የፔንታቱክ መጻሕፍት ስሞች በውስጣቸው የሚታይ ታሪክ

የፔንታቱክ መጻሕፍት ስሞች

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) በፔንታቱክ ውስጥ የሚገኙ የአምስቱን መጻሕፍት ስም ዘርዝር። ለ) በግዕዝ የእያንዳንዳቸው ርዕስ ትርጉም ምንድን ነው? የግዕዝ ትርጉሞቻቸውን ካላወቅህ ግዕዝ የሚያውቅ የኦርቶዶክስ ቄስ እንዲረዳህ ጠይቅ። ሐ) ከዚህ ቀደም በመጽሐፍ ቅዱስ ካለህ እውቀት በመነሣት አምስቱ መጻሕፍት እያንዳንዳችው ስለምን እንደሚያስተምሩ በራስህ አባባል ጠቅለል ባለ መልኩ ጻፍ።

በፔንታቱክ ውስጥ አምስት መጻሕፍት ይገኛሉ። ሙሴ እነዚህን አምስት መጻሕፍት በሚጽፍበት ጊዜ ለእያንዳንዱ መጽሐፍ ስም ወይም ርዕስ አልሰጠም ነበር። በኋላ አንዱን መጽሐፍ ከሌላው ለመለየት አይሁድ ለእያንዳንዱ ጥቅልል የራሱ የሆነ ስም ሰጡት። የመጻሕፍቱን ርዕስ ብዙ ጊዜ የሚወስዱት በጥቅሱ ውስጥ ከሚገኘው ከመጀመሪያው ዓረፍተ ነገር መጀመሪያ ቃል ላይ ነበር። ለምሳሌ፡- ዘፍጥ. 1፡1፡- «በመጀመሪያ» … የሚል ቃል እናገኛለን፤ ስለዚህ አይሁድ የመጀመሪያውን የብሉይ ኪዳን መጽሐፍ «መጀመሪያ» አሉት። ኋላም የግሪክ ቋንቋ የሚያውቁ አይሁድ የዕብራይስጡን መጽሐፍ ቅዱስ ወደ ግሪክ ሲተረጉሙትና ሴፕቱዋጀንት የሚባለውን መጽሐፍ ቅዱስ ሲያዘጋጁ የመጽሐፉን ወይም የጥቅሉን ዋና አሳብ በአጭሩ ሊገልጥ የሚችል የራሳቸው የሆነ ርእስ ሰጡት። የእንግሊዝኛውና የአማርኛው የመጽሐፍ ቅዱስ ርእሶች የተገኙት በሴፕቱዋጀንት መጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ከሚገኙት ርእሶች ነው። በአዲሱ የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ ስሞቹን ወደ አማርኛ ከመተርጎም ይልቅ ውስጥ ታዋቂነት ያለውን የግዕዙን ስም እንዲይዝ ተደርጓል።

  1. ዘፍጥረት፡- በአማርኛ ዘፍጥረት የሚለው ቃል የመጣው እግዚአብሔር ሰማይን፥ ምድርንና በውስጧ ያሉትን ነገሮች እንዴት እንደፈጠረ ከሚናገረው ከመጽሐፉ የመጀመሪያ ሁለት ምዕራፎች ነው። የዘፍጥረት መጽሐፍ እግዚአብሔር ዓለምን እንዴት እንደፈጠረ ከመናገር እጅግ የሚበልጥ ነገር ስላቀፈ ይህ ስም ከሁሉ የተሻለና ትክክለኛ ስም አይደለም። በግሪክ «ጀነሲስ» የሚባለው የመጽሐፉ ስም «ጅማሬ» የሚል ትርጉም ያለው ነው። ይህ ስም በዘፍጥረት መጽሐፍ ውስጥ ስለሚገኙት ነገሮች የተሻለ መግለጫ ነው። የዘፍጥረት መጽሐፍ ስለ ፍጥረት ሁሉ ጅማሬ ይነግረናል። ስለ ሰው ልጅ ጅማሬ፥ ስለ ኃጢአትና ስለ ሞት ጅማሬ፥ ስለ ሥልጣኔ ጅማሬ፥ በዓለም ስለሚገኙ የተለያዩ ነገዶች ጅማሬና እግዚአብሔር ከእስራኤል ሕዝብ ጋር ስለገባው ቃል ኪዳን ጅማሬ ይገልጻል። 
  2. ዘጸአት፡- ዘጸአት የሚለው ቃል የአማርኛና የእግሊዝኛ ትርጉም፥ «መልቀቅ» ወይም «መውጣት» ማለት ሲሆን፥ የሚናገረውም እግዚአብሔር የእስራኤልን ሕዝብ ከግብፅ ባርነት እንዴት ነፃ እንዳወጣ ነው፤ ነገር ግን አብዛኛውን የኦሪት ዘጸአት ክፍል እግዚአብሔር በሲና ተራራ ከእስራኤል ሕዝብ ጋር ስለገባው ቃል ኪዳን ይናገራል። 
  3. ዘሌዋውያን፡-. ዘሌዋውያን የሚለው የአማርኛና የእንግሊዝኛ ቃል፥ ሌዋውያን ተብለው ከሚጠሩት ከአንዱ የእስራኤል ነገዶች የተገኘ ነው። ሌዋውያን የካህናት ነገድ ሲሆኑ ስሙም የሚያመለክተው በኦሪት ዘሌዋውያን ከተጻፉ ሕጎች አብዛኛው እነርሱ እግዚአብሔርን እንዴት እንደሚያመልኩና በፊቱም በሥነ ምግባራቸው እንዴት ንጹሐን ሆነው መኖር እንዳለባቸው ለማመልከት፥ በተለይ የተሰጣቸው ስለነበር ነው። ነገር ግን እነርሱ ብቻ ሳይሆኑ የቀሩት እስራኤላውያን በሙሉ ሊከተሉአቸው የሚገባ በርካታ ሕጎችንም በመጽሐፉ ውስጥ እናገኛለን። 
  4. ዘኁልቁ፡- ዘኁልቁ የሚለው የአማርኛና የእንግሊዝኛ ቃል ትርጉም በዚህ መጽሐፍ ውስጥ የእስራኤል ሕዝብ እንዴት ሁለት ጊዜ እንደተቆጠሩ የሚያሳይ ነው። በመጀመሪያ ልክ ግብፅን ለቀው ሲወጡ ብዛታቸውን ለማወቅ ሲባል ተቆጠሩ። ከዚያም ከ40 ዓመታት በኋላ እንደገና ወደ ተስፋይቱ ምድር ለመግባት በተዘጋጁበት ጊዜ ተቆጠሩ። ኦሪት ዘኁልቁ የእስራኤል ሕዝብ ወደ ተስፋይቱ ምድር መግባትን በመቃወማቸው ለ40 ዓመታት በምድረ በዳ ስለመንከራተታቸው ይናገራል። 
  5. ዘዳግም፡- ዘዳግም የሚለው የአማርኛና የእንግሊዝኛ ቃል ሕግን ከመድገም ጋር የተያያዘ ነው። በኦሪት ዘዳግም የእስራኤል ሕዝብ ወደ ተስፋይቱ ምድር ለመግባት በዝግጅት ላይ ነበሩ። ከ40 ዓመታት በፊት በሲና ተራራ እግዚአብሔር ሕግን ለሕዝቡ ሲሰጥ ያልነበረ አዲስ ትውልድ ነበር፤ ስለዚህ ሙሴ ከመሞቱ በፊት ሕጉን ለዚህ አዲስ ትውልድ በድጋሚ ሲሰጥ እናያለን። የኦሪት ዘዳግም አብዛኛው ክፍል እግዚአብሔር ለእስራኤላውያን በሲና ተራራ የገባውን ቃል ኪዳን እንዲፈጽምላቸው መጠበቅ ስለሚገባቸው ሕግጋት የሚናገር ነው።

በፔንታቱክ ውስጥ የሚታይ ታሪክ

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) በፔንታቱክ ውስጥ የተጠቀሰው የመጀመሪያው ታሪካዊ ተግባር ምንድን ነው? (ዘፍጥ. 1፡)። ለ) በፔንታቱክ ውስጥ የተጠቀሰው የመጨረሻ ታሪካዊ ተግባር ምንድን ነው?

በፔንታቱክ ውስጥ ስለ ጥንቱ ታሪክ የሚገልጡ ሦስት መጻሕፍት አሉ፤ እነዚህ መጻሕፍት ዘፍጥረት፥ ዘጸአትና ዘኁልቁ ናቸው። በፔንታቱክ የተጠቀሰው የመጀመሪያው የዓለም አፈጣጠር ታሪክ ነው። እግዚአብሔር ዓለምን የፈጠረው መቼ እንደሆነ አናውቅም። ይህን በተመለከተ ምሁራን የተለያየ አስተሳሰብ አላቸው። አንዳንዶቹ ይህ የሆነው በ4000 ዓ.ዓ. ገደማ ነበር ይላሉ። ሌሎች ደግሞ ከ10000 ዓመታት ወይም ከዚያ በፊት ሊሆን ይችላል ይላሉ። ከዘፍጥ. 1-11 ድረስ ያለው ታሪክ መቼ እንደተፈጸመ በትክክል ለማወቅ አይቻልም። በፔንታቱክ ውስጥ ከሚገኙት ታሪኮች መካከል በትክክል ቀኑን ልንገምት የምንችልበት የመጀመሪያ ታሪክ የአብርሃም ሕይወት ታሪክ ነው። አብርሃም የኖረው በ2150 ዓ.ዓ. ገደማ ሲሆን የዘፍጥረት መጽሐፍ ታሪክ ያከተመው በ1800 ዓ.ዓ. አካባቢ ነበር። የቀሩት የፔንታቱክ መጻሕፍት ታሪክ ሙሴ ከተወለደበት ከ1525 ዓ.ዓ. ጀምሮ ሕዝቡ ነጻ እስከወጡበት እስከ 1440፥ ከዚያም እስከ ሙሴ ሞት ድረስ 1400 ዓ.ዓ. ይቀጥላል።

ፔንታቱክ የተጻፈበት ጊዜ

የፔንታቱክ አብዛኛው ክፍል የተጻፈው የእስራኤል ሕዝብ በምድረ በዳ በተንከራተቱባቸው ዓመታት ነው። ስለዚህ ሁሉም መጻሕፍት ማለትም ዘፍጥረት፥ ዘጸአት፥ ዘሌዋውያን፥ ዘኁልቁና ዘዳግም የተጻፉት ከ1446-1406 ዓ.ዓ. ነው።

ይሁን እንጂ በፔንታቱክ የተጻፉ ታሪካዊ ድርጊቶች የተፈጸሙባቸውን ጊዜያት ለመወሰን ስንሞክር አንድ ዐቢይ ችግር ይገጥመናል። ይህ ችግር የሚነሣው በዘጸአት ውስጥ በዕብራይስጡና በግሪኩ መጽሐፍ ቅዱስ መካከል ባለ የአንድ ጥቅስ ልዩነት ምክንያት ነው። የዕብራይስጡ መጽሐፍ ቅዱስ በዘጸ. 12፡40 አይሁድ በግብፅ ለ430 ዓመታት እንደነበሩ ይናገራል። የግሪኩ መጽሐፍ ቅዱስ ግን ለ215 ዓመታት ነበሩ ይላል። 430 ዓመታት የሚለው በይበልጥ ትክክል ሳይሆን አይቀርም (1ኛ ነገሥት 6፡1 ተመልከት)። በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የቁጥሮችን ወይም የታሪኮችን ትክክለኛነት የማይቀበሉ አንዳንድ ምሁራን ወደኋላ ያደርጉታል።

የፔንታቱክ ታሪክ የተፈጸመው በሦስት የዓለም ክፍሎች ነው። የተጀመረው ከዘፍ. 1-11 ያለው ታሪክ በተፈጸመበትና የዔድን ገነት ባለበት መስጴጦምያ ነው። የእስራኤል ሕዝብ አባት የሆነው አብርሃም የመጣው ከመስጴጦምያ ሲሆን የይስሐቅና የያዕቆብ ሚስቶችም የመጡት ከዚሁ አገር ነበር። ከዚያም ታሪኩ ሦስቱ ዋና ዋና የእስራኤል ሕዝብ አባቶች አብርሃም፥ ይስሐቅና ያዕቆብ በእንግድነት ወደኖሩባት፥ እግዚአብሔር ለእነርሱና ለዘራቸው ሊሰጥ ቃል ወደገባላቸው ወደ ከነዓን ምድር ያመራል። በመጨረሻ ታሪኩ ስለ ጥቂቱ የያዕቆብ ቤተሰብ (70 ሰዎች) እንዴት ወደ ግብፅ እንደሄዱና ቁጥራቸው ወደ 2 ሚሊዮን አድጎ ታላቅ ሕዝብ እንደሆኑ ይነግረናል። ሕዝቡ ግን ባልተጠበቀ ሁኔታ የግብፅን የባዕድ አምልኮት ባሕል ለመዱ፤ የጣዖት አምልኮአቸውንም ተማሩ (ዘጸ. 32፡1-10)። እናም ግብፅን እንደራሳቸው አገር አድርገው መቁጠር ጀመሩ (ዘኁ. 11፡4-6)።

የውይይት ጥያቄ፥ በዚህ ዘመን ያለን ክርስቲያኖች በምድር ላይ በእንግድነት እንድንኖር የሚገባን ቢሆንም እንኳ ብዙ ጊዜ የባዕድ አምልኮዎችን ልማድ የምንለማመደው እንዴት ነው? (ዕብ. 11፡13 ና 1ኛ ጴጥ. 1፡1 ተመልከት)። 

የፔንታቱክ አብዛኛው ታሪክ የሚያተኩረው የተመረጡት የእግዚአብሔር ሕዝብ ማለት እስራኤላውያን ከዓመታት የባርነት ቆይታ በኋላ ወደ ተስፋይቱ ምድር እንዴት እንደተመለሱ ነው። የፔንታቱክ ታሪክ የሚያበቃው በዘዳግ. 34 ስለ ሙሴ ሞት በተጻፈው ትረካ ነው።

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

%d bloggers like this: