ጳውሎስ ጢሞቴዎስ ቆራጥ ወታደር ሆኖ ለክርስቶስ እንዲሠራ ያደፋፍረዋል (2ኛ ጢሞ. 2፡1-26)

ስደት ሲጠናከርና አማኞች ለእምነታቸው የመሞታቸው ጉዳይ ቁርጥ ሲሆን፥ አማኞች በተለይም የቤተ ክርስቲያን መሪዎች ሊያስታውሷቸው የሚገቧቸው ወሳኝ ነገሮች ምን ምንድን ናቸው? እግዚአብሔርን በሚያስከብር መንገድ ስለመመላለስ የሚያስተምሩ ቁልፍ እውነቶች ምን ምንድን ናቸው? እምነታችን ለቀጣዩ ትውልድ በጥንቃቄ መተላለፉን እንዴት ልናረጋግጥ እንችላለን? ጳውሎስ የእግዚአብሔር ሕዝብ ታማኝ መሪ መሆን ማለት ምን ማለት እንደሆነ ለጢሞቴዎስ ያብራራል።

ሀ) ታማኝ የቤተ ክርስቲያን መሪ የወንጌሉን እውነት ብቃት ላላቸው ሰዎች በጥንቃቄ ያስተምራል። ይህም እምነቱ ከትውልድ ወደ ትውልድ ሳይቋረጥ እንዲተላለፍ ያስችላል። ጳውሎስ የወንጌሉን ወሳኝ እውነቶች ወዳጁና ሠልጣኙ ለነበረው ጢሞቴዎስ አስተላልፎአል። አሁንም ጢሞቴዎስ ታማኝ ሰዎችን ፈልጎ እነዚህን እውነቶች እንዲያስተምር ይመክረዋል። ጳውሎስ ሠልጣኞቹን የሚመርጠው በሁለት ዐበይት ብቃቶች ላይ በመመርኮዝ ነበር። በመጀመሪያ፥ ሠልጣኞቹ ለእግዚአብሔርና ለወንጌል እውነቶች ታማኞች መሆን ነበረባቸው። ሁለተኛ፥ የሚመረጡት ሰዎች ሌሎችን የማስተማር ብቃት ያላቸው መሆን ነበረባቸው። ሠልጣኞቹ የተማሩትን እውነት ወስደው ለቤተ ክርስቲያን አባላት ማስተላለፍ ያስፈልጋቸው ነበር። በመጨረሻም፥ እነዚህ ጢሞቴዎስ ያሠለጠናቸው ሰዎች ሌሎችን ሰዎች ማሠልጠን ይኖርባቸዋል። በዚህ ዓይነት መንገድ የወንጌል እውነታዎች ከስሕተት ተጠብቀው ወደ እያንዳንዱ አዲስ ትውልድ ይደርሱ ነበር።

ጳውሎስ ጢሞቴዎስ የቤተ ክርስቲያኒቱን አባላት በሙሉ ከሚያሠለጥናቸው ሰዎች ጋር እኩል በሆነ ደረጃ እንዲያስተምር አለመናገሩ ልብ ሊባል የሚገባው ነው። ጳውሎስ የሚያሠለጥናችውን ሰዎች በጥንቃቄ እንዲመረጥ ለጢሞቴዎስ ነግሮታል። የሠለጠኑት ሰዎች ደግሞ ቤተ ክርስቲያን በማስተማር የክርስቲያን እምነት ይጠብቃሉ።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ለቤተ ክርስቲያን መሪዎች ሌሎችን በጥንቃቄ መምረጥና ማሠልጠን አስፈላጊ የሚሆነው ለምንድን ነው? ለ) አብዛኞቹ የቤተ ከርስቲያን መሪዎች ሌሎችን በጥንቃቄ የሚያሠለጥኑ ይመስልሃል? ካልሆነ፥ ለምን? ሐ) የወንጌሉን መሠረታዊ እውነቶች ያስተማረ ማን ነው? መ) አንተስ እነዚህኑ መሠረታዊ እውነቶች ለማን ለማስተማር እየሞከርህ ነው? አንድን ሰው እያስተማርክ ካልሆነ፥ እየተማርክ ባላኸው እውነት እስከ አምስት የሚደርሱትን ክርስቲያን ወጣቶች እንድታስተምር እግዚአብሔር እነዚህን ሰዎች በልብህ ውስጥ እንዲያስቀምጥ በጸሎት ጠይቀው። ሠ) ከሌሎች ሽማግሌዎች ጋር በመመካከር፥ እነዚህን ግለሰቦች ለማስተማርና ደቀ መዝሙር ለማድረግ ፈቃድ ጠይቅ። በየሳምንቱ እነዚህን ወጣቶች የምታስተምርበት ጊዜ ወስን። ረ) ለእነዚህ የአዲስ ትውልድ መሪዎች ምን እውነቶችን ማስተማር ያስፈልጋል?

ለ) የቤተ ክርስቲያን መሪ እንደ ስደት፥ ሞትና አጠቃላይ የአመራር ችግሮች ያሉትን በትዕግሥት መጋፈጥ ይኖርበታል። የቤተ ክርስቲያን መሪ ከሰይጣንና ከመንግሥቱ ጋር እንደሚዋጋ ወታደር ነው። ስለሆነም፥ በጦር ሜዳ ላይ የሚዋጉ ወታደሮች ጉዳት እንደሚደርስባቸውና ሊሞቱም እንደሚችሉ መገንዘብ ይኖርበታል።

ሐ) መሪ በግል ጉዳዮች ሳቢያ ከአገልግሎቱ መደናቀፍ የለበትም። ማለትም፥ ትዳር በሚገኝበት ንግድ ራሱን አያጠላልፍም። «የጦር አዛዥ » የሆነውን ክርስቶስን በሚያስከብር መንገድ ይመላለስ ዘንድ የገንዘብን ፍቅር፥ ምቹ አኗኗር፥ የትምህርት ፍቅርና ግላዊ ክብር ወደ ጎን መተው ይኖርበታል።

መ) በውድድሩ የተደነገገውን ሕግ ተከትሎ ኦሎምፒክ ላይ እንደሚሮጥ አትሌት፥ የቤተ ክርስቲያን መሪ ክርስቶስ መንፈሳዊ ሩጫውን እንዲሮጥ በሰጠው ሕግጋት መሠረት ሩጫውን መቀጠል ይኖርበታል። ስለሆነም እንደ የገንዘብ ፍቅር፥ የግል ክብርና ጥቅማ ጥቅም ለማግኘት ማገልገል፥ ወሲባዊ ኃጢአት የመሳሰሉት ነገሮች ከሩጫው ሕግ ውጪ ናቸው። መንፈሳዊ ውድድራችንን አሽንፈን ከክርስቶስ መልካም አደረግህ የሚል የሙገሳ ቃል እንድንሰማ ከተፈለገ፥ ክርስቶስ በሰጠን ደንብ መሠረት መሮጥ ያኖርብናል።

ሠ) የቤተ ክርስቲያን መሪ የወደፊቱን ሽልማት እያስታወሰ እንደ ትጉሕ ገበሬ ጠንክሮ መሥራት ይኖርበታል። ገበሬ መሬቱን ለማለስለስ ጠንክሮ ሲሠራ ይቆይና በመጨረሻው ዘሩን ይዘራል። ከዚያም ሲጠባበቅ ቆይቶ የመከር ጊዜ ሲደርስ አዝመራውን ይሰበስባል። በተመሳሳይ መንገድ፥ የቤተ ክርስቲያን መሪ የወንጌሉን እውነቶች በመትከል ከእግዚአብሔር ቤተሰብ አባላት ጋር በጥንቃቄ ተግባሩን ያከናውናል። ብዙውን ጊዜ ሽልማቱ የሚመጣው በምድር ላይ ሳለህ ላይሆን ይችላል። ነገር ግን በሰማይ ለክርስቶስ በታማኝነት በማገልገልህ ትሸለማለህ። ስለሆነም፥ በምድር ላይ ፈጣን ሽልማቶችን ከመጠበቅ ይልቅ የቤተ ክርስቲያን መሪ የመንግሥተ ሰማይን በረከቶች በጉጉት መጠበቅ ይኖርበታል።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ስለ ወታደር፥ አትሌትና ገበሬ ከተሰጠው ምሳሌ ስለ ቤተ ክርስቲያን እመራር ሌሎች ምን እውነቶችን ልትገነዘብ ትችላለህ? ለ) ሕይወትህን ገምግም፡፡ ምን ዓይነት ወታደር አትሌትና ገበሬ እንደሆንክ ራስህን መለስ ብለህ መርምር። የጦር አዛዥህ ከሆነው ከክርስቶስ ሽልማት ታገኝ ዘንድ ከሕይወትህ ሊለወጡ የሚገባቸው ነገሮች ምን ምንድን ናቸው?

ረ) ሁልጊዜም የቤተ ክርስቲያን መሪ ሕይወቱና አገልግሎቱን በክርስቶስ ላይ ማተኮር አለበት። ሰዎች ስጦታዎቹን፥ ችሎታዎቹን ወይም ሥልጣኑን እንዲያደንቁለት አይፈልግም። ዋናው ነገር የክርስቶስ ወንጌል እንጂ የመሪው ሁኔታ አይደለም። ምንም እንኳን የቤተ ክርስቲያን መሪ እንደ ጳውሎስ ሊታሰርና ሊገደል ቢችልም፥ ማንም ሰው ሕይወት ለዋጩን የወንጌል መልእክት ሊያስር ወይም ሊገድል አይችልም። የቤተ ክርስቲያን መሪ መልእክቱ ሳይደናቀፍ ወደ ፊት ይገሰግስ ዘንድ የሚገጥመውን ችግር ሁሉ ለመቋቋም መቁረጥ ይኖርበታል።

በ2ኛ ጢሞ. 2፡11-13፥ ጳውሎስ ምናልባትም የቀድሞይቱን ቤተ ክርስቲያን መዝሙር እየጠቀሰ ይሆናል። መዝሙር በታማኝነት መመላለስ ሽልማትን እንደሚያስከትልና ክርስቶስን መካድ ደግሞ ቅጣትን እንደሚያመጣ የሚያመለክት ነው። ከክርስቶስ ጋር ከሞትን (ለኃጢአት ባሕሪያችን ስንሞትና እስከምንሞትበት ጊዜ ድረስ ለክርስቶስ በታማኝነት ስንኖር)፥ ለዘላለም ከእርሱ ጋር እንኖራለን። አሁን ስደትንና መከራን ከታገስን፥ በኋላ በእርሱ ተሸልመኝ የንግሥናው ተካፋዮች እንሆናለን። ነገር ግን ክርስቶስን ከካድን፥ ወደ መንግሥተ ሰማይ ስንደርስ በሆነ መንገድ እርሱም እኛን ይክደናል (ማቴ. 10፡33 አንብብ)። ጳውሎስ የሚናገረው ዓይነት ክህደት አንደኛውን ክርስቶስን ትቶ የሐሰት ጣዖታትን መከተልን የሚያመለክት ይመስላል። እንደ እውነቱ ከሆነ፥ በተለያዩ ሁኔታዎች ውስጥ ለጊዜው ታማኝነት ማጉደላችን የማይቀር ነው። ነገር ግን የሚወድደን ክርስቶስ ምን ጊዜም ታማኝነቱን ስለማያጓድልብን ልንበረታታ ይገባናል።

ሰ. የቤተ ክርስቲያን መሪ በመጨረሻ ለኃፍረት እንዳይጋለጥና ዳሩ ግን ከጌታ ዘንድ ሙገሳ እንዲሰጠው መጽሐፍ ቅዱስን በጥንቃቄ ማጥናትና ተግባራዊ ማድረግ ይኖርበታል። ይህም በሐሰተኛ ትምህርት እንዳይወሰድ ወይም ፊሊጦስና ሄሜኔዎስ እንዳደረጉት ሰይጣን የውሸት እውነቶችን ለማሰራጨት በመሣሪያነት እንዳይጠቀምበት ይረዳዋል። ብዙውን ጊዜ የቤተ ክርስቲያን መሪዎች ከመጽሐፍ ቅዱስ ጋር የጠለቀ ግንኙነት የላቸውም። አንዳንዶች እንዲያውም ጊዜ ወስደው አያነቡትም። አብያተ ክርስቲያናት ወንጌሉን በማያውቁና ከዚህም የተነሣ ከሐሰት ሊጠብቋቸው በማይችሉ መሪዎች ተሞልተዋል። ያልሠለጠነና ያልተማረ የቤተ ክርስቲያን መሪ (ሽማግሌ) በቀላሉ የሰይጣን መሣሪያ ሊሆን ስለሚችል አደገኛ ነው። እንደ ፊሊጦስና ሄሜኔዎስ ሐሰተኛ ነገር አስተምረን የሰዎችን እምነት ልናናጋ እንችላለን። ብዙውን ጊዜ በእግዚአብሔር እውነት የሠለጠኑ ሰዎችም መልካም ስብከት አያቀርቡም። እግዚአብሔር ሕዝቡ ሊሰማ ወደሚገባው እውነት እንዲመራቸው በጸሎት አይጠይቁትም። ሰባኪዎች እግዚአብሔር ቃሉ በተጻፈበት ጊዜ ሊያስተላልፍ የፈለገው መልእክት ምን እንደሆነ ለመረዳት ይችሉ ዘንድ መጽሐፍ ቅዱስን በሚገባ አያጠኑትም። ስለዚህም ጥቅሶችን ከዐውደ ምንባቡ ውጭ በመጠቀም ጸሐፊው ሊያስተላልፍ የፈለገውን መልእክት ሳይረዱ ይሰብካሉ። አንዳንዶች እንዲያውም፥ መንፈስ ቅዱስ መናገር ያለብኝን ስለሚነግረኝ መጽሐፍ ቅዱስን ማጥናት የለብኝም ይላሉ። ይህ ጳውሎስ እግዚአብሔር ስለሚያመሰግነው አገልጋይ ከተናገረው ውጪ ነው። ይህ የዝግጅት ጉድለት አደገኛ በመሆኑ ሰይጣን ሐሰተኛ ትምህርቶችን ለማስፋፋት ወይም ሕዝቡ በእምነት እንዳያድግ ለመከላከል ሊጠቀምበት ይችላል።

የእውነትን ቃል በትክክል ለመያዝ ሁለት ዐበይት ነጥቦች ያስፈልጋሉ። በመጀመሪያ፥ «መንፈስ ቅዱስ መጀመሪያ ለአማኞች በሰጠው ጊዜ የዚህ ጥቅስ ወይም ምንባብ መልእክት ምን ነበር?» የሚል ጥያቄ ማንሣት ያስፈልጋል። ይህ ጥያቄ ተፈትኖ የጠራው አገልጋይ እውነቶችን በተገለጹበት ምንባብና በጠቅላላው የመጽሐፍ ቅዱስ ዐውድ እንዲገነዘብ ይረዳዋል። ሐሰተኛ ወይም ሚዛናዊነቱን ያልጠበቀ ትምህርት ወደ ቤተ ክርስቲያን ሰርጎ ከሚገባባቸው መንገዶች አንዱ ሰዎች አንድን ጥቅስ ወይም እውነት ከዐውዱ ገንጥለው በማውጣት ሌሎች የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች ስለአነሡት ርእሰ ጉዳይ ምን እንደሚል ሳያገናዝቡ መጠቀማቸው ነው። ሁለተኛው ዐቢይ ነጥብ፥ «ይህ መልእክት ለዛሬው ዘመን ምን ትምህርት ያስተላልፋል? መንፈስ ቅዱስ በዚህ ጥቅስና ምንባብ ውስጥ ያሉትን እውነቶች እንድንጠቀም የሚፈልገው እንዴት ነው?» የሚል ነው። መንፈስ ቅዱስ የእግዚአብሔርን ቃል የሰጠው ለዘመናትና ትውልዶች ሁሉ ነው። ነገር ግን ዛሬ የእግዚአብሔር ቃል እንደሆነ በመቁጠር በሕይወታችን ውስጥ ተግባራዊ የምናደርገው እውነት መንፈስ ቅዱስ መጀመሪያ ለአማኞች የሰጠው መሆን አለበት። ለአንድ የቤተ ክርስቲያን መሪ የእግዚአብሔር ሕዝብ ለሚጋፈጧቸው ሁነኛ ችግሮች ተዛማጅነት የሌሏቸውን እውነቶች ማስተማሩ አደገኛ ነው። እንዲሁም ደግሞ የቤተ ክርስቲያን መሪ የእግዚአብሔርን ቃል መንፈስ ቅዱስ መጀመሪያ ከገለጠበት መንገድ ውጪ መጠቀሙ አደገኛ ነው።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) የቤተ ክርስቲያንህ አገልጋዮች የእውነትን ቃል የሚይዙበት መንገድ ጳውሎስ የተፈተኑ አገልጋዮች እንዲላቸው የሚያደርግ ይመስልሃል? መልስህን አብራራ። ለ) ባለፈው ወር ውስጥ የሰማሃቸውን ስብከቶች አብራራ። ሰባኪው መንፈስ ቅዱስ ምንባቡን መጀመሪያ በገለጠ ጊዜ ሊያስተላልፍ ስለፈለገው መልእከት ትክክለኛ ግንዛቤ ያለው ይመስልሃል? ሰባኪው መንፈስ ቅዱስ መጀመሪያ የገለጠውን እውነት በቀጥታና በግልጽ ለዛሬው ዘመን ክርስቲያናዊ ሕይወት አዛምዷልን? ሐ) ቤተ ክርስቲያንህ ውስጥ የሚሰጠው ትምህርት መንፈስ ቅዱስ መጀመሪያ ለገለጠው እውነት ታማኝነት እንዲኖረውና ዛሬ መንፈስ ቅዱስ ለቤተ ክርስቲያንህ ሊያስተላልፍ ከሚፈልገው መልእክት ጋር ተዛማጅነት እንዲኖረው ምን ማድረግ ያሻል?

ሸ) የቤተ ክርስቲያን መሪ እግዚአብሔር ሊጠቀምበት ከፈለገ የእግዚአብሔር ንጹሕ መሣሪያ ለመሆን መወሰን አለበት። ይህም «የተቀደሰ ለጌታውም የሚጠቅም ለበጎም ሥራ ሁሉ የተዘጋጀ ዕቃ» እንዲሆን ያስችለዋል። ጳውሎስ ይህን እውነት ሁለት የሸክላ ዕቃዎችን በምሳሌነት በመጠቀም ያብራራል። ሰዎች እጃቸውን ለመታጠብ የሚጠቀሙት ዓይነት ተራ ሳህንና ለእንግዶች ምርጥ ምግብ ለማቅረብ የሚያስችል የሸክላ ዕቃ አለ። የቤተ ክርስቲያን መሪ በሕይወቱ ውስጥ ንስሐ ያልተገባበት ኃጢአት እንዲኖር ሲፈቅድ፥ ክርስቶስ እንደ ልዩ የሸክላ ዕቃ ሊጠቀምበት እይችልም። በመሆኑም ተራ ዕቃ ይሆናል። ጳውሎስ አንድ የቤተ ክርስቲያን መሪ ክርስቶስ የሚጠቀመው ልዩ የሸክላ ዕቃ ለመሆን ሁለት ነገሮችን ማድረግ እንዳለበት ገልጾአል። በመጀመሪያ፥ «ከክፉ የጎልማሳነት ምኞት መራቅ» አለበት። ሕይወቱንና አገልግሎቱን ከሚያቆሽሹት ኃጢአቶች (የወሲብ ኃጢአቶች፥ የገንዘብና የሥልጣን ፍቅር) መራቅ አለበት። ሁለተኛ፥ የኃጢአት ባሕሪውን እግዚአብሔርን በሚያስከብሩ ነገሮች መተካት አለበት። እነዚህም እንደ ጽድቅ፥ እምነት፥ ፍቅርና ሰላም ያሉ ናቸው።

ቀ) የቤተ ክርስቲያን መሪ ከቤተ ክርስቲያን ምእመናን ጋር ያለውን ግንኙነት መጠበቅ አለበት። በትናንሽ ጉዳዮች ሐሳቡን ከማይቀበሉት ሰዎች ጋር መጣላት የለበትም። ሰዎች በመንፈሳዊ ሕይወታቸው ሲታገሉ በትዕግሥት እያስተማረ ሊረዳቸው ይገባል።

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

%d