አማኝ ከሥራ፣ ከመከራ፣ ከበሽታና ከኃጢአት ጋር ያለው ግንኙነት (ያዕ. 4፡13-5፡20)

፩. አማኝ ከሥራ ጋር ያለው ግንኙነት (ያዕ. 4፡13-5፡6)

አንደበት የመንፈሳዊ ሕይወት አንደኛው ቴርሞ ሜትር እንደሆነ ተመልክተናል። በመቀጠልም ያዕቆብ ሌላኛውን የመንፈሳዊ ሕይወት ቴርሞ ሜትር ያብራራል። ይህም ገንዘባችንና ስለ ገንዘባችን እና የሥራ እንቅስቃሴአችን የምናስብበት ነው። ያዕቆብ ስለ ሕይወታችንና ሥራችን በምናቅድበት ጊዜ ልንጠነቀቅ የሚገባንን ሁለት ሁኔታዎችን ያመለክታል።

ሀ) ለወደፊት ዕቅድ የምናወጣው እንዴት ነው? ብዙውን ጊዜ ዕቅዶችን የምናወጣው ለእግዚአብሔር ሳንገዛና ፈቃዱም ምን እንደሆነ ሳንጠይቅ ነው። ያዕቆብ ይህን ችግር ይገልጻል። አንድ ሰው ለእግዚአብሔር ሳይገዛና በፈቃዱ ላይ ሳይደገፍ ስለ ወደፊት ሕይወቱ ዕቅዶችን ያወጣል። ይህንንም በማድረጉ እግዚአብሔር የወደፊቱን ሁኔታ እንደሚወስንና ሕይወትም አጭር መሆኗን ይዘነጋል። ይህ ምን ያህል ሞኝነት ነው! እግዚአብሔር ዕቅዶችን እንድናወጣ ይፈልጋል። ነገር ግን ዕቅድ ከማውጣታችን በፊት ለእግዚአብሔር ፈቃድ ለመገዛት ከጥቅማችን አስቀድመን እግዚአብሔርንና መንግሥቱን መሻት ይኖርብናል (ማቴ. 6፡33)።

ለ) በገንዘብ ላይ ከመጠን በላይ በማተኮር ፍትሕን መርሳት እንደሌለብን፡- ያዕቆብ በጠንካራ ቃላት ሀብታሞችን አስጠንቅቋቸዋል። ከእነዚህም አብዛኞቹ አማኞች አልነበሩም። እነዚህ ሰዎች ክፉዎች የሆኑት ሀብታሞች ስለሆኑ አልነበረም። ሀብታቸውን ለእግዚአብሔር መንግሥት የሚያውሉ እንደ አርማቲየሱ ዮሴፍ ያሉ መንፈሳዊ ሀብታሞች አሉ (ማቴ. 27፡57-59)። ያዕቆብን ያሳሰበው ገንዘብን አምላካቸው አድርገው የሚሰግዱለት ሀብታሞች ናቸው። እነዚህ ሰዎች በሕይወታቸው ገንዘብን ከምንም በላይ ያስበልጡታል። ገንዘቡን ስለሚያገኙበት መንገድና በዚህ ሂደት ውስጥ በሌሎች ሰዎች ላይ ስለሚደርሰው አደጋ ቅንጣት ታክል ሳይጨነቁ ተጨማሪ ገንዘብ ለማግኘት ይፍጨረጨራሉ። በፍጥነት ሀብት ለማካበት ሲሉ የሠራተኞቻቸውን ደመወዝ በአግባቡ አይከፍሉም። ድሆችን ለመርዳት ገንዘብ አይሰጡም። ይልቁንም የግል ጥቅማቸውን ለማበራከት ሲሉ ያገኙትን ሁሉ ይሰበስባሉ። እነዚህ ሰዎች በሚሞቱበት ጊዜ ሀብታቸው ከእነርሱ እንደሚወሰድ ዘንግተዋል። ያዕቆብ ይህን የጻፈው በዘመኑ ድሆችን ይበዘብዙ የነበሩትን ሃብታም ነጋዴዎች በማስመልከት መሆኑ አይጠረጠርም። አንድ ቀን ምናልባትም ያዕቆብ እንደ ነቢይ በስምንት ዓመታት ጊዜ ውስጥ ሮማውያን ኢየሩሳሌምን በማፈራረስ የሀብታም ነጋዴዎችንና ሃይማኖታዊ መሪዎችን ንብረት እንደሚዘርፉ ተረድቶ ይሆናል።

የውይይት ጥያቄ፡- ህ) ብዙ አማኞች በእግዚአብሔር ላይ ሳይደገፉ ለወደፊት ዕቅዶች የሚወጥኑባቸውን መንገዶች ግላጽ። ለ) በገንዘብ ላይ የተሰጠው ከፍተኛ ትኩረት ድሆችን ለመርዳት ወይም ፍትሕን ለማስፈን እንደማያስችል የሕይወት ዘይቤ ሰዎችን ሲመራ የተመለከትክበትን ሁኔታ ግለጽ። አማኝ ከመከራ፥ ከበሽታና ከኃጢአት ጋር ያለው ግንኙነት (ያዕ. 5፡7-20)

፪. አማኝ በመከራ ጊዜያት የሚሰጠው ምላሽ (ያዕ. 5፡7-13)

ሀ) ትዕግሥት፡- በያዕቆብ መልእክት የመጨረሻው ክፍል ውስጥ ጸሐፊው ወደ መከራ ርእሰ ጉዳይ በመመለስ አማኝ ለመከራ ምን ዓይነት ምላሽ መስጠት እንዳለበት ያብራራል። ቀደም ሲል ያዕቆብ በመከራ ጊዜ አማኞች መደሰት እንዳለባቸው ገልጾአል (ያዕ. 1፡3)። አሁን ግን ስለ ትዕግሥት ይጽፋል። የትዕግሥት አመለካከት በሁለት መንገዶች ሊታይ ይችላል። ከእነዚህም መካከል እግዚአብሔርን የሚያስከብረው አንደኛው ብቻ ነው።

በመጀመሪያ፥ ክርስቲያኖችና ሙስሊሞች የሚጋሩት ያመጣብኝን ልቻለው ዓይነት ትዕግሥት አለ። የዚህ ዓይነቱ አመለካከት «እግዚአብሔር የሁሉም ተቆጣጣሪ ነው። እርሱ የፈለገውን ያደርጋል። እኔም ላደርግ የምችለው ያመጣውን መሸከም ብቻ ነው» የሚል ነው። የዚህ ዓይነቱ ትዕግሥት እግዚአብሔር ታላቅና ራቅ ብሎ የሚገኝ፥ ተግባራቱም ለእኛ ትርጉም የማይሰጡ መሆኑን ያመለክታል። ይህ አመለካከት ፍጡራን እንደመሆናችን መጠን እግዚአብሔር የሚያደርገውን ሁሉ መቀበልና እንደተጫነች አህያ ሸክምን ሁሉ መቋቋም እንዳለብን ያሳያል።

ሁለተኛ፥ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ትዕግሥት፥ ፥«አፍቃሪ አባቴ ሁኔታዎችን ሁሉ ስለሚቆጣጠር ከሁሉም የሚሻለውን ነገር ያውቃል። ለልጆቹ ሁሉም ነገር ለበጎ እንደሚደረግ ቃል ገብቶልኛል (ሮሜ 8፡28)። ስለሚወደኝ ክርስቶስን እንድመስል እየለወጠኝ ነው። የሚያስፈልገኝን ሁሉ አይነፍገኝም» የሚል አቋም አለው። መጽሐፍ ቅዱሳዊ ትዕግሥት እግዚአብሔር ነገሮችን በመቆጣጠር ላይ በመሆኑ እና ሁሉን በማወቁ ላይ የተመሠረተ ነው። ይህ አመለካከት እግዚአብሔር አፍቃሪ አምላክ በመሆኑ፥ በረጅም ጊዜ ዕቅድ ለሕይወታችን በሚበጀው ነገር ላይ እንደሚያተኩር ያምናል። ያዕቆብ የሚናገረው ስለዚህ ዓይነቱ ትዕግሥት ነው። ገበሬዎች መሬታቸውን ካረሱና ዘር ከዘሩበት በኋላ ሰብላቸውን ከማጨዳቸው በፊት ለስድስት ወራት በተስፋ መጠባበቅ እንደሚያስፈልጋቸው ሁሉ፥ «እኛም ጨለማ በነገሠባት የመከራ ጊዜ ውስጥ ሆነን እግዚአብሔር ወደፊት ታላቅ ነገር እንደሚያደርግልን በትዕግሥት እንጠባበቃለን። ብዙውን ጊዜ ይህ ሽልማት ወይም ለውጥ የሚመጣው በሚቀጥሉት ሳምንታት፥ ወራት ወይም ዓመታት ውስጥ ሊሆን ይችላል። አንዳንድ ጊዜ ግን እግዚአብሔር እስክንሞት ድረስ መከራ እንድንቀበል ሊያደርግ ይችላል። እንደዚህ ዓይነት ሁኔታ በሚያጋጥመን ጊዜ ተስፋችን የሚያርፈው በመንግሥተ ሰማይ መከራ፥ ሥቃይ ወይም ሞት እንደማይኖር በመገንዘባችን ላይ ይሆናል (ራእይ 21፡3-4)። መከራን በትክክል ካስተናገድን እግዚአብሔር ይሸልመናል።

የውይይት ጥያቄ፡- አንተ ወይም አንተ የምታውቀው ሰው ያለፈበትን የመከራ ጊዜ ግለጽ። ሀ) ይህን የመከራ ጊዜ እግዚአብሔር ያመጣውን ልቻላው በሚል ስሜት ለመጋፈጥ የቻሉት እንዴት ነበር? ለ) ይህንን የመከራ ጊዜ በተስፋ እና መንፈሳዊ ትዕግሥት መጋፈጥ የቻሉትስ እንዴት ነበር?

በመከራ ጊዜ የመታገሥ ምሳሌ የሆነው ያዕቆብ ለአይሁዳውያን አማኞች በመከራ የታገሡትን የእምነት ጀግኖች ይጠቅስላቸዋል። የብሉይ ኪዳን ነቢያት መከራን በትዕግሥት በመጋፈጣቸው ቀዳማይ ጀግኖች ነበሩ። ለምሳሌ ያህል፥ ኢዮብ ካጋጠመው መከራ ሁሉ ባሻገር ከእግዚአብሔር ፊቱን ለመመለስ ባለመፍቀዱ የተከበረ የእግዚአብሔር ሰው ለመሆን በቅቷል። ከእነዚህ የእምነት ጀግኖች ሕይወት የሚመጣው ትምህርት የኋላ ኋላ እግዚአብሔር ርኅራኄንና ምሕረትን በማሳየት በትዕግሥት የሚጠባበቁትን ሰዎች እንደሚሸልም ነው።

ለ) አለማጉረምረም፡- መከራ በምንቀበልበት ጊዜ ብዙዎቻችን እናጉረመርማለን። አንዳንድ ጊዜ መከራ መቀበላችን ፍትሐዊ እንዳልሆነ በመግለጽ በእግዚአብሔር ላይ እናማርራለን። ብዙ ሰዎች የከረረ ፈተና በሚገጥማቸው ጊዜ እምነታቸውን ይተዋሉ። ነገር ግን በአብዛኛው ቁጣችንን በሌሎች ሰዎች ላይ እንገልጻለን። በትዳር ጓደኞቻችን፥ በልጆቻችን፥ ወዘተ… ላይ እናማርራለን። አንዳንድ ሰዎች መራርነት ያጠቃቸዋል። ያዕቆብ ፈራጁ ክርስቶስ በቅርቡ የሚመጣ መሆኑን በመግለጽ፥ በመከራ ጊዜ ለነበረን ባሕሪ ፍርድን እንደሚሰጠን ያስታውሰናል።

ሐ) የቃላችንን እውነተኛነት ለመግለጽ መማል አያስፈልገንም፡- ምንም እንኳን ይህ ከመከራ ጋር ባይገናኝም፥ ያዕቆብ ከእምነትና መሐላ ጋር በተያያዘ አንደበታችንን ስለምንጠቀምበት ሁኔት ያብራራል። ያዕቆብ ይህንን ትእዛዝ ያገኘው ከክርስቶስ መሆኑ አይጠረጠርም (ማቴ. 5፡33-37)። ኢየሱስም ሆነ ያዕቆብ በሰዎች ሕይወት ውስጥ የእውነትን አለመኖር የሚያመለክት አሳብ ነበር ያስተላለፉት። ያዕቆብ ለሰዎች እውነት መናገራችንን ለማረጋገጥ ምንም ዓይነት መሐላ መጠቀም እንደሌለብን ይናገራል። መሐላ የሚያስፈልገው ሰው ንግግራችንን በሚጠራጠርበት ጊዜ ነው። እውነተኛ ሰዎች ከሆንን፥ የምንናገረው ሁሉ እውነት ይሆናል። ስለሆነም አንድ ሰው በሚጠይቀን ጊዜ «አዎ» ብለን እንመልሳለን። ከዚያም ሁኔታዎች፥ ምንም ያህል ባይመቻቹም እንኳን ቃላችንን እንጠብቃለን። አልያም «አይሆንም» ብለን እንመልሳለን። ከዚያም ሰዎች ምንም ያህል ጫና ቢያሳድሩብንም እንኳ በቃላችን እንጸናለን።

መ) ጸሎት፡- በመከራ ጊዜ መታገሥ ማለት አለመጸለይ ማለት አይደለም። ያዕቆብ በመከራ ጊዜ ተግተን መጸለይ እንዳለብን ይነግረናል። ይህ ጸሎት በቀዳሚነት እግዚአብሔር የመከራውን ጊዜ በሕይወታችን ውስጥ ለማከናወን የሚፈልገውን ተግባር ለማከናወን፥ ባህሪያችንን ለመለወጥና እኛን ለበለጠ አገልግሎት ለማዘጋጀት እንዲጠቀምበት የምንጠይቅበት ነው። ፈቃዱ ከሆነ መከራን ከሕይወታችን እንዲያርቀው እንጸልያለን።

ሠ) ማመስገን፡- ጳውሎስ ሁልጊዜም ደስ መሰኘት እንዳለብን ነግሮናል (ፊልጵ. 3፡1)። ለአማኞች (በተለይም በመከራ ውስጥ ላሉ) እግዚአብሔር ቀደም ሲል በሕይወታቸው ውስጥ የፈጸማቸውና አሁንም በመፈጸም ላይ ያለውን መልካም ነገር ማስታወሱ ጠቃሚ ነው። በመከራው ላይ ከማተኮር ይልቅ በረከቶቻችንን መቁጠር ይኖርብናል። ይህንኑ ምሥጋና ለመግለጽ ከሁሉም የሚሻለው መንገድ የምሥጋና መዝሙሮችን መዘመር ነው።

፫. አማኝ በበሽታ ጊዜ የሚሰጠው ምላሽ (ያዕ. 5፡14-18)

በአንድም ሆነ በሌላ ጊዜ፥ አማኞች ሁሉ የሚጋፈጡት አንደኛው የመከራ ዓይነት ሕመም ነው። ለዚህ ዓይነቱ መከራ ምን ዓይነት ምላሽ መስጠት ይኖርብናል? ዝነኛ የፈውስ አገልጋዮችን መሻት ያስፈልገናል? በሐኪሞች ብቻ መታመን አለብን? ምንም እንኳ እግዚአብሔር በሐኪሞች ወይም በፈውስ አገልጋዮች አማካኝነት ፈውሱን ሊያመጣ ቢችልም፥ በምንታመምበት ጊዜ የራሳችን ጸሎትና የሐኪም እርዳታ ሳይፈውሱን ሲቀር ልናደርግ የሚገባን ትክክለኛው ነገር ወደ ቤተ ክርስቲያን ሽማግሌዎች መሄድ ነው። እግዚአብሔር ለቤተ ክርስቲያን ሽማግሌዎች ለመንጋው እንክብካቤ የሚያደርጉላቸውን ሥልጣን ሰጥቷቸዋል። ስለሆነም፥ ግለሰቡ የቤተ ክርስቲያን ሽማግሌዎች መጥተው እንዲጸልዩለት ሊጠራቸው ይገባል። በዚህ ጊዜ ሽማግሌዎች ምን ማድረግ ያስፈልጋቸዋል? ሦስት ነገሮችን ማድረግ የሚያስፈልጋቸው ይመስላል።

ሀ) ሽማግሌዎቹ ታማሚው ኃጢአት ሠርቶ እንደሆነ ሕይወቱን እንዲመረምር መርዳት ይኖርባቸዋል። ምናልባትም በሽታው እግዚአብሔር ግለሰቡን ለመቅጣት የተጠቀመበት መንገድ ሊሆን ይችላል። ነገር ግን ሁሉም በሽታ የኃጢአት ውጤት አይደለም። ስለሆነም ሽማግሌዎች በሽታው የደረሰበት ኃጢአት በመሥራቱ ነው ከሚል ድምዳሜ መድረስ የለባቸውም። ነገር ግን ኃጢአት በሽታን ከሚያስከትሉ መንሥዔዎች አንዱ ስለሆነ ሽማግሌዎቹ አማኙ ሕይወቱን እንዲገመግም ማገዝ ይኖርባቸዋል። በአማኙ ሕይወት ውስጥ ንስሐ ያልተገባበት ኃጢአት ካለና እግዚአብሔርም ለዚያው ኃጢአት እየቀጣው ከሆነ፥ መጸለዩ ፋይዳ የለውም። ለፈውስ ከመጸለይ አስቀድሞ ኃጢአትን መናዘዝ አስፈላጊ ነው። መልካሙ ዜና ግለሰቡ ኃጢአቱን ከተናዘዘና አኗኗሩን ለመቀየር ቃል ከገባ እግዚአብሔር ሙሉ በሙሉ ይቅር ይለዋል። ይህም አንደኛውን የፈውስ መሰናክል ያስወግደዋል።

ለ) ቀጣዩ ደረጃ ታማሚውን በዘይት መቀባት ነው። ክርስቲያኖች ስለዚህ ጉዳይ የተለያዩ ግንዛቤዎች አሏቸው። በጥንቱ ዓለም ውስጥ ዘይት ከዐበይት መድኃኒቶች እንደ አንዱ ይቆጠር ስለነበር (ሉቃስ 10፡33-34 አንብብ)። አንዳንድ ክርስቲያኖች ይህ የሚያመለክተው ሽማግሌዎች ታማሚውን አማኝ ወደ ሐኪም ቤት መውሰድና ሕክምና እንዲያገኝ መርዳት እንደሚገባቸው ነው ይላሉ። ሌሎች ደግሞ ዘይት የመንፈስ ቅዱስ ምልክት ስለሆነ፥ ይህ የሚያሳየው መንፈስ ቅዱስ ግለሰቡን እንዲፈውስ ለመጠየቅ ነው ይላሉ። ምናልባትም ያዕቆብ ለማለት የፈለገው እነዚህ ሁለቱንም ሊሆን ይችላል። የታመመ ሰው መድኃኒት እንዲወስድ ማድረግና ዳሩ ግን ፈውስ የሚመጣው ከእግዚአብሔር መሆኑን መገንዘብ ያሻል። ግለሰቡን የሚፈውሰው ዘይቱ እንዳልሆነ መገንዘቡ ጠቃሚ ነው። የሚፈውሰው የእምነት ጸሎት መሆኑን ያዕቆብ ገልጿል። ዛሬ ዘይት መጠቀም ያስፈልገናል? ምናልባት አያስፈልገንም። ይህ መንፈስ ቅዱስን የሚያመለክት ነው ብለን ካመንን ዘይት መጠቀም ያስፈልገናል? አዎ። ነገር ግን በዘይቱ ውስጥ አንድ ምትሃታዊ ኃይል እንዳለ ወይም ዘይቱን የሆነ ፈዋሽ መባረክ እንዳለበት ወይም ደግሞ የዘይቱ ዓይነት የተለየ መሆን እንዳለበት ማሰብ የለብንም። ይህ ያዕቆብ የፈውስን በር ይከፍታል ብሎ ከሚናገረው ጸሎት የተለየ ነው።

ሐ) ሽማግሌዎች በእምነት መጸለይ ይኖርባቸዋል። በዚህም ጊዜ እግዚአብሔር ጸሎታቸውን ሰምቶ እንደ ፈቃዱ ምላሽ ይሰጣል። ያዕቆብ ከእግዚአብሔር ፈውስ ለማምጣት ይህን ጸሎት እንደሚጠቀም ይናገራል። እግዚአብሔር የሚጠቀመው መድኃኒቱን ወይም ዘይቱን ሳይሆን ጸሎቱን ነው።

ይህ ማለት እግዚአብሔር እነዚህን ሦስት ደረጃዎች ከተከተልን ሁልጊዜም በሽተኞችን ለመፈወስ ይገደዳል ማለት ነው? አይደለም። አንዳንድ ሰዎች ከተጸለየላቸውና ዘይት ከተቀቡ በኋላ እንኳን ላይፈወሱ ወይም ሊሞቱ ይችላሉ። ይህንን ትምህርት በሌሎች የአዲስ ኪዳን ክፍሎች ውስጥ ከቀረቡት ትምህርቶች ጋር ሚዛናዊ ማድረግ ይኖርብናል። በሌሎች ክፍሎች እንደተገለጸው፥ ምንም እንኳን በእግዚአብሔር ላይ እምነት ሊኖረን ቢገባም፥ ሁልጊዜም የእግዚአብሔር ፈቃድ እንዲፈጸም መጠየቅ ይኖርብናል። አንዳንድ ጊዜ ፈውሱ የሚመጣው በሞት በኩል ይሆናል፥ ምክንያቱም በዚህ ጊዜ እግዚአብሔር ባለበት መንግሥተ ሰማይ ከምንም ዓይነት በሽታ ተለይቶ ይኖራል። አንዳንድ ጊዜ ደግሞ እግዚአብሔር አንድን ግለሰብ እንደሚፈውስ ለአንዳንዶች ይናገራል። ይህ ማረጋገጫ የተሰጠው ሰው በሽተኛው እንደሚፈወስ በመተማመን ሊጸልይ ይችላል። አንዳንድ ጊዜ እግዚአብሔር ምን ለማድረግ እንደሚፈልግ አናውቅም። እግዚአብሔር ፈውስን ያመጣል በሚል እምነት ብንጸልይም፥ የእግዚአብሔር መንገዶች ከእኛ የተሻሉና የተለዩም ሊሆኑ እንደሚችሉ መገንዘብ ይኖርብናል።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) አንድ ሰው በሚታመምበት ጊዜ ቤተ ክርስቲያንህ ውስጥ የሚደረገው የተለመደ አሠራር ምንድን ነው? ሽማግሌዎች ተጠርተው ይጸልያሉ? ሽማግሌዎች ተጠርተው ሲመጡ ምን ያደርጋሉ? የታመመው ግለሰብ ወደ ፈውስ አገልጋዮች ይሄዳል? ሐኪም ቤት ይሄዳል? ለ) ያዕቆብ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ተገቢው የፈውስ ንድፍ ምን መሆን አለበት ይላል? ሐ) በዚህ እግዚአብሔር ስለሚፈውስበት መንገድ በተገለጸው ትምህርትና በ1ኛ ቆሮ. 12 ውስጥ በተገለጸው የፈውስ ስጦታ መካከል ያለው ልዩነት ምንድን ነው? መ) ብዙ ሽማግሌዎች በዚህ ዓይነቱ የፈውስ አገልግሎት ውስጥ የማይሳተፉት ለምንድን ነው? ሠ) እግዚአብሔር ሁልጊዜም የሚፈውስ ይመስልሃል? እግዚአብሔር አንድን ሰው ባይፈውስ መልሱ ምንድን ነው ማለት ነው?

መ) እግዚአብሔር በልጆቹ ሕይወት ውስጥ ፈውስን ሊገልጥ ከሚፈልግበት ዐቢይ መንገድ አማኞች ኃጢአታቸውን ተናዝዘው አንዱ ለሌላው እንዲጸልይ በማድረግ ነው? ያዕቆብ በክርስቶስ አካል ውስጥ ስሜታዊ፥ መንፈሳዊና አካላዊ ጤንነት የሚኖረን ሰዎች ኃጢአታቸውን ተናዝዘው ንጹሕ ግንኙነት በሚመሠርቱበት ጊዜ መሆኑን ይናገራል። ይህ ምናልባትም እያንዳንዱን ኃጢአት በቤተ ክርስቲያን ጉባኤ ፊት መናዘዝ አለብን ማለት ላይሆን ይችላል። ነገር ግን በአንድ ሰው ላይ ኃጢአት በምንፈጽምበት ጊዜ ለዚያ ሰው ኃጢአታችንን መናዘዝ ይኖርብናል። ይሁንና ኃጢአታችን በቤተ ክርስቲያን አባላት ሁሉ ላይ ተጽዕኖ ካስከተለ፥ በምእመናኑ ሁሉ ፊት ኃጢአታችንን መናዘዝ ይኖርብናል። ይህም አካላዊ ሕመማችን ብቻ ሳይሆን ግንኙነታችን በሙሉ እንዲፈወስ ያደርጋል። በክርስቶስ አካል ውስጥ አንድ ሰው በሚታመምበት ጊዜ የአካሉ ክፍሎች በሙሉ በጸሎት መሳተፍ ይኖርባቸዋል። እግዚአብሔር ቅዱስና ጻድቅ የሆነውን የልጆቹን ጸሎት ያከብራል። ይህም በኤልያስ ጸሎት ውስጥ ተመልክቷል።

፬. አማኝ በኃጢአት የሚወድቁትን ሰዎች ምን ሊያደርግ ይገባል (ያዕ. 5፡19-20)

አዲስ ኪዳን አማኞች እጅግ የተቀራረበ ኅብረት እንደሚኖራቸውና በንጽሕና በመቆየት እርስ በርሳቸው እንደሚረዳዱ ይጠብቃል። ነገር ግን ተፈጥሮአዊ ዝንባሌአችን ከጋራ ተጠያቂነት ራሳችንን ማራቅ ነው። ኃጢአታችንን ማንም ሰው እንዲያውቀው አንፈልግም። ኃጢአት እየሠራን እያለን አንድ ሰው ስለዚያ ጉዳይ ቢያነሣ እንቆጣለን። ሌላ ሰው ኃጢአት እየሠራ ንስሐ ለመግባት አለመፈለጉን ብናውቅ፥ እናማለን ወይም ትከሻችንን ሰብቀን አስከፊ ሁኔታ ውስጥ እንደገባ እንናገራለን። ያዕቆብ በክርስቶስ አካል ውስጥ አንዱ ለሌላው ኃላፊነት ሊሰማው ይገባል ይላል። ፍቅር ማለት ኃጢአትን መደበቅ ወይም ችላ ማለት አይደለም። ፍቅር ማለት ለምንወደው ሰው ከሁሉም የተሻለውን ነገር እንመኝለታለን ማለት ነው። ይህም ከሁሉም የሚሻለው ነገር ግለሰቡ ከኃጢአቱ ጋር መጋፈጥ፥ መናዘዝና ንስሐ መግባት የሚያስፈልገው መሆኑ ነው። ይህም ከእግዚአብሔር ቅጣት እንዲያመልጡ ይረዳቸዋል። ይህም ቅጣት ሞት ሊሆን ይችላል። ኃጢአቱ ምንም ዓይነት ታላቅ ቢሆንም እግዚአብሔር ይቅር ይላል። ብዙዎቻችን ለአማኞች የዚህ ዓይነት ፍቅር በማሳየት በቅድስና እንዲመላለሱ ብናግዝ፥ አብያተ ክርስቲያኖቻችን ተለውጠው የፍቅርና የንጽሕና ሠገነቶች ይሆኑ ነበር። ይህ ለእግዚአብሔር ምን ያህል ታላቅ ክብር እንደሚያመጣ አስብ!

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) አንድን አማኝ ስለፈጸመው ኃጢአት ተጋፍጠኸው ታውቃለህ? ካልሆነ፥ ለምን? ከሆነ፥ የተከሰተውን ሁኔታ ግለጽ። ለ) ብዙዎቻችን ሰዎችን ስለ ኃጢአታቸው ከመጋፈጥ ይልቅ በኃጢአታቸው እንዲቀጥሉ የምናደርገው እንዴት ነው? ሐ) አንዳችን የሌላውን ኃጢአት ብንጋፈጥና ኃጢአት በምንፈጽምበት ጊዜ ወይም እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ በማንመላለስበት ወቅት ሌሎች ጉድለታችንን እንዲነግሩን ብንጠይቅ፥ አብያተ ክርስቲያኖቻችን እንዴት ይለወጣሉ? መ) በያዕቆብ መጽሐፍ ውስጥ እግዚአብሔር በሚፈልገው መንገድ ስለመኖር የተረዳሃቸው ሌሎች ጠቃሚ ትምህርቶች ምን ምንድን ናቸው?

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading