የመሪዎች ሚስቶች የተከበሩ፥ አንደበታቸውን የሚገዙና ከሀሜት የሚርቁ፥ እንዲሁም በሁሉም ነገር እምነት የሚጣልባቸው መሆን አለባቸው።

የውይይት ጥያቄ፡- እነዚህን ባሕርያት ከልስ። ሀ) እያንዳንዱ ባሕሪ ለአንድ መሪ አስፈላጊ የሚሆነው ለምንድን ነው? ለ) አንድ መሪ ከእነዚህ ባሕርያት አንዱን በሚያጣበት ጊዜ ምን ይከሰታል? ሐ) ከእነዚህ ባሕርያት የሚጎድልህ የትኛው ነው? ለመሪነት ብቁ ትሆን ዘንድ ይህንኑ ባሕሪ ለማሳደግ ምን ማድረግ ይኖርብሃል።

(ማስታወሻ፥ ምንም እንኳ ጳውሎስ በዚህ ስፍራ ትኩረት የሰጠው ለመሪዎች ቢሆንም፥ እነዚህ ባሕርያት ለክርስቲያኖች ሁሉ አስፈላጊ መሆናቸውን ከሌሎች የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች እንመለከታለን። እነዚህ ባሕርያት የመንፈሳዊ ሰው መገለጫዎች ናቸው። ጳውሎስ እየተናገረ ያለው ሁሉም የቤተ ክርስቲያን መሪዎች እነዚህን ባሕርያት በመያዝ መንፈሳዊ ሞዴሎች እንዲሆኑና ክርስቲያኖችም ይህንኑ ሕይወት ለመኖር መጣር እንደሚገባቸው ነው።)

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading