፩. እውነተኛ አስተማሪዎችና አማኞች በተለይ ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ እውነተኛ አስተምህሮን ይከተላሉ (1ኛ ዮሐ 4፡1-8)
“ወዳጆች ሆይ፥ መንፈስን ሁሉ አትመኑ። ነገር ግን መናፍስት ከእግዚአብሔር ሆነው እንደሆነ መርምሩ ብዙዎች ሐሰተኞች ነቢያት ወደ ዓለም መጥተዋል” (1ኛ ዮሐ 4፡1)። ብዙውን ጊዜ ጥያቄ ማንሣት ወይም አንድን ነገር መገምገም የዐመፀኝነት ወይም የእምነት ማጣት ምልክት ነው ብለን እናስባለን። ነገር ግን መጽሐፍ ቅዱስ አንድ ነገር ከእግዚአብሔር ወይም ከሰይጣን መሆኑን ለማወቅ በሚገባ እንድንገመግም፥ እንድንፈትን በተደጋጋሚ ያዝዘናል። ይህ ትእዛዝ የተሰጠው ለቤተ ክርስቲያን መሪዎች ብቻ አይደለም። አማኞች ሁሉ ከቤተ ክርስቲያን ስብከት፥ ከጓደኞቻቸው፥ ከካሴቶችና ከቪዲዮዎች፥ ከመጻሕፍት፥ ወዘተ.. የሚተላለፈውን መልእክት የመገምገም ኃላፊነት አለባቸው። አንድ ሰው ሐሰተኛ ትምህርት በሚያምንበት ጊዜ፥ የኋላ ኋላ ኃላፊነትን የሚወስደው ራሱ ነው። ምንም እንኳን እግዚአብሔር የቤተ ክርስቲያን መሪዎች መንጋውን ባያስተምሩ ወይ ባይጠብቁ በኃላፊነት የሚጠይቃቸው ቢሆንም፥ ነገሮችን የመገምገም የመጨረሻው ኃላፊነት የሚውለው በእያንዳንዱ ግለሰብ ላይ ነው። ለመሆኑ አንድ ነገር ከእግዚአብሔር ወይም ከሰይጣን መሆኑን ለማወቅ የምንመረምረው ወይም የምንገመግመው እንዴት ነው? ይህ የዮሐንስ መልእክት የመጨረሻው ክፍል ይህን በተመለከተ አንዳንድ አሳቦችን ይሰጠናል።
ሀ) አንድ ሰው ከእግዚአብሔር መሆኑን ያለመሆኑን የምንገመግመው ያቀረበው ትምህርት ከእግዚአብሔር ቃል ጋር መስማማት ያለመስማማቱን በመመልከት ነው። በዮሐንስ ዘመን፥ የክርስቶስን ማንነት የሚጠራጠር ሐሰተኛ ትምህርት ተሰጥቶ ነበር። ይህ ሐሰተኛ ትምህርት ክርስቶስ ፍጹም አምላክ አይደለም ብሎ ያስተምር ነበር። ሌሎች ደግሞ ፍጹም ሰው አይደለም ብለው ያስተምሩ ነበር። በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በግልጽ የቀረበውን ትምህርት የሚቃረን መልእክት የሚያቀርብ ማንኛውም ሰው ይህንኑ አሳብ ያገኘው ከክርስቶስ ተቃዋሚዎች ሁሉ በስተጀርባ ከሚሠራው ሰይጣን ነው። (በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የቀረበውን ግልጽ ትምህርት ከሚጻረሩ አሳቦች መካከል የሚከተሉት ለአብነት ሊጠቀሱ ይችላሉ። መጽሐፍ ቅዱስ ስሕተት የሌለው የእግዚአብሔር ቃል አለመሆኑን፥ ክርስቶስ ብቸኛ አዳኝ ሰውና አምላክ አለመሆኑን፥ ብሎም የሥላሴ አለመኖርን፥ በተጨማሪም ድነት (ደኅንነት)፥ በልሳን መናገር፥ በጥምቀት ወይም አንዳች ተግባር በማከናወን መሆኑን፥ የመጽሐፍ ቅዱስን ግልጽ መልእክቶች በመጻረር ማስተማር ነው።)
ለ) የግለሰቡን ባህሪ በማጥናት ለእግዚአብሔር ቤተ ክርስቲያን መሪዎችና ለእግዚአብሔር ቃል እውነት የሚሰጡትን ግምት በመገምገም አንድ ሰው ከእግዚአብሔር እንደሆነ ወይም እንዳልሆነ እንለያለን። ዮሐንስ ከእግዚአብሔር የተወለዱ ሰዎች «እኛን» ይሰሙናል ይላል። ይህም ዮሐንስን እና ሐዋርያትን፥ እንዲሁም መንፈስ ቅዱስ የመረጣቸውን መሪዎች የሚያመለክት ነው። ከክርስቶስ ወደ ሐዋርያት፥ ከዚያም በቤተ ክርስቲያን ታሪክ ሁሉ እያለፈ እስከ ዛሬ የደረሰ የእውነት መሥመር አለ። ይህም እውነት በአዲስ ኪዳን ውስጥ የሚገኝ ነው። አንድ ነገር እውነት ወይም ውሸት መሆኑን ለመገምገም ትልቁ ምንጭ መጽሐፍ ቅዱስ ነው። እግዚአብሔር በተጨማሪም የቤተ ክርስቲያን መሪዎች እውነትን እንዲጠብቁ ኀላፊነት ሰጥቷቸዋል። ይህም ማለት የቤተ ክርስቲያኑ ልጆች የእግዚአብሔርን ቃል በማጥናት እና የእግዚአብሔርን እውነት በማወቅ ራሳቸውን በጥንቃቄ እንዲዘጋጁ ማድረግ አለበት ማለት ነው። ቃሉን ካላጠኑ፥ እግዚአብሔር የሰጣቸውን ይህን ወሳኝ አገልግሎት ሊያከናውኑ አይችሉም። በተጨማሪም፥ ይህ ማለት የቤተ ክርስቲያን አባላት እውነት ናቸው ብለው የሚያስቧቸውን አዳዲስ ትምህርት በሳል መንፈሳዊ መሪዎችን ሳያማክሩ መቀበል የለባቸውም ማለት ነው። መሪዎቻችንን እና መሪዎቻችን አንድ ትምህርት ከእግዚአብሔር ቃል ጋር መስማማት ያለመስማማቱን እንዲመረምሩ ኃይል የሚሰጣቸውን መንፈስ ቅዱስ ማክበር ይኖርብናል። ሽማግሌዎቹ ሁሉ የእግዚአብሔርን ቃል በግልጽ እስካልጣሱ ድረስ አባላት በመሪዎች ላይ ማመጻቸው የእግዚአብሔር ፈቃድ አይደለም።
፪. እውነተኛ አስተማሪዎች እና አማኞች ሌሎች አማኞችን በመውደድ ለእግዚአብሔር ያላቸውን ፍቅር ያሳያሉ (1ኛ ዮሐ. 4፡9-21)
ሐሰተኛ አስተማሪዎች ብዙውን ጊዜ ከሚታወቁባቸው መንገዶች አንዱ ከትምህርታቸው የተነሣ በአማኞች ኅብረት ውስጥ የሚከሰተውን ሁኔታ በመመልከት ነው። ብዙውን ጊዜ እነዚህ ሐሰተኛ አስተማሪዎች ስለ ሌሎች ወይም ስለ ክርስቲያናዊ አንድነት ግድ የላቸውም። የሚያሳስባቸው ሕዝቡ ትምህርታቸውን መቀበሉ ብቻ ነው። በመሆኑም ዮሐንስ፥ ሐሰተኛ አስተማሪዎችን ለይተን ከምናወቅባቸው ዐበይት መንገዶች አንዱ ከራሳቸው ይልቅ ሌሎች የተሻለ መንገድ እንዲያስቡ በማሰብ በፍቅር እና በርኅራኄ የተሞላ ሕይወት መምራታቸውን ማጤን እንደሆነ ይናገራል። እነዚህ ሰዎች በአማኞች መካከል ከትችት ይልቅ የፍቅርን እና የመቀባበልን መንፈስ እየፈጠሩ ናቸው? ከእግዚአብሔር ከተላኩ፥ ከትምህርታቸውና ከተግባራቸው በስተጀርባ ፍቅር ማቆጥቆጥ አለበት። ትምህርታቸው ከመንፈስ ቅዱስ ከሆነ በአማኞች መካከል ከክፍፍል ይልቅ ፍቅር እና አንድነትን ማስፋፋት ይኖርበታል።
(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)