የ2ኛ ጢሞቴዎስ መዋቅር
2ኛ ጢሞቴዎስ እንደ መጽሐፍ ሳይሆን ጳውሎስ ከመሞቱ በፊት የእምነት ልጁ ለሆነው ጢሞቴዎስ የሰጠውን ግላዊ ምክር የሚያስተላልፍ ሆኖ ስለቀረበ፥ ይህንንም መልእክት በአስተዋጽኦ መልክ ማቅረቡ አስቸጋሪ ነው። ጳውሎስ ጢሞቴዎስ በስደት ውስጥ እግዚአብሔርን በሚያስከብር መንገድ እንዴት መመላለስ እንዳለበት አስተዋይነት የተሞላበትን ምክር ይለግሰዋል። ይህ መጽሐፍ በአራት ክፍሎች ሊከፈል ይችላል።
- ጳውሎስ ጢሞቴዎስ እንዴት እግዚአብሔርን በሚያስከብር መንገድ ለመመላለስ እንደሚችል ይመክረዋል (2ኛ ጢሞ. 1፡2)። ጳውሎስ ጢሞቴዎስ ከፍርሃትና ዓይን አፋርነት ተላቅቆ ለእግዚአብሔር በጽናት እንዲቆምና የክርስቶስ ተከታይ በመሆኑ እንዳያፍር ያስጠነቅቀዋል። በጦርነት ውስጥ መከራ እንደሚቋቋም ብርቱ ወታደር፥ ሕይወቱን ለክርስቶስ በንጽሕና እንደሚጠብቅና ሐሰትን ለመዋጋት የእግዚአብሔርን ቃል በጥንቃቄ እንደሚጠቀም አገልጋይ ሆኖ መመላለስ ያስፈልገው ነበር።
- ጳውሎስ የሐሰት ትምህርቶች እየተስፋፉ መሄዳቸውን በመግለጽ ጢሞቴዎስ እንዴት ለእውነት ታማኝ ሆኖ ሊመላለስ እንደሚገባ ያሳስበዋል (2ኛ ጢሞ. 3)። ጳውሎስ ጢሞቴዎስ የተጠናከረ የሐሰተኛ አስተማሪዎች ተቃውሞ እንደሚደርስበት በመግለጽ፥ ይህንኑ ለመጋፈጥ ራሱን እንዲያዘጋጅ ያሳስበዋል። ጳውሎስ ጢሞቴዎስ የእርሱን ምሳሌነት እንዲከተልና በተቃውሞ ፊት መንፈሳዊ ሕይወቱን እንዲጠብቅ፥ እንደዚሁም ሐሰትን ለመከላከል የእግዚአብሔርን ቃል በጥንቃቄ እንዲያጠናና እንዲጠቀም ያበረታታዋል።
- ጳውሎስ ጢሞቴዎስ እንዴት ታማኝ የእግዚአብሔር አገልጋይ ሆኖ መኖር እንደሚችል የመጨረሻ ማደፋፈሪያ ያቀርብለታል (2ኛ ጢሞ. 4፡1-5)። ጳውሎስ ጢሞቴዎስ ሰዎች ለመስማት ባይፈልጉ እንኳን የእግዚአብሔርን ቃል በማሰራጨት የወንጌል መልእክተኛ ሆኖ አገልግሎቱን በታማኝነት እንዲፈጽም ያበረታታዋል።
- ጳውሎስ እየቀረበ ስላለው ሞቱ በመግለጽ፥ ጢሞቴዎስ ወደ እርሱ እንዲመጣ ይጠይቀዋል። በተጨማሪም ለወዳጆቹ ሰላምታ ያስተላልፋል (2ኛ ጢሞ. 4፡6-22)። ጳውሎስ ለጢሞቴዎስ በቅርቡ እንደሚሞትና በሰማይ ግን እንደሚከብር ይነግረዋል። ጢሞቴዎስ ዮሐንስ የተባለውን ማርቆስን ይዞ እንዲመጣና ሳይሞት በፊት በቶሎ ወደ ሮም እንዲደርስ ያሳስበዋል። ጳውሎስ በችግሩ ጊዜ ትተውት የተለዩትን ሰዎች ከዘረዘረ በኋላ፥ ድጋፍ ለሰጡት ታማኝ ሰዎች ሰላምታ ይሰጣል።
የ2ኛ ጢሞቴዎስ አስተዋጽኦ
- ጳውሎስ ጢሞቴዎስ እግዚአብሔርን በሚያስከብር መንገድ እንዴት መመላለስ እንደሚገባው ይመክረዋል (2ኛ ጢሞ. 1-2)።
ሀ) ጳውሎስ ጢሞቴዎስ በቆራጥነት ለወንጌሉ እንዲቆም ያበረታታዋል (2ኛ ጢሞ. 1፡1-14)።
ለ) ጳውሎስ ከሄኔሲፎሩ በስተቀር ሁሉም እንደተዉት ይናገራል (2ኛ ጢ ሞ . 1፡15-18)።
ሐ) ጳውሎስ ጢሞቴዎስ ታማኝ ወታደር ሆኖ ለክርስቶስ እንዲሠራ ያደፋፍረዋል (2ኛ ጢሞ. 2)።
- ጳውሎስ የሐሰት ትምህርት እየተስፋፋ እንደሚሄድ በመግለጽ ጢሞቴዎስ ለዚህ የሐሰት ትምህርት እንዴት ምላሽ እንደሚሰጥና በታማኝነት እንደሚቆም ያስገነዝበዋል (2ኛ ጢሞ. 3)።
ሀ. ጳውሎስ በመጨረሻው ዘመን የሰዎች ባሕሪ ምን እንደሚመስል ያብራራል (2ኛ ጢሞ. 3፡1-9)።
ለ. ጳውሎስ በተቃውሞና በፈተናዎች ሳይረቱ እግዚአብሔርን እንዴት በታማኝነት ማገልገል እንደሚቻል የራሱን የሕይወት ምሳሌነት ጠቅሶ ያስረዳል። ጢሞቴዎስ እርሱን በመምሰልና በመጽሐፍ ቅዱስ እውነቶች ላይ በመደገፍ ሐሰትን እንዲከላከል ይመክረዋል (2ኛ ጢሞ.3፡10-17)።
- ጳውሎስ ጢሞቴዎስ እንዴት ታማኝ የእግዚአብሔር አገልጋይ ሆኖ እንደሚኖር የማጠቃለያ ማበረታቻ ይሰጠዋል (2ኛ ጢሞ. 4፡1-5)።
- ጳውሎስ እየቀረበ ስላለው ሞቱ በመግለጽ፥ ጢሞቴዎስ ወደ እርሱ እንዲመጣ ይጠይቀዋል፥ ለወዳጆቹም ሰላምታ ይልካል (2ኛ ጢሞ. 4፡6-22)።
(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)