በብርሃን መመላለስ (1ኛ ዮሐንስ 1፡1-2፡6)

አንድ ቀን ግርማዊ ወደ ዩኒቨርሲቲ ካፊቴሪያ ሲሄድ ሦስት ተማሪዎች በሃይማኖት ጉዳይ ላይ ይከራከሩ ነበር። ከሦስቱ ልጆች አንዱ ሙስሊም፥ ሌላኛው የአዲሱ ትውልድ (New Age) እምነት ተከታይ፥ ሦስተኛው ደግሞ የጂሆቫ እምነት ተከታይ ነበር። ግርማዊ ደግሞ የወንጌላውያን አብያተ ክርስቲያን አባል ነበር። እያንዳንዳቸው ስለ እምነታቸው ገለጻ አደረጉ። ከዚያም በአራቱም ሃይማኖቶች ውስጥ ስላሉት ጥሩ ጥሩ ነገሮች ተወያዩ። በውይይታቸው መጨረሻ ላይ በአራቱ ሃይማኖቶች ውስጥ አንድ አንድ ጥሩ ነገሮች እንዳሉ ተስማሙ። በውይይቱ፥ መጨረሻ ላይ ግርማዊ ከካፊቴሪያው ወጥቶ ሲሄድ ብዙ ጥያቄዎች አእምሮውን አጨናነቁት። «በሁሉም ሃይማኖቶች ውስጥ መልካም ነገሮች ካሉ፥ ሁሉም ሃይማኖት ወደ እግዚአብሔር የሚያደርሰን ትክክለኛ ሃይማኖት ነው ማለት ይቻላል? ወደ እግዚአብሔር የሚያደርሱ ብዙ መንገዶች አሉ? ወይስ ሰው የሚድነው በክርስቶስ ኢየሱስ ብቻ ነው? እግዚአብሔር የሚያሳስበው አንድ ሰው እርሱን ለማወቅ እና መልካም ሕይወት ለመኖር መቅናቱ ብቻ ነው? ወይስ ለእግዚአብሔር እውነት ወሳኝ ጉዳይ ነው?» ሲል አሰላሰለ።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) የግርማዊን ጥያቄዎች እንዴት ትመልሳለህ? ለ) እግዚአብሔር ከእውነት በላይ ሃይማኖታዊ ቅናትን ይፈልጋል? ወይስ ትክክለኛ እምነትን? ሐ) አንድ ሰው ድነት (ደኅንነት) የሚያገኘው ክርስቶስን በማመን ብቻ እንደሆነ ከተናገረ፥ ይህ ትዕቢትን አያሳይምን? መልስህን አብራራ። መ) እውነትን ማወቅና ማመን አስፈላጊ ነው የምንል ከሆነ፥ ብዙ ክርስቲያኖች ስለ አንድ ነገር እውነተኛነት ብዙም የማይጨነቁት ለምንድን ነው? ሠ) ከሰዎች አስተሳሰብ ይልቅ ፍጹማዊ እውነትን የምናውቅበት ብቸኛው ምንጭ ምንድን ነው?

መጽሐፍ ቅዱስ እውነት ለእግዚአብሔር አስፈላጊ መሆኑን በግልጽ ይናገራል። ለዚህም ነው እግዚአብሔር እውነትን በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የገለጠው። ይህም የእርሱ የሆነው እውነት ነው። የእግዚአብሔርን ማንነት፥ ባህሪውን እና ከእርሱ ጋር ኅብረት ለመፍጠር ከሚፈልጉት ሰዎች ምን እንደሚፈልግ በትክክል የምናውቀው ከመጽሐፍ ቅዱስ ብቻ ነው። ስለ ክርስቶስ እና በእርሱ መንገድ ስለሚገኘው የድነት (ደኅንነት) መንገድ ማወቃችን ወሳኝ ነው። ምክንያቱም ክርስቶስ እንዳለው ወደ እግዚአብሔር የሚያደርስ አንድ ጠባብ መንገድ እርሱ ብቻ ነው። ሌሎች ሰፋፊ መንገዶች ሁሉ ወደ ዘላለማዊ ሞት የሚወስዱ ናቸው (ማቴ. 7፡13-14)። ስለሆነም፥ አንድም መጽሐፍ ቅዱስ ውሸት ነው ብለን ማመን አለብን፥ አለዚያም የመጽሐፍ ቅዱስን ትምህርት ተቀብለን ወደ እግዚአብሔር የሚያደርሰን አንድ የድነት (ደኅንነት) መንገድ ብቻ እንዳለ መቀበል አለብን። ስለሆነም ዋናው ነገር የእኛ አሳብ አይደለም። በመሆኑም ድነት (ደኅንነት) የሚገኘው በክርስቶስ ነው የሚለው አሳብ ከእኛ የፈለቀ አይደለም። ይህም በመሆኑ ትዕቢትን እያመለክትም። እግዚአብሔር አንድ ብቸኛ የድነት (ደኅንነት) መንገድ እንዳለ ገልጾአል። እኛም ይህንኑ የእግዚአብሔርን ቃል እንደ ገደል ማሚቶ እንደግማለን።

የ1ኛ ዮሐንስ መልእክት እውነት ወሳኝ መሆኑን አበክሮ ይገልጻል። ዮሐንስ የሃይማኖት ቅናት ወይንም ስለ ክርስቶስ ደብዛዛ ግንዛቤ መያዙ በቂ አይደለም ይላል። ክርስቲያኖች ስለ እውነት ጥርት ያለ መረዳት ሊኖረን ይገባል። እውነትን ከሚያውቁት ሰዎች ጋር በፍቅር እና በትሕትና አብረን ልንኖር ሲገባንም፥ በመጽሐፍ ቅዱስ የተገለጸ አንድ እውነት ብቻ እንዳለ መግለጽ ይኖርብናል። ይህ አመለካከት ዛሬ በዓለም ውስጥ ሰፊ ተቀባይነት ያለው አይደለም። ክርስቲያኖችን ጨምሮ ድነት (ደኅንነት) የሚገኘው በክርስቶስ ብቻ መሆኑን የማይቀበሉ ብዙ ሰዎች አሉ። ሰዎች እንደ «ኢየሱስ ብቻ» ተከታዮች በሥላሴ ባያምኑም ችግር አለው? ክርስቶስ ነቢይ እንጂ እምላክ አልነበረም ቢሉስ? ድነት (ደኅንነት) የሚገኘው በመልካም ተግባርና እግዚአብሔርን የሚያስደስት ሥራ በመሥራት ነው የሚሉትስ ወገኖች? አንዳንዶች ድነትን የሚያገኙት በልሳኖች የሚናገሩት አማኞች ብቻ ናቸው ብለው ቢያስተምሩ ችግር አለው? ምንም እንኳን ብዙ ክርስቲያኖች ስለ እነዚህ ጉዳዮች ደንታ ባይኖራቸውም፥ ይህ ለእግዚአብሔር አስፈላጊ መሆኑን በ1ኛ ዮሐንስ መልእክት ውስጥ እንመለከታለን። እውነት አስፈላጊ ነው ፍቅርና መቀባበል ከእውነት ጋር መዋሃድ አለባቸው። እግዚአብሔርን ማስደሰት የሚቻለው ይህ ሲሆን ብቻ ነው (ኤፌ. 4፡15)።

እግዚአብሔር መጀመሪያ ሰውን ሲፈጥር ቀዳሚ ዓላማው ከሰው ጋር ኅብረት ማድረግ ነበር። እግዚአብሔር ከእንስሳት በተለየ ሁኔታ ሰውን በምሳሌው ፈጥሮታል። ከመጀመሪያ ጀምሮ እግዚአብሔር ከአዳም እና ሔዋን ጋር በመደበኛነት ኅብረት ያደርግ ነበር። (ዘፍጥ. 3፡8-9)። የሰው ልጆች ከእግዚአብሔር ጋር ኅብረት በሚያደርጉበት ጊዜ እጅግ የላቀ እርካታ ያገኙ ነበር። አዳምና ሔዋን ኃጢአት በሠሩ ጊዜ ይሄ ሁሉ ተለወጠ። በእግዚአብሔር እና በሰው መካከል ክፍተት ተፈጠረ። መጀመሪያ በእንስሳት መሥዋዕቶች፥ የኋላ ኋላም ክርስቶስ የኃጢአትን ዋጋ ለመክፈል በመስቀል ላይ በመሞቱ ከእግዚአብሔር ጋር ኅብረት የምናደርግበት መንገድ እንደገና ተከፈተ። ሐዋርያው ዮሐንስ ከእግዚአብሔር ጋር እንዴት ኅብረታችንን ጠብቀን ልንኖር እንደምንችል በመግለጽ መልእክቱን ይጀምራል። በሕይወት ውስጥ እውነተኛ ደስታ ሊገኝ የሚችለው ከእግዚአብሔር ጋር እያደገ የሚሄድ ኅብረት ሲኖረን ነው።

፩. መግቢያ፡- ከእግዚአብሔር ጋር የሚደረገው ኅብረት በእውነት ላይ የተመሠረተ ነው፤ ይህም እውነት ክርስቶስ በሥጋ የተገለጠ አምላክ መሆኑን የተመለከቱት የዓይን ምስክሮቹ ሐዋርያት ያስተማሩት ነው (1ኛ ዮሐ. 1፡1-4)።

ከክርስትና እምነት መሠረታዊ እውነቶች አንዱ እግዚአብሔር ሰው መሆኑ ነው። ዘላለማዊ የእግዚአብሔር ልጅ የሆነው ክርስቶስ ወደዚህ ዓለም መጥቶ ተወልዶአል፥ ኖሮአል፥ ሞቶአል፥ ከሙታንም ተነሥቶ ወደ ሰማይ አርጓል። በዚህ ዓለም ላይ ሲመላለስ ከመኖሩም በላይ ለኃጢአታችን ሞቷል፥ ከሞትም ተነሥቶ ወደ መንግሥተ ሰማያት አርጓል። እግዚአብሔር ለኃጢአታችን መፍትሔ የሰጠው በዚህ መንገድ ነበር። ፍጹማዊ መሥዋዕት ሊቀርብ የሚችለው በዚህ መንገድ ብቻ ነበር። በዚህ ዓይነት የእግዚአብሔርን ኃይል የተላበሰ እና ዳሩ ግን ችግሮቻችንን የሚረዳ፥ ብሎም ከሰማይ ለእኛ የሚማልድ ዘላለማዊ ሊቀ ካህናት ሊኖረን ችሏል። የዮሐንስ ልብ ለዚህ ታላቅ ምሥጢር ሲከፈት እንመለከታለን። እግዚአብሔር ለሰው ልጆች የገለጸው ፍቅር ምንኛ ታላቅ ነው። ነገር ግን ይህ መሠረታዊ እውነት በሐሰተኛ አስተማሪዎች ሲጠቃ ተመለከተ። አንዳንዶች ክርስቶስ አምላክ መሆኑን ሲጠራጠሩ፥ ሌሎች ደግሞ ሰው መሆኑን ይጠራጠሩ ነበር። ስለሆነም ዮሐንስ በመግቢያው ላይ ሰላምታ ከማቅረብ ይልቅ ሥነ መለኮታዊ እውነትን ይነግረናል። በዚህም ክርስቶስ በሥጋ የተገለጠ አምላክ መሆኑንና ይህንን መረዳት ለአማኞች ለምን እንደሚያስፈልግ ተናግሯል። ለእግዚአብሔር እውነት ወሳኝ ነው። ምክንያቱም ይህ ዘላለማዊ ሕይወትና ዕጣ ፈንታቸው የዛሬ አኗኗራቸውን ይወስነዋል። ዮሐንስ ትኩረት ከሰጠባቸው ነገሮች መካከል የሚከተሉት ይገኙባቸዋል፡

ሀ) ክርስቶስ ከመጀመሪያው የነበረ አምላክ ነው። ይህም ዘላለማዊነቱን ያመለክታል። እርሱ የሕይወት ቃል ነው። እግዚአብሔር እውነትን ለሰዎች ያስተላለፈበት ምንጭ ነው። እርሱ ዘላለማዊ ሕይወት ነው። እንዲሁም ክርስቶስ ከአብ ጋር እኩል እና ነገር ግን የተለየ ነው።

ለ) ክርስቶስ ፍጹም ሰው ነው። ዮሐንስ የክርስቶስን ንግግር እርሱ ራሱ እንደ ሰማ፥ በዓይኑ እንዳየው እና በእጁ እንደ ዳሰሰው ይናገራል። ክርስቶስ መንፈስ አልነበረም። ወይም ደግሞ ክርስቶስ የምናብ ውጤት አልነበረም። ክርስቶስ በታሪክ ውስጥ የነበረ የታሪክ ሰው መሆኑን ያስመሰክራል። ዮሐንስ ክርስቶስን ያየው ሲሆን፥ ምናልባትም ከሞት የተነሣውን ጌታ ከተመለከቱት እና በሕይወት ካሉት የመጨረሻዎች ሰዎች ዮሐንስ አንዱ ሳይሆን አይቀርም። በዚህ ጊዜ ሌሎች ደቀ መዛሙርት ሁሉ ሞተው ነበር።

ሐ) ይህ አምላክ ሰው የመሆኑ ሁኔታ የሁለት ዓይነት እውነት መሠረት ነው። በመጀመሪያ፥ እንደ ክርስቶስ አካል ለሚኖረን ኅብረት መሠረት ነው። ዮሐንስ ክርስቶስ አምላክና ሰው መሆኑን የሚያምኑ አማኞች ከእርሱና ከሌሎች አማኞች ጋር ኅብረት ሊያደርጉ እንደሚችሉ ይናገራል። ዮሐንስ ይህን ሊል ክርስቶስ ፍጹም አምላክና ፍጹም ሰው እንደሆነ የማያምኑ ሰዎች የእግዚአብሔር ቤተሰብ አባል አለመሆናቸውን እና ከዚህም የተነሣ የአማኞችን አምላክ ኅብረት እያደረጉ ደስ ሊሰኙ እንደማይችሉ ማሳየቱ ነው። ሁለተኛ፥ ይህ ከእግዚአብሔር አብና ወልድ ጋር ኅብረት ለመፍጠር መሠረት ይሆናል። አሁንም ክርስትና ልዩ ሃይማኖት ያለመሆኑን እንመለከታለን። አንድ ሰው ከእግዚአብሔር አብና ወልድ ጋር ኅብረት ሊያደርግ የሚችለው ስለ ክርስቶስ ትክክለኛ እውቀት ካለውና የኃጢአትን ዋጋ ለመክፈል ክርስቶስ በመስቀል ላይ እንደ ሞተ በግሉ ሲያምን ብቻ ነው። ዮሐንስ እውነትን ስናውቅ እና ከእግዚአብሔር ጋር ያለን ግንኙነት ግልጽ፥ እንዲሁም በእውነት ላይ የተመሠረተ ሲሆን፥ በፍጹም ደስታ እንደምናገኝ ያስረዳል።

የውይይት ጥያቄ፡– ሀ) ይህ ክፍል አማኞች የመጽሐፍ ቅዱስን እውነቶች በትክክል መረዳታቸው ምን ያህል አስፈላጊ እንደሆነ ያሳያል። ይህንን አሳብ አብራራ። ለ) ይህ ክፍል ዋናው አምልኳችን ወይም ቅናታችን እንጂ እውነት አይደለም ለሚሉ ወገኖች ምን ዓይነት ማስጠንቀቂያ ይሰጣል? ሐ) ይህ ክፍል ሁሉም ሃይማኖቶች ወደ እግዚአብሔር ያመጣሉ የሚለውን አሳብ እንዴት ፉርሽ እንደሚያደርግ ግለጽ።

፪. ከእግዚአብሔር ጋር ኅብረት ማድረግ ማለት የኃጢአትን ይቅርታ አግኝተን በቅድስና እና በታዛዥነት መመላለስ ማለት ነው (1ኛ ዮሐ. 1፡5-2፡6)

የተሳሳተ ግንዛቤ በአማኞች ላይ ተጽዕኖ ከሚያሳድርባቸው መንገዶች አንዱ ወደ ተሳሳቱ ተግባራት መምራት ነው። ከቀድሞዎቹ አማኞች አንዳንዶቹ የሰው ሥጋ ክፉ እንደሆነና መንፈስ ብቻ የተቀደሰ መሆኑን የሚያመለክት ሐሰተኛ ትምህርት ይሰሙ ነበር። ይህም በትክክለኛ መንገድ እግዚአብሔርን እስካመለክነውና ለመንፈሳችን ጥንቃቄ እስካደረግን ድረስ፥ በሥጋችን የምንሠራው አሳሳቢ አይደለም ወደሚለው አመለካከት መራቸው። ዮሐንስ ግን በመንፈሳችን ከእግዚአብሔር ጋር የምናደርገው ኅብረት በትክክለኛ እውቀትና ተግባራት ላይ የተመሠረተ መሆኑን ይገልጻል። ስለሆነም ዮሐንስ ለአማኞቹ የምንኖርበት ሁኔታ በልባችን ውስጥ ያለውን እውነት ምንነት ያረጋግጣል ይላቸዋል።

ሀ) ከእግዚአብሔር ጋር ኅብረት የሚያደርጉ ሰዎች በብርሃን ወይም በቅድስና መመላለስ ይኖርባቸዋል። ቅድስና ከእግዚአብሔር ቀዳማይ ባሕርያት አንዱ ነው። እግዚአብሔርን የሚከተሉትና ከእርሱ ጋር ግንኙነት ለማድረግ የሚፈልጉ ሰዎች ለቅድስና ራሳቸውን ማዘጋጀት ይኖርባቸዋል። በእውነትና በቅድስና ብርሃን ለመኖር በምንፈልግበት ጊዜ በኃጢአት ብንወድቅ የክርስቶስ ኢየሱስ ደም ከኃጢአት ሁሉ ያነጻናል።

ለ) እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር ኅብረት ለማድረግ ፍጹማን እንድንሆን አይጠብቅብንም። እንዲያውም፥ ፍጹምና ኃጢአት የለሽ መሆኑን የሚናገር ሰው ውሸተኛ መሆኑን እንገነዘባለን። የእግዚአብሔርም ቃል በእንዲህ ዓይነቱ ሰው ሕይወት ውስጥ አይሠራም። ኃጢአት አድርገን በእግዚአብሔርና በእኛ መካከል ያለው ኅብረት በሚበላሽበት ወቅት ምን ማድረግ ይኖርብናል? በኃጢአታችን ምክንያት የተበላሸውን ግንኙነት እንዴት መጠገን ይቻላል? መጀመሪያ ለእግዚአብሔር፥ ቀጥሎም ለበደልነው ሰው ኃጢአታችንን በመናዘዝ ከእግዚአብሔር ጋር ወደ ነበረን ኅብረት ልንመለስ እንችላለን። የበደልነውን ሰው ይቅርታ የምንጠይቀው ኃጢአታችን ሌላውን ሰው የሚያካትት ከሆነ ነው። እግዚአብሔር ኃጢአታችንን በክርስቶስ ደም ተሸፍኖ ስለሚመለከትና ይቅር ስለሚለን፥ ንስሐ መግባታችን ከእግዚአብሔር ጋር ያለንን ኅብረት ያድሰዋል። ዮሐንስ ይቅርታ እንደሚደረግልን ብቻ ሳይሆን፥ ኃጢአት በምንፈጽምበት ጊዜ ስለ እኛ በእግዚአብሔር ፊት የሚቆምና የሚማልድ ጠበቃ በሰማይ እንዳለን ይናገራል። ዮሐንስ «ጠበቃ» የሚለውን ቃል የወሰደው ከሕግ ሙያ ነው። አንድ ሰው ተከስሶ ችሎት ፊት በሚቀርብበት ጊዜ ከወንጀሉ ነፃ መሆኑን የሚያረጋግጥለት ጠበቃ ይቀጥራል። በተመሳሳይ ሁኔታ፥ በእግዚአብሔር አብ ፊት በምንቆምበት ጊዜ (ሰይጣን በኃጢአታችን ሲከስሰን) ክርስቶስ በችሎቱ ፊት ቆሞ ንጹሕ ለመሆናችን ይከራከርልናል። ኃጢአት ሠርተን ሳለን እንዴት ንጹሐን ልንሆን እንችላለን? ንጹሐን የምንሆንበት ምክንያት ቀደም ሲል ክርስቶስ በመስቀል ላይ በመሞት ለወንጀላችን (ለኃጢአታችን) ክፍያ የፈጸመ በመሆኑ ነው። ስለሆነም ክርስቶስ አማኙ ኃጢአት አልፈጸመም አይልም። ነገር ግን፥ «የኃጢአቱ ዋጋ ስለተከፈለ ሊቀጣ አይችልም። ስለሆነም ነፃ ነህ ተብሎ መሰናበት አለበት» ሲል ይከራከራል። (ማስታወሻ፡ ኃጢአትን በምንሠራበት ጊዜ ደኅንነታችንን አናጣም። ነገር ግን ከእግዚአብሔር ጋር ያለን ኅብረት ይቋረጣል። ይህ አንድ ልጅ ወላጆቹን በማይታዘዝበት ጊዜ ከሚሆነው ሁኔታ ጋር ተመሳሳይ ነው። በመሆኑም ልጁ ባለመታዘዙ ምክንያት ልጅነቱን አያጣም። ነገር ግን ቀደም ሲል እንደ ነበረው ከወላጆቹ ጋር መልካም ግንኙነት ላይኖረው ይችላል።)

ሐ) ከእግዚአብሔር ጋር ኅብረት ለማድረግና እውነተኛ የእግዚአብሔር ልጆች መሆናችንን ለማረጋገጥ ኃጢአታችንን መናዘዝ ብቻ ሳይሆን፥ እውነትን መታዘዝ አለብን። ከእግዚአብሔር ጋር ያለን ግንኙነት የሚገለጸው ኃጢአት ባለመሥራታችን ብቻ አይደለም። ነገር ግን ለእግዚአብሔር ቃል በመታዘዝ የጽድቅን ኑሮ በመኖራችን ይገለጻል።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ለአማኞች በተደጋጋሚ ኃጢአታቸውን በመናዘዝ ንጹሕ ሕይወት መምራት አስፈላጊ የሚሆነው ለምንድ ነው? ለ) በቤተ ክርስቲያንህ ውስጥ አብዛኞቹ ክርስቲያኖች ለኃጢአት ትኩረት በመስጠት በእግዚአብሔር ፊት ንጹሕ ሕይወት ለመኖር የሚሞክሩ ይመስልሃል? የራስህን ሕይወት መርምርና ያልተናዘዝክበት ኃጢአት ካለ ተመልከት። ከእግዚአብሔር ጋር ያለህ ኅብረት እንዲታደስ ኃጢአትህን ተናዘዝ። ሐ) ብዙውን ጊዜ ከእግዚአብሔር ጋር ስላለን ግንኙነት ስናስብ፥ ስለ ጽድቅ ሳይሆን ኃጢአትን ስላለመሥራት እናስባለን። እግዚአብሔር ለእርሱ በመታዘዝና በጽድቅ እንድንኖር የሚጠይቃቸውን የተለያዩ ነገሮች ዘርዝር። እነዚህ ነገሮች ለምን እንደሚያስፈልጉ ግለጽ።

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

%d bloggers like this: