የአንደኛ ጴጥሮስ መልእክት የመጨረሻው ዐቢይ ክፍል የእግዚአብሔር ምርጥ ሕዝብ መሆናችንን በሚያንጸባርቅ መልኩ ከዓለም የተለየ ሕይወት ልንኖር የምንችልባቸውን የተለያየ የሕይወት ክፍሎች ይመረምራል።
ሀ. ክርስቲያኖች ለመንግሥት መሪዎች መገዛት አለባቸው (1ኛ ጴጥ. 2፡13-17)። ሁሉም የመንግሥት ባለሥልጣናት እግዚአብሔርን ቢያከብሩም ባያከብሩም እግዚአብሔርን ቢያምኑም ባያምኑም፥ በእግዚአብሔር የተሾሙ ናቸው። ስለሆነም አማኞች መሪዎቻቸውን ማክበርና መታዘዝ ይኖርባቸዋል። ይህም ማለት ቀረጥን እንዲከፍሉ በሚጠየቁበት ጊዜ ከማጭበርበር ይልቅ መክፈል አለባቸው ማለት ነው። ወደ ማኅበራዊ ስብሰባዎች በመሄድ መሳተፍ አለባቸው ማለት ነው። ለከተማችንና ለሀገራችን ይበጀናል የምንላቸውን ሰዎች ለመመረጥ የሚያግዝ ድምጽ መስጠትንም ይጨምራል።
የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ክርስቲያኖች ለመንግሥት መሪዎች ሊገዙ የሚችሉባቸውን ሌሎች ምሳሌዎች ዘርዝር። ለ) ክርስቲያኖች ብዙውን ጊዜ መንግሥት የመሠረታቸውን ግዴታዎች ላለማሟላት ጥረት የሚያደርጉባቸውን መንገዶች ዘርዝር። እግዚአብሔር ይህንን አመለካከት እንዴት እንደሚመለከት ግለጽ።
ለ. ክርስቲያን ባሪያዎች (ሠራተኞች) መከራ ቢቀበሉም እንኳን ለሰብአዊ ጌቶቻቸው መገዛት አለባቸው (1ኛ ጴጥ. 2፡18-25)። ጌቶቻቸው (አሠሪዎቻቸው) መልካም፥ አፍቃሪ ወይም ሰው የሚጠሉ መሆናቸው ለውጥ አያመጣም። አማኞች ምንም ኃጢአት ሳይሠራ መከራ የተቀበለውን የክርስቶስን ምሳሌነት መከተል ይኖርብናል። ይህም በባህሪያችንና በተግባራችን ሁሉ ሊገለጥ የሚገባው ነው። ክርስቶስ ምንም ኃጢአት ሳይሠራ ለእኛ ኃጢአት ሲል ሞቷል። ከዚህም የተነሣ፥ ይቅርታ ተደርጎልን የክርስቶስን ጽድቅ ሰጥቶናል። በተመሳሳይ መንገድ ባሪያዎች (ሠራተኞች) ምንም ዓይነት ጥፋት ሳይፈጽሙ መከራ መቀበላቸውን ማረጋገጥ አለባቸው። ክርስቲያን ባሪያዎች ለእምነታቸው ወይም ትክክለኛ የሆነውን ነገር በማድረጋቸው መከራን በሚቀበሉበት ጊዜ እንዴት የትሕትና መንፈስ ሊኖራቸው ይችላል? ጴጥሮስ ለዚህ ቁልፉ ለእግዚአብሔር ሥልጣን መገዛት እንደሆነ ይናገራል። እግዚአብሔር ይህን እውነት እንዳስከተለ መገንዘብ፥ ክርስቲያን ራሱን ለእግዚአብሔር አሳልፎ ይሰጣል። እግዚአብሔር አንድ ቀን ፍትሕን ይሰጠዋል። ከሁሉም በላይ ክርስቶስ ዛሬም እረኛችን በመሆኑ ነፍሳችንን ይጠብቃል። እንደ ባሪያዎች ስንሰደድ ወይም አለአግባብ ሥቃይ ሲደርስብን እርሱ ይታደገናል።
(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)