የ2ኛ ጢሞቴዎስ በማን ተጻፈ፣ ለማን ተጻፈ፣ መቼና የት ተጻፈ

የ2ኛ ጢሞቴዎስ ጸሐፊ

የውይይት ጥያቄ፡– 2ኛ ጢሞ. 1፡1 አንብብ። ሀ) የመጽሐፉ ጸሐፊ ማን ነው? ለ) መጽሐፉ የተጻፈው ለማን ነው? ሐ) 2ኛ ጢሞቴዎስን በመጽሐፍ ቅዱስ መዝገብ ቃላት ውስጥ በመመልከት ስለ ጸሐፊው፥ መልእክቱን ስለሚቀበሉት ሰዎችና ስለ መጽሐፉ የተገለጸውን ጠቅለል አድርገህ ጻፍ።

ጳውሎስ የ2ኛ ጢሞቴዎስ መልእክቱን የጀመረው እንደተለመደው ራሱን፥ «በእግዚአብሔር ፈቃድ የኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያ የሆነው ጳውሎስ» በማለት ነበር። ልክ እንደ 1ኛ ጢሞቴዎስ ሁሉ፥ ጳውሎስ ይህንንም መልእክት የጻፈው ለጢሞቴዎስ የራሱን ሐዋርያዊ ሥልጣን ለማስገንዘብ ብቻ አልነበረም። ነገር ግን ጢሞቴዎስ የቤተ ክርስቲያኒቱን ተግባራት ለማከናወን በሚፍጨረጨርበት ወቅት ይህንን ደብዳቤ የሥልጣኑ መሠረት አድርጎ እንዲጠቀምበት ይፈልጋል።

መልእክቱ የተጻፈው ለማን ነበር?

ጳውሎስ በዚህ ደብዳቤ መግቢያ ውስጥ ለተወደደው ልጄ ለጢሞቴዎስ ሲል ጽፎአል። ጳውሎስ ትዳር ስላልነበረው ከአብራኩ የወጣ ልጅ አልነበረውም። ጢሞቴዎስ ግን ከ15 ዓመታት በላይ አብሮት የሠራ ከመሆኑም በላይ እንደ ልጁ የሚያየው አገልጋይ ነበር። ስለሆነም ጳውሎስ በሰማዕትነት ከማለፉ ጥቂት ቀደም ብሎ ጥልቅ ፍቅሩን የገለጸበትን መልእክት ለጢሞቴዎስ ጽፎአል። ይህም የጳውሎስ የመጨረሻው መልእክት ነበር።

ጳውሎስ 2ኛ ጢሞቴዎስን የጻፈበት ጊዜና ስፍራ

ምሁራን በጳውሎስ ሕይወት መጨረሻ ምን እንደ ተፈጸመ ይከራከራሉ። አንዳንዶች የሐዋርያት ሥራ መጽሐፍ ከተጻፈ በኋላ ጳውሎስ በችሎት ፊት ተመርምሮ ጥፋተኛ ሆኖ በመገኘቱ በሮም ውስጥ እንደ ተገደለ ያስባሉ። ይህ እውነት ከሆነ 2ኛው የጢሞቴዎስ መልእክት የተጻፈው ከ63-65 ዓ.ም ባለው ጊዜ ውስጥ መሆኑ ነው። ይህም በሐዋርያት ሥራ ታሪክ መጨረሻ ላይ ጳውሎስ ሊሞት ጥቂት ወራት ሲቀሩት የተጻፈው መሆኑን ያሳያል።

ይሁንና ጳውሎስ የሐዋርያት ሥራ መጽሐፍ ከተጻፈ በኋላ ከእስር ቤት የተፈታ ይመስላል። ከዚያ በኋላ ለቀጣይ አያሌ ዓመታት በምዕራባዊ የሮም ግዛት (ስፔን) ካገለገለ በኋላ ወደ ምሥራቅ ትንሹ እስያና ግሪክ የተጓዘ ይመስላል። በ66 ዓ.ም አካባቢ ጳውሎስ እንደገና ታስሮ ወደ ሮም ተወሰደ። ጳውሎስ ልብሶቹንና መጽሐፎቹን ለመያዝ ጊዜ አለማግኘቱና በኋላ ጢሞቴዎስ እንዲያመጣለት መጠየቁ (2ኛ ጢሞ. 4፡13)፥ በድንገት መታሰሩን የሚያመለክት ይመስላል። በዚህ ጊዜ የችሎቱ ምርመራ ተስፋ የሚጣልበት ባለመሆኑ፥ ጳውሎስ 2ኛ ጢሞቴዎስን በሚጽፍበት ጊዜ የሞት ፍርድ እንደሚፈረድበት ይጠባበቅ ነበር። በዚህ ጊዜ ቤት ተከራይቶ ለመቀመጥና ከጎብኚዎች ጋር ለመነጋገር አልቻለም ነበር። ነገር ግን በሰንሰለት ታስሮ በቀዝቃዛ እስር ቤት እንዲቀመጥ ተደርጓል (2ኛ ጢሞ. 2፡9)። በመሆኑም ጎብኚዎች ሊያገኙትና ሊጠይቁት አልቻሉም (2ኛ ጢሞ. 1፡16-17)። ፍጻሜው እንደ ቀረበ በማወቅ፥ ጳውሎስ ጢሞቴዎስ ከኤፌሶን ወደ ሮም በመምጣት የሕይወቱን የመጨረሻ ጥቂት ወራት አብሮት እንዲያሳልፍ ጠይቆታል። ስለሆነም ይህ የ2ኛ ጢሞቴዎስ መልእክት የተጻፈው በሮም ከተማ ከ66-67 ዓ.ም ባለው ጊዜ ውስጥ ኤፌሶን ከተማ ለነበረው ጢሞቴዎስ ሳይሆን አይቀርም። 2ኛው የጢሞቴዎስ መልእክት ጳውሎስ በእምነቱ ከመሠዋቱ በፊት የጻፈው የመጨረሻ መልእክቱ ነበር።

በዚህ የጳውሎስ የሕይወቱ መጨረሻ አካባቢ ይገዛ የነበረው ቄሳር ኔሮ በመባል የሚታወቅ ክፉ ሰው ነበር። ይህ ሰው ከ54-68 ዓ.ም ባለው ጊዜ ውስጥ የሮም ንጉሠ ነገሥት ነበር። ጳውሎስ በሐዋርያት ሥራ ታሪክ መጨረሻ ላይ ከኔሮ ፊት የቀረበ ሲሆን፥ በዚህ ጊዜ የተፈታ ይመስላል። በ64 ዓ.ም ግን፥ ኃይለኛ እሳት ተነሥቶ አብዛኛውን የሮም ክፍል አቃጠለ። ሕዝቡ ኔሮ እሳቱን እንዳቀጣጠለ በመግለጽ ይከስሰው ጀመር። ምናልባትም ኔሮ ይህን ያደረገው ክብሩን የሚገልጽበትን ሕንጻ ለመገንባት የሚችልበትን ስፍራ ለማግኘት በመፈለጉ ይሆናል። ኔሮ ይህንን ክስ ለማስቀየስ ሲል በሮም ከተማ የነበሩትን ሌሎች የሕዝብ ቡድኖችን ይወቅስ ጀመር። እነዚህም የኔሮ የወቀሳ ማነጣጠሪያዎች ክርስቲያኖች ሲሆኑ፥ የተቀረው የሮም ማኅበረሰብ የእነዚህኑ ክርስቲያኖች እምነቶችና ተግባራት እንደ እንግዳ ነገር ይመለከት ነበር። በመሆኑም ሕዝቡ በክርስቲያኖችና በኔሮ ላይ ቁጣውን ይገልጽ ጀመር። በዚህም ጊዜ የኔሮ ወታደሮች በሺዎች የሚቆጠሩ ክርስቲያኖችን በመያዝ ወደ ስፖርት ስታዲዮሞች ወሰዷቸው። በዚያም ብዙዎቹ እስከነነፍሳቸው ሲቃጠሉ የተቀሩት ከአንበሶች ጋር እንዲፋለሙ ተደርገዋል። ይህ የፀረ ክርስቲያን ስሜት እያደገ በመሄዱ፥ ስደት እየተስፋፋ ይሄድ ጀመር (1ኛና 2ኛ ጴጥሮስ)። ኔሮን ለማክበርና ለእርሱ መሥዋዕት ለማቅረብ ያልፈለጉ ክርስቲያኖች በሙሉ ለከፍተኛ ስደት ተዳረጉ። ምናልባትም ጳውሎስ የክርስቲያኖች መሪ በመሆን ይታወቅ ስለነበር ሳይሆን አይቀርም፥ እርሱና ጴጥሮስ ታስረው ወደ ሮም ከተወሰዱ በኋላ፥ በዚያም ኔሮ ክርስቲያኖችን ማሳደዱን ሊያቆም በተቃረበበት ወቅት ጳውሎስ አንገቱ ተቀልቶ ወደ ዘላለማዊ ቤቱ የተጓዘው።

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

%d bloggers like this: