በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ወደሚካሄደው የቀብር ሥነ ሥርዓት እየሄድክ ነው እንበል፥ ወደ ቤተ ክርስቲያኒቱ ገብተህ ስትቀመጥ፥ ከቤተ ክርስቲያኒቱ መድረክ ላይ የተኛው አስከሬን ያንተው መሆኑን ትገነዘባለህ። የራስህን የቀብር ሥነ ሥርዓት እየተመለከትህ ነው እንበል። ፕሮግራሙን እየተከታተልህ እያለ፥ ከልጆችህ ታላቁ ብድግ ብሎ በልጅነቱ ከአንተ ጋር ስለነበረው ግንኙነትና ስለ አንተ የሚያስታውሳቸውን ነገሮች ለማኅበረ ምእመናኑ ይናገራል። ሁለተኛ፥ ባለቤትህም በበኩሏ ባሏ እንደ መሆንህ መጠን ስለ አንተ የምታስታውሰውን ትናገራለች። ሦስተኛ፥ የቤተ ክርስቲያኒቱ ሽማግሌም ስለ አንተ የሚያውቀውንና የሚያስታውሰውን ይናገራል። አራተኛ፥ የሥራ ባልደረባህም እንዲሁ በሥራ ቦታ ምን ዓይነት ሰው እንደነበርክ ይመሰክራል። አምስተኛ፥ የማኅበረሰብህ አባል የሆነ ሰውም እንዲሁ በማኅበራዊ ሕይወት ውስጥ የነበረህን ድርሻ ያብራራል። ስድስተኛ በመንፈሳዊ ዓይንህ በክርስቶስ ፊት ቆመህ የእርሱን ግምገማ ትሰማለህ። እነዚህ ሰዎች ሁሉ እውነትን የሚናገሩ ሲሆን፥ የሚያሳዝኑህን ነገሮችንም እንዲሁ ይናገራሉ።
የውይይት ጥያቄ፡- ይህን ትዕይንት በአእምሮህ ስትስል፥ ሀ) እያንዳንዱ ሰው ስለ አንተ በእውነት ምን ሲናገር ደስ ይልሃል? ለ) በቀብር ሥነ ሥርዓትህ ላይ እንዲነገሩ የምትፈልጋቸው ምስክርነቶች ስለ ባሕሪህና ስለ ተግባሮችህ አስፈላጊ ነገሮችን ይናገራሉ። ሰዎች ስለ አንተ እንዲናገሩ የምትፈልገውን ከራስህ እውነተኛ ማንነትህ ጋር አነጻጽር። በምትሞትበት ጊዜ የምትፈልገው ነገር የሆንከውን ይሆን ዘንድ ልትለውጣቸው የሚገቡህ የሕይወትህ ክፍሎች ምን ምንድን ናቸው?
መጽሐፍ ቅዱስ ሁላችንም እንደምንሞትና አንድ ቀን በክርስቶስ ፊት ቆመን ስለ ሕይወታችን የሚሰጠውን ግምገማ እንደምንከታተል ያስተምራል። ያም ግምገማ በክርስቶስ ማመን አለማመናችንን የሚመለከት አይሆንም። ሁሉም የሕይወታችን ክፍሎችና የነበሩን የግንኙነት ዓይነቶች በሙሉ ይገመገማሉ። ዛሬ በሕይወታችን አስፈላጊው ነገር ምን እንደሆነ ለይተን ካላወቅን፥ ክርስቶስ ወይም ሌሎች ሰዎች በምን ዓይነት ባሕርያት ወይ ተግባራት እንደሚያስታውሱን ካልወሰንን፥ አብዛኞቻችን በሕይወት ውስጥ ጠቃሚ በሆኑት ጉዳዮች ላይ እናተኩርም። በምንሞትበት ጊዜ፥ የቤተሰብ ውርሳችን፥ ጎሳችን፥ ትምህርታችን፥ ሀብታችን፥ ወይም ኃይላችን ወሳኝ ጠቀሜታ አይኖራቸውም። ይልቁንም የተሻልን ወላጆችና አፍቃሪ የትዳር ጓደኞች መሆናችን ወሳኝነት ይኖረዋል። እውነትን የምንወድና ለሌሎች የምናስብ፥ የቤተ ክርስቲያን መሪዎች፥ እውነተኛና ታማኝ ሠራተኞች፥ የማኅበረሰቡን ሕይወት ለማሻሻል የጣርንና ለእግዚአብሔር ክብር በታማኝነት የተመላለስን ሰዎች በሆንን ብለን እንመኛለን። እነዚህ በሰው ሕይወት ውስጥ ጉልህ ሚና ያላቸውና በክርስቶስም ፊት በምንቆምበት ጊዜ የምንገመገምባቸው ነጥቦች ናቸው (1ኛ ቆሮ. 3፡10-15)።
በ2ኛ ጢሞቴዎስ ውስጥ፥ ጳውሎስ በሰማዕትነት ከማለፉ ጥቂት ቀደም ብሎ የጻፈውን የመጨረሻ ደብዳቤ እናገኛለን። ጳውሎስ ሕይወቱን መለስ ብሎ ሲመለከትና ወደፊት እሻግሮ የዘላለምን ሕይወት ሲያይ፥ ስለ ሕይወት የነበረውን አመለካከት ይገልጻል። ጳውሎስ ወደ ኋላ ከዚያ ወደፊት ሲመለከት፥ «በመሥዋዕት እንደሚደረግ፥ የእኔ ሕይወት ይሠዋልና፥ የምሄድበትም ጊዜ ደርሶአል፡፡ መልካሙን ገድል ተጋድዬአለሁ፥ ሩጫውን ጨርሼአለሁ፥ ሃይማኖትን ጠብቄአለሁ፤ ወደ ፊት የጽድቅ አክሊል ተዘጋጅቶልኛል፥ ይህንም ጻድቅ ፈራጅ የሆነው ጌታ ያን ቀን ለእኔ ያስረክባል፥ ደግሞም መገለጡን ለሚወዱት ሁሉ እንጂ ለእኔ ብቻ አይደለም» ይላል (2ኛ ጢሞ. 4፡6-8)። ጳውሎስ ሊሞት ሲቃረብ ያሳለፈውን ሕይወት የተመለከተው በጸጸት ሳይሆን በእርካታ ነበር። እንዲሁም የወደፊት ሕይወቱን ክርስቶስ ምን ይለኛል በሚል ፍርሃት ሳይሆን በልበ ሙሉነት ቃኝቶታል። ይህ የሆነው ጳውሎስ ሕይወቱን ለወንጌሉ እንደሚገባ አድርጎ እንደኖረ ያውቅ ስለነበር ነው። ከሥራ ጓደኞቹ፥ ከማኅበረሰቡ ጋር የነበረው ግንኙነት ፈሪሃ እግዚአብሔር የነገሠበት ነበር። ስለሆነም በእግዚአብሔር ፊት በሚቆምበት ጊዜ እንደማያፍር ያውቅ ነበር።
የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ለአንድ ሰው በሕይወቱ መጨረሻ የኋላውን ያለ ጸጸት፥ የፊቱን ደግሞ በልበ ሙሉነት መመልከት አስፈላጊ የሚሆነው ለምንድን ነው? ለ) አሁን ሞተህ በእግዚአብሔር ፊት ብትቀርብ የምትጸጸትባቸው አንዳንድ ነገሮች ምን ምንድን ናቸው? በክርስቶስ ፊት ብትቆም ምንን ትፈራለህ? በምትሞትበት ጊዜ ከጸጸት ወይም ከፍርሃት ነፃ ትሆን ዘንድ ቅድሚያ በምትሰጣቸው ነገሮች፥ በባሕሪህና በተግባርህ ውስጥ ሊለወጡ የሚገባቸው ነገሮች ምን ምንድን ናቸው?
(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)
Today I am first time to join with this holy Bible study center;next I am follow contuniously . God bless you!