በመጨረሻዎቹ ቀናት የሚኖረው ክሕደት እና ጳውሎስ ለጢሞቴዎስ የሰጠው ዐደራ (2ኛ ጢሞ. 3፡1-17)

ጳውሎስ በመጨረሻው ዘመን የሰዎች ባሕሪ ምን እንደሚመስል ይገልጻል (2ኛ ጢሞ. 3፡1-9)

ብዙውን ጊዜ ነገሮች ከዓመት ዓመት እየተሻሻሉ ይሄዳሉ ብለን እናስባለን። ብዙ ሰዎች ትምህርት የተከታተሉ አዳዲስ ሥራዎችን በመፍጠር ብዙ ገንዘብ ያገኛሉ፥ ከግብርና ቦታቸው ራቅ ባሉ አካባቢዎች የተሻሉ ቤቶችን ይሠራሉ፥ የራሳቸውን ቴሌቪዥን፥ መኪና ወዘተ… ይገዛሉ። የተባበሩት መንግሥታት ድርጅትን በመሳሰሉ ተቋማት አማካኝነት በዓለም ላይ ብዙ ገንዘብና ብዙ ሥራም ማግኘት ይቻላል። ይሁንና ጳውሎስ በመንፈስ ቅዱስ ተረድቶ ዓለምን ሲመለከት ሰዎች ወደ መጨረሻው ዓለም እየቀረቡ በሚመጡበት ጊዜ ዓለም የበለጠ በክፋት እንደምትሞላ ተገንዝቧል። ትምህርትና ሥልጣኔ በመጨረሻው ዘመን ላይ አዎንታዊ ገጽታ ከማሳየት ይልቅ አሉታዊ ጥላ ያጠላል። ጳውሎስ በዚህ ክፍል ውስጥ በመጨረሻው ዘመን የሚለወጡትን አንዳንድ ነገሮች ጠቃቅሷል።

ሀ) ሰዎች ከመጠን በላይ ራስ ወዳድ በመሆን ደስ ያሰኛቸውን እያደረጉ ለራሳቸው ብቻ ይኖራሉ። እግዚአብሔር ስለሚፈልገው ነገር ግድ አይኖራቸውም። ሃይማኖተኞችና መንፈሳውያን ቢመስሉም፥ ከእግዚአብሔር ጋር እውነተኛ ግንኙነት አይኖራቸውም። (የአምልኮት መልክ አላቸው ኃይሉን ግን ክደዋል።)

ለ) ሰዎች ሌሎችን ለራሳቸው ፍላጎት በማገልገል እውነት እንዳይስፋፋ ያደርጋሉ። ጳውሎስ ሙሴን የተቃወሙትን ሁለት ሰዎች ማለትም አያኔስንና ኢያንበሬስን ይጠቅሳል። እነዚህ ሁለት ሰዎች በብሉይ ኪዳን ውስጥ አልተጠቀሱም። ነገር ግን በአይሁድ ትውፊቶች ውስጥ ሙሴን የተቃወሙ የግብጻውያን የችሎት አስማተኞች መሆናቸው ተገልጾአል (ዘጸ. 7፡11)።

የውይይት ጥያቄ፡– በወላጆችህ ዘመን የነበረውን የሥነ ምግባር መመዘኛ ዛሬ ከብዙ ወጣቶች (ክርስቲያኖችን ጨምሮ) ከምንመለከተው የሥነ ምግባር መመዘኛ ጋር አነጻጽር። ተቀባይነት ያላቸው ልምምዶች ጳውሎስ ከገለጻቸው ጋር የሚመሳሰሉት እንዴት ነው? ይህ ክርስቶስ ወደሚመለስበት የመጨረሻው ዘመን እየቀረብን መሄዳችንን የሚያመለክተው እንዴት ነው?

ጳውሎስ ከተቃውሞና ፈተናዎች ባሻገር እግዚአብሔርን እንዴት በታማኝነት ማገልገል እንደሚያሻ የራሱን ምሳሌነት ጠቅሶ ያብራራል። ጢሞቴዎስ ሐሰትን ለመዋጋት የጳውሎስን ሕይወት መከተልና ቅዱሳት መጻሕፍትን መጠቀም ያስፈልገው ነበር (2ኛ ጢሞ. 3፡10-17)።

ጳውሎስ ስለ መጨረሻው ዘመን ሲያስብ፥ ሁለት የሕይወት መንገዶችን ያነጻጽራል። አጠቃላዩ ማኅበረሰብ አንዱ ሌላውን ለማታለል ሲሞክር ሰይጣን ደግሞ የበለጠ ያታልላቸዋል። እነዚህ ሰዎች ከፈሪሃ እግዚአብሔር ርቀው የተሳካ ሕይወት ለመኖር የቻሉ ቢመስላቸውም፥ የኋላ ኋላ ግን እግዚአብሔር ይፈርድባቸዋል።

ከዚህ በተቃራኒ ጳውሎስ ጢሞቴዎስ የእርሱን ምሳሌነት እንዲከተል ያበረታታዋል። ምንም እንኳን ጳውሎስ ለጊዜው ስደት ቢደርስበትም፥ ሕይወቱን የኖረው ዓላማ ባለው መልኩ ነበር። ይኸውም ወንጌልን በዓለም ሁሉ ማድረስ ነበር። በስደት ጊዜ ታጋሽ፥ ለሰዎች ፍቅርን የሚገልጽና ክርስቶስ በሁኔታዎች ሁሉ እንደሚረዳው የሚተማመን አገልጋይ ሆኖ ተመላልሷል። እያደር እየተናደ በሚሄድ የሕይወት ጠርዝ ላይ ሆኖ ጢሞቴዎስ በእግዚአብሔር ቃል ላይ አጽንኦት እንዲሰጥ ጳውሎስ ያደፋፍረዋል። የእግዚአብሔርን ፍጹማዊ እውነት የሚያገኘው ከቃሉ ነውና። ጳውሎስ የእግዚአብሔር ቃል ሰዎች የፈጠሩት አለመሆኑን ይገልጻል። ነገር ግን እግዚአብሔር አጽናፈ ዓለሙን በቃሉ ትእዛዝ እንደፈጠረ ሁሉ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ያለው ሁሉ የመነጨው ከእርሱ ነው። ጢሞቴዎስ ሐሰተኛ ትምህርትን ለመከላከል መጽሐፍ ቅዱስን በዋናነት መጠቀም ያስፈልገው ነበር። ጢሞቴዎስ እውነትን ለማስተማር፥ እግዚአብሔር በሚፈልገው መንገድ የማይመላለሱትን ሰዎች ለመገሠጽ፥ ግራ የተጋቡትን ለማረምና ሰዎችን በጽድቅ ጎዳና ለማሠልጠን የእግዚአብሔርን ቃል መጠቀም ነበረበት።

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

%d bloggers like this: