የእግዚአብሔር ምርጥ ሕዝብ በቤተ መቅደሱ ውስጥ ሕያዋን ድንጋዮች ናቸው (1ኛ ጴጥ. 2፡4-12)።

በስደትና መከራ ጊዜ ክርስቲያኖች ከሚዘነጓቸው ነገሮች አንዱ ክርስቲያናዊ ማንነታቸውን ነው። ክርስቲያኖች ብዙውን ጊዜ የተረገጡ፥ የተጨቆኑና ማኅበረሰቡ እንደ ከንቱ ነገር የሚቆጥራቸው ናቸው። «ደደቦች ናችሁ» የሚለው ቃል ብዙውን ጊዜ በክርስቲያኖች ጆሮ ያቃጭላል። ሰይጣን ብዙውን ጊዜ በዚህ ሰዓት ወደ እኛ በመቅረብ ክርስቶስን በመከተላችንና እንደ ሌሎች ሰዎች ባለመሆናችን የሞኝነት ውሳኔ እንደ ወሰንን እንድናስብ በማግባባት ይፈትነናል። እንዲሁም እግዚአብሔር ለእኛ ያለውን ፍቅር እንድንጠራጠር ይፈትነናል። ጴጥሮስ ለእነዚህ የሰይጣን ውሸቶች ምላሽ ሲሰጥ በእግዚአብሔር ዓይኖች ፊት ማን እንደሆንን፥ እንዲሁም የእኛ ሁኔታ በክርስቶስ ላይ ከደረሰው ጋር እንዴት እንደሚመሳሰል ያስረዳል።

የአማኞች እውነተኛ ማንነት፡

ሀ) ሕያዋን ድንጋዮች፡ ጴጥሮስ የአማኞችን እምነት ለመግለጽ የራሱን ስም ተጠቅሟል። የጴጥሮስ የመጀመሪያው ስም ስምዖን እንደ ነበር ታስታውሳለህ። ነገር ግን ክርስቶስ ከጴጥሮስ ጋር በተገናኘበት ወቅት የጴጥሮስን ስም ወደ ድንጋይነት ለወጠው። (በአረማይክ ኬፋ፥ በግሪክ ደግሞ ጴጥሮስ ሁለቱም ድንጋይ ወይም ዓለት የሚል ፍቺ ይሰጣሉ።) [(ዮሐ. 1፡42)]። በኢየሩሳሌም ያለውን ዓይነት በክብር ያሸበረቀ ቤተ መቅደስ በማሰብ ጴጥሮስ እያንዳንዱን አማኝ በእግዚአብሔር ልዩ ቤት (የእግዚአብሔር ሕዝብ) በጥንቃቄ እንደ ተጠረበ ድንጋይ መሆኑን ይናገራል። የእግዚአብሔር ቤት ከድንጋይና ከስሚንቶ የተሠራ ሕይወት የሌለው ሕንጻ ሳይሆን፥ ሕያው ቤት ነው። አንድ ሰው በሚያምንበት ጊዜ በዚህ ዘወትር እያደገ በሚሄደው በእግዚአብሔር ቤት ውስጥ ሕያው ድንጋይ ይሆናል። ይህ ሕያው ቤት ዘላለማዊ እና ሰዎች ከሚያንጹአቸው የአምልኮ ሕንፃዎች የላቀ ነው። (ማስታወሻ፡ ይህ ለአምልኮ የምንገነባው ሕንፃ ለእግዚአብሔር እርሱ እየገነባ ካለው የቤተሰቡ መንፈሳዊ ቤት ጋር ሲነጻጸር እንደማይስተካከለው ያስታውሰናል። ለእግዚአብሔር ምንም ያህል ታላቅ የጸሎት ቤት ብንሠራም፥ አንድ ቀን መደምሰሱ አይቀርም። ነገር ግን እግዚአብሔር ለልጆቹ ሕይወት የሚሠራውን ቤት ማንም ሊያጠፋው አይችልም።)

ለ) ቅዱስ ካህናት፡- ክርስቲያኖች ባሪያዎች ወይም ጌቶች፥ የተማሩ ወይም ያልተማሩ፥ ብዙ ስጦታ ወይም አንድ ስጦታ ብቻ ያላቸው ሊሆኑ ይችላሉ። ነገር ግን እያንዳንዱ አማኝ ካህን ነው። ካህን እንደ መሆኑ መጠን እያንዳንዱ ክርስቲያን ለእግዚአብሔር መሥዋዕቶችን የማቅረብ ዕድል አለው። እነዚህም መሥዋዕቶች እግዚአብሔርን ደስ ያሰኙታል። ይህ በብሉይ ኪዳን ለሌዋውያን የተወሰኑ ልዩ የሕዝብ ቡድኖችን ብቻ እግዚአብሔርን በዚህ መልኩ ከሚያገለግሉበት መንገድ የተለየ ነው። ዛሬ በዘመናችን ከተቀሩት አማኞች የበለጡ ናቸው ተብለው የሚታመኑትን የተወሰኑ ሰዎች (ካህናት፥ ሽማግሌዎች ወይም መጋቢዎች) ለአገልግሎት በመለየትና እግዚአብሔርን የማገልገል በረከት እንዲያገኙ በማድረግ ልንሳሳት አይገባም። እንዲህ ዓይነቱ ተግባር ሌሎች ምእመናን ቁጭ ብለው እንዲመለከቱ የሚያደርግ በመሆኑ ተገቢነት ሊኖረው አይችልም። ጴጥሮስ አማኞች ሁሉ ካህናት የመሆንና እግዚአብሔርን የማገልገል መብትና ዕድል እንዳላቸው ይመለከታል። ለእግዚአብሔር የምናቀርባቸው መሥዋዕቶች ምን ምን ናቸው? ጴጥሮስ የምሥጋናን መሥዋዕት ማቅረብ እንዳለብን ይገልጻል። ይህን ሲል ግን በቤተ ክርስቲያን ውስጥ የምሥጋና መዝሙር መዘመሩን ብቻ ማለቱ አይደለም። ነገር ግን ለእግዚአብሔር የምናቀርበው ምሥጋና እግዚአብሔርን በሚያስከብር መንገድ የምንኖረው ሕይወት ነው። ሰውነታችን (ሮሜ 12፡1-2)፥ ገንዘባችን (ፊልጵ. 4፡18)፥ ምሥጋናችን (ዕብ. 13፡15)፥ እንዲሁም መልካም ተግባራችን (ዕብ. 1፡16) ሁሉ ለእግዚአብሔር የምንሠዋው መሥዋዕቶቻችን ናቸው። እንዲሁም በአኗኗራችን፥ ለሌሎች በመማለድ፥ በጠፋው ዓለም ውስጥ እግዚአብሔርን በመወከል የእግዚአብሔርን ቅድስና እያንጸባረቅን የክህነት አገልግሎት ልናበረክት እንችላለን።

ሐ) የተመረጠ ሕዝብ፡ በብሉይ ኪዳን የነበሩት አይሁዶች ከዓለም ሕዝብ ሁሉ ተመርጠው የእግዚአብሔር ልዩ ሕዝቦች (ዘጸ. 19፡5-6) ሆነዋል። ጴጥሮስ ብዙውን ጊዜ አይሁዶች ከእግዚአብሔር ጋር ስላላቸው ልዩ ግንኙነት ሲናገሩ ሲሰሙ የኖሩት አሕዛብም የእግዚአብሔር ምርጥ ሕዝቦች መሆናቸውን ይናገራል። እግዚአብሔር በምድር ላይ ላሉት ሰዎች ሁሉ እነዚህ የቤተሰቡ አባላት እንዲሆኑ መርጧቸዋል። ጠላቶቹ የነበርነውን ሰዎች የቤተሰቡ አባላት በማድረጉ እግዚአብሔር ታላቅ ምሕረቱን ገልጾአል።

መ) የንጉሥ ካህናት፡ ይህ የንጉሥን ስፍራ ከካህናት ለይተው ለሚመለከቱ አይሁዶች የሚቻል አልነበረም። ነገር ግን ጴጥሮስ ክርስቲያኖች እንደ ሌዊ ዝርያዎች ካህናት ብቻ ሳይሆኑ፥ እንደ ዳዊት ነገድ የንጉሥ ልጆች መሆናችንን ያስረዳል። በምድር ላይ ሰዎች የዝነኛ ሰው ወይም የመንግሥት ባለሥልጣን ልጆች በመሆናቸው ይኩራራሉ። ጴጥሮስ ክርስቲያኖች የነገሥታት ንጉሥና የጌቶች ጌታ ልጆች በመሆናቸው ሊመኩ እንደሚችሉ ይናገራል። ይህ በምድር ላይ ለሰዎች፥ በግልጽ ላይታይ ቢችልም።

ሠ) እንግዶችና መጻተኞች፡ ጴጥሮስ አሁን ከማንነታችን ውስጥ በጣም አስቸጋሪ የሆነውን ክፍል ያብራራል። የተመረጥን፥ ካህናትና የንጉሥ ቤተሰብ መሆናችንን እናውቃለን። ዓለም ግን የዚህ ዓይነቱን ክብር አትሰጠንም። ይልቁንም ከዓለም ተቃውሞ ይሰነዘርብናል። ስለሆነም፥ ጴጥሮስ በክርስቶስ ያገኘነው ማንነት ተፈጻሚነትን የሚያገኘው በመንግሥተ ሰማይ ውስጥ መሆኑን በድጋሚ ያስገነዝበናል። አሁን ግን በምድር ላይ ጊዜያዊ ጎብኚዎች የሆንን ያህል ልንመላለስ ይገባል። ይህ በሁለት መንገዶች ተጽዕኖ ያሳድርብናል። በመጀመሪያ፥ የዓለም የኃጢአት ፍላጎቶች ሕይወታችንን እንዲበክሉ መፍቀድ የለብንም። በኃጢአት በተጨማለቀው ዓለም ውስጥ በመኖራችን ኃጢአት ወደ ሕይወታችን እንዲገባ መፍቀድ የለብንም። ሁለተኛ፥ ሌሎች በክርስቶስ አምነው ይድኑ ዘንድ የእግዚአብሔር ልጆች እንዴት እንደሚኖሩ ልናሳያቸው ይገባ ነበር። ክርስቶስ በሚመለስበት ጊዜ (በሚጎበኝበት ቀን) ዛሬ ወደ ክርስቶስ እንዲመጡ መልካም ተጽዕኖ ያሳደርንባቸው ሰዎች እግዚአብሔር ባለበት በዚያ ያከብሩናል።

የውይይት ጥያቄ፡- ለክርስቲያኖች ሰይጣንና ዓለም የሚሰጡንን ስም ከመስማት ይልቅ በእግዚአብሔር ዓይኖች ፊት ማን መሆናችንን መገንዘቡ ለምን ያስፈልጋል? ለ) አማኞች እነዚህን እውነቶች ቢያስታውሱ፥ ስደትና መከራን እንዴት በተሻለ ሁኔታ ሊቀበሉ ይችላሉ?

ጴጥሮስ የእውነተኛ ማንነታችንን ከመግለጹም በላይ፥ በክርስቶስ የታየውን የእግዚአብሔር መንገድ ምሥጢርነት ጭምር ያብራራል። ልክ እንደኛው ክርስቶስም ሕያው ድንጋይ ነበር። ነገር ግን እርሱ ከእኛ የበለጠ እና የላቀ ድንጋይ ነው። እርሱ የማእዘን ድንጋይ ነው። የማእዘን ድንጋይ የጥንት ዘመን ጠቅላላው ሕንጻ የሚያርፍበት ወሳኙ ድንጋይ ነበር። ወይም ደግሞ ውብ ሆኖ የተቀረጸ እና ቤቱን አያይዞ የሚያቆም ዋነኛው ድንጋይ ነው፡፡ አዲስ ሕንጻ የሆነችው ቤተ ክርስቲያን የቆመችው በእኛ፥ በወንጌላውያን ወይም ሽማግሌዎች ሳይሆን በክርስቶስ ላይ ነው።

እግዚአብሔር የመረጠው ይህ ልዩ ድንጋይ ምን ሆነ? በዓለም እንደ ከንቱ ነገር በመቆጠሩ የክርስቶስ ኢየሱስ ድንጋይ ተጣለ፥ ያውም ክርስቶስ ተገደለ። እግዚአብሔር ግን ሰዎች የናቁትን ድንጋይ ወስዶ ክርስቶስን የአዲስ ሕዝብ ራስ አደረገው። በተጨማሪም ይህ ድንጋይ በእርሱ ለማመን የማይፈልጉትን ሁሉ ለፍርድ አሳልፎ የሚሰጥ ዳኛ ሆነ። በተመሳሳይ ሁኔታ፥ ዓለም ሊጥለንና ከንቱዎች አድርጎ ሊቆጥረን ይችላል። እግዚአብሔር ግን ዓለም የናቀውን በመውሰድ ልዩ እና ዘላለማዊ የሆነው ሕንጻ አካል ያደርገናል። ስለሆነም ስደትና ታላቅ መከራ በሚያጋጥመን ጊዜ ተስፋ መቁረጥ የለብንም። ሰዎች በእግዚአብሔር ዘላለማዊ ቤት ውስጥ ምን ያህል አስፈላጊዎች እንደሆንን አያውቁም።

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading