የ1ኛ ዮሐንስ ልዩ ባሕርያት፣ ማዋቅር እና አስተዋጽኦ

የ1ኛ ዮሐንስ ልዩ ባሕርያት

  1. ዮሐንስ ክርስቲያኖችን «ልጆቼ ሆይ» እያለ ይጠራል። በእድሜ መግፋቱንና አብዛኞቹ አማኞች ከእርሱ ታናናሾች የነበሩ መሆናቸውን ያሳያል። ይህ በተጨማሪም፥ ዮሐንስ አማኞቹን በቅርብ እንደሚያውቃቸው ያሳያል።
  2. እንደ ዮሐንስ ወንጌል ሁሉ፥ የ1ኛ ዮሐንስ ጸሐፊ እውነትን በተቃራኒ አሳቦች ይገልጻል። በመሆኑም እንደ ጨለማና ብርሃን (1ኛ ዮሐ. 1፡5-7)፥ ሕይወትና ሞት (1ኛ ዮሐ. 3፡14-15)፥ እውነትና ውሸት (1ኛ ዮሐ. 2፡21)። ፍቅርና ጥላቻ (1ኛ ዮሐ 4፡19-21) የመሳሰሉትን ቃላት ይጠቀማል።
  3. ዮሐንስ የፍቅር ሐዋርያ በመባል ይጠራል። በዚህች አጭር መልእክት ውስጥ «ፍቅር» የሚለው ቃል 25 ጊዜ ተጠቅሷል።
  4. ዮሐንስ በመጨረሻው ዘመን ለሚገለጠው ገዢ የወል ስም ይሰጠዋል። ዮሐንስ ይሄንን ገዢ «የክርስቶስ ተቃዋሚው» ሲል ይጠራል። ይህም ሐሰተኛው መሢሕ በሁሉም ነገር የክርስቶስ ተቃዋሚ (ተቃራኒ) እንደሚሆን ያመለክታል (1ኛ ዮሐ 2፡18)። እንዲሁም ዮሐንስ ውሸትን የሚያስተምሩ ሰዎች ሁሉ በዚሁ የመጨረሻው ዘመን ገዢ መንፈስ የሚሠሩ መሆናቸው፥ የክርስቶስ ተቃዋሚዎች መሆናቸውን ይገልጻል።
  5. ዮሐንስ «ማወቅ» የሚለውን ቃል ከ40 ጊዜያት በላይ ደጋግሞ ጠቅሷል። ይህም ዮሐንስ መልእክቱን ከጻፈባቸው ዐበይት ምክንያቶች አንዱ ክርስቲያኖች እውነትን እንዲያውቁና በእግዚአብሔር የተስፋ ቃሎች ላይ ተመሥርተው በልበ ሙሉነት እንዲመላለሱ ለማገዝ መሆኑን ያሳያል።

የ1ኛ ዮሐንስ መዋቅር

በአንዳንድ በኩል የ1ኛ ዮሐንስ መልእክት ግልጽ ምክንያታዊ መዋቅርን የተከተለ አይደለም። ዮሐንስ ከአንድ ጉዳይ ወደ ሌላው፥ ከዚያም ወደ አንዳንድ ጉዳዮች እንደገና እየተመለሰ አጽንኦት የሚሰጥ ይመስላል። አንዳንድ ምሁራን ይህ መልእክት በሦስት ክፍሎች እንደ ተከፈለ ይናገራሉ።

  1. ከእግዚአብሔር ጋር ኅብረትን ለማድረግ እንዴት በብርሃን መመላለስ እንደሚቻል (1ኛ ዮሐ. 1፡1-2፡17)። ጸሐፊው ከመግቢያው ቀጥሎ ከእግዚአብሔር አብና ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ኅብረት እንዲኖረን ኃጢአታችንን መናዘዝ እንዳለብን ያስረዳል። ይሄም ኃጢአታችን ክርስቶስ በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደም እንደ ተሸፈነ ያስረዳል። ከዚያም የእግዚአብሔርን ትእዛዛት በመከተል መመላለስ ይኖርብናል። በተለይም እርስ በርሳችን ከመጠላላት ይልቅ መዋደድ ይኖርብናል። በእግዚአብሔር ቃል ውስጥ ያለውን እውነት ማመን አለብን። እንዲሁም፥ የዓለም ክፉ የአኗኗር ዘይቤ ሕይወታችንን እንዳይበክል መጠንቀቅ ይኖርብናል
  2. በሐሰተኛ ትምህርቶች መካከል እንዴት መኖር እንደሚቻል (1ኛ ዮሐ. 2፡18-3፡24)። ዮሐንስ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ክፍፍል የሚመጣው ከሐሰት ትምህርት መስፋፋት ሳቢያ እንደሆነ በመግለጽ፥ ክርስቲያኖች ለዚህ ሁኔታ ምን ዓይነት ምላሽ ሊሰጡ እንደሚገባ ያስጠነቅቃል። የክርስቶስ ተቃዋሚዎች እኛን ወደ ተሳሳተ አቅጣጫ ለመምራት በትጋት እየሠሩ መሆናቸውን ይነግረናል። ስለሆነም፥ ከመጀመሪያው የሰማናቸውን እውነቶች በጥንቃቄ መያዝ ይኖርብናል። እንዲሁም የተቀደሰ ሕይወት በመምራት ከእግዚአብሔር ጋር ያለንን ግንኙነት መጠበቅ አለብን። እርስ በርሳችን በመዋደድ ክርስቲያናዊ ሕይወትን ማጠናከር አለብን።
  3. ሐሰተኛና እውነተኛ አስተማሪዎችን እንዴት መለየት እንደሚቻል (1ኛ ዮሐ. 4፡1-5፡1-21)። ዮሐንስ ክርስቲያኖች የመጣውን ትምህርት ሁሉ ከእግዚአብሔር እንደሆነ በማሰብ እንዳይቀበሉና ነገር ግን መናፍስትን እንዲመረምሩ በማዘዝ፥ አማኞች አንድ ትምህርት ከእግዚአብሔር መሆን አለመሆኑን ለመፈተን የሚጠቀሙባቸውን ሦስት መፈተኛዎች ይሰጣል። እነዚህም ሦስት ዐበይት መፈተኛዎች፥ ሀ) ትክክለኛ እምነት። የዮሐንስ መልእክት ክርስቶስ በሥጋ የተገለጠ አምላክ በመሆኑ ላይ ያተኩራል። ለ) የእግዚአብሔር ቃል በሚያዘው መሠረት በጽድቅ መኖር ነው፤ ሐ) ከጥላቻና ክፍፍል ይልቅ የእግዚአብሔርን ሕዝብ መውደድ።

የ1ኛ ዮሐንስ አስተዋጽኦ

  1. ከእግዚአብሔር ጋር ኅብረት ለማድረግ በብርሃን መመላለስ (1ኛ ዮሐ. 1፡1-2፡17)።

ሀ) መግቢያ፡ ከእግዚአብሔር ጋር የሚደረግ ኅብረት ሐዋርያት ባስተማሩት እውነት ላይ የተመሠረተ ነው። እነዚህም ሐዋርያት ኢየሱስ ሰው ሆኖ በሥጋ የተገለጠ አምላክ መሆኑን በዓይናቸው አይተዋል (1ኛ ዮሐ 1፡1-4)።

ለ) ከእግዚአብሔር ጋር ኅብረት ማድረግ ማለት የኃጢአትን ይቅርታ አግኝተን በቅድስናና በታዛዥነት መመላለስ ማለት ነው (1ኛ ዮሐ. 1፡5-2፡6)።

ሐ) ከእግዚአብሔር ጋር ኅብረት ለማድረግ ሌሎች አማኞችን መውደድ ይኖርብናል (1ኛ ዮሐ 2፡7-14)።

መ) ከእግዚአብሔር ጋር ኅብረት ማድረግ ማለት የዓለምን የአኗኗር ዘይቤ አለመውደድ ማለት ነው (1ኛ ዮሐ 2፡15-17)

  1. በሐሰተኛ ትምህርቶች መካከል እንዴት መኖር እንደሚገባ (1ኛ ዮሐ 2፡18-3፡24)።

ሀ) የእግዚአብሔር ልጆች የሰይጣንን ውሸቶች ከማመን ይልቅ እውነትን አጥብቀው መያዝ አለባቸው (1ኛ ዮሐ 2፡18-27)።

ለ) የእግዚአብሔር ልጆች ተስፋችንን በክርስቶስ ዳግም ምጽአት ላይ ማኖር አለብን። ይህም የጽድቅን ኑሮ እንድንኖር ይረዳናል (1ኛ ዮሐ 2፡28–3፡10)። ሐ) የእግዚአብሔር ልጆች እርስ በርሳቸው በመዋደድ አንድነትን መጠበቅ አለባቸው (1ኛ ዮሐ. 3፡11-24)።

  1. ሐሰተኛና እውነተኛ ትምህርትን፥ እንዲሁም አማኞችን እንዴት መለየት እንደሚቻል (1ኛ ዮሐ 4፡1-5፡21)

ሀ) እውነተኛ አስተማሪዎችና አማኞች በተለይም ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ የሚይዙት አስተምህሮ ትክክለኛ ነው (1ኛ ዮሐ. 4፡1-8)።

ለ) እውነተኛ አስተማሪዎችና አማኞች ሌሎች አማኞችን በመውደድ ለእግዚአብሔር ያላቸውን ፍቅር ይገልጻሉ (1ኛ ዮሐ 4፡7-21)።

ሐ) እውነተኛ አስተማሪዎችና አማኞች በክርስቶስ ኢየሱስ ላይ ትክክለኛ እምነት ሲኖራቸው፥ ከእርሱ ጋር ያላቸው ግንኙነትም የተስተካከለ ነው (1ኛ ዮሐ 5፡1-12)።

መ) እውነተኛ አስተማሪዎችና አማኞች የእግዚአብሔር ልጆች መሆናቸውን ያውቃሉ። ይህንንም በተቀደሰ አኗኗር ያሳያሉ (1ኛ ዮሐ 5፡13-21)።

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading