የሕይወት እንጀራ አገልግሎት

የብሉይ ኪዳን ጥናት መግቢያ

በፔንታቱክ ውስጥ የሚገኙ የሥነ ጽሑፍ ዓይነቶች

ፔንታቱክ በአንድ ጸሐፊ (ሙሴ) የተጻፈ የቅዱሳት መጻሕፍት አንድ ክፍል ቢሆንም፥ በውስጡ አራት የተለያዩ የሥነ-ጽሑፍ ዓይነቶች ይገኛሉ፡፡ አንድ የተወሰነ ክፍል ወስደን ለመተርጎም በምናጠናበት ጊዜ ሰሚገባ እንተረጉመው ዘንድ የሥነ-ጽሑፍ ዓይነት ወስነን በዚያው መልክ መተርጎም ይገባናል። በፔንታቱክ ውስጥ አራት ዋና ዋና የሥነ-ጽሑፍ ዓይነቶች ይገኛሉ። ፩. የታሪክ ጽሑፎች፡- በብሉይ ኪዳን ውስጥ በብዛት የምናገኘው የሥነ -ጽሑፍ ዓይነት የታሪክ ጽሑፍ ወይም ትረካ ነው። መጽሐፍ ቅዱሳችንን በአጠቃላይ በሚመለከትም ይህ እውነት ነው። የብሉይ ኪዳንን ሥነ ጽሑፍ ስንመለከት ከመቶ አርባው እጅ (40%) ትረካ ነው። በታሪክ ጽሑፎች ውስጥ የቅዱሳት መጻሕፍት ጸሐፊው ማንኛውም ሰው በሚረዳው በቀላል ቋንቋ ታሪኩን ይተርካል። የሚናገረውም ምን እንደተፈጸመ ነው። ይህም ሆኖ መጽሐፍ ቅዱስን ልዩ የሚያደርገው የሚናገረው ታሪክ ተራ ያለመሆኑ ነው። ታሪኮቹ የተጻፉት በድሮ ጊዜ ምን እንደተፈጸመ ሊነግሩን ብቻ አይደለም። የውይይት ጥያቄ፥ ሮሜ 15፡4 እና 1ኛ ቆሮ. 10፡11 አንብብ። የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪኮች ዛሬ ለእኛ ያላቸው ዓላማ ምንድን ነው? እንዳንድ ምሁራን የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክን «የድነት (ደኅንነት) ታሪክ» ብለው ይጠሩታል። ሌሎች ደግሞ «የእግዚአብሔር ታሪክ» ይሉታል። የታሪክ ጽሑፎች ዋና ዓላማ እግዚአብሔር በፍጥረት ውስጥና በሕዝቡ መካከል ሲሠራ ማሳየት ነው። በመጽሐፍ ቅዱስ ዳር እስከ ዳር የምናየው አንድ ዋና ዓላማ እግዚአብሔር በታሪክ ውስጥ በተለያዩ ሰዎች ሕይወትና በልዩ ነገድ ውስጥ ሲሠራ ድነትን (ደኅንነትን) እየገለጠ መሆኑን ነው፤ ስለዚህ መጽሐፍ ቅዱስ የሚናገረው ከዚህ በፊት ስለተፈጸሙት እውነተኛ ታሪካዊ ክስተቶች ቢሆንም ጸሐፊው ስለ እነርሱ በሚጽፍበት ጊዜ ሁለት ዓላማዎችን ይዞ ነበር። የመጀመሪያው፥ ባለፈው ጊዜ ምን እንደተፈጸመ በትክክል መናገር ሲሆን፥ ሁለተኛው ደግሞ፥ የእግዚአብሔር ሰዎች ባለፉት ጊዜያት ከኖሩት ሰዎች አዎንታዊ ወይም አሉታዊ ምሳሌነት በመማር እግዚአብሔርን ደስ የሚያሰኝ ሕይወት እንዴት መኖር እንደሚችሉ ለማሳየት ነው። ለምሳሌ፡- ሳምሶን በአሉታዊ ምሳሌነቱ ትምህርት ልናገኝበት ለምንችለው ታሪክ አንድ ጥሩ ምሳሌ ነው (መሳ. 13-16)። ክርስቲያኖች እንደመሆናችን፥ ሳምሶን በፍትወተ ሥጋ ኃጢአት በመውደቁ ሕይወቱን እንዴት እንዳጠፋ በመመልከት። ሕይወታችንና አገልግሎታችን እንዳይበላሽ በፍትወተ ሥጋ ኃጢአት እንዳንወድቅ መጠንቀቅ እንዳለብን እንማራለን።  የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) አንዳንድ ክርስቲያን መሪዎች ሳምሶን በወደቀበትአኳኋን የሚወድቁት እንዴት ነው? ለ) ከሳምሶን ሕይወት መጥፎ ምሳሌነት ምን ሊማሩ ይገባ ነበር?  ከታሪኮች በጎ ምሳሌነትም ልንማር ይገባናል። ለምሳሌ፥ አብርሃም ይስሐቅን ለመሠዋት ከፈቀደበት ታሪክ እግዚአብሔር ከማንኛውም ነገር ይልቅ ከቤተሰባችንም በላይ እንዴት እርሱን መውደድ እንዳለብን እንደሚፈልግ እንማራለን (ዘፍ. 22)። የብሉይ ኪዳንን ታሪካዊ ክፍሉች የምንተረጉምባችው በርካታ መመሪያዎች አሉ። ከዚህ በታች የተሰጡት እግዚአብሔር ከታሪክ ውስጥ ምን ሊያስተምረን እንደሚፈልግ ለመረዳት እንድንችል ሁል ጊዜ በአእምሮአችን ውስጥ ልንጠብቃችው ከሚገቡን ነገሮች ጥቂቶቹ ናቸው። የብሉይና የአዲስ ኪዳን ታሪኮችን መረዳት የሚገባን በሦስት የተለያዩ ደረጃዎች ነው። በመጀመሪያ፥ እያንዳንዱ ታሪክ ከፍተኛ ደረጃ አለው። ታሪኩ በዚህ ደረጃው ስለ እግዚአብሔር ሰፊ ነገር ያስተምረናል። በዚህ ደረጃ ጸሐፊው ሊነግረን የሚፈልገው፥ እግዚአብሔር በአንድ ሕዝብ ወይም በግለሰቦች ሕይወት ውስጥ ሊሠራ ያለውን ዓለም አቀፋዊ ዕቅድ ነው። አብዛኛው የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ ስለ እግዚአብሔር አካላዊ ሕልውና፥ ዓለምን ስለ መፍጠሩ፥ ስለ ሰው ልጅ ክፋትና በእግዚአብሔር ስለ መቤዠት አስፈላጊነት አንዳንድ ነገሮችን ያስተምረናል። ይህ ከፍተኛ ደረጃ እግዚአብሔር ሁሉን ነገር ለማስተካከል ስለ ሚሰጠው መሢሕም ይናገራል። የውይይት ጥያቄ፥ አንድ የብሉይ ኪዳን ታሪክ ምረጥ። ይህ የመረጥከው ታሪክ (ስለ እግዚአብሔር ባሕርይና ዓላማ፥ ከሰው ልጅ ጋር አብሮ ስለ መሥራቱ፥ ለስው ልጅ ኃጢአተኛነት ወይም እግዚአብሔር የሰውን ልጅ ለመዋጀት ስላለው ዕቅድ ምን ያስተምረናል? ሁለተኛው፥ የታሪኩ መካከለኛ ክፍል ነው። ይህ ደረጃ ማዕከላዊ የሚያደርገው በብሉይ ኪዳን የእግዚአብሔር ሕዝብ የነበሩትን እስራኤልን ነው። በአዲስ ኪዳን ይህ ደረጃ የሚያተኩረው በኢየሱስና በቤተ ክርስቲያን ጅማሬ ላይ ነው። የብሉይ ኪዳን ታሪክ የሚያተኩረው በእስራኤል ሕዝብ አካባቢ ነው። የእስራኤል ሕዝብ በአብርሃምና በዘሮቹ እንዴት እንደተጀመረ በዘፍጥረት እናነባለን። ከዘጸአት ጀምሮ እስከ 2ኛ ዜና ባለው ክፍል ደግሞ እግዚአብሔር ለእስራኤል ሕዝብ የተስፋይቱን ምድር እንዴት እንደሰጣቸው፥ በዳዊት በኩል የተሳካላቸው ሕዝብ አድርጎ እንዴት እንደለወጣችው፥ ሕዝቡ እንዴት በኃጢአት እንደወደቁና እግዚአብሔር እንደቀጣቸው እንመለከታለን። አብዛኛውን ጊዜ የብሉይ ኪዳን ታሪኮች እግዚአብሔር ከእስራኤል ሕዝብ ጋር እንዴት ይሠራ እንደነበረ ያመለክታሉ። ስለዚህ አንድን ታሪክ በምናጠናበት ጊዜ እግዚአብሔር ስለ እስራኤል ሕዝብ ምን እንደሚል መገመት አለብን። የውይይት ጥያቄ፥ ሌላ የብሉይ ኪዳን ታሪክ ምረጥ። ያ ታሪክ በእስራኤል ሕዝብ አጠቃላይ ታሪክ ላይ ምን የሚጨምረው ነገር አለ? ሦስተኛው፥ የእስራኤልን ሕዝብ ታሪክ የተሟላ የሚያደርጉት የግለሰቦች ታሪኮች አሉ። የአብርሃም፥ የሙሴ፥ የዳዊት፥ ወዘተ ታሪኮች ተጽፈው ይገኛሉ። ከእነዚህ ታሪኮች በርካታ መንፈሳዊ እውነቶችን እንማራለን። እያንዳንዱ የግለሰብ ታሪክ የመጽሐፍ ቅዱስ ትረካ የተመሠረተበት ነው። ጸሐፊው የእያንዳንዱን ግለሰብ ታሪክ ሲጽፍ ትልቅ ዓላማ ነበረው። ሊነግረን የፈለገው የእስራኤልን ሕዝብ ታሪክ ቢሆንም፥ የእያንዳንዱ ግለሰብ ታሪክ የሚጫወተው ትልቅ ሚና አለው፤ ነገር ግን ከዚህም በላይ ጸሐፊው ሊነግረን የፈለገው ስለ እግዚአብሔርና ከሰዎች ጋር ስላለው ግንኙነት ነው። ስለ እግዚአብሔር ማስተማር         ስለ እስራኤል ማስተማር                  ስለ ግለሰቦች ማስተማር የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪኮች በትምህርት ቤት እንደምናጠናቸው ዓይነት የጥንት ሰዎች ታሪክ ብቻ አይደሉም። ይልቁንም እግዚአብሔርን ለመግለጥና ለሰዎች በሰዎች በኩል ምን እንዳደረገ የሚነግሩን ናቸው። የመጽሐፍ ቅዱስ ትኩረት በእግዚአብሔር ላይ እንጂ ሰዎች ባደረጉት ነገር ላይ አይደለም።  በብሉይ ኪዳን የታሪክ ጽሑፎች ውስጥ የቃላትን ተምሳሌታዊ ትርጉም መፈለግ የለብንም። ታሪኩን ልክ ተጽፎ እንዳለ በቀጥታ ለመረዳት መሞከር ያሻል። ይህም ማለት ድርጊቱ በተፈጸመበት ታሪካዊ መሠረት ልንረዳው ያስፈልጋል ማለት ነው። ለመረዳት የማንችላቸው ባሕላዊ ነገሮች ካሉ ለመረዳት መሞከር አለብን። አንድን ታሪክ ከመተርጎማችን በፊት ባሕላዊ ነገሮችን ስለ መረዳት አስፈላጊነት ጥሩ ምሳሌ የሚሆንን ቦዔዝ በምሽት መጎናጸፊያውን በሩት ላይ ስለማኖሩ የሚናገረው ታሪክ ነው። በአይሁድ ባሕል ይህ አንድ ሰው የማግባት መግለጫ ነው (ሩት 3፡9)። እነዚህን የተለያዩ ባሕላዊ ተግባሮች ለመረዳት ካልቻልን፥ በታሪኩ ውስጥ ልንረዳቸው የማንችላቸው በርካታ ነገሮች ይኖሩና የእግዚአብሔርን ሥራና በታሪኩ ውስጥ በተመለከትነው መንገድ አንድን ነገር የፈጸመበትን ምክንያት ምን እንደሆነ ሳንረዳ እንቀራለን። ታሪኩን ለማሟላት አንዳንድ ነገሮችን በመገመት የራሳችንን አስተሳሰብ እንዳንጨምር መጠንቀቅ አለብን። አንዳንድ ጊዜ የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪኮች ዋናውን ትምህርት በቀጥታ አያስተምሩም። እንደ አንዳዶቹ የመጽሐፍ ቅዱስ የማስተሪያ ክፍሎች፥ (ለምሳሌ፡- ሮሜ) እግዚአብሔር እንድናውቅ የሚፈልገውን ነገር በቀጥታ አይናገሩም። ይልቁንም በታሪኩ ውስጥ ያለውን ትምህርት የምናገኘው በተዘዋዋሪ መንገድ ነው። ብዙውን ጊዜ ታሪኮቹ በሌላ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል የሚገኙ ቀጥተኛ ትምህርቶችን ይገልጻሉ። ለምሳሌ፡- በዳዊትና በቤርሳቤህ ታሪክ ውስጥ ዝሙት ስሕተት እንደሆነ በቀጥታ አልተናገረም። ይህ ዘጸ. 20፡14 ላይ በቀጥታ ተነግሯል። ይህ ታሪክ ግን በተዘዋዋሪ መንገድ እግዚአብሔር ዝሙትን እንደሚጠላ ያስተምራል። እያንዳንዱን ታሪክ ለሥነ- ምግባር ወይም ለማስተማሪያነት ከመፈፈለግ ይልቅ አንድ ታሪክ የሌላ ትልቅ ታሪክ ክፍል አካል መሆኑንና ዋናው ትኩረቱም የትልቁን ታሪክ ዋና ትምህርት ማግኘት እንጂ ትንሹ ታሪክ ላይ እንዳልሆነ ልናስታውስ ያስፈልገናል። በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሚገኙ ታሪኮች እያንዳንዳቸው መንፈሳዊ መመሪያን ለማስተማር የተመረጡ ናቸው። የመጽሐፍ ቅዱስ ጸሐፊዎች ሊጠቀሙባቸው የሚችሉ በርካታ ታሪኮች ነበሩ። አንድን ታሪክ በተለይ የመረጡበት ምክንያት ምንድን ነው? ምክንያቱም እነዚያ ታሪኮች የሥነ ምግባር ወይም መንፈሳዊ ትምህርት ለማስተማር የተመረጡ ነበሩ፤ ስለዚህ አንድ ታሪክ በባሕላዊ መልኩ አንድ ጊዜ በግልጽ ከተረዳነው በኋላ ከታሪኩ የሚገኘውን ዋና መንፈሳዊ ትምህርት መፈለግ አለብን። ይህ ትምህርት ብዙ ጊዜ የሚገኘው በታሪኩ ውስጥ የሚገኙ ሰዎች ባደረጉት ምርጫ ወይም በፈጸሙት ተግባር ነው። ታሪኩን በመረዳት ሂደት ውስጥ ራሳችንን በውስጡ በማስገባት በዚያን ጊዜ የምንኖር ብንሆን ኖሮ ምን ይሰማን ወይም ምን እናደርግ ነበር? ብሎ መጠየቅ ብዙ ጊዜ በጣም ጠቃሚ ነው። በትረካው ጽሑፍ ውስጥ ጸሐፊው የተፈጸመውን ነገር በትክክል የሚገልጽ መሆኑን መገንዘብ መልካም ነው። እርሱ ይህ ጥሩ ነው ላይል ይችላል። ለምሳሌ፡- በዘፍ. 38 ይሁዳ ሴተኛ አዳሪ ናት ብሎ ከገመታት ሴት ጋር እንደ አመነዘረ እናነባለን። ይህ ስሕተት

በፔንታቱክ ውስጥ የሚገኙ የሥነ ጽሑፍ ዓይነቶች Read More »

የፔንታቱክ መጻሕፍት ስሞች በውስጣቸው የሚታይ ታሪክ

የፔንታቱክ መጻሕፍት ስሞች የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) በፔንታቱክ ውስጥ የሚገኙ የአምስቱን መጻሕፍት ስም ዘርዝር። ለ) በግዕዝ የእያንዳንዳቸው ርዕስ ትርጉም ምንድን ነው? የግዕዝ ትርጉሞቻቸውን ካላወቅህ ግዕዝ የሚያውቅ የኦርቶዶክስ ቄስ እንዲረዳህ ጠይቅ። ሐ) ከዚህ ቀደም በመጽሐፍ ቅዱስ ካለህ እውቀት በመነሣት አምስቱ መጻሕፍት እያንዳንዳችው ስለምን እንደሚያስተምሩ በራስህ አባባል ጠቅለል ባለ መልኩ ጻፍ። በፔንታቱክ ውስጥ አምስት መጻሕፍት ይገኛሉ። ሙሴ እነዚህን አምስት መጻሕፍት በሚጽፍበት ጊዜ ለእያንዳንዱ መጽሐፍ ስም ወይም ርዕስ አልሰጠም ነበር። በኋላ አንዱን መጽሐፍ ከሌላው ለመለየት አይሁድ ለእያንዳንዱ ጥቅልል የራሱ የሆነ ስም ሰጡት። የመጻሕፍቱን ርዕስ ብዙ ጊዜ የሚወስዱት በጥቅሱ ውስጥ ከሚገኘው ከመጀመሪያው ዓረፍተ ነገር መጀመሪያ ቃል ላይ ነበር። ለምሳሌ፡- ዘፍጥ. 1፡1፡- «በመጀመሪያ» … የሚል ቃል እናገኛለን፤ ስለዚህ አይሁድ የመጀመሪያውን የብሉይ ኪዳን መጽሐፍ «መጀመሪያ» አሉት። ኋላም የግሪክ ቋንቋ የሚያውቁ አይሁድ የዕብራይስጡን መጽሐፍ ቅዱስ ወደ ግሪክ ሲተረጉሙትና ሴፕቱዋጀንት የሚባለውን መጽሐፍ ቅዱስ ሲያዘጋጁ የመጽሐፉን ወይም የጥቅሉን ዋና አሳብ በአጭሩ ሊገልጥ የሚችል የራሳቸው የሆነ ርእስ ሰጡት። የእንግሊዝኛውና የአማርኛው የመጽሐፍ ቅዱስ ርእሶች የተገኙት በሴፕቱዋጀንት መጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ከሚገኙት ርእሶች ነው። በአዲሱ የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ ስሞቹን ወደ አማርኛ ከመተርጎም ይልቅ ውስጥ ታዋቂነት ያለውን የግዕዙን ስም እንዲይዝ ተደርጓል። ዘፍጥረት፡- በአማርኛ ዘፍጥረት የሚለው ቃል የመጣው እግዚአብሔር ሰማይን፥ ምድርንና በውስጧ ያሉትን ነገሮች እንዴት እንደፈጠረ ከሚናገረው ከመጽሐፉ የመጀመሪያ ሁለት ምዕራፎች ነው። የዘፍጥረት መጽሐፍ እግዚአብሔር ዓለምን እንዴት እንደፈጠረ ከመናገር እጅግ የሚበልጥ ነገር ስላቀፈ ይህ ስም ከሁሉ የተሻለና ትክክለኛ ስም አይደለም። በግሪክ «ጀነሲስ» የሚባለው የመጽሐፉ ስም «ጅማሬ» የሚል ትርጉም ያለው ነው። ይህ ስም በዘፍጥረት መጽሐፍ ውስጥ ስለሚገኙት ነገሮች የተሻለ መግለጫ ነው። የዘፍጥረት መጽሐፍ ስለ ፍጥረት ሁሉ ጅማሬ ይነግረናል። ስለ ሰው ልጅ ጅማሬ፥ ስለ ኃጢአትና ስለ ሞት ጅማሬ፥ ስለ ሥልጣኔ ጅማሬ፥ በዓለም ስለሚገኙ የተለያዩ ነገዶች ጅማሬና እግዚአብሔር ከእስራኤል ሕዝብ ጋር ስለገባው ቃል ኪዳን ጅማሬ ይገልጻል።  ዘጸአት፡- ዘጸአት የሚለው ቃል የአማርኛና የእግሊዝኛ ትርጉም፥ «መልቀቅ» ወይም «መውጣት» ማለት ሲሆን፥ የሚናገረውም እግዚአብሔር የእስራኤልን ሕዝብ ከግብፅ ባርነት እንዴት ነፃ እንዳወጣ ነው፤ ነገር ግን አብዛኛውን የኦሪት ዘጸአት ክፍል እግዚአብሔር በሲና ተራራ ከእስራኤል ሕዝብ ጋር ስለገባው ቃል ኪዳን ይናገራል።  ዘሌዋውያን፡-. ዘሌዋውያን የሚለው የአማርኛና የእንግሊዝኛ ቃል፥ ሌዋውያን ተብለው ከሚጠሩት ከአንዱ የእስራኤል ነገዶች የተገኘ ነው። ሌዋውያን የካህናት ነገድ ሲሆኑ ስሙም የሚያመለክተው በኦሪት ዘሌዋውያን ከተጻፉ ሕጎች አብዛኛው እነርሱ እግዚአብሔርን እንዴት እንደሚያመልኩና በፊቱም በሥነ ምግባራቸው እንዴት ንጹሐን ሆነው መኖር እንዳለባቸው ለማመልከት፥ በተለይ የተሰጣቸው ስለነበር ነው። ነገር ግን እነርሱ ብቻ ሳይሆኑ የቀሩት እስራኤላውያን በሙሉ ሊከተሉአቸው የሚገባ በርካታ ሕጎችንም በመጽሐፉ ውስጥ እናገኛለን።  ዘኁልቁ፡- ዘኁልቁ የሚለው የአማርኛና የእንግሊዝኛ ቃል ትርጉም በዚህ መጽሐፍ ውስጥ የእስራኤል ሕዝብ እንዴት ሁለት ጊዜ እንደተቆጠሩ የሚያሳይ ነው። በመጀመሪያ ልክ ግብፅን ለቀው ሲወጡ ብዛታቸውን ለማወቅ ሲባል ተቆጠሩ። ከዚያም ከ40 ዓመታት በኋላ እንደገና ወደ ተስፋይቱ ምድር ለመግባት በተዘጋጁበት ጊዜ ተቆጠሩ። ኦሪት ዘኁልቁ የእስራኤል ሕዝብ ወደ ተስፋይቱ ምድር መግባትን በመቃወማቸው ለ40 ዓመታት በምድረ በዳ ስለመንከራተታቸው ይናገራል።  ዘዳግም፡- ዘዳግም የሚለው የአማርኛና የእንግሊዝኛ ቃል ሕግን ከመድገም ጋር የተያያዘ ነው። በኦሪት ዘዳግም የእስራኤል ሕዝብ ወደ ተስፋይቱ ምድር ለመግባት በዝግጅት ላይ ነበሩ። ከ40 ዓመታት በፊት በሲና ተራራ እግዚአብሔር ሕግን ለሕዝቡ ሲሰጥ ያልነበረ አዲስ ትውልድ ነበር፤ ስለዚህ ሙሴ ከመሞቱ በፊት ሕጉን ለዚህ አዲስ ትውልድ በድጋሚ ሲሰጥ እናያለን። የኦሪት ዘዳግም አብዛኛው ክፍል እግዚአብሔር ለእስራኤላውያን በሲና ተራራ የገባውን ቃል ኪዳን እንዲፈጽምላቸው መጠበቅ ስለሚገባቸው ሕግጋት የሚናገር ነው። በፔንታቱክ ውስጥ የሚታይ ታሪክ የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) በፔንታቱክ ውስጥ የተጠቀሰው የመጀመሪያው ታሪካዊ ተግባር ምንድን ነው? (ዘፍጥ. 1፡)። ለ) በፔንታቱክ ውስጥ የተጠቀሰው የመጨረሻ ታሪካዊ ተግባር ምንድን ነው? በፔንታቱክ ውስጥ ስለ ጥንቱ ታሪክ የሚገልጡ ሦስት መጻሕፍት አሉ፤ እነዚህ መጻሕፍት ዘፍጥረት፥ ዘጸአትና ዘኁልቁ ናቸው። በፔንታቱክ የተጠቀሰው የመጀመሪያው የዓለም አፈጣጠር ታሪክ ነው። እግዚአብሔር ዓለምን የፈጠረው መቼ እንደሆነ አናውቅም። ይህን በተመለከተ ምሁራን የተለያየ አስተሳሰብ አላቸው። አንዳንዶቹ ይህ የሆነው በ4000 ዓ.ዓ. ገደማ ነበር ይላሉ። ሌሎች ደግሞ ከ10000 ዓመታት ወይም ከዚያ በፊት ሊሆን ይችላል ይላሉ። ከዘፍጥ. 1-11 ድረስ ያለው ታሪክ መቼ እንደተፈጸመ በትክክል ለማወቅ አይቻልም። በፔንታቱክ ውስጥ ከሚገኙት ታሪኮች መካከል በትክክል ቀኑን ልንገምት የምንችልበት የመጀመሪያ ታሪክ የአብርሃም ሕይወት ታሪክ ነው። አብርሃም የኖረው በ2150 ዓ.ዓ. ገደማ ሲሆን የዘፍጥረት መጽሐፍ ታሪክ ያከተመው በ1800 ዓ.ዓ. አካባቢ ነበር። የቀሩት የፔንታቱክ መጻሕፍት ታሪክ ሙሴ ከተወለደበት ከ1525 ዓ.ዓ. ጀምሮ ሕዝቡ ነጻ እስከወጡበት እስከ 1440፥ ከዚያም እስከ ሙሴ ሞት ድረስ 1400 ዓ.ዓ. ይቀጥላል። ፔንታቱክ የተጻፈበት ጊዜ የፔንታቱክ አብዛኛው ክፍል የተጻፈው የእስራኤል ሕዝብ በምድረ በዳ በተንከራተቱባቸው ዓመታት ነው። ስለዚህ ሁሉም መጻሕፍት ማለትም ዘፍጥረት፥ ዘጸአት፥ ዘሌዋውያን፥ ዘኁልቁና ዘዳግም የተጻፉት ከ1446-1406 ዓ.ዓ. ነው። ይሁን እንጂ በፔንታቱክ የተጻፉ ታሪካዊ ድርጊቶች የተፈጸሙባቸውን ጊዜያት ለመወሰን ስንሞክር አንድ ዐቢይ ችግር ይገጥመናል። ይህ ችግር የሚነሣው በዘጸአት ውስጥ በዕብራይስጡና በግሪኩ መጽሐፍ ቅዱስ መካከል ባለ የአንድ ጥቅስ ልዩነት ምክንያት ነው። የዕብራይስጡ መጽሐፍ ቅዱስ በዘጸ. 12፡40 አይሁድ በግብፅ ለ430 ዓመታት እንደነበሩ ይናገራል። የግሪኩ መጽሐፍ ቅዱስ ግን ለ215 ዓመታት ነበሩ ይላል። 430 ዓመታት የሚለው በይበልጥ ትክክል ሳይሆን አይቀርም (1ኛ ነገሥት 6፡1 ተመልከት)። በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የቁጥሮችን ወይም የታሪኮችን ትክክለኛነት የማይቀበሉ አንዳንድ ምሁራን ወደኋላ ያደርጉታል። የፔንታቱክ ታሪክ የተፈጸመው በሦስት የዓለም ክፍሎች ነው። የተጀመረው ከዘፍ. 1-11 ያለው ታሪክ በተፈጸመበትና የዔድን ገነት ባለበት መስጴጦምያ ነው። የእስራኤል ሕዝብ አባት የሆነው አብርሃም የመጣው ከመስጴጦምያ ሲሆን የይስሐቅና የያዕቆብ ሚስቶችም የመጡት ከዚሁ አገር ነበር። ከዚያም ታሪኩ ሦስቱ ዋና ዋና የእስራኤል ሕዝብ አባቶች አብርሃም፥ ይስሐቅና ያዕቆብ በእንግድነት ወደኖሩባት፥ እግዚአብሔር ለእነርሱና ለዘራቸው ሊሰጥ ቃል ወደገባላቸው ወደ ከነዓን ምድር ያመራል። በመጨረሻ ታሪኩ ስለ ጥቂቱ የያዕቆብ ቤተሰብ (70 ሰዎች) እንዴት ወደ ግብፅ እንደሄዱና ቁጥራቸው ወደ 2 ሚሊዮን አድጎ ታላቅ ሕዝብ እንደሆኑ ይነግረናል። ሕዝቡ ግን ባልተጠበቀ ሁኔታ የግብፅን የባዕድ አምልኮት ባሕል ለመዱ፤ የጣዖት አምልኮአቸውንም ተማሩ (ዘጸ. 32፡1-10)። እናም ግብፅን እንደራሳቸው አገር አድርገው መቁጠር ጀመሩ (ዘኁ. 11፡4-6)። የውይይት ጥያቄ፥ በዚህ ዘመን ያለን ክርስቲያኖች በምድር ላይ በእንግድነት እንድንኖር የሚገባን ቢሆንም እንኳ ብዙ ጊዜ የባዕድ አምልኮዎችን ልማድ የምንለማመደው እንዴት ነው? (ዕብ. 11፡13 ና 1ኛ ጴጥ. 1፡1 ተመልከት)።  የፔንታቱክ አብዛኛው ታሪክ የሚያተኩረው የተመረጡት የእግዚአብሔር ሕዝብ ማለት እስራኤላውያን ከዓመታት የባርነት ቆይታ በኋላ ወደ ተስፋይቱ ምድር እንዴት እንደተመለሱ ነው። የፔንታቱክ ታሪክ የሚያበቃው በዘዳግ. 34 ስለ ሙሴ ሞት በተጻፈው ትረካ ነው። (ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

የፔንታቱክ መጻሕፍት ስሞች በውስጣቸው የሚታይ ታሪክ Read More »

የፔንታቱክ መግቢያ

ከዚህ በፊት በነበሩት ትምህርቶች፥ ስለብሉይ ኪዳን አንዳንድ የመግቢያ አሳቦች አጥንተናል፤ የእግዚአብሔር ቃል እንደሆነም ተመልከተናል። ከብዙ ዓመታት በፊት 39 የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት የእግዚአብሔር ቃል ይሆኑ ዘንድ በአይሁዶች እንዴት እንደተለዩ ተምረናል። በዚህ ሳምንት ፔንታቱክ ወይም የሙሴ ሕግ ተብለው የሚጠሩትን የመጀመሪያዎቹ አምስት የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት መመልከት እንጀምራለን።  ብሉይ ኪዳን የተጻፈው በሁለት ቋንቋዎች ነበር። አብዛኛዎቹ የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት የተጻፉት በዘመኑ የአይሁድ ቋንቋ በነበረው በዕብራይስጥ ነበር፤ ነገር ግን የባቢሎንና በመካከለኛው ምሥራቅ ይኖሩ የነበሩ ሰዎች ዋና የንግድ ቋንቋ በነበረው በአራማይክ የተጻፉ አንዳንድ የብሉይ ኪዳን ክፍሎችም አሉ። ለምሳሌ፡- ዳን. 2-7ና የዕዝራ አንዳንድ ክፍሎች የተጻፉት በአራማይክ ቋንቋ ነው። ይህ የሆነው በዚህ ጊዜ ብዙ አይሁድ በመካከለኛው ምሥራቅ ተበትነው በአሕዛብ መካከል በምርኮ ላይ ስለ ነበሩ ነው።  የውይይት ጥያቄ፥ የሚከተሉትን ጥቅሶች ተመልከት፥ ዘዳ. 28፡61፤ ኢያ. 8፡31፤ (ሉቃ. 2፡22)፤ 2ኛ ዜና 31፡3፤ (ሉቃ. 2፡23)፤ ነህ. 8፡3። የመጀመሪያዎቹ አምስት የመጽሐፍ ቅዱስ መጻሕፍት ብዙ ጊዜ በአይሁድ ምን ተብለው ይጠሩ ነበር? የመጀመሪያዎቹ አምስት የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት አንዳንድ ጊዜ «ፔንታቱክ» እየተባሉ ይጠሩ ነበር። ፔንታቱክ የሚለው የግሪክ ቃል ትርጉም «አምስት ጥቅል መጻሕፍት» ማለት ነው። ይህም የሚያመለክተው በሙሴ የተጻፉትና በአይሁድ ዘንድ እንደ አንድ ክፍል የሚቆጠሩትን የመጀመሪያዎቹን አምስት የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት ነው። ይህን ስም ብዙ ጊዜ የሚገለገሉበት በክርስቶስ ጊዜ የግሪክ ቋንቋ ይናገሩ የነበሩ አይሁድ ነበሩ። የዕብራይስጥ ቋንቋ ይናገሩ የነበሩ አይሁድ ግን ለእነዚሁ መጻሕፍት ሌሎች ስሞች ነበሯቸው። ብዙ ጊዜ «ሕግ» ወይም «ቶራህ» ብለው ይጠሯቸው ነበር። ቶራህ ለሕግ የተሰጠ የዕብራይስጥ ስም ነው።  በመጽሐፍ ቅዱስ በአጠቃላይ የመጀመሪያዎቹ አምስት የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት የተለያዩ ስሞች ተሰጥተዋቸዋል። አንዳንድ ጊዜ «የሕግ መጻሕፍት»፥ «ሕግ»፥ «የሙሴ የሕግ መጻሕፍት»፥ «የሙሴ ሕግ»፥ «በሙሴ መጽሐፍ ውስጥ ያለ ሕግ»፥ «የጌታ ሕግ»፥ «የጌታ ሕግ መጽሐፍ» እና «የሕግ መጽሐፍ» ተብለው ተጠርተዋል።  አይሁድ የብሉይ ኪዳን መጻሕፍትን በሙሉ የሚያከብሩና በእግዚአብሔር መንፈስ ምሪት መጻፋቸውን የሚያምኑ ቢሆኑም ፔንታቱክ ወይም የሙሴ ሕግ መጻሕፍትን ከሁሉ አብልጠው ያከብሯቸዋል።  የፔንታቱክ መጻሕፍት ጸሐፊ  የብሉይ ኪዳን የመጀመሪያ መጻሕፍትን ማን ጻፋቸው? እስካለፈው 100 ዓመታት ድረስ አይሁድም ሆኑ ክርስቲያኖች ሙሴ እንደጻፋቸው ያምኑ ነበር፤ ምክንያታቸውም የተመሠረተው በመጽሐፍ ቅዱስና በሽማግሌዎች ወግ ላይ ነው። ቀደም ሲል እንዳየነው፥ ከመጀመሪያዎቹ አምስት የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት ስሞች አንዱ «የሙሴ ሕግ» የሚለው ነው። የውይይት ጥያቄ፥ ዘጸ. 24፡3-4 እና ዮሐ. 5፡46-47 አንብብ። በእነዚህ ቁጥሮች መሠረት የመጀመሪያዎቹን አምስት የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት የጻፈው ማን ነው?  ከዘፍጥረት እስከ ዘዳግም ያሉትን መጻሕፍት የጻፈው ሙሴ ነው ብሎ መጽሐፍ ቅዱስ በቀጥታ ባይነግረንም እንኳ በፔንታቱክ ውስጥ የተካተቱ አንዳንድ ነገሮችን እርሱ እንደጻፋቸው ግልጽ ነው። በሲና ተራራ የተቀበላቸውን ሕግጋት እርሱ እንደጻፋቸው እናውቃለን። ከሙሴ ሞት በኋላ ኢያሱ ወዲያውኑ ተተክቶ ሕዝቡን መምራት ሲጀምር እንዲታዘዘው የተሰጠው፥ በሙሴ የተጻፈ መጽሐፍ ነበር፤ (ኢያሱ 1፡7-8 ተመልከት)። ከአዲስ ኪዳን ዘመን ቀደም ብሎ የመጀመሪያዎቹን አምስት የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት የጻፈው ሙሴ እንደሆነ አይሁድ አምነው ነበር። በአዲስ ኪዳን ውስጥም ቢሆን የፔንታቱክ መጻሕፍት አብዛኛዎቹን ሙሴ እንደጻፈ ተጠቅሶአል። ዘጸአት (ማር. 7፡10)። ዘሌዋውያን (ሮሜ 10፡5)፤ ዘዳግም (ማቴ. 19፡7-8) የተጻፉት በሙሴ እንደሆነ ኢየሱስና ሌሎች በግልጥ ተናግረዋል። የሕግ መጻሕፍት አመዳደብ እንደ ሙሴ መጻሕፍት ሲሆን ይህም ሙሴ በጸሐፊነት የሚታይ መሆኑን ያመለከታል (ሉቃስ 24፡44 ተመልከት)። በ1900 ዓ.ም. አካባቢ ግን ፔንታቱክን የጻፈው በእርግጥ ሙሴ ለመሆኑ ምሁራን ይጠራጠሩት ጀመር። የፔንታቱክን መጻሕፍት በሚመረምሩበት ጊዜ ከአንድ በላይ የሆኑ ጸሐፊዎች እንደጻፉት የሚያሳዩ በርካታ ነገሮችን አገኙ። ለምሳሌ፡- በኦሪት ዘፍጥረት ሁለት የተለያዩ የፍጥረት ትረካዎች አሉ (ዘፍ. 1 ና 2)፤ ሙሴ ከኖረበት ዘመን ከ500 ዓመታት በኋላ ይኖሩ የነበሩ የእስራኤል ነገሥታት ተጠቅሰዋል (ዘፍጥ. 36፡31)፤ እስከ ዘመነ መሳፍንት ድረስ ወደ ከነዓን ያልመጡ ፍልስጥኤማውያን ተጠቅሰው እናያለን (ዘፍጥ. 21፡34)፤ ደግሞም «እስከ ዛሬ ድረስ» የሚለው ቃል መጽሐፉ የተጻፈው ከሙሴ በኋላ መሆኑን የሚጠቁም ሐረግ ይመስላል (ዘፍጥ. 32፡32)። በተጨማሪም እነዚህ ምሁራን በአጻጻፍ ስልትና በቃላት አጠቃቀም ረገድ ያለው ልዩነት ራሱ የተለያዩ ጸሐፊዎች እንደጻፉት ያሳያል ይላሉ። በዚህ ምክንያት የፔንታቱክ ጸሐፊ ማን ነው? የሚለውን ጥያቄ በሚመለከት አለመግባባት አለ። እነዚህ አምስት የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት ስለተገኙበት መንገድ አምስት ዋና አመለካከቶች ወይም አሳቦች አሉ። የፔንታቱክን መጻሕፍት ሁሉ የጻፈው ሙሴ ነው። ሙሴ ያልጻፈው የፔንታቱክ ክፍል ከእርሱ ሞት በኋላ የተጻፈው ዘዳግም 34 ብቻ ነው። ይህንን አቋም የያዙ ሰዎች እንደሚሉት ሙሴ ሌሉች መጻሕፍት ተጠቅሞ ሊሆን ይችላል፤ ነገር ግን እነዚህን አምስት መጻሕፍት ያዘጋጀና የጻፈ እርሱ ነው ይላሉ። አቋማቸውን ለመደገፍም የሚከተለውን መረጃ ይጠቁማሉ፡- ሀ. ዘኁል. 33፡2 እና በፔንታቱክ ውስጥ ያሉ ሌሎች ጥቅሶች መጻሕፍቱን የጻፈው ሙሴ ነው ይላሉ።  ለ. በብሉይና በአዲስ ኪዳን የሚገኙ ሌሎች መጻሕፍት ሙሴ የፔንታቱክ ጸሐፊ እንደሆነ ይናገራሉ፤ (ዘኁል. 24፡3-4ና ዮሐ. 5፡46-47)።  ሐ. በአይሁድም ሆነ በክርስትና አፈ ታሪክ መሠረት ጸሐፊው ሙሴ እንደሆነ ይነገራል። መ. መጽሐፉን በጥልቀት በማጥናት የምንረዳው ነገር ጸሐፊው የድርጊቱ የዓይን ምስክር እንዲሁም የግብፅን ቋንቋና ባሕል የሚያውቅ ሰው መሆኑን ነው። እነዚህን መመዘኛዎች ሊያሟላ የሚችል ከሙሴ የተሻለ ሰው በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ጨርሶ አልተጠቀሰም። ሙሌ የፔንታቱክ ዋነኛው ጸሐፊ ነው። ኦሪት ዘፍጥረትን በሚመለከት የተጻፉት ጽሑፎች በሙሉ ለይቶ፥ አቀናብሮና አስተካክሎ ያዘጋጀ እርሱ ነው። ከቀሩት አራት መጻሕፍትም አብዛኛውን የጻፈው እርሱ ነው፤ ነገር ግን ሙሴ ከሞተ ከረጅም ጊዜ በኋላ አንድ ያልታወቀ ሰው አንዳንድ ጥቃቅን ነገሮችን አክሉባቸዋል። አምስቱ መጻሕፍት ሙሉ በሙሉ የተጠናቀቁት በመጽሐፈ ኢያሱ መጨረሻ አካባቢ ወይም ምናልባት በነቢዩ ሳሙኤል ጊዜ ነው።  የመጀመሪያዎቹ አምስቱ የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት የተጻፉት በተለያዩ ሰዎች ሲሆን የተጻፉትም በብዙ መቶ ዓመታት ጊዜ ውስጥ ነው። ይህ አሳብ የተጀመረው በ1876 ሲሆን «በመረጃ የተደገፈ መላምት» ወይም «ጄ.ኢ.ዲ.ፒ. ቲዎሪ» በመባል ይታወቃል። ይህንን አመለካከት የሚደግፉ አብዛኛዎቹ ምሁራን ፔንታቱክም ሆነ የተቀረው የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል ስሕተት የሌለበት እውነተኛ የእግዚአብሔር ቃል መሆኑን አያምኑም። የአይሁድን ሃይማኖታዊ ልምምድ ለማሳየት የጥንት ሰዎች የጻፉት አድርገው ማመኑ ይቀላቸዋል። መጽሐፍ ቅዱስ በዓለም ዙሪያ እንደሚገኙ እንደ ሌሎች ሃይማኖታዊ መጻሕፍት ነው ይላሉ። እነዚህ ምሁራን በተአምራት፥ በነቢያትም ሆነ በመሳሰለው ለማመን ፈቃደኞች አይደሉም። ትንቢትና ተአምራትን ላለመቀበል አስቀድመው አእምሮአቸውን ያዘጋጁ ናቸው። ይህን መጽሐፍ ቅዱስን በመረዳትና በመተርጎም በኩል ተጽዕኖ ያደርግባቸዋል። ይህ አመለካከት በተለይ ላለፉት 50 ዓመታት ተከታዮች ያተረፈ ቢሆንም፤ በአሁኑ ጊዜ ግን እያሽቆለቆለ በመምጣት ላይ ይገኛል። ይህ አመለካከት ቀደም ብለን ባነሳነው ጉዳይ ላይ በማተኮር፥ ለፔንታቱክ መጻሕፍት አንድ ጸሐፊ ብቻ ሊኖር እንደማይችል ይናገራል። በመሠረቱ ይህ አመለካከት ፔንታቱክ ቢያንስ የአራት ዋና ዋና መጻሕፍት ጥርቅም ሆኖ በአራት መቶ ዓመታት የጊዜ ገደብ ውስጥ እንደተጻፈ የሚያስተምር ነው። ሀ. የመጀመሪያው መጽሐፍ የሚጠራው በዕብራይስጥ ቋንቋ የእግዚአብሔር ስም በሚጀመርበት «ጄ» በሚለው ፊደል ነው። ስሙም «ጄሆቫ» (ያህዌ) ነው። ይህ ጽሑፍ በ9ኛው መቶ ክፍለ ዘመን (ዓ.ዓ.) የያህዌ እግዚአብሔርን ታላቅነት ለማግነን በፈለጉ አይሁድ እንደተጻፈ ይናገራል።  ለ. ሁለተኛው ጽሑፍ የሚጠራው አይሁድ ለእግዚአብሔር ከሰጡት «ኤሎሂም» ከሚለው ስም በተገኘው «ኢ» በሚለው ፊደል ነው። የዚህ ጽሑፍ ጸሐፊ ከእስራኤል የሰሜኑ ክፍል የመጣ ሲሆን የጻፈውም በ8ኛው መቶ ክፍለ ዘመን (ዓ.ዓ.) እንደሆነ የዚህ አመለካከት አራማጆች ይናገራሉ። ይህ ጸሐፊ «ኤሎሂም» በሚለው የእግዚአብሔር ስም ላይ አተኩሯል።  እነዚህ የመጽሐፍ ቅዱስ ምሁራን ሁለቱ ጽሑፎች ከተጻፉና ሰማርያ በ722 ዓ.ዓ. በአሦራውያን እጅ ከወደቀች በኋላ ከይሁዳ ሳይሆን አይቀርም ተብሎ የሚታሰብ ሰው ወደ አንድ መጽሐፍ አጣምሮአቸዋል የሚል አሳብ ይሰነዝራሉ። ሐ. ሦስተኛው ጽሑፍ ከመጨረሻው የፔንታቱክ መጽሐፍ በእንግሊዝኛ ዲዮተሮኖሚ ከሚለው ስም የመጀመሪያ ፊደል በመውሰድ «ዲ» ብለው ሰይመውታል። ይህ ሰው ኦሪት ዘዳግምን ከጻፈ በኋላ ከመጽሐፈ ኢያሱ እስከ 2ኛ ነገሥት ላሉት መጻሕፍት ደግሞ የመጨረሻ ማስተካከያ አድርጓል። ይህ

የፔንታቱክ መግቢያ Read More »

የመካከለኛው ምሥራቅ መልክዓ ምድር

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) የአንድን ስፍራ መልክዓ ምድር መረዳት በዚያ ስፍራ የሚኖሩ ሰዎችን አኗኗር ለመረዳት እንዴት ይጠቅማል? ለ) መጽሐፍ ቅዱስን ለመረዳትና ለመተርጎምስ እንዴት ይጠቅማል? የብሉይ ኪዳን ታሪክ እምብርት የከነዓን ምድር ነው። በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ይህ ስፍራ አራት ስሞች ተሰጥቶታል። በመጀመሪያ፥ ብዙ ጊዜ የሚጠራበት «ከነዓን» የሚለው ስም ነው። የውይይት ጥያቄ፥ ዘፍ. 9፡18-27 ተመልከት። ከነዓን ማን ነው? የኖኅ የልጅ ልጆች ከነበሩት መካከል ከነዓን የሚባለው አንዱ እንደ ነበረ በብሉይ ኪዳን እናነባለን። አባቱ በሠራው ኃጢአት ምክንያት እግዚአብሔር ከነዓንን ለሴምና ለያፌት ዘሮች ባሪያ እንዲሆን ረግሞት ነበር። በዘፍጥረት 10 እንደምናነበው የከነዓን ዝርያዎች በዮርዳኖስ ወንዝ በስተምዕራብ በዮርዳኖስ ወንዝና በሜዲትራኒያን ባሕር መካከል ሰፍረው ነበር። ይህ አካባቢ የኖኅ የልጅ ልጅ በሆነው በከነዓን ዝርያዎች ስም ከነዓን ተብሎ ተጠራ። ደግሞም ይህ አካባቢ ከነዓን ይባል የነበረው «የሐምራዊ ምድር» ለማለትም ነው። ምክንያቱም በከነዓን ይኖሩ የነበሩ ሰዎች በዘመኑ ሀብታሞች ሊለብሱ የሚችሉትን ሐምራዊ ቀለም ያላቸው ልብሶችን ይሠሩ ስለነበር ነው። ጳለስጢና የሚለው ቃል ከኤፍራጥስ ጀምሮ እስከ ግብፅ ያለውን ምድር በሙሉ የሚያጠቃልል ሲሆን፥ ከነዓን የሚለው ቃል ግን በጳለስጢና ውስጥ ያለ አነስተኛ ምድርን የሚጠቅስ ነው። ሁለተኛ፥ ምድሪቱ አንዳንድ ጊዜ «የተስፋይቱ ምድር» በመባል ትጠራለች። ምክንያቱም እግዚአብሔር ከአብርሃም ጋር ቃል ኪዳን ባደረገ ጊዜ (በዘፍ. 15፡7) የከነዓንን ምድር ለአብርሃም ርስት አድርጎ እንደሚሰጠው ቃል ገብቶለታል። አብርሃምና ዝርያዎቹ ከ400 ዓመታት ለሚበልጥ ጊዜ ምድሪቱን ባይወርሱም እንኳ በእግዚአብሔር የተስፋ ቃል መሠረት የእነርሱ ነበረች። ለእስራኤል በርስትነት ተስፋ የተሰጠች ምድር ስለሆነች «የተስፋይቱ ምድር» ሆና ቆይታለች (ሕዝ. 48 ተመልከት)። ሦስተኛ፥ ምድሪቱ አንዳንዴ «ጳለስጢና» ተብላ ተጠርታለች። ይህ ስም በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ባይገኝም፥ አሕዛብ ለከነዓን ምድር የሚሰጡት የተለመደ ስም ነው። (ስለ ፍልስጥኤማውያን፥ ስለ ለስጢናና ስለ ጳለስጢናውያን በትላንትና ትምህርታችን የተመለከትነውን ከልስ።) አራተኛ፥ ምድሪቱ አንዳንዴ «እስራኤል» ተብላ ተጠርታለች። ይህ የሚያመለክትው ከ1400 ዓ.ዓ. . 70 ዓ.ም. እና ከ1948 ዓ.ም. ጀምሮ የአይሁድ ምድር መሆንዋን ነው። ከአይሁድ አባቶች አንዱ የሆነው ያዕቆብ በኋላ ስሙ እስራኤል ተብሎ እንደተለወጠ ይታወቃል (ዘፍ. 32፡28)። ስለዚህ እስራኤል የሚለው ስም የሚያመለክተው የያዕቆብን ዝርያዎችና በእግዚአብሔር የተስፋ ቃል ኪዳን መሠረት ስለወረሷት ምድር ነው። እግዚአብሔር በጣም ትንሽ የሆነችውን የከነዓንን ምድር ይወርሱ ዘንድ ለአይሁድ የሰጠው ለምንድን ነው? እንደ አሜሪካ፥ ኢራቅ ወይም ኢትዮጵያን የመሳሰሉ ትልልቅ አገሮች ለምን አልሰጣቸውም? ስለከነዓን ምድር በጣም አስፈላጊ የሆነው ነገር ምንድን ነው? የከነዓን ምድር ትልቅ አይደለችም። የእስራኤል መንግሥት በጣም ትልቅ የነበረችው በዳዊትና በሰሎሞን ዘመን ሲሆን በዚያን ጊዜም 800 ኪሎ ሜትር ርዝመትና 200 ኪሎ ሜትር ስፋት ነበራት፤ ይህም ከአሰብ እስከ አዲስ አበባ ያለው ርቀት ማለት ነው። ብዙ ጊዜ ግን የእስራኤል ምድር 225 ኪሎ ሜትር ርዝመትና 100 ኪሎ ሜትር ስፋት ብቻ ነበራት፤ ይህ ከአዲስ አበባ እስከ ሻሸመኔ ድረስ ካለው ርቀት ጋር የሚወዳደር ነው። ከነዓን የዓለም እምብርት ለመባል ትችላለች፤ ምክንያቱም ሁለት ዋና ዋና አህጉራት ማለትም አፍሪካና እስያ የሚገናኙባት ቦታ ናት። በጥንት ዘመን ደግሞ በጣም ጠቃሚ የነበረችው:- በአፍሪካ፥ በእስያና እንዲሁም በአውሮጳ ዋና የንግድ መሥመር ላይ ትገኝ ስለነበረ ነው። አሁንም ቢሆን በታሪክ ውስጥ እጅግ ጠቃሚ ሚና መጫወቷን ቀጥላለች፤ ምክንያቱም መካከለኛው ምሥራቅ በነዳጅ ዘይት ከፍተኛ ሀብት ያለው አካባቢ ስለሆነ ነው። የዚህ ዘመን ሥልጣኔ በነዳጅ ዘይት ላይ የተመሠረተ ነው። እንደ እውነቱ ከሆነ መጽሐፍ ቅዱስ ራሱ እነዚህን ስፍራዎች ለመያዝ አሕዛብ በሚያደርጉት ትግል በምድር ላይ የመጨረሻው ጦርነት የሚካሄደው በእስራኤል ነው ይላል። በተጨማሪ፥ የዓለም የሥነ- መለኮት ትምህርት ማዕከልም ናት። የዓለም ሦስቱ ዋና ዋና ሃይማኖቶች ይሁዲነት፥ ክርስትናና እስልምና መሠረታቸውን ያገኙት ከእስራኤል ነው። በጥንቱ መካከለኛ ምሥራቅ የነበሩ ታላላቅ አገሮች የተለያዩ የጥንት ሕዝቦች የት እንደ ነበሩና ከአሁኑ ዓለም ጋር እንዴት እንደሚወዳደሩ ለማወቅ የጥንቶቹን ዋና ዋና የመጽሐፍ ቅዱስ ሕዝቦችና በጊዜያችን ከየትኛው አገር እንደሆኑ እንመለከታለን።  ፩. ኢትዮጵያ ወይም ኩሽ፡- በዕብራይስጥ መጽሐፍ ቅዱስ ከግብፅ በስተደቡብ ቀጥሉ የሚገኘው አገር ኩሽ ተብሎ ይጠራ ነበር። ኋላም በሰፕቱዋጀንት የግሪክ መጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ግሪኮች ይህንን ምድር ኢትዮጵያ ብለው ጠርተዋል፤ ስለዚህ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ኩሽና ኢትዮጵያ የአንድ ስፍራ ሁለት ስሞች ናቸው። የእንግሊዝኛና የአማርኛ ትርጉም መጽሐፍ ቅዱሶች ለዚህ ምድር «ኢትዮጵያ» የሚለውን የግሪክ ስም ይጠቀማሉ። የኩሽ ወይም የኢትዮጵያ ምድር ከአሁንዋ ኢትዮጵያ ጋር አንድ አይደለም፤ ነገር ግን በዓለም ታሪክ ውስጥ «ኑቢያ» ተብላ ትጠራ የነበረችው ዛሬ በሰሜን ሱዳን የምትገኝ አገር ነች። በመጽሐፍ ቅዱስ መልክዓ ምድር መሠረት ኑቢያ የመጨረሻዋ ደቡባዊ ክፍል ያለችው አገር ነች። የአሁንዋ ኢትዮጵያ መጀመሪያ ስምዋን ያገኘችው ከግሪኩ መጽሐፍ ቅዱስ ነው፤ ነገር ግን ኢትዮጵያ ወይም ኩሽ ብሉ መጽሐፍ ቅዱስ ከጠራው ስፍራ ጋር ሙሉ ለሙሉ ተመሳሳይ አይደለችም። የአሁንዋ ኢትዮጵያ ከአክሱም መንግሥት ውስጥ በተለያዩ ነገሥታት አመራር ሥር የነበረችና አሁን ወዳለው የክልል ዳርቻ እያደገች የመጣች ነች። የሳባ ሕዝብ ዛሬ የመን ተብሎ በሚጠራው በደቡብ ምዕራብ ዐረቢያ የነበረ ሳይሆን አይቀርም። ነገር ግን አንዳንዱ የግዛቱ ክፍል በቀይ ባሕር ወደ ሰሜን ኢትዮጵያ ተስፋፍቶ ሊሆን ይችላል።  ፪. ግብፅ፡- ልክ እንደ ጥንትነቷ ያለች ብቸኛ አገር ግብፅ ናት። በሰሜን ምሥራቅ አፍሪካ የምትገኝና ከጥንቱ ዓለም ታላላቅ ሥልጣኔዎች የአንደኛው ማዕከል የነበረች አገር ናት። በብሉይ ኪዳንም በተደጋጋሚ አገሪቱ በዚህ ሁኔታ ተጠቅሳለች። የሕይወቷ ሁሉ ምንጭ የሆነው ከኢትዮጵያና ከሱዳን የሚፈሰው የዓባይ ወንዝ ነው። የዓባይ ወንዝ በበጋም ሆነ በክረምት ጊዜ ለሰብልና ለከብቶች ውኃን ስለሚሰጥ የግብፅ ምድር ሁልጊዜ ምግብ ያገኛል። አብርሃምና ያዕቆብ በድርቅ ጊዜ ወደ ግብፅ የሄዱት በዚህ ምክንያት ነው።  ፫. ከነዓን፡- የከነዓን ምድር የሚገኘው ከግብፅ በስተሰሜን ነው። በመጠን አነስተኛ ብትሆንም፥ የተለያዩ ሕዝቦችን ይዛለች። በዮርዳኖስ ወንዝ በስተምሥራቅ የጥንት እስራኤል ጠላቶች የነበሩ ሦስት የአሕዛብ መንግሥታት ነበሩ። በደቡብ ኤዶም፥ ከኤዶም በስተሰሜን ሞዓብና ከሞዓብ በስተሰሜን ደግሞ አሞን ነበሩ። እነዚህ አገሮች ይገኙ የነበሩት በአሁኑ ጊዜ ዮርዳኖስ ተብሎ በሚታወቀው አገር ምዕራባዊ ጫፍ ነው። ከዮርዳኖስ ወንዝ በስተምዕራብ የእስራኤል ምድር ይገኛል። ታሪክ ሁሉ እስራኤላውያን የኖሩት በከነዓን ተራራማ አገር በአገሪቱ በስተ ደቡብ ከቤርሳቤህ በሰሜን እስከሚገኘው ዳን ድረስ ነው። በምዕራብ ሜዲትራኒያን ባሕር ዳርቻ በዘመነ መሳፍንት የእስራኤላውያን ዋና ጠላቶች የነበሩት ጳለስጢናውያን ይገኛሉ። ልክ እንደ ጥንቱ ዘመን ይህ ምድር ዛሬ እስራኤል ተብሎ ይጠራል። ነገር ግን ከዚህ አካባቢ የተወሰነው ክፍል በዘመናችን ባሉ ፍልስጥኤማውያን፥ በሶርያና በዮርዳኖስ የይገባኛል ጥያቄ ውስጥ ወድቋል። ፬. ሶሪያ፡- ከእስራኤል በስተ ምሥራቅ የአራሚያን ወይም የሶርያ ሕዝቦች ይገኛሉ። ዋና ከተማቸው ደማስቆ የሆነው ሶርያውያን ብዙ ጊዜ የእስራኤል ጠላቶች ሆነው ሲቆዩ፥ በተለይ የእስራኤል መንግሥት ለሁለት ተከፍሎ በነበረ ጊዜ ዋና ጠላቶች ነበሩ። ዛሬ ይህ ሕዝብ ያለበት አገር ሶርያ ተብሎ ይጠራል።  ፭. ፎኒሺያ (ፊንቄ)፡- ከእስራኤል በስተሰሜን ምዕራብ በሜዲትራኒያን ባሕር ዳርቻ ፎኒሺያ (ፊንቄ) የምትባል አገር ነበረች። በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ይህ አካባቢ በተለይ የሚታወቀው በዋና ከተማዎቹ በጢሮስና በሲዶና ነው። ይህ ሕዝብ በጣም የሚታወቀው የሜዲትራኒያን ባሕር በሙሉ ይካሄድ በነበረው የባሕር ላይ ንግድ ነው። ዳዊትና ሰሎሞን ቤተ መቅደሱንና ቤተ መንግሥቱን ለመገንባት የሠለጠነ የሰው ኃይል ፍለጋ ወደ ጢሮስ ሄደው ነበር። በአሁኑ ጊዜ ይህ አካባቢ ሊባኖስ በመባል ይታወቃል። ፮. አሦር፥ ባቢሎን፥ ሜዶንና ፋርስ፡- ከእስራኤል በስተሰሜን ምሥራቅ ራቅ ብሉ አሦር፥ ባቢሎን፥ ሜዶንና ፋርስ የሚባሉ አራት አገሮች ነበሩ። የእነዚህ አራት አገሮች ሕዝቦች በተለይ መስጴጦምያ በሚባለው አካባቢ ይኖሩ ነበር። መስጴጦምያ የሚባለው አካባቢ የፋርስ ባሕረ ሰላጤን ይዞ በስተሰሜን ምዕራብ ከሁለት ታላላቅ ወንዞች ማለትም ከኤፍራጥስና ጤግሮስ አጠገብ የሚገኝ ነው።  ሀ. አሦር፡- አሦር የሚገኘው ከመስጴጦምያ በስተሰሜን በጤግሮስ ወንዝ አጠገብ ነበር። ዋና ከተማው ነነዌ ነበረ። በ700 ዓ.ዓ. አሦር በመስጴጦምያ፥ ጳለስጢናና በግብፅ ሁሉ ላይ

የመካከለኛው ምሥራቅ መልክዓ ምድር Read More »

የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት ታሪክ ጥናት

የውይይት ጥያቄ፥ የዓለምን፥ የኢትዮጵያንና የራስህንም ነገድ የሚመለከቱ ታሪኮችን ማወቅ ለምን ያስፈልጋል? ሕይወታችን በሙሉ በታሪክ፥ ወይም ባለፈው ጊዜ በእኛ ሕይወት ውስጥ በተፈጸመውም ሆነ በዓለም ዙሪያ በመሆን ላይ ባሉት ክስተቶች ተጽእኖ ሥር ነው። ለምሳሌ፡- ኢጣሊያን፥ ሩሲያን፥ አሜሪካን፥ እንግሊዝን፥ ወዘተ ሳናውቅና ከኢትዮጵያ ጋር ስላላቸው ግንኙነት ሳንረዳ፥ አዲሲቷን ኢትዮጵያ መረዳት ያስቸግረናል። እነዚህ ሕዝቦች ሁሉ በኢትዮጵያ ላይ አሉታዊም ሆነ አዎንታዊ ተጽእኖ ስለነበራቸው ያ ተጽዕኖ አሁንም ድረስ ውጤት አለው። እንዲሁም ደግሞ የምኒልክን ወይም የኃይለ ሥላሴን መንግሥት ሥረ-መሠረት ሳናውቅ አዲሲቷን ኢትዮጵያን ለመረዳት አንችልም። ለእነዚህ የተለያዩ ሕዝቦችና አገሮች ያለን አመለካከት የተለያየ ቢሆንም፥ ሁሉም ግን በእኛ ላይ ያሳደሩት ተጽዕኖ አለ። ያለፉትን ክስተቶች የበለጠ በተረዳን ቁጥር በአሁኑ ጊዜ በአገራችን የሚደረገውን ነገር በተሻለ ሁኔታ እየተረዳን እንሄዳለን።  መጽሐፍ ቅዱስን ስለመረዳትም ተመሳሳይ ነገር ማለት ይቻላል። መጽሐፍ ቅዱስ ታሪካዊ መጽሐፍ ነው። በብሉይ ኪዳን ውስጥ የተጻፉ ታሪኮች ከብዙ መቶ ዓመታት በፊት በመካከለኛው ምሥራቅ የተፈጸሙ የእውነተኛ ክስተቶች ታሪክ ነው። በዚያ ዘመን የነበሩ ታሪኮችንና የምድሪቱን ሁኔታ የበለጠ በተረዳን ቁጥር፥ መጽሐፍ ቅዱስን በተሻለ ሁኔታ እንረዳለን። ለምሳሌ በከነዓን ምድር ላይ የነበራቸውን ሚና ለመረዳት ስለ ግብፅ፥ ባቢሎን፥ ፋርስ፥ ሮም፥ ግሪክ ወዘተ ማወቅ በጣም አስፈላጊ ነው። የአይሁድና የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ ከዓለም ታሪክ ጋር የተሳሰረ ነው። ይሁን እንጂ ከዓለም አመለካከት አንጻር አይሁድ በዓለም ታሪክ ውስጥ መጠነኛ ሚና ተጫውተዋል። ከእግዚአብሔር አመለካከት አንጻር ግን የታሪክ እምብርት ናቸው። እግዚአብሔር ስለመረጣቸው፥ መጽሐፍ ቅዱስን በእነርሱ በኩል ስለሰጠ፥ መሢሑ ኢየሱስ ክርስቶስን ወደዚህ ዓለም በእነርሱ በኩል ስለላከ ወዘተ. አይሁድ ከሌላው ሕዝብ ሁሉ ይልቅ እጅግ አስፈላጊ ሕዝብ ናቸው። ይህም ማለት አይሁድ በትውልዳቸው ከሌላ ዘር የተሻሉ ናቸው ማለት አይደለም። ነገር ግን ዓለምን በካህንነት እንዲያገለግሉ በእግዚአብሔር ተመርጠው ነበር፤ (ዘጸ. 19፡5-6)። ብሉይ ኪዳን የዓለምን ሕዝቦች ታሪክ ለመናገር አይፈልግም። በግብፅና በመሰጴጦምያ ስለነበሩት አስደናቂ የሥልጣኔ ክስተቶች አያስተምርም፡፡ እነዚህን ሕዝቦች የሚጠቅሰው ከእስራኤል ሕዝብ ጋር በነበራቸው ግንኙነት አንጻር ብቻ ነው። ብሉይ ኪዳን ከምዕራቡ ዓለምና ከመካከለኛው ምሥራቅ አስቀድሞ ስለታየው የቻይና ታላቅ ሥልጣኔ የሚናገረው ነገር የለም። ብሉይ ኪዳን እጅግ ጥንታዊ መጽሐፍ ነው። በውስጡ የያዛቸው ታሪኮች ወደማይታወቅ ኋለኛ ዘመን ይሄዳሉ፤ ስለዚህ አንዳንድ ድርጊቶች የተፈጸሙበትን ዘመን መናገር አስቸጋሪ ነው። ለምሳሌ፡- ዓለም የተፈጠረችበትን አዳምና ሔዋን በምድር ላይ መኖር የጀመሩበትን ዘመን በትክክል መናገር የሚቻልበት መንገድ የለም፤ ነገር ግን በከርሰ-ምድር ጥናት አማካይነት እርግጠኛ ልንሆንባቸው የምንችል ድርጊቶች የተፈጸሙባቸው ዘመናትም አሉ። ለምሳሌ፡- አብዛኛዎቹ የእስራኤል ነገሥታት የነገሡበትን ጊዜ በአንድና በሁለት ዓመት ልዩነት መወሰን ይቻላል። የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) የሚከተሉትን ሰዎች በታሪካዊ ቅደም ተከተል አስቀምጥ፡- ዳዊት፥ አዳምና ሔዋን፥ ሄኖክ፥ ኖኅ፥ ሳኦል፥ አብርሃም፥ ሰሎሞን። ለ) በብሉይ ኪዳን ታሪክ ውስጥ እጅግ ጠቃሚ ሚና የተጫወቱ ሌሎች የብሉይ ኪዳን ሰዎችን ጥቀስ። የተለያዩ ሰዎች በተለያዩ መንገዶች የታሪክን ዘመናት ይቆጥራሉ። ቻይናዎች የራሳቸው መንገድ አላቸው። አይሁድ ከፍጥረት ጀመረ ብለው የሚናገሩት የራሳቸው መንገድ አላቸው። ክርስቲያኖችም የራሳቸው መንገድ አላቸው። ዛሬ አብዛኛው የዓለም ሕዝብ የክርስቲያንን የቀን መቁጠሪያ ይከተላል። ክርስቲያኖች ታሪክን በሁለት ታላላቅ ዘመናት ይከፍሉታል። የመጀመሪያው ዘመን ከክርስቶስ ልደት በፊት (ዓመተ ዓለም) ይባላል። ይህ ዘመን ከዓለም ፍጥረት ይጀምርና እስከ ክርስቶስ መወለድ ድረስ ይቀጥላል። ሁለተኛው ዘመን ከክርስቶስ ልደት በኋላ ያለው ሲሆን በአማርኛ ዓመተ ምሕረት (ዓ.ም.) ብለን እንጠራዋለን። (በእንግሊዝኛ ኤ.ዲ. ተብሎ ሲታወቅ የመጣውም ከላቲኑ «አኖ ዶሚኒ» ማለትም «የጌታችን ዓመት» ነው።) በክርስቲያኖች የቀን መቁጠሪያ ዓመቱ ወደ ኢየሱስ ልደት በቀረበ መጠን ቁጥሩ እየቀነሰ ይመጣል። ከክርስቶስ ልደት በኋላ ቁጥሩ እየጨመረ ይመጣል። የሚከተለውን መግለጫ ተመልከት፡- አብርሃም (2000 ዓ.ዓ.)                    ዳዊት (1000 ዓ.ዓ.)                                  ክርስቶስ (አልቦ ዜሮ (0) ዓ.ዓ.)                                                           አሁን (2019 ዓ.ም.) በብሉይ ኪዳን ዘመን ቁጥሩ እንዴት እያነሰ ይሄድ እንደነበር ወደ ክርስቶስ ደግሞ እየቀረበ እንደመጣ ከከላይ የቀረበወን ገለጻ ልብ በል። ከክርስቶስ በፊት በ2000 ዓመታት ገደማ የኖረው አብርሃም ከክርስቶስ ልደት በፊት 1000 ዓ.ዓ. ገደማ ከኖረው ከዳዊት ዘመን የበለጠ ቁጥር አለው። በሌላ አንጻር ስናየው ኢየሱስ ክርስቶስ ከተወለደ ሁለት ሺህ አስራ ዘጠኝ ዓመታት አልፈዋል ማለት ነው። በኢትዮጵያና በአውርጳ የዘመን አቆጣጠር መካከል ልዩነት የሚታየው ለምንድነው? ምክንያቱ ኢየሱስ ክርስቶስ የተወለደበትን ጊዜ በሚመለከት አለመግባባት በመኖሩ ነው። ሰዎች የክርስቲያንን የቀን መቁጠሪያ ይጠቀማሉ፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ በተወለደበት ዘመን ቀን አቆጣጠርን ማንም አልጀመረም። ስለዚህ ኢየሱስ ክርስቶስ መቼ እንደተወለደ ትክክለኛውን ጊዜ ሊያውቁ አልቻሉም። ምዕራባውያን አገሮች የተከተሉት ግሪጐሪ የተባለው ሰው የጀመረበትን የቀን አቆጣጠር ነበር። ይህም የቀን መቁጠሪያ በ1582 ዓ.ም. የጀመረ ሲሆን የግሪጐሪያን የቀን መቁጠሪያ በመባል ይታወቃል። ኢትዮጵያ ደግሞ ሌላ ቀን መቁጠሪያን ትጠቀማለች። ሁለቱም የቀን መቁጠሪያዎች አዲሱን ዘመን የሚጀምሩት ከኢየሱስ ልደት ቢሆንም፣ እነዚህ የቀን መቁጠሪያዎች በስምንት ዓመታት ይለያያሉ። የመጽሐፍ ቅዱስ ምሁራን የመጽሐፍ ቅዱስን ታሪክ በተለያዩ ክፍለ ጊዜያት ይከፍላሉ። ቀጥሉ በብሉይ ኪዳን ያለውን የእስራኤል ታሪክ ባጭሩ እንመለከታለን። ፩. ከአይሁድ የእምነት አባቶች (ፓትሪያርኮች) በፊት የነበረው ዘመን (2500-2000 ዓ.ዓ.) ከዘፍ. 1-11 የጥንት ታሪኮችን አጭር መግለጫ እንመለከታለን። ታሪኩ የሚጀምረው የመጀመሪያዎቹ ወንድና ሴት ከተፈጠሩበት አጠቃላይ ታሪክ አጀማመር ነው። እግዚአብሔር ዓለምን እንዲሁም አዳምንና ሔዋንን የፈጠረበትን ጊዜ የሚያውቅ ማንም የለም። በእነዚህ የኦሪት ዘፍጥረት 11 ምዕራፎች የብዙ ሺህ ዓመታት ታሪክ አጠር ባለ መልኩ ቀርቧል። የእነዚህ ምዕራፎች ዋና ዓላማ ዓለም እንዴት እንደተጀመረች፥ ኃጢአት በዓለም እንዴት እንደተስፋፋ እንዲሁም ከአዳም እስከ አብርሃም ያለውን የአይሁድ የዘር ሐረግ ለመከተል ነው።  አይሁድ ሴማውያን ከተባሉ ዘሮች የተገኙ ነገዶች ወይም የሴም ዝርያ ናቸው። ሴማውያን በብዛት የሚኖሩት በመካከለኛው ምሥራቅ፥ በኤፍራጥስና በጤግሮስ ወንዞች መካከል በሚገኘውና መሰጴጦምይ በተባለው ሥፍራ ነው። የጥንት ሥልጣኔ የተጀመረው በዚያ ስፍራ ነው። ጽሑፍ፥ ሒሣብ፥ ሥነ ጥበብ፥ ሕግ፥ ሕክምና፥ ወዘተ በመጀመሪያ የተጀመረው በዚህ ስፍራ ነው። በ2100 ዓ.ዓ. ገደማ የመሰጴጦምያ ዋና ከተማ በደቡብ መሰጴጦምያ የምትገኘው የዑር ከተማ ነበረች። የደቡብ መሰጴጦምያን አብዛኛዎቹን ክፍሎች በሚቆጣጠር በአንድ ንጉሥ ሥር የምትገዛ ነበረች። ይህ ሁኔታ ባስገኘው ሰላም ምክንያት ለሥልጣኔ በፍጥነት ማደግ ምቹ ሁኔታ ተፈጥሯል። አብርሃምና አባቱ ካራን የመጡት ከዚህ ስፍራ እንደነበር እናያለን። አብርሃም የኖረበትን ትክክለኛ ዘመን ባናውቅም እንኳ፥ ዑርን ትቶ ወደ ከነዓን የሄደው በዚህ ዘመን መጨረሻ አካባቢ ነው፡፡  ይህ ከተማ በሥልጣኔ ያደገና የላቀ እንደነበረ ማወቃችን፥ አብርሃም በሥልጣኔ እጅግ የበለፀገችውን አገር ትቶ ኋላ ቀር ወደ ሆነችው ወደ ከነዓን ለመሄድ ያደረገውን አስቸጋሪ ምርጫ ያሳየናል። እግዚአብሔር ሰውን ከአዲስ አበባ ወጥቶ በሐመር ባኮ፥ ወይም ራቅ ካሉ አካባቢዎች በአንዱ እንዲኖር የተናገረውን ያህል ነው። ምርጫው አስቸጋሪ ነበር። አብርሃም ያደረገውን በእምነት የመታዘዝ ከፍተኛ እርምጃ ያሳየናል። የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ዑርን ለቆ እንዲወጣ እግዚአብሔር ለአብርሃም የሰጠው ትእዛዝ አስቸጋሪ የነበረው ለምንድነው? ለ) ዛሬ እግዚአብሔር ለእኛ የሚሰጠን አስቸጋሪ የሆነ ተመሳሳይ ትእዛዝ ምንድነው? (ማቴ. 28፡19-20 ተመልከት)። ሐ) በአሁኑ ጊዜ የአብርሃም ምሳሌነት ለእኛ መልካም ትምህርት የሚሰጠን እንዴት ነው?  ፪. የአይሁድ የእምነት አባቶች (የፓትሪያርኮች) ዘመን (2000-1600 ዓ.ዓ.) በእነዚህ ዓመታት የዑር ከተማ ኃይል ማሽቆልቆል ጀመረ። መሰጴጦምያ በአንድ ንጉሥ መገዛቷ ቀረና «የከተማ ግዛቶች» ወደሚባሉ ትናንሽ ክልሉች ተከፋፈለች። ይህም ማለት ዋና ዋናዎቹ ከተሞች በአካባቢያቸው ያሉ ክልሉችን ሁሉ መቆጣጠር ጀመሩ። በእያንዳንዱ ከተማም ንጉሥ ነበር። ይሁን እንጂ ሕዝቡ እንደ ቀድሞው ታላቅና ኃያላን አልነበሩም። ይህም በተለይ የከነዓንን ምድር በሚመለከት

የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት ታሪክ ጥናት Read More »

የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት እንዴት እንደተሰበሰቡ

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) በእንግሊዝኛው መጽሐፍ ቅዱስ የብሉይ ኪዳንን መጻሕፍት ቅደም ተከተል ከአማርኛው መጽሐፍ ቅዱስ ቅደም ተከተል ጋር አወዳድር። የተለያየ ቅደም ተከተል ያላቸው መጻሕፍት የትኞቹ ናቸው? ለ) የካቶሊክ እምነት ተከታይን መጽሐፍ ቅዱሱን እንዲያሳይህ ጠይቀው። ከአንተ መጽሐፍ ቅዱስ ይለያልን? በእነርሱ ብሉይ ኪዳን ውስጥ ስንት መጻሕፍት አሉ? ሐ) በመጽሐፍ ቅዱሳቸው ውስጥ ስንት የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት እንዳሉ አንዱን የኦርቶዶክስ ቄስ ጠይቅ። ለመጀመሪያዎቹ 39 መጻሕፍት የቀድሞ ክርስቲያኖች እንዴት «ብሉይ ኪዳን» የሚል ስያሜ እንደሰጡ ተመልክተናል። ነገር ግን የብሉይ ኪዳን ክፍል መሆን ያለባቸው መጻሕፍት የትኞቹ እንደሆኑ ከእግዚአብሔር ቃል ውጭ እንደሆኑ ሊቆጠሩ የሚገባቸው መጻሕፍትስ የትኞቹ እንደሆኑ ክርስቲያኖች ከስምምነት ላይ የደረሱት እንዴት ነው?  የመጽሐፍ ቅዱስ ምሁራን የተለያዩ የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት በእግዚአብሔር መንፈስ የተጻፉ የእግዚአብሔር ቃል ስለመሆናቸው ይከራከራሉ። እንደምታስታውሰው የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት ተጽፈው የተጠናቀቁት በ1000 ዓመታት ውስጥ ነው። ከኦሪት ዘፍጥረት ጀምሮ እስከ ዘዳግም ያሉት የመጀመሪያዎቹ መጻሕፍት የተጻፉት በ1400 ዓ.ዓ. ነው። የመጨረሻ የሆነው መጽሐፍ ትንቢተ ሚልክያስ የተጻፈው በ400 ዓ.ዓ. ነው። በእነዚህ የ1000 ዓመታት ጊዜ ውስጥ መጽሐፍ ቅዱስን እንዲጽፉ እግዚአብሔር በተለያዩ ሰዎች ተጠቅሞአል። በመጀመሪያው ምዕተ ዓመት ከክርስቶስ ልደት ወዲህ በመጽሐፍ ቅዱሳችን ውስጥ ያሉት 39 መጻሕፍት በሙሉ በእግዚአብሔር መንፈስ ምሪት የተጻፉ እንደሆነ እናውቃለን። የብሉይ ኪዳንን መጻሕፍት በአንድ ላይ ለማቀናጀት ብዙ ደረጃዎችን ማለፍ እንዳስፈለገ የመጽሐፍ ቅዱስ ምሁራን ይገምታሉ። የመጀመሪያ ደረጃ፡- በንግግር የማስተላለፍ ባሕል ነው። የመጀመሪያው ደረጃ የእግዚአብሔርን ቃል ከትውልድ ወደ ትውልድ በንግግር የማስተላለፍ ዘዴ ነው። የእግዚአብሔር ነቢያት በእግዚአብሔር ሕዝቦች ፊት ቆመው «እግዚአብሔር እንዲህ ይላል» በማለት የእግዚአብሔርን መልእክት ያስተላልፉ ነበር (ሕዝ.5፡5 ተመልከት)። በዚህ የንግግር ዘዴ ይተላለፉ የነበሩ አንዳንድ መልእክቶች ሳይጻፉ ብዙ ዘመን ሳያልፋቸው አይቀርም። ለምሳሌ፡- ከዘፍጥረት 1-50 ያሉት ሲሆኑ፥ ሌሎቹ ደግሞ ቶሉ የመጻፍ ዕድል አግኝተዋል። ሁለተኛ ደረጃ፡- የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት ተጻፉ። የተለያዩ የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት ጸሐፊዎች በመንፈስ ቅዱስ ምሪት አማካይነት የእግዚአብሔርን ቃል በተለያዩ መጻሕፍት ጽፈዋል። ሦስተኛ ደረጃ፡- አይሁድ የእግዚአብሔር ቃል ናቸው ብለው የሚያስቧቸውን የተለያዩ መጻሕፍት መሰብሰብ ጀመሩ። ይህ ረጅም ጊዜ የወሰደ ሥራ ነው። ለምሳሌ፡- መዝሙረ ዳዊት በአንድ ላይ ተጠርዞ ለመቀመጥ ብዙ መቶ ዓመታት ወስዶአል። አንዳንዶቹ መዝሙሮች የተጻፉት በ1400 ዓ.ዓ. በሙሴ፥ ሌሎቹ ደግሞ በ500 ዓ.ዓ. በዕዝራ የተጻፉ ናቸው። የብሉይ ኪዳን መጻሕፍትን በማሰባሰብና በማደራጀት ረገድ ዕዝራ ከፍተኛ ሚና እንደተጫወተ ብዙ ምሁራን ይገምታሉ። አራተኛ ደረጃ፡- አይሁድ የእግዚአብሔር ቃል ናቸው ብለው የተቀበሏቸውን የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት ሁሉ ሰብስበው ቅደም ተከተል በማስያዝ አስቀመጡአቸው። ይህ ማለት አንዳንዶቹን መጻሕፍት የእግዚአብሔር ቃል እንዳልሆኑ ቆጥረው አገለሉዋቸው ማለት ነው። አይሁዳውያን እስከ መጀመሪያው መቶ ዓመት መጨረሻ ድረስ የእግዚአብሔር ቃል ናቸው ብለው የሚያምኑባቸውን የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት በአሁኑ መልካቸው ስለማስቀመጣቸው መረጃ የለንም። ዳሩ ግን ከክርስቶስ መምጣት በፊት 200 ዓ.ዓ. ማለትም የመጨረሻው መጻሕፍት ከተጻፈ ከ200 ዓመት በኋላ የእግዚአብሔር ቃል ናቸው ብለው አይሁድ የገመቱአቸውን መጻሕፍት በሙሉ አይሁዳውያን አውቀውና መርጠው እንደነበር የሚገልጥ ማስረጃ አለ። ይህ ሂደት በጣም የተወሳሰበ ሊመስል ይችላል፤ ነገር ግን ክርስቲያኖች እንደመሆናችን መጠን ቃሉን በመጻፍ ሂደት ውስጥ ከሰዎች ጋር የሠራው እግዚአብሔር የተጻፉትን መጻሕፍት ያለአንዳች ስሕተት ሰዎች እንዲለዩ በማድረግ ረገድም እንደሠራ እናምናለን። እነዚህ መጻሕፍት የእግዚአብሔርን ቃልና ሥልጣን ይዘዋል። የቀድሞ አይሁዳውያን የእግዚአብሔር ቃል የሆኑትን ክፍሎች ከብዙ መጻሕፍት መካከል ለመለየት የተጠቀሙበት መመዘኛ ምንድነው? በአዲስ ኪዳን ዋናው መመዘኛ፡- «ይህ መጽሐፍ የተጻፈው በአንድ ሐዋርያ ነው ወይስ አብሮት በሚሠራ ሰው?» የሚል ነበር። የብሉይ ኪዳንን መጻሕፍት ለመለየት ግን አራት ዋና ዋና መመዘኛዎች የነበሩ ይመስላል። እነርሱም፡- መጽሐፉ በውስጣዊ ብቃቱና በመልእክቱ የእግዚአብሔር ሥልጣን እንዳለውና በእርሱ መንፈስ እንደተጻፈ የሚያሳይ ነገር አለን? የአይሁድ የሃይማኖት መሪዎች መጻሕፍቱን በሚመዝኑበት ጊዜ የእግዚአብሔር ጣት እንዳለበት እንዲያዩ መንፈስ ቅዱስ መርቶአቸዋል። የመጽሐፉ ጸሐፊ እግዚአብሔር በመለኮታዊነቱ መሪ እንዲሆን የመረጠው ሰው ነበርን? ለምሳሌ ንጉሥ፥ ካህን፡ ነቢይ፥ ወይም እግዚአብሔር በኃይል የተጠቀመበት በእስራኤል ላይ የሚፈርድ ሰው ነበርን?  በመጽሐፉ ውስጥ የሚገኙ ትምህርቶች በሙሉ እርስ በእርስና እንዲሁም የእግዚአብሔር ቃል መሆኑ በታወቀ በሌላ መጻሕፍት ውስጥ ከሚገኙ ትምህርቶች ጋር የሚስማማ ነውን? ለምሳሌ፡-በትንቢት መጻሕፍት ውስጥ የሚገኙ ትምህርቶች በመጀመሪያዎቹ አምስት የሙሴ መጻሕፍት ውስጥ እግዚአብሔር ከተናገረው ነገር ጋር የሚስማሙ ናቸውን? መጻሕፍቱ በአይሁድ የአምልኮ ጊዜ በተግባር ላይ ሊውሉ የቻሉ ናቸውን ወይስ ለሌላ ለተለየ ዓላማ ምንም አገልግሎት የማይሰጡ ናቸው? እያንዳንዱን መጽሐፍ በእጅ መገልበጥ ከባድ ድካም የሚጠይቅ ስለነበር፥ አይሁዳውያን ይገለብጡ የነበረው የእግዚአብሔር ቃል መሆናቸውን ያወቁዋቸውና ለእግዚአብሔር በሚሰጡት አምልኮ ውስጥ ሊጠቀሙባቸው የሚችሉትን ዓይነት ብቻ ነበር። እነዚህ አይሁዳውያን፥ እግዚአብሔር በቅዱሳት መጻሕፍት ውስጥ እንዲካተት የፈለገውን ነገር ብቻ መምረጣቸውን እንዴት እናውቃለን? በአንድ በኩል ስናየው፥ ልናውቅ አንችልም። ሰዎች ቃሉን እንዲጽፉ በማድረግ ከእነርሱ ጋር ግንኙነት ያደረገው እግዚአብሔር፥ በዓለም ላሉ ሰዎች ሁሉ እንዲደርስ የፈለገው ቃሉ ብቻ ተጠብቆ እንዲቆይ እንዳደረገ ማመን አለብን። በሌላ አንፃር ስናየው ግን የብሉይ ኪዳን መጻሕፍትን ሁሉ በምንመረምርበትና ዛሬ ካሉ ሌሎች መጻሕፍት ጋር በምናወዳድርበት ጊዜ ልዩነቱን ለማየት እንችላለን። በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ያልተካተቱት መጻሕፍት የመጽሐፍ ቅዱስን ያህል ጥራትና ብቃት ያለው መልእክት የላቸውም። በተጨማሪ የመጽሐፍ ቅዱስ መጻሕፍት እንደ ሌሎቹ መጻሕፍት ሳይሆኑ ምንም ዓይነት ያለመስማማት በማይታይበት ሁኔታ የመልእክት አንድነት ይታይባቸዋል። ሌሎች መጻሕፍት የእግዚአብሔር ቃል አለመሆናቸውን የምናየው እርስ በርስ የሚቃረኑ ትምህርቶች ስላሉባቸው ነው። እግዚአብሔር ብሉይ ኪዳንን እንዲጽፉ የተጠቀመባቸው የተለያዩ ሰዎች ቢሆኑም የብሉይ ኪዳን የመልእክት አንድነት ግን የሚያስደንቅ ነው። በተለያዩ መጻሕፍት መካከል ያሉ ትምህርቶች የተጻፉት በመቶ ዓመታት ልዩነት ቢሆንም፥ አንዳቸው ከሌላቸው ጋር በማይቃረን ሁኔታ ይስማማሉ። የእግዚአብሔር ልጆች መጻሕፍት እንደመሆናችን መጠን ዛሬ በእጃችን ያሉት ቅዱሳት የእግዚአብሔር ቃል መሆናቸውን በእርግጠኝነት መናገር እንችላለን። የእግዚአብሔር ሥልጣን ይገኝባቸዋል፤ ስሕተት አያስተምሩም፤ ስለ እውነተኛው እግዚአብሔርና ከእርሱ ጋር ሊኖረን ስለሚገባ ግንኙነትም በትክክል ያስተምሩናል። የእግዚአብሔር ቃል የሆነውንና ያልሆነውን የወሰኑት አይሁድ እንዳልሆኑ ማስታወስ ጠቃሚ ነው። ይልቁንም እግዚአብሔር በእስትንፋሱ የተጻፈውንና በእርሱ መሪነት የተሰጠውን ቃል ለመለየት ሰዎችን ተጠቀመባቸው።  የውይይት ጥያቄ፥ ክርስቲያኖች ቅዱሳት መጻሕፍት የእግዚአብሔር ቃል እንደሆኑ እርግጠኞች መሆን ያለባቸው ለምንድን ነው? የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) መጽሐፍ ቅዱስ ብቻ የተሟላና አንዳችም ስሕተት የሌለበት የእግዚአብሔር ቃል ከሆነ፥ ዛሬ እኛ በምንጽፋቸው መጻሕፍትና በምናዘጋጃቸው መልእክቶች ላይ እንዴት ተጽእኖ ያሳድርባቸዋል? ለ) እነዚህስ ጽሑፎቻችንና መልእክቶቻችን «የእግዚአብሔር ቃል» መሆን የሚችሉት እንዴት ነው? ሐ) «መጽሐፍ ቅዱስ የእግዚአብሔር ቃል ነው» ከምንለው አሳብ ጋር ( የእኛ መልእክት በምን ይለያል? ዛሬ ሰዎች በሚሰጡት ስብከትና በሚጽፏቸው መልእክቶች አማካይነት እግዚአብሔር የሚናገር ቢሆንም፥ ለእነዚህ ጽሑፎችና ትምህርቶች ስለምንሰጠው የሥልጣን መጠን ጥንቃቄ ማድረግ አለብን። የእግዚአብሔርን ሙሉ ሥልጣን የያዘው፥ የተጻፈው የእግዚአብሔር ቃል ማለትም መጽሐፍ ቅዱስ ብቻ ነው። ምንም ስሕተት የሌለበት እርሱ ብቻ ነው። የትኛውም መጽሐፍ ወይም ስብከት እንደ መጽሐፍ ቅዱስ አንዳችም ስሕተት የሌለበት ሊሆን አይችልም። እንደ መጽሐፍ ቅዱስ ሥልጣን ያለው መልእክትም ሆነ መጽሐፍ የለም፤ የምንጽፈውም ሆነ የምንናገረው ነገር የሚመዘነው በመጽሐፍ ቅዱስ ነው። ሰባኪዎችና ጸሐፊዎች እንደመሆናችን መጠን መጽሐፍ ቅዱስን በጥንቃቄ ማጥናት የእኛ ሐላፊነት ነው። በመጨረሻ ግን ደካሞችና ኃጢአተኞች መሆናችንን በትሕትና መቀበል አለብን። ስለ መጽሐፍ ቅዱስ ያለን መረዳት ውሱን ነው። ምንም ነቀፋና ስሕተት የለብንም ብለን ለመናገር አንችልም። የውይይት ጥያቄ፥ ጸሐፊዎች፥ አስተማሪዎችና ሰባኪዎች ይህንን መገንዘብ የሚያስፈልጋቸው ለምንድነው? ክርስቲያኖች ሁሉ መጽሐፍ ቅዱስ የተሟላ መሆኑን ያምናሉ፤ (ራእ. 22፡18-19)። የዮሐንስ ራእይ ከተጻፈ ወዲህ በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ ምንም ዓይነት መጽሐፍ መጨመር አይቻልም። ይህም ማለት ዛሬ በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ መጨመር ያለባቸው በመንፈስ መሪነት የተጻፉ መጻሕፍት አሉ የሚሉ ዛሬ የተነሡ የሐሰት ትምህርት አራማጅ ክፍሎች ተሳስተዋል ማለት ነው። ከመጽሐፍ ቅዱስ ጋር እኩል አድርገው የሚያስተምሩትም ስሕተት ነው። በ200 ዓ.ዓ. እይሁድ እንደ

የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት እንዴት እንደተሰበሰቡ Read More »

ትምህርት ብሉይ ኪዳን

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) የመጽሐፍ ቅዱስ ሁለት ዋና ዋና ክፍሎች የትኞቹ ናቸው? ለ) እንደዚያ ተብለው ለምን ተጠሩ? ሐ) ኪዳን የሚለውን ቃል ትርጉም ከመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት በመመልከት የተሟላ ትርጉም ጻፍ። መ) በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሚገኙ የተለያዩ ኪዳኖችን ዘርዝር። ሠ) ኪዳን የሚለው ቃል ከእግዚአብሔር ጋር ያለንን ግንኙነት እንዴት ይገልጻል? ክርስቲያኖች እንደመሆናችን መጽሐፍ ቅዱስ የእግዚአብሔር ቃል መሆኑን እናምናለን። በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ እግዚአብሔር ራሱን ለእኛ ይገልጥልናል። እርሱ ምን እንደሚመስልና ከእርሱ ጋርም ሕያው የሆነ ግንኙነት እንዲኖረን ከእኛ ምን እንደሚፈልግ እንማራለን። መጽሐፍ ቅዱስ የእግዚአብሔር ቃል በመሆኑ ስለ እግዚአብሔር ማንነት፥ ወደ መንግሥተ ሰማያት ስለሚወስደው መንገድ፥ ለእግዚአብሔር ስለመኖር ያለንን አሳብ ሁሉ የምንበይንበት መመዘኛ ነው። ማንኛውም አሳባችን፣ የባሕላችን አስተምህሮት፥ ወይም የሌሎች ሰዎች ትምህርት በመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት መመዘን አለበት። ከመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት ጋር የማይስማማ ማንኛውም ትምህርት መወገዝ አለበት። እንዲሁም እግዚአብሔር ስለ ራሱና ስለ ፈቃዱ የገለጠውን ነገር በሚገባ እንድንረዳ መጽሐፍ ቅዱስን በትክክል መተርጎም እንዳለብን ተምረናል። ይህንን ካላደረግን ግን በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የራሳችንን አሳብ እንጨምራለን፥ መጽሐፍ ቅዱስንም እንዳይናገረን እናደርገዋለን። የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) «ብሉይ» የሚለው ቃል ትርጉም ምን እንደሆነ አንድን የኦርቶዶክስ ካህን ወይም ሌላ ሰው ጠይቅ። ለ) «ኪዳን» የሚለው ቃል ትርጉም በአማርኛ ምንድን ነው? እኛ ክርስቲያኖች መጽሐፍ ቅዱስ ሁለት ዋና ክፍሎች እንዳሉት እናውቃለን። የመጀመሪያው ክፍል «ብሉይ ኪዳን» ሲባል፥ ሁለተኛው ደግሞ «አዲስ ኪዳን» ይባላል። በኢየሱስ የማያምኑ አይሁድ የዕብራውያን መጽሐፍ ቅዱስ በሚባለው ብሉይ ኪዳን ብቻ ያምናሉ። ለእነዚህ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች ሁለቱ ስሞች ለምን እንደተሰጡ ለመረዳት ሁለት ዋና ዋና ቃላትን መመልከት ያስፈልገናል። ፩. ኪዳን፡-. ኪዳን የሚለው ቃል ትርጉሙን የወሰደው ሁለት ሰዎች ወይም ቡድኖች በመካከላቸው እርስ በርስ ከሚያደርጉት ስምምነት ነው። ከብዙ መቶ ዓመታት በፊት ኢየሱስ ከሞተና አሁን በአዲስ ኪዳን ውስጥ ያሉ በርካታ መጻሕፍት ከተጻፉ በኋላ ክርስቲያኖች ቅዱሳት መጻሕፍትን ለመግለጥ «ኪዳን» የሚለውን ቃል መጠቀም ጀመሩ። መጽሐፍ ቅዱስ እግዚአብሔር ራሱንና ፈቃዱን የገለጠበት መሆኑና እግዚአብሔር ራሱን ከሰው ልጆች ጋር በኪዳን ወይም በስምምነት ግንኙነት እንዲኖረው እንዳደረገ ተገነዘቡ። በማንኛውም «ኪዳን» ውስጥ ሦስት ዋና ዋና ክፍሎች አሉ፡- በመጀመሪያ፥ በኪዳኑ ውስጥ የሚካተቱ አባላት አሉ። በመጽሐፍ ቅዱስ «ኪዳን» የሚለው ቃል የሚናገረው እግዚአብሔር ከተለያዩ ሰዎች ጋር ኅብረት እንዳደረገ ነው። አንዳንድ ጊዜ እግዚአብሔር እንደ አብርሃምና ዳዊት ካሉ ጋር ስምምነት አድርጓል። በሌላ ጊዜ ደግሞ እግዚአብሔር ከኖኅ ጋር እንዳደረገው ዓይነት ከሰው ልጆች ሁሉ ጋራ ስምምነት አድርጓል። የብሉይ ኪዳን ዋና ክፍል ግን እግዚአብሔር ከአብርሃም ልጆች ጋር (ማለትም ከአይሁድ ጋር) ስላደረገው ኪዳን የሚናገር ነው። የውይይት ጥያቄ፥ የአዲሱ ኪዳን ስምምነት የተደረገው ከማን ጋር ነው? ] ሁለተኛ፥ ቃል ኪዳኑ እንዲጠበቅ እንዲሟላና እንዲፈጸም በአንዱ ወይም በሁለቱም የኪዳኑ አባላት መጠበቅ ያለባቸው ቅድመ ሁኔታዎች በኪዳኑ ውስጥ መኖር አለባቸው። በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ሁለት ዓይነት ኪዳኖች ይገኛሉ። በሲና ተራራ ለአይሁድ ተሰጥቶ እንደነበረው (ዘጸ. 19:24) ዓይነት ያሉ አንዳንድ ኪዳኖች ቅድመ ሁኔታዎች ነበሩዋቸው። በሌላ አባባል እግዚአብሔር «እነዚህን ትእዛዛት ከጠበቃችሁ ለእናንተ እንደዚህ አደርግላችኋላሁ» ብሏል። ሌላው ዓይነት ኪዳን ግን ምንም ዓይነት ቅድመ ሁኔታ የሌለው የተስፋ ቃል ኪዳን ብቻ ነበር። የእግዚአብሔር ቃል ኪዳን ግን ምንም ዓይነት ቅድመ ሁኔታ የሌለው የተስፋ ቃል ብቻ ነበር። እግዚአብሔር ቃል ኪዳን ለገባላቸው ሰዎች ያለምንም ቅድመ ሁኔታ አንድ ነገር እንደሚያደርግላቸው ተናግሯል (ዘፍ. 12፡1-3)። የዚህ ቃል ኪዳን ምሳሌ እግዚአብሔር ከአብርሃም፥ ከዳዊትና ዛሬም ከክርስቲያኖች ጋር ያለው አዲሱ ቃል ኪዳን ዓይነት ነው። እግዚአብሔር በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሰጣቸውን ኪዳኖች በምናጠናበት ጊዜ ቅድመ ሁኔታ ያላቸውንና የሌላቸውን ለይቶ ማየት አስፈላጊ ነው። ሦስተኛ፡ በኪዳኑ ውስጥ አንዱ ክፍል ለሌላው የሚሰጣቸው ተስፋዎች አሉ። በብሉይ ኪዳን ብዙ ጊዜ ኪዳኑን የሚጀምር እግዚአብሔር ስለሆነ፥ ተስፋንም ለተለያዩ ሰዎች የሚሰጥ እርሱ ነው። እነዚህ ተስፋዎች እንደሚፈጸሙ ጥርጥር የለም። ምክንያቱም ተስፋውን የሰጠው ሊዋሽ ወይም አሳቡን ሊቀይር የማይቻለው አምላክ ስለሆነ ነው። የውይይት ጥያቄ፥ ኤር. 31፡31-34 አንብብ። በእነዚህ ቁጥሮች እግዚአብሔር ለእስራኤላውያን የሰጣቸው ተስፋ ምንድነው?  የውይይት ጥያቄ፥ ማቴ. 26፡26-29 አንብብ። ኢየሱስ ለደቀ መዛሙርቱ የሰጠውን ጽዋ ምን ብሎ ጠራው? የመጀመሪያዎቹ 39 መጻሕፍት ብሉይ ኪዳን፥ 27ቱ ደግሞ አዲስ ኪዳን ተብለው እንዲጠሩ የወሰኑት የጥንት ክርስቲያኖች እግዚአብሔር ከሰዎች ጋር ያለው ኅብረት እምብርት የኪዳኑ አሳብ እንደሆነ ተገንዝበው ነበር። በብሉይ ኪዳን ውስጥ እግዚአብሔር ለሰው ልጅ የሰጣቸው አያሌ የተለያዩ ኪዳኖች ይገኛሉ።  ከኖኅና ከሰው ልጆች ሁሉ ጋር የተደረገ ኪዳን (ዘፍጥ. 9፡1-17)፥ – የሰውን ዘር ካጠፋው ውኃ በኋላ እግዚአብሔር ከኖኅና ከእርሱ በኋላ ከተነሡ የሰው ልጆች ሁሉ ጋር ቃል ኪዳን አደረገ። በዚህ ኪዳን ውስጥ ይታዘዙት ዘንድ እግዚአብሔር የሰጣቸው ግልጥ የሆኑ ትእዛዛት ነበሩ። ደግሞም በዚያ ቃል ኪዳን ውስጥ የሰውን ልጆች በውኃ ላያጠፋ እግዚአብሔር የገባውም ቃል ኪዳን ነበር። ብዙውን ጊዜ በሰማይ ላይ የምናየው ቀስተ ደመና ያንን ቃል ኪዳን የሚያስታውስ ነው።  ከአብርሃምና ከዘሩ ጋር የተገባ ቃል ኪዳን (ዘፍጥ. 12፡1-3)።  የውይይት ጥያቄ፥ ዘፍ. 12፡1-3 አንብብ። እግዚአብሔር ለአብርሃም የሰጠውን የተለያዩ ቃል ኪዳኖች ዘርዝር። በብሉይ ኪዳን ከምናያቸው ቃል ኪዳኖች ሁሉ እጅግ በጣም አስፈላጊ የሆነው እግዚአብሔር ከአብርሃም ጋር ያደረገው ነው። እግዚአብሔር ከዘፍጥ. 12-25 እንዲሁም በአጠቃላይ በብሉይ ኪዳን ላይ በዚህ ቃል ኪዳን ላይ መመሥረቱን ቀጠለ። ይህ ቃል ኪዳን በብሉይና በአዲስ ኪዳን ውስጥ ያሉትን ሌሎች ቃል ኪዳኖች ለመረዳት የሚያስችል መሠረት ነው። ከአብርሃም ጋር በተገባው ቃል ኪዳን ውስጥ በቀጥታ አብርሃምን ራሱን ብቻ የሚመለከቱ በርካታ የተስፋ ቃሎች አሉ፤ ነገር ግን ለብሉይ ኪዳን ትምህርቶችና ታሪክ መሠረት የሆኑ ሌሎች በርካታ የተስፋ ቃሉችም አሉ። ሀ. እግዚአብሔር የአብርሃም ዘሮች የሆኑትን አይሁድ ወይም እስራኤላውያን ታላቅ ሕዝብ እንደሚሆኑ የተስፋ ቃል ሰጣቸው። የብሉይ ኪዳን የታሪክ መጻሕፍት ከዘጸአት ጀምሮ እስከ 2ኛ ዜና ድረስ ይህ ሕዝብ እዚህ ግባ ከማይባል ከአንድ ቤተሰብ ወደ ታላቅ ሕዝብነት እንዴት እንዳደገ የሚናገሩ ናቸው። ለ. እግዚአብሔር የአብርሃም ዘሮች የተስፋ ምድር የሆነችውን ከነዓንን እንደሚወርሱ ተናገረ። ይህች ምድር የእነርሱ ርስት ትሆናለች አለ። የኢያሱ፥ የመሳፍንትና የ1ኛና 2ኛ ሳሙኤል መጻሕፍት እነዚህ የተስፋ ቃሉች በረጅም ጊዜ ውስጥ እንዴት እንደተፈጸሙ የሚናገሩ ናቸው። ሐ. እግዚአብሔር ከአብርሃም በተለይም ከይሁዳ የዘር ግንድ አንድ ልዩ የሆነ ንጉሥ እንደሚወጣ የተስፋ ቃል ሰጣቸው (ዘፍጥ. 17፡6፥16፤ 49፡10)። ይህ የተስፋ ቃል በመጀመሪያ በዳዊት ተፈጸመ። በመጨረሻም በኢየሱስ ክርስቶስ ተፈጽሟል።  እግዚአብሔር በሲና ተራራ ከእስራኤል ሕዝብ ጋር ቃል ኪዳንን አደረገ (ዘጸ. 19-24)። እግዚአብሔር ምንም ዓይነት ቅድመ ሁኔታዎችን ከሰዎች ካልጠየቀባቸው ከሌሉቹ ቃል ኪዳኖች በተቃራኒ፥ በሲና ተራራ እግዚአብሔር ከአይሁድ ሕዝብ ጋር ያደረገው ስምምነት ቃል ኪዳኑ ይፈጽም ዘንድ እነርሱም ሊያሟሉት የሚገባ ቅድመ ሁኔታ ነበር። ብሉይ ኪዳን ብለን ከምንጠራቸው ከሠላሳ ዘጠኙ መጻሕፍት መካከል አብዛኛዎቹ እግዚአብሔር ከእስራኤል ጋር ስለገባው ቃል ኪዳን ከሚናገሩ ነገሮች ጋር የተያያዙ ነበሩ። በብሉይ ኪዳን እግዚአብሔር ከእስራኤል ጋር ቃል ኪዳን እንዴት እንደጀመረ (ዘፍጥረት እስከ ዘዳግም)፥ ለእስራኤላውያን የከነዓንን ምድር በመስጠት የገባላቸውን ተስፋ እንዴት እንዳከበረ (ኢያሱ እስከ 2ኛ ሳሙኤል)፥ እንዲሁም እስራኤላውያን ከእግዚአብሔር ጋር የነበራቸውን ቃል ኪዳን እንዴት እንዳፈረሱና ለጊዜው እንደተፈረደባቸው (1ኛ ነገሥት እስከ ሚልክያስ) እናነባለን።  ከካህኑ ከፊንሐስ ጋር የተገባ ቃል ኪዳን (ዘኁል. 25፡10-13)። በዚህ ቃል ኪዳን እግዚአብሔር ለፊንሐስ ዘሮች ካህናት የመሆን መብት ሰጥቷል። ከንጉሥ ዳዊት ጋር የተገባ ቃል ኪዳን (2ኛ ሳሙ. 7፡5-16)፡ እግዚአብሔር ለዳዊት የእርሱ ዘሮች በእስራኤል ሕዝብ ላይ ንጉሥ የመሆን መብት እንዳላችው ቃል ኪዳን ገባለት። በ መጨረሻ ይህ ቃል ኪዳን የይሁዳ አንበሳ በሆነው በኢየሱስ ክርስቶስ ተፈጸመ። እርሱ በእስራኤልና በሕዝቦች ሁሉ ላይ ንጉሥ ነው። አንድ ቀን ኢየሱስ ወደዚህች ምድር በመመለስ እንደገና ይነግሣል (ራዕ. 20፡4)። 

ትምህርት ብሉይ ኪዳን Read More »

መጽሐፍ ቅዱስን ለመተርጎም የሚጠቅሙ አጠቃላይ ሕጎች

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) እግዚአብሔር ለአንተ የተናገረባቸውን የተለያዩ መንገዶች ዘርዝር። ለ) በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ እግዚአብሔር ለሰዎች የተናገረባቸውን የተለያዩ መንገዶች ዘርዝር (ዕብ. 1፡1-2 ተመልከት)። በዘመናት ሁሉ እግዚአብሔር ራሱንና ፈቃዱን ለሰዎች በተለያዩ መንገዶች ገልጿል። ለአንዳንዶች እግዚአብሔር በቀጥታ በሚሰማ ድምፅ ተናግሯል። ለሌሎች በሕልምና በራእይ ተናግሯቸዋል። አንዳንዶች የእግዚአብሔር ግፊት በልባቸው ይሰማቸዋል። እግዚአብሔር እስካሁንም ድረስ ራሱንና ፈቃዱን በእነዚህ መንገዶች የሚገልጽ ቢሆንም፥ ዛሬ ራሱንና ፈቃዱን የሚገልጥበት ዋና መንገድ መጽሐፍ ቅዱስ ነው። ይህ እውነት በጣም አስፈላጊ የሆኑ ሁለት ጭብጦችን ያስተምረናል፡ እያንዳንዱ ክርስቲያን እግዚአብሔርን በጥልቀት ለማወቅ ብቻ ሳይሆን፥ የእግዚአብሔርን ፈቃድ ለማወቅና ለመታዘዝ ቃሉን የማንበብና የማጥናት ኃላፊነት አለበት። ክርስቲያን የእግዚአብሔርን ቃል ማንበብ ስለሚችል እግዚአብሔርን ላለመታዘዝ ምንም ምክንያት ማቅረብ አይችልም። ማንበብና መጻፍ የማይችሉ ክርስቲያኖች እንዲማሩ የሚያነቃቃቸው አንዱ ነገር የእግዚአብሔርን ቃል ለማንበብ እንዲችሉ ነው። መጽሐፍ ቅዱስ በእያንዳንዱ ነገድ ቋንቋ እንዲተረጎም የሚያስፈልግበት አንዱ ዋና ምክንያት ይህ ነው። እግዚአብሔር ፈቃዱ ከእኛ እንዲሰወር አይሻም፤ ይልቁንም እርሱን እንድናውቀውና በፈቃዱ እንድንኖር ይፈልጋል። መጽሐፍ ቅዱስ በእያንዳንዱ ሰው ቋንቋ ሊጻፍ ይገባዋል፤ ምክንያቱም ይህ ሲሆን ሰዎች ያነበቡትን ነገር በግልጥ ይረዱታል። በዚህ መንገድ ከእግዚአብሔር ጋር ኅብረት ማድረግና እርሱን የበለጠ በማወቅ ለፈቃዱ ታዛዥ መሆን ይቻላል። የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ለመጽሐፍ ቅዱስ ትርጓሜ ሥራ ድጋፍ ለማድረግ ስለ ቤተ ክርስቲያን መሪዎች ኃላፊነት ይህ ምን ሊያስተምረን ይገባል? ለ) የቤተ ክርስቲያን አባላት በግላቸው መጽሐፍ ቅዱስን ያጠኑ ዘንድ ለማበረታታት ስለ መሪዎች ኃላፊነት ይህ ምን ያስተምረናል?  እግዚአብሔር ከእኛ ጋር ግንኙነት ማድረግ የሚችልባቸው የተለያዩ መንገዶች በመጽሐፍ ቅዱስ ዳኝነት መመዘን አለባቸው። ብዙ ሐሰተኞች አስተማሪዎች ብድግ እያሉ እግዚአብሔር ተናግሮአል ይላሉ፤ ነገር ግን ተናግሮናል የሚሉት ነገር እግዚአብሔር በቃሉ በግልጥ ከተናገረው ነገር ጋር የሚቃረን ነው። ሰይጣንም ሕልምን መስጠት ይችላል። ሰይጣንም አንዳንድ ነገሮችን እንድናደርግ በልባችን ሊያነሣሣን ይችላል። እውነትን ከውሸት ለመለየት የምንችለው ሐሰተኛ አስተማሪዎች የሚናገሩትን ነገር ከእግዚአብሔር ቃል ጋር በማወዳደር ብቻ ነው። እግዚአብሔር የማይዋሽና የማይለወጥ ስለሆነ ዛሬ ለእኛ የሚገለጥልን ነገር ሁሉ በመጽሐፍ ቅዱስ ከገለጠው ነገር ጋር የግድ መስማማት አለበት።  የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) አንዳንድ ሰዎች እግዚአብሔር ተናገረን የሚሉበትን መንገድ ለመግለጥ የሚያስችሉ መግለጫዎችን ዘርዝር። ለ) ከመጽሐፍ ቅዱስ ጋር ስታወዳድረው እነዚህ ሰዎች የሚሉት ነገር ከእግዚአብሔር ጋር ይስማማል ወይስ ይቃረናል? ሐ) ሐሰተኛ አስተማሪዎች እግዚአብሔር ተናገረን ሲሉ ሰምተህ ታውቃለህን? መ) እግዚአብሔር በቃሉ እንዴት እንደተናገረህ የሚያስረዱ ምሳሌዎችን ጥቀስ። መጽሐፍ ቅዱስ እግዚአብሔር ራሱንና ፈቃዱን ለሰው ልጆች የገለጠበትና ዛሬም የሚገልጥበት መንገድ ነው ካልን፥ ልጆቹ እንደ መሆናችን ቃሉን ማጥናት ተቀዳሚ ተግባራችን መሆን አለበት። እግዚአብሔር መጽሐፍ ቅዱስን የሰጠን ከእርሱ ጋር የግል ግንኙነት ለመመሥረት እንድንችል ነው፤ ስለዚህ ከእግዚአብሔር ጋር በጸሎት ብቻ ሳይሆን ያለማቋረጥ መጽሐፍ ቅዱስን በማንበብ ካልተገናኘን እግዚአብሔር እንድናውቀው የሚፈልገውን ያህል እርሱን አናውቀውም።  የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ብዙ ክርስቲያኖች የእግዚአብሔርን ቃል ለማንበብ በጣም ጥቂት ጊዜ የሚሰጡት ለምንድነው? ለ) የእግዚአብሔርን ቃል ከማንበብና ከመጸለይ በጣም አስፈላጊ የሆነው የትኛው ይመስልሃል? ለምን? ከእግዚአብሔር ጋር ባለን ግንኙነት ያለማቋረጥ ልንከተላቸው የሚገባን ሁለት መንፈሳዊ ሥርዓቶች አሉ። ከእነዚህም አንዱ ጸሎት ነው። ብዙ ሰዎች በጸሎት ጊዜያቸውን ማሳለፍ ይወዳሉ። ለመጸለይ በማለዳ ይነቃሉ። ስለብዙ ነገር ይጸልያሉ። አንዳንድ ጊዜ ለእግዚአብሔር የልመና ጸሎት ብቻ ስለሚያቀርቡ ጸሎታቸው የስስታምነት ይሆናል። በጸሎታቸው እግዚአብሔርን ለማምለክና ለማመስገን ጥቂት ጊዜ ብቻ ይሰጣሉ። በጸሎት ከእግዚአብሔር ጋር እንነጋገራለን፥ እናመልከዋለንም። ደግሞም የከበደንን ነገር ወደ እርሱ ዘንድ በማምጣት እርሱ እንዲያቃልለው እንለምነዋለን፤ ነገር ግን እግዚአብሔር ለእኛ ሊናገረንና እርሱን ልናደምጠውም ይገባል። ሁለተኛው መንፈሳዊ ሥርዓት የእግዚአብሔርን ቃል ማንበብ ነው። የእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ እኛን የሚናገረን፥ የሚያበረታታን፥ የሚመራን፥ ራሱንና ፈቃዱን ለእኛ የሚገልጠው ወዘተ በቃሉ ነው። ክርስቲያን በመንፈሳዊ ሕይወቱ እንዲያድግ መጸለይና መጽሐፍ ቅዱስን ማንበብ ሚዛናዊ በሆነ መንገድ ሊከናወኑ ይገባል። ሁለቱም እኩል አስፈላጊዎች ናቸው። የውይይት ጥያቄ፥ የዚህ ሳምንት የጸሎት ጊዜህን መርምር። ሀ) የእግዚአብሔርን ቃል ለማንበብ ምን ያህል ጊዜ እንደወሰድክ ተከታተል። ል) ለመጸለይ ምን ያህል ጊዜ እንደወሰድህ ጻፍ። ሐ አንተ ልታደርገው ቀለል የሚልህ የትኛውን ነው? ለምን? መ) በሕይወትህ ውስጥ ጸሎትንና የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናትን እንዴት የማያቋርጥ ልምምድ ማድረግ ትችላለህ?  ብዙ ሰዎች መጽሐፍ ቅዱስን በተለይም ብሉይ ኪዳንን ለመረዳት በጣም አስቸጋሪ እንደሆነ አድርገው ይገምታሉ፤ ስለዚህ የሚወዱአቸውንና የሚረዱአችውን ክፍሎች ያነብባሉ። ለመረዳት የሚከብዱትንና አስቸጋሪ የሆኑትን ክፍሎች አያነብቧቸውም። የውይይት ጥያቄ፥ ብዙ ጊዜ የማታነብባቸውንና ለመረዳት አስቸጋሪ የሚሆኑብህ ክፍሎች ያሉባቸውን የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት ዘርዝር። ነገር ግን መጽሐፍ ቅዱስ በሙሉ የእግዚአብሔር ቃል ከሆነ፥ እግዚአብሔር ለእያንዳንዱ መጽሐፍና ምንባብ ዓላማ አለው፤ ስለዚህ መጽሐፍ ቅዱስን በሙሉ ማንበብና መረዳት ለሁላችንም ጠቃሚ ነው። በጣም አስቸጋሪ የሆኑ የብሉይ ኪዳን ክፍሎች እንኳ ስለ እግዚአብሔርና ስለ ፈቃዱ የሚገልጡት ነገር አላቸው። እጅግ ከባድ የምንላቸው ክፍሎች ሁሉ «ለትምህርት፥ ለተግሣጽ፥ ልብን ለማቅናትና ጻድቅ ለሆነ ምክር» የሚጠቅሙ ናቸው (2ኛ ጢሞ. 3፡16)፤ ስለዚህ እግዚአብሔር በቃሉ በሚገኙ የተለያዩ ክፍሎች በኩል ለእኛ ሊገልጥ የፈለገውን ፈቃዱን መረዳት ጠቃሚ ነው። ብሉይ ኪዳንን በምናጠናበት ጊዜ በጣም አስቸጋሪ በሆኑ መጻሕፍት ውስጥ እንኳ የእግዚአብሔር ዓላማና መልእክት ምን እንደሆነ ለመረዳት እንጥራለን። መጽሐፍ ቅዱስን ለመረዳትና በትክክል ለመተርጎም ስንፈልግ ልናስታውሳቸው የሚገቡ ሦስት መሠረታዊ እውነቶች አሉ፡- የመጽሐፍ ቅዱስ መሠረታዊ ትምህርት (መልእክት) ግልጥ ነው፤ ማንኛውም ክርስቲያን ሊያነበውና ሊረዳው ይችላል። እግዚአብሔር የጻፈው የተደበቀ መልእክት አይደለም። ፈቃዱ እንዲታወቅና ልጆቹ ሁሉ እንዲከተሉት ይፈልጋል። እኛ ልጆቻችን በሚገባቸው መንገድ አንድን ነገር እንዲያደርጉ ትእዛዝ እንደምንሰጣቸው ሁሉ እግዚአብሔርም በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ትእዛዛቱን የሰጠው ክርስቲያኖች ሁሉ እርሱ የገለጠውን ነገር መረዳት በሚችሉበት መንገድ ነው። የእግዚአብሔርን ቃል በማስተዋል የሚያነብ ማንኛውም ክርስቲያን እግዚአብሔር ማን እንደሆነ፥ ሰዎች ኃጢአተኞች እንደሆኑና ክርስቶስ ለሰዎች ኃጢአት ሁሉ በመስቀል ላይ እንዴት እንደሞተ በቂ ግንዛቤ ያገኛል። የእግዚአብሔር ቃል መረዳት የተሰጠው «ለተማሩ» ወይም «በመጽሐፍ ቅዱስ» ወይም በሥነ መለኮት ትምህርት ዲግሪ ላላቸው ብቻ አይደለም። የእግዚአብሔርን ቃል ለማጥናት ሰፊ ጊዜ የሰጡና የብሉይ ኪዳንን ዘመንና ባሕል በከፍተኛ ሁኔታ የተገነዘቡ ሰዎች የበለጠ ሊረዱአቸው የሚችሉአቸው አስቸጋሪ የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርቶች ቢኖሩም፥ መሪዎች እንደመሆናችን መጠን መጽሐፍ ቅዱስ እኛ ብቻ ልንረዳው የምንችልና ለእነርሱ ግን በጣም ከባድ ነው ብለን ለቤተ ክርስቲያናችን ምእመናን በፍጹም መናገር የለብንም። በመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት መሠረት ክርስቲያኖች ሁሉ የእግዚአብሔር ካህናት ስለሆኑ፥ የእግዚአብሔርን ቃል በመንፈስ ቅዱስ እርዳታ ሊያጠኑና ሊተረጉሙት ይችላሉ (1ኛ ጴጥ. 2፡4-10፤ 1ኛ ዮሐ. 2፡27 ተመልከት)። የውይይት ጥያቄ፥ ክርስቲያኖች መጽሐፍ ቅዱስን መረዳት የሚችሉት ልዩ መሪዎች ብቻ እንደሆኑ በማሰብ መጽሐፍ ቅዱሳቸውን ለራሳቸው ማጥናት በሚያቆሙበት ጊዜ አደገኛ የሚሆነው ለምንድነው? እግዚአብሔር ራሱንና ፈቃዱን ለሰው ልጆች ሁሉ በግልጽ ገልጧል። የጻፈው የተደበቀ መልእክት አይደለም። ብዙ ክርስቲያኖች እግዚአብሔር መጽሐፍ ቅዱስን የጻፈው «በሰምና ወርቅ» ነው ብለው ያስባሉ። እግዚአብሔር መጽሐፍ ቅዱስ እንዲጻፍ በሚያደርግብት ጊዜ የተጻፈውን ነገር እውነተኛ ትርጉም ከቃላቱ በስተጀርባ ሰውሮታል ብለው ይገምታሉ። ስለዚህ መጽሐፍ ቅዱስን ለመተርጎም በሚሞክሩበት ጊዜ ዘወትር የተሰወረ ትርጉምን ይፈልጋሉ። የምናመልከው አምላክ ግን ራሱንና ፈቃዱን በምሥጢራዊ ቃላት የሚሰውር አይደለም። እግዚአብሔር እኛን በቀጥታ ይናገረናል፤ እንድናውቀውና እንድንታዘዘውም ይፈልጋል። ጓደኛችን ስለ ሕይወት በማንሣት አንድ ነገር እንድናደርግለት በመጠየቅ ደብዳቤ ቢጽፍልን የተሰወረ ትርጉም ከደብዳቤው መፈለግ የተለመደ አይደለም። የጻፈውን መልእክት እንዳለ እንቀበለዋለን። የእግዚአብሔርም ቃል ከዚህ ጋር ተመሳሳይ ነው። በአንድ በኩል ስናየው እግዚአብሔር ለእኛ የጻፈው ደብዳቤ ነው። እግዚአብሔር ስለ ራሱ ይነግረናል። ደግሞም እስካሁን ምን ሲያደርግ እንደነበረና እኛ ምን እንድናደርግ እንደሚፈልግ ይነግረናል። እግዚአብሔር ራሱንና ፈቃዱን ምሥጢራዊ ትርጉም ያላቸውን ቃላት በመጠቀም መደበቅ ልማዱ አይደለም። ብዙ ጊዜ መጽሐፍ ቅዱስን ለመረዳት አስቸጋሪ የሆነው ከእኛ የተለየ ቋንቋ ለሚናገሩና በተለየ ባሕል ውስጥ ለሚኖሩ ሰዎች የተጻፈ በመሆኑ ነው። ሁላችንም ብንሆን አንድን ነገር በምንሠራበት ወይም በምንናገርበት ጊዜ

መጽሐፍ ቅዱስን ለመተርጎም የሚጠቅሙ አጠቃላይ ሕጎች Read More »

የብሉይ ኪዳን ቅጂዎቻችን እንዴት ሊደርሱን እንደቻሉ

እኛ ክርስቲያኖች የእግዚአብሔር ቃል ነው ብለን የምናምነው መጽሐፍ ቅዱስን ብቻ ነው። የእግዚአብሔርን ሙሉ ሥልጣን የያዘ ከመሆኑም ሌላ ክርስቲያን እውነትን የሚረዳበት መሠረት ነው። በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ እግዚአብሔር ማንነቱን፥ ሰው ማን እንደሆነ፥ ከዘላለማዊ አምላክም ጋር ግንኙነት ለማድረግና እርሱን ደስ ለማሰኘት ምን ማድረግ እንዳለበት አስፈላጊውን እውነት ሁሉ እንደገለጠ እናምናለን። ዳሩ ግን ለመረዳት አስቸጋሪ የሆነ ሌላም እውነት ገልጾልናል። ይህም ክርስቲያኖች እንደመሆናችን መጠን የምናምነው እውነት አንዳችም ስሕተት የሌለበት የመጀመሪያው መጽሐፍ ቅዱስ ነው የሚል ነው። ዛሬ በእጃችን የሚገኘው መጽሐፍ ቅዱስ የያዛቸው ዋና ዋና ትምህርቶች ምንም ስሕተት የሌለባችው ቢሆኑም የመጽሐፍ ቅዱስ ቅጂዎችን በመገልበጥ ረገድ የታዩ አንዳንድ ስሕተቶች እንዳሉ እንገነዘባለን። ዛሬ በእጃችን ስላለው የመጽሐፍ ቅዱስ ቅጂ ጥቂት ነገሮችን እናጠናለን። ብሉይ ኪዳን ረጅም ዕድሜ ያለው መጽሐፍ ነው። በ1400 ዓ.ዓ. አካባቢ ሙሴ የመጀመሪያዎቹን አምስት መጻሕፍት መጻፍ ጀመረ። ይህም ከ3500 ዓመታት ያህል በፊት ማለት ነው። የመጨረሻው የብሉይ ኪዳን መጽሐፍ የተጻፈው በ400 ዓ.ዓ. ገደማ ነበር፤ ስለዚህ የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት በሙሉ ተጽፈው ለማለቅ 1000 ዓመታት ያህል ወስደዋል። በሌላ በኩል አዲስ ኪዳን ተጽፎ ያለቀው በ100 ዓ.ም. ነው። የአዲስ ኪዳን ዕድሜ በ2000 ዓመታት ያነሠ ነው፤ ስለዚህ አዲስ ኪዳንን በመገልበጥ ረገድ የተሠራው ስሕተት በብሉይ ኪዳን ከተሠራው ስሕተት ያነሰ ነው፤ ደግሞም ምሁራን የመጀመሪያዎቹ የአዲስ ኪዳን መጻሕፍት ከተጻፉ በኋላ በ150 ዓመታት ጊዜ ውስጥ ተሠርተው የነበሩ ቅጂዎችን በከርሰ ምድር ጥናት አማካኝነት አግኝተዋል፤ ስለዚህ ምሁራን ከብሉይ ኪዳን መጻሕፍት ይበልጥ የአዲስ ኪዳን መጻሕፍትን ትክክለኛነት ለማረጋገጥ ችለዋል። ምሁራን ያገኙአቸው አብዛኛዎቹ የብሉይ ኪዳን ቅጂዎች የመጀመሪያዎቹ መጻሕፍት ከተጻፉ ከብዙ መቶዎች ወይም ከአንድ ሺህ ዓመታት በኋላ የተገለበጡ ናቸው፤ ስለዚህ ከአዲስ ኪዳን ይልቅ በርካታ ስሕተት የመፈጸም ዕድል ያለው በብሉይ ኪዳን ውስጥ ነው። በጥንቱ ዓለም የጽሕፈት መኪናዎች፡ የጽሑፍ ማባዣዎችም ሆነ ወረቀት አልነበሩም። መጻሕፍት ሁሉ በእጅ መጻፍ ነበረባቸው። በጥንት ዘመን ሰዎች ለመጻፍ ይጠቀሙ የነበረው በተለያዩ ነገሮች ነበር። አንዳንዶች እግዚአብሔር ለእስራኤላውያን ትእዛዝን በሚሰጥበት ጊዜ እንደተጠቀመው በድንጋይ ይጠቀማሉ (ዘጸ. 24፡12፤ 31፡18፤ ኢያ. 8፡32-35 ተመልከት)። ሌሉች በእርጥብ ሸክላ ላይ ይጽፉ ነበር። እርጥቡ ሸክላ ሲደርቅ በላዩ ላይ የተጻፈው ነገር ቋሚ ሆኖ ይቀራል። ሌሉች በእንስሳት ቆዳ ላይ ይጽፉ ነበር። በኋላ ደግሞ ሰዎች ፓፒረስ ተብሎ በሚጠራ ከሸምበቆ በተሠራ ነገር ላይ ይጽፉ ነበር። በድንጋይና በሸክላ የተጻፉት ነገሮች ለብዙ መቶ ዓመታት የቆዩ ቢሆኑም በእንስሳት ቆዳና በፓፒረስ የተጻፉት ግን ጊዜያዊና የሚበሰብሱ ነበሩ፤ ስለዚህ በሚያረጁበት ጊዜ ተገልብጠው ሌላ ቅጂ ሊዘጋጅላቸው ያስፈልግ ነበር። ሰዎች ለራሳቸው የግል ቅጂ እንዲኖራቸው ሲፈልጉም በእጃቸው በመጻፍ ሊገለብጡት ያስፈልግ ነበር። አይሁድ ብዙ ጊዜ የሚጽፉት በእንስሳት ቆዳ ላይ ሲሆን፥ እያንዳንዱ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል በብራና ጥቅል ላይ ይጻፍ ነበር። (ለምሳሌ ሉቃ. 4፡16-21)።  በጥንት ዘመን ብዙ ሰዎች ማንበብ አይችሉም ነበር። ጸሐፍት የተባሉ የተወሰኑ ሰዎች ብቻ ማንበብና መጻፍ ይችሉ ነበር። እነዚህ ሰዎች የኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ደብተራዎችን የሚመስሉ ነበሩ። እነዚህ ጸሐፍት ለጥንታዊቷ እስራኤል በጣም አስፈላጊ ሰዎች ነበሩ። ለነገሥታቱ ልዩ አማካሪዎች በመሆናቸው፥ እንደ ዲፕሉማትና አምባሳደር ሆነው ወደ ሌሉች አገሮች ይላኩ ነበር። ለአይሁድ ግን ከሁሉ የሚበልጠው የእነዚህ ሰዎች ሥራ ቅዱሳት መጻሕፍትን መገልበጣቸው ነበር። ቅዱሳት መጻሕፍቱ ይቀመጡ የነበሩት ሰዎች በሚያመልኩበት በቤተ መቅደስ ስለነበር፥ በጥንቷ እስራኤል ጸሐፍቱ የአምልኮ መሪዎች የሆኑት ካህናትና ሌዋውያን ነበሩ። እነዚህ የጥንት ጸሐፍት የእግዚአብሔር ቃል ቅዱስ መሆኑን ያውቁ ስለነበር፥ ቅዱሳት መጻሕፍትን በጥንቃቄ ይገለብጡ ነበር። በ586 ዓ.ዓ. የኢየሩሳሌም ቤተ መቅደስ ከተደመሰሰና እስራኤላውያን በአሕዛብ መካከል ከተበተኑ በኋላ ቅዱሳት መጻሕፍትን ይገለብጡ የነበሩ ጸሐፍት ለአይሁድ ሕዝብ በጣም አስፈላጊ ሰዎች ሆኑ። እንደ ዕዝራ ያሉ ካህናት ጸሐፍት የሃይማኖት ሰዎች ሆኑ። እነዚህ ጸሐፍት (አንዳንድ ጊዜ «የሕግ መምህራን» ይባሉ የነበሩ) ኢየሱስ በኖረበት ዘመን በሕዝቡ ላይ ታላቅ ሥልጣን ያላቸው ጠንካራ የፖለቲካ ፓርቲ ሆኑ። የኢየሱስ ጠላቶችም ነበሩ (ማቴ. 12፡38-39 ተመልከት)።  የውይይት ጥያቄ፡- የብሉይ ኪዳን መጻሕፍትን ለመጠበቅ አይሁድ ያደረጉት ነገር ወይም ሁኔታ ከጥቂት ትውልድ በፊት የኦርቶዶክስ አብያተ ክርስቲያናት በኢትዮጵያ ያደርጉት ከነበረው ሁኔታ ጋር እንዴት ይመሳሰላል? በ586 ዓ.ዓ. የኢየሩሳሌም ቤተ መቅደስ እስከተደመሰሰበት ጊዜ ድረስ መጽሐፍ ቅዱስን በመገልበጥ ረገድ ስሕተት ለመሥራት የሚያደርስ በቂ ምክንያት አልነበረም። ዋናው የመጽሐፍ ቅዱስ ቅጂ ያለው በኢየሩሳሌም ቤተ መቅደስ ውስጥ ነበር። እንደ እስራኤል ነገሥታት ያሉ አንዳንድ ሰዎች አንዳንድ ጊዜ የብሉይ ኪዳን መጻሕፍትን ቢገለብጡም (ዘዳግ. 17፡18፤ 2ኛ ነገሥት 11፡12 ተመልከት)፤ ዛሬ በእጃችን እንዳለው የእግዚአብሔር ቃል በበርካታ ቁጥር አልነበረም። የእስራኤል ሕዝብ በዓለም ሁሉ በተበተኑበት ጊዜ ግን የተለያዩ ቅጅዎችና ትርጉሞች መኖር አስፈላጊ ሆነ። ለምሳሌ፡- እንደ ዳንኤልና ሕዝቅኤል ያሉ ሰዎች በባቢሎን ነበሩ። በባቢሎን ይኖሩ የነበሩ አይሁድ የራሳቸው የመጽሐፍ ቅዱስ ቅጂ ማግኘት አስፈለጋቸው። ብዙዎቹ አይሁድ በኋላ ወደ እስራኤል ቢመለሱም፥ ሌሎች በርካታ አይሁድ በባቢሎን ቀሩ። በባቢሎንም ሆነው ቅዱሳት መጻሕፍትን መገልበጥ ቀጠሉ። በባቢሎንና በኢየሩሳሌም ይኖሩ የነበሩ ጸሐፍት ቅጂዎቻቸውን ለማወዳደር ዕድሉ አልነበራቸውም፤ ስለዚህ በየስፍራው ባሉት ቅጂዎች መካከል ልዩነቶች መታየት ጀመሩ። ደግሞም በ200 ዓ.ዓ. አንዳንድ አይሁድ በግሪክ ቋንቋ የእግዚአብሔር ቃል አስፈለጋቸው። በግብፅና በሌሎች አካባቢዎች ስለኖሩና መጀመሪያ መጽሐፍ ቅዱስ የተጻፈበትን የዕብራይስጥን ቋንቋ ስለረሱ በሚናገሩት በግሪክ ቋንቋ መጽሐፍ ቅዱስ አስፈለጋቸው፤ ስለዚህ ምሁራን ብሉይ ኪዳንን ወደ ግሪክ ቋንቋ ተረጎሙት። ይህም ትርጉም ሴፕቱዋጀንት በመባል ይታወቅ ጀመር። ክርስቶስ በኖረበት ዘመን ሴፕቱዋጀንት እጅግ ተወዳጅ ቅዱስ መጽሐፍ ሲሆን፥ ብዙ የአዲስ ኪዳን ጸሐፊዎችም ከዚህ ትርጉም ይጠቅሱ ነበር፤ ስለዚህ ሦስት ዋና ዋና የብሉይ ኪዳን ቅጂዎች አሉን። እነርሱም በኢየሩሳሌም የነበረው፥ በባቢሎን የነበረውና በግሪክ ቋንቋ የተጻፈው ናቸው፡፡ በሌሉች ስፍራዎች የነበሩ ሰዎችም የየራሳቸውን ቅጅ መገልበጥ ጀመሩ። ለምሳሌ:- ሳምራውያን አምስቱን የሙሴ መጻሕፍት (ፔንታቱክ) ለራሳቸው አምልኮ ገለበጡ፤ ስለዚህ በአዲስ ኪዳን ዘመን በርካታ የብሉይ ኪዳን ቅጂዎች ሲኖሩ፥ ማንም ሰው በቅጂው ውስጥ ስሕተት እንደነበረና እንዳልነበረ ለማወቅ አላወዳደረም፤ ስለዚህ በትርጉሞች ውስጥ ስሕተቶች እየጨመሩ መጡ። የትርጉሞች ወይም የቅጂዎች ስሕተቶችም እየጨመሩ የመጡት ጸሐፊዎቹ በሚገለብጡበት ጊዜ በሠሩት ስሕተት ምክንያት ነው። የመጻሕፍቱን ቅጂዎች በመገልበጥ እንዴት ስሕተቱ ሊፈጸም እንደሚችል የሚከተለውን መግለጫ እንመልከት፡- የማዕከላዊው ቤተ ክርስቲያን ጽሕፈት ቤት በየአውራጃው ለሚገኙ የአብያተ ክርስቲያናት ጽሕፈት ቤቶች አንድ ደብዳቤ እንደላከ አስብ። በደብዳቤውም ውስጥ የተወሰኑ መመሪያዎችና ደንቦች ነበሩ። እነዚህ የአውራጃ አብያተ ክርስቲያናት ይህንን ደብዳቤ በእጃቸው ገልብጠው ለወረዳ አብያተ ክርስቲያናት ቢሮዎች ይልካሉ፤ የወረዳ አብያተ ክርስቲያናት ቢሮዎች ደግሞ ይህን ደብዳቤ በእጃቸው ገልብጠው ለየአብያተ ክርስቲያናት ቢሮዎች ይልካሉ። እያንዳንዱ ቤተ ክርስቲያን ደግሞ ደብዳቤዎችን በእጁ ገልብጦ ለየአባላቱ ማደል ነበረበት እንበል። ይህን ነገር ማድረግ ቢኖርብን በዚህ ሂደት ውስጥ የሚሆኑ ሁለት ዋና ነገሮች ሲፈጸሙ እናይ ነበር። የመጀመሪያው፥ በእጅ በመገልበጥ ረገድ ስሕተት መታየት መጀመሩ ነው። ሰዎች በእጃቸው በመጻፍ በሚገለብጡበት ጊዜ አንዳንድ ፊደላትን ወይም ቃላትን ይተዋሉ። ደብዳቤው ከማዕከላዊው ቢሮ ማለትም መጀመሪያ ከተጻፈበት ቦታ እየራቀ በሄደ ቁጥር የስሕተቱ መጠን እየጨመረ ይሄዳል። ሁለተኛው፥ ስሕተቶቹ አንድ የተወሰነ መንገድ የሚከተሉ መሆናቸው ነው። አንድ የአውራጃ ቤተ ክርስቲያን ጽሕፈት ቤት ከማዕከላዊ ቤተ ክርስቲያን ጽሕፈት ቤት የመጣውን ደብዳቤ በሚገለብጥበት ጊዜ አንድ ቃል ቢተው ከዚያ አውራጃ ቤተ ክርስቲያን ጽሕፈት ቤት ደብዳቤ የሚደርሳቸው የወረዳ ቤተ ክርስቲያን ጽሕፈት ቤቶች ሁሉ ተመሳሳይ ስሕተት የያዙ ይሆናሉ። ይህም ስሕተት ያንን ቃል ያለመያዝ ይሆናል።  የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት በተለያዩ ስፍራዎች በእጅ ጽሑፍ በሚገለበጡበት ጊዜም የተሠራው ስሕተት ይህንኑ የመሰለ ነበር፤ ስለዚህ የመጽሐፍ ቅዱስ ምሁራን ያደረጉት አንድ ዋና ነገር ስሕተቱ ከየት እንደመጣ ለማወቅ የተገኙትን የተለያዩ ቅጂዎች ማወዳደር ነበር። በኢየሩሳሌም የተገለበጡትን መዛግብት ከባቢሎን፥ ከግሪክ እንዲሁም በኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ከሚገኘው የግዕዝ መጽሐፍ ቅዱስ ጋር ሁሉ ያመሳክራሉ። በዚህ ዓይነት የመጽሐፍ ቅዱስ ምሁራን ከመጀመሪያው መጽሐፍ

የብሉይ ኪዳን ቅጂዎቻችን እንዴት ሊደርሱን እንደቻሉ Read More »

ብሉይ ኪዳን የእግዚአብሔር ቃል ነው

የውይይት ጥያቄ፡- 2ኛ ጢሞ. 3፡16-17 ና 2ኛ ጴጥ. 1፡20-21 አንብብ። ሀ) እነዚህ ቁጥሮች መጽሐፍ ቅዱስን በማስገኘት ረገድ ስለ እግዚአብሔር ድርሻ ምን ይናገራሉ? ለ) እነዚህ ቁጥሮች መጽሐፍ ቅዱስን በማስገኘት ረገድ የሰው ድርሻ ምንድን ነው ብለው ያስተምራሉ? ሐ) እነዚህ ቁጥሮች እግዚአብሔር መጽሐፍ ቅዱስን ለእኛ የሰጠበት ምክንያት ምንድነው ብለው ያስተምራሉ? መ) መጽሐፍ ቅዱስ በአንተ ሕይወት ውስጥ ለትምህርት፥ ለተግሣጽ፥ ልብን ለማቅናትና በጽድቅ ላለው ምክር እንዴት እንዳገለገለ ግለጥ። መጽሐፍ ቅዱስ ምንድን ነው? እንደ ቁርአንና ሌሎች ሃይማኖታዊ ጽሑፎች ሁሉ የሰው ሥራ ነውን? ወይስ ሰውን መሣሪያ አድርጎ ሳይጠቀም እግዚአብሔር በቀጥታ ለሰዎች የሰጠው ነው? ዓላማውስ ምንድን ነው? መጽሐፍ ቅዱስ በራሱ ኃይል ያለው የምትሀት መጽሐፍ ነውን? እነዚህ ብሉይ ኪዳንን ማጥናት ከመጀመራችን በፊት ልንመልሳቸው የሚገቡ በጣም አስፈላጊ ጥያቄዎች ናቸው። ክርስቲያኖችም ሆኑ አይሁዶች ብሉይ ኪዳን የተለየ የእግዚአብሔር ቃልና በውስጡም እግዚአብሔር ራሱንና ዓላማውን ለሰው ልጅ የገለጠበት መጽሐፍ እንደሆነ ይናገራሉ። ክርስቲያኖች ከአይሁዶች የሚለዩት አዲስ ኪዳንም የእግዚአብሔር ቃል እንደሆነ ስለሚያምኑ ነው። ብዙውን ጊዜ ክርስቲያኖች ስለ እግዚአብሔር ቃል ሁለት የተሳሳቱ ግንዛቤዎች አሉአቸው። የመጀመሪያው፥ ብዙ ክርስቲያኖች እግዚአብሔር እንዲጻፍ የፈለገውን ቃል ለተለያዩ ሰዎች ቃል በቃል አጽፎአቸዋል ብለው ያስባሉ፤ ስለዚህ አንዳንዶች ብሉይ ኪዳን በሚጻፍበት ጊዜ ጸሐፊዎቹ ምንም ድርሻ አልነበራቸውም ብለው ያስተምራሉ። በዚህ መልክ የተጻፉ አንዳንድ ክፍሎች ቢኖሩም (ለምሳሌ ዘጸ. 24፡4-7)። እነዚህን የብሉይ ኪዳን ክፍሎች የጻፉት ጸሐፊዎች ግን የሚጽፉት ጉዳይ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሚገባ የቅዱሳት መጻሕፍት አካል መሆኑን እንኳ አያውቁም ነበር። አልፎ አልፎም ጸሐፊዎቹ ከሌሎች መጻሕፍት የቀዱበት አጋጣሚ ነበር (ለምሳሌ፡- ዘኁል. 22፡14-15፤ ኢያ. 10፡13)። በሁለተኛ ደረጃ፥ እራሳቸውን ክርስቲያን አድርገው የሚቆጥሩ አንዳንድ ሰዎች መጽሐፍ ቅዱስ የእግዚአብሔር ቃል እንደሆነ ያለማሰባቸው ነው። ይልቁንም መጽሐፍ ቅዱስ የሰው ሥራ እንደሆነ ያስተምራሉ። መጽሐፍ ቅዱስ የአይሁድን ሃይማኖታዊ ልምምድ ለመረዳት የሚጠቅም እንጂ፥ እውነት አይደለም ብለው ያስባሉ። ሌሎች ደግሞ መጽሐፍ ቅዱስ እንደ ቁርአን ወይም እንደ ሂንዱ እምነት መጻሕፍት ነው፤ ምክንያቱም ሁሉም የሚናገሩት ሰው እግዚአብሔርን ለማወቅ ያደረገውን ጥረት ነው ይላሉ። አንዳንድ ሰዎች መጽሐፍ ቅዱስ ገና ተጽፎ አላለቀም በማለት ዛሬም ቢሆን «የእግዚአብሔር ቃል» የሚሏቸውን ብዙ የሐሰት ትምህርቶች (ኑፋቄዎች) በመጨመር ላይ ይገኛሉ። የእነዚህ ትምህርቶች አመንጪ የሆኑት ሰዎች አሳባቸውን ከመጽሐፍ ቅዱስ እኩል በመቁጠር በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ ያክላሉ፤ (ለምሳሌ፡- የይሖዋ ምስክሮች፥ የክርስቲያን ሳይንስ አማኞች፥ የሞርሞን ተከታዮች፥ ወዘተ)። ስለ መጽሐፍ ቅዱስ በርካታ የተሳሳቱ አሳቦች በመኖራቸው፥ እምነታችን የተመሠረተውም በእርሱ ላይ በመሆኑ፥ ክርስቲያን የሆንነው ስለ መጽሐፍ ቅዱስ ማመን ያለብን ነገር ምን እንደሆነ ግልጽ አሳብ ሊኖረን ያስፈልጋል። ስለዚህ ጉዳይ አጭር አሳብ ከዚህ እንደሚከተለው ቀርቧል፡- መጽሐፍ ቅዱስ የእግዚአብሔር ቃል ነው። በ2ኛ ጢሞ. 3፡16 እና 2ኛ ጴጥ. 1፡19 መጽሐፍ ቅዱስ የእግዚአብሔር መንፈስ ያለበት መጽሐፍ እንደሆነና ጸሐፊዎቹ በመንፈስ ቅዱስ ተመርተው እንደጻፉት እናነባለን። መጽሐፍ ቅዱስ የእግዚአብሔር ቃል መሆኑን ራሱ በግልጥ ይናገራል፤ ስለዚህ እኛ ክርስቲያኖች ስለ መጽሐፍ ቅዱስ የሚከተሉትን ነገሮች እናምናለን፡- ሀ. መጽሐፍ ቅዱስ የእግዚአብሔር ሙሉ ሥልጣን አለው። የእግዚአብሔርን ቃልና ፍላጎቶች ይዟል፥ ስለዚህ መጽሐፍ ቅዱስን በምናነብበት ጊዜ እግዚአብሔር በመካከላችን ያለና የሚናገረን ያህል ነው። እግዚአብሔር የተናገረውም የተጻፈውም ቃሉ እኩል ሥልጣን አላቸው።  የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) የእግዚአብሔርን ቃል ስለ መስበክም ሆነ ስለ ማስተማር ይህ ምንን ያስተምረናል? ለ) ሥልጣኑ ያለው የት ላይ ነው? (ኢሳ. 55፡11 ተመልከት)።  የቤተ ክርስቲያን መሪዎች እንደ መሆናችን መጠን ሥልጣን ያለው የእግዚአብሔር ቃል ብቻ እንደሆነ ማስታወስ አለብን። የእኛ ቃላት ሥልጣን የሌላቸውና ስሕተት ሊገኝባቸው የሚችሉ ናቸው፤ ስለዚህ በምንሰብክበትና በምናስተምርበት ጊዜ የእኛ ኃላፊነት ሰዎች የእኛን አሳብ ሳይሆን የእግዚአብሔርን ቃል እንዲሰሙ፥ የእግዚአብሔርን ቃል ያለ አንዳች ስሕተት በግልጥ ማወጅ ነው (2ኛ ቆሮ. 4፡1-5፤ 2ኛ ጢሞ. 2፡15 ተመልከት)። ሰዎች የእግዚአብሔርን ቃል በሚሰሙበት ጊዜ ሥልጣኑና ኃይሉ ሕይወታቸውን ይለውጠዋል። ለ. መጽሐፍ ቅዱስ የእግዚአብሔርም የሰውም ሥራ ነው። መጽሐፍ ቅዱስን ለማስገኘት እግዚአብሔር ሰዎችን በመሣሪያነት በመጠቀም በራሳቸው ቃላትና የአስተሳሰብ መንገድ እንዲጽፉት አደረገ፤ ነገር ግን የጻፉት ቃል ውጤት ብሉይ ኪዳንን ጨምሮ በሙሉ የእግዚአብሔር ቃል ነው። ኢየሱስ እንዳለው በመጽሐፍ ቅዱስ ከሁሉ የምታንሰው ፊደል ወይም ነጥብ እንኳ በእግዚአብሔር ቁጥጥር ስለ ተጻፈ ሳይፈጸም አያልፍም (ማቴ. 5፡18 ተመልከት)።  ሐ. መጽሐፍ ቅዱስ የእግዚአብሔር ሥራ ስለሆነ አንዳችም ስሕተት የለበትም። እግዚአብሔር ሊዋሽና ስሕተት ሊሠራ ጨርሶ እንደማይችል ሁሉ (ዕብ. 6፡ 18) ቃሉም አይዋሽም። ስለዚህ የእግዚአብሔር ቃል በግልጥ ከሚያስተምረው ነገር ጋር የማይስማማ ማንኛውም ዓይነት አመለካከት ስሕተት ነው። እውነት ምን እንደሆነ የሚተረጉመው የእግዚአብሔር ቃል መጽሐፍ ቅዱስ ነው። በማንኛውም ጊዜ እኛም ሆንን ሌሉች የአንዳንድ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎችን እውነትነት በሚመለከት መጠየቅ ስንጀምር፥ በእግዚአብሔር ቃል ላይ እንፈርዳለን፥ በእግዚአብሔር ላይም ፈራጆች ሆንን ማለት ነው። መጽሐፍ ቅዱስ የእግዚአብሔር ሥልጣን አለው እያልን ትክክል መሆን አለመሆኑን መጠየቅ አንችልም። መጽሐፍ ቅዱስ ስሕተት ካለው በሕይወታችን ላይ ምንም ሥልጣን ሊኖረው አይችልም። ይሁን እንጂ ይህንን ዐረፍተ ነገር በመጠኑ ግልጽ ማድረግ ይኖርብናል። መጽሐፍ ቅዱስ በቅጅዎቹ ሳይሆን በመጀመሪያው አንዳችም ስሕተት የለበትም። ይህም ማለት ሙሴ፥ ዳዊት፥ ጳውሎስ ወይም ሉቃስ ቅዱሳት መጻሕፍትን ሲጽፉ ሙሉ ለሙሉ የእግዚአብሔር ቃልና አንዳችም ስሕተት የሌለበት ነገር ጽፈዋል፤ ነገር ግን ሌሎች ሰዎች የእግዚአብሔርን ቃል በሚገለብጡበት (በሚቀዱበት) ጊዜ አንዳንድ ስሕተቶች ነበሩ ማለት ነው። በጥንት ዘመን በርካታ መጻሕፍትን ለማባዛት የሚያስችሉ ማተሚያ ቤቶች እንዳልነበሩ ማስታወስ ያስፈልጋል። ዛሬ እንኳ መጽሐፍ ቅዱስ በሚታተምበት ጊዜ የሆሄያት ስሕተት ሊኖር ይችላል፤ ስለዚህ ቅዱሳት መጻሕፍት በእጅ ሲጻፉ በዘመናት ሁሉ የነበሩ ጸሐፊዎች አንዳንድ ስሕተቶችን ሠርተዋል፥ ስለዚህ በአሁኑ ጊዜ ባሉት በርካታ ትርጉሞች ውስጥ ተርጓሚዎቹ አንዳንድ ጥቅሶችን በተለየ መንገድ ሊተረጉሙ እንደሚችሉ በመግለጥ የግርጌ ማስታወሻዎችን ጽፈዋል።  የውይይት ጥያቄ፥ ማር.16ን በአዲሱ የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ ትርጉም ተመልከት። ከ9-20 ስላሉት ቁጥሮች በገጹ በስተግርጌ ላይ ምን ተጽፏል? ይህንን ሐቅ ለመረዳት ያስቸግራል። በአሁኑ ዘመን፣ የመጀመሪያዎቹ ጹሑፎች የትኞቹ እንደነበሩ ለመወሰን ዐብይ ሥራቸው አድርገው የያዙት የመጽሐፍ ቅዱስ ምሁራን አሉ። በሺህ የሚቆጠሩ የብሉይና የአዲስ ኪዳን ቅጂዎችን በመመልከት፣ የመጀመሪያው ቃል የቱ እንደነበር ሳይንሳዊ በሆነ መንገድ ለመወሰን ይታገላሉ። የእነዚህ ምሁራን ሥራ ያላለቀ ስለሆነና እኛም በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ስላሉ ጥቅሶች መቶ በመቶ እርግጠኞች መሆን ባንችልም፥ ሆኖም ግን ምሁራኑ የሚከተሉትን ነገሮች ይነግሩናል።  መጽሐፍ ቅዱስ ከማንኛውም ሌላ ጥንታዊ መጽሐፍ በተሻለ ሁኔታ ተጠብቋል፤ ምክንያቱም አይሁዶችና ክርስቲያኖች የእግዚአብሔር ቃል እንደሆነ ያምኑ ስለነበር በትክክል ሊገለብጡት ይችሉ ዘንድ ከፍተኛ ጥንቃቄ አድርገዋል፤ ስለዚህ ከቁርአንም ሆነ ከማንኛውም ሌላ ጥንታዊ መጽሐፍ በተሻለ ሁኔታ ትክክለኛነቱ የተጠበቀ ነው። ደግሞም በሚጽፉበት ጊዜ ጸሐፊዎቹን የመራቸው መንፈስ ቅዱስ በመሆኑ፥ ቅጂዎቹ ለዘመናት በሚጻፉበት ጊዜ ሁሉ ጉልህ ስሕተት እንዳይፈጽሙ ረድቶአቸዋል።  በተለያዩ ቅጂዎች መካከል ያሉት ልዩነቶች በአንድነት ሲታዩ፥ የአጠቃላዩ መጽሐፍ ቅዱስ ትንሽ ክፍል ናቸው። በሁሉም ቅዱሳት መጻሕፍት መካከል ስምምነት ስላለ፥ በእጃችን ያለው መጽሐፍ ቅዱስ ዘጠና ከመቶ በላይ (90%) ከመጀመሪያው መጽሐፍ ቅዱስ ጋር አንድ ዓይነት እንደሆነ እርግጠኞች ልንሆን እንችላለን።  በቅዱሳት መጻሕፍት ቅጂዎች መካከል ያለው ማንኛውም ልዩነት በየትኛውም የመጽሐፍ ቅዱስ ዋና ትምህርት ላይ ለውጥ የሚያመጣ አይደለም። ስለ እግዚአብሔር፥ ስለ ክርስቶስ ወይም ስለ መንፈስ ቅዱስ ማንነት፥ ስለ ድነት (ደኅንነት) መንገድ፥ ወዘተ ባለን ግንዛቤ ላይ የሚያመጡት አንዳችም ለውጥ የለም፤ ልዩነቶቹ እምነታችንን የሚለውጡ አይደሉም (ለምሳሌ በዕዝ. 2፡3-70 እና በነህ. 7፡6-73 ያሉትን ዝርዝሮች አነጻጽር። በእነዚህ ሁለት ዝርዝሮች ውስጥ ያሉትን ልዩነቶች ጥቀስ)። መ. መጽሐፍ ቅዱስ በነገሮች ሁሉ ላይ የመጨረሻው ባለሥልጣን ነው። እግዚአብሔር ማን እንደሆነ፥ ቀድሞ ምን እንዳደረገና ወደፊትም ምን እንደሚያደርግ፥ እንዲሁም ከፍጥረቱ የሚፈልገው ነገር ምን እንደሆነ በመናገር ረገድ የመጨረሻው ባለሥልጣን መጽሐፍ ቅዱስ ነው። ሌሎች እምነቶችና ልምምዶች በሙሉ መመዘን ያለባቸው በመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት

ብሉይ ኪዳን የእግዚአብሔር ቃል ነው Read More »