ዘፍጥረት 4-11 የኃጢአት በመላው ዓለም መሠራጨት

ከዘፍጥረት 4-11 ባለው ክፍል ውስጥ ሦስት ዋና ዋና ክንዋኔዎች አሉ። አንደኛ፥ አዳምና ሔዋን የመጀመሪያውን ክፋትና ኃጢአት ከሠሩበት ሰዓት ጀምሮ መስፋፋቱንና ከእነርሱ በኋላ የሚመጡትን ዝርያዎቻቸውን በሙሉ ማጥፋቱን ቀጠለ። ሁለተኛ፥ ከአዳም ጀምሮ እስከ አብርሃም ድረስ ያለውን የድነት (ደኅንነት) መስመር ማሳየት ነው። ሦስተኛው፥ እንደ ዓለም ፈቃድ መኖርን ትተው በእግዚአብሔር ፊት በጽድቅ የኖሩ የተለያዩ ሰዎችን ማሳየት ነው። 

፩. ኃጢአትና ፍርድ በሰው ዘር ላይ እንዴት እንደመጣ ተጠቅሶ እናገኛለን።

በእነዚህ ምዕራፎች ሁሉ የኃጢአትና የሞት ዋና አሳብ እንዴት እንደተጠቀሰ አስተውል።

ሀ. በዘፍ. 4 ቃየን በተገቢው መንገድ ለእግዚአብሔር መሥዋዕትን ማቅረብ እንዴት እምቢ እንዳለ እናነባለን። አንዳንዶች እግዚአብሔር ያልተቀበለው ደም የሌለበት ስለ ነበረ ነው ይላሉ፤ ነገር ግን እግዚአብሔር የቃየንን መሥዋዕት ያልተቀበለበት መሠረታዊ ምክንያት እርሱን የማምለኪያ ትክክለኛ መንገድ ስላልነበረው ነው። እግዚአብሔር ባዘዘው መሠረት አምልኮውን አላቀርብም አለ። ይህም የመጀመሪያውን ነፍስ ግድያ አስከተለ። ቃየን ወንድሙ አቤልን ገደለ።

የውይይት ጥያቄ፥ ዛሬ እግዚአብሔርን በተሳሳተ ዝንባሌ ወይም ውስጣዊ አሳብ ማምለክ እንዴት ይቻላል?

ለ. የቃየንን ዝርያዎች የማያቋርጥ ዓመፅ እንመለከታለን። የቃየን ዝርያዎች ለሥልጣኔ ለእድገትና ለበርካታ ከተሞች መቆርቆር ምክንያት የሆኑ ቢሆንም፥ ብዙ ሚስቶችን ማግባት ጀመሩ። እንዲያውም ላሜሕ አንድ ወጣት ሰው በመግደሉ ጉራውን ነዛ (ዘፍ. 4፡23-24)።

** ማስታወሻ፡- (ብዙ ሰዎች ቃየን እና ሴት ከየት ሚስት እንዳገኙ በማሰብ ይደነቃሉ። የኦሪት ዘፍጥረት ታሪክ ብዙ ጊዜ ትኩረት የሚያደርገው በወንዶች ልጆች እንጂ በሴቶች ልጆች ላይ በደረሰው አይደለም፡፡ ከዘፍ. 5፡4 እንደምንረዳው አዳምና ሔዋን ወንዶች ልጆች ብቻ ሳይሆኑ፥ ሴቶች ልጆችም ነበሯቸው፤ ስለዚህ ቃየንና ሴት የራሳችውን እኅቶች እንዳገቡ መገመቱ ትክክል ነው። ይህ ነገር ከብዙ ዓመታት በኋላ ከግብፅ እስከ ወጡበት ጊዜ ድረስ በእግዚአብሔር የተከለከለ አልነበረም [ዘሌ. 18])።

ሐ. ከአዳም እስከ ኖኅ ያለው የትውልዶች ታሪክ በተተነተነበት በዘፍ. 5 በተደጋጋሚ የሚነገር አንድ ቃል አለ። ይህም ቃል «ሞት» የሚል ነው። ለበርካታ ዓመታት ቢኖርም እንኳ የሰው ልጅ መጨረሻው ያው ሞት ነው።

መ. በዘፍጥረት 6 የእግዚአብሔር ልጆች የሰውን ሴቶች ልጆች በማግባት ኃጢአት እንደሠሩ እንመለከታለን። ይህ ለመረዳት በጣም አስቸጋሪ የሆነ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል ነው፤ ስለዚህ ጉዳይ ምንነት የሚቀርቡ በርካታ አሳቦች አሉ፡-

1) «የእግዚአብሔር ልጆች» የሚለው ቃል ተፈጥሮአዊ ደረጃቸውን ትተው የሰውን ሴቶች ልጆች ስለ አገቡ መላእክት የሚናገር ሊሆን ይችላል። ይህንን አመለካከት ለመቀበል በጣም አስቸጋሪ የሚያደርገው መላእክት እንደማያገቡ ኢየሱስ ማስተማሩ ነው (ማር. 12፡25)። ሥጋዊ አካል የሌላቸው መንፈሳዊ ፍጥረታት ስለሆኑ ሴቶችን እንዴት ሊያገቡ ይችላሉ?

«የእግዚአብሔር ልጆች» የሚለው ቃል የፖለቲካ መሪዎችን ያመለክታል የሚሉም አሉ። (የጥንት ሰዎች መሪዎቻቸውን «አምላክ» ብለው ይጠሩ ነበር።) ኃጢአቱም፡- እነዚህ መሪዎች ከሴቶች ጋር የፍትወተ ሥጋ ፍላጎታቸውን ለመፈፀም የጋብቻን ቅድስና በመተላለፍ ብዙ ሴቶችን ማግባት መጀመራቸው ነው። በዚህም የሕዝቡን የሥነ- ምግባር መሠረት አበላሹት።

3) «የእግዚአብሔር ልጆች» ፈሪሃ-እግዚአብሔር ያላቸው፥ የተለዩና ሴት የተባለው ሰው ዘሮች ነበሩ። «የሰዎች ሴቶች ልጆች» የቃየን ዝርያዎች ነበሩ። ኃጢአቱ፡- ዛሬ ክርስቲያኖች የማያምኑትን እንዳያገቡ እንደተነገራቸው ሁሉ እግዚአብሔርን የሚፈሩ ሰዎች እግዚአብሔርን ከማይፈሩት ጋር ጋብቻ መመሥረታቸው ነበር (1ኛ ቆሮ. 7፡39፤ 2ኛ ቆሮ. 6፡14)። ይህ ነገር የእግዚአብሔር ቤተሰቦች የሆኑ ሰዎች ምግባረ ብልሹ እንዲሆኑና ብዙ ሰዎች በእግዚአብሔር ላይ ካላቸው እምነት እንዲርቁ መንገድ ከፍቷል።

ከእነዚህ አመለካከቶች የትኛው እንደሚሻል ማወቅ በጣም አስቸጋሪ ነው። ከሁሉ የሚሻለው ምርጫ 1ኛው ወይም 3ኛው አመለካከት ይመስላል። እያንዳንዱ አመለካከት የራሱ ችግር አለው። ዛሬም ቢሆን ከኃጢአታቸው በስተኋላ ያለው አሳብ ግልጥ ነው። እነዚህ የእግዚአብሔር ልጆች ከሚያገቡአቸው ሴቶች መንፈሳዊ መመዘኛን ከመፈለግ ይልቅ፥ ስለ አካላዊ ውበትና ስለ ፍትወተ ሥጋ ፍላጎት ብቻ ያስባሉ።

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ዛሬ ሰዎች የትዳር ጓደኛ በሚመርጡበት ጊዜ ያላቸው ተመሳሳይ አመለካከት ምንድን ነው? ለ) አንድ ክርስቲያን የሚያገባው በመልክ ቁንጅናና ከጥሩ ቤተሰብ በመገኘት ብቻ ከሆነ ስሕተት የሚሆነው ለምንድን ነው? ሐ) የትዳር ጓደኛን የመምረጫ እጅግ ጠቃሚ መመዘኛዎች የትኞቹ ናቸው?

በኦሪት ዘፍጥረት 6 የሚገኘው ታሪክ በተፈጸመ ጊዜ ክፋትና ኃጢአት እጅግ ተስፋፍቶ ስለ ነበር እግዚአብሔር ሰውን በመፍጠሩ ተጸጸተ። ከእግዚአብሔር ጋር ትክክለኛ በሆነ ግንኙነት ይኖር የነበረ አንድ ሰው ኖኅ ብቻ ነበር፤ ስለዚህ ከዘፍ. 6-9 ባለው ክፍል እግዚአብሔር የሰውን ዘር ለማጥፋት ስለተጠቀመበት የጥፋት ውኃ እናነባለን። የጥፋት ውኃ ዓላማ በክፉው የሰው ልጅ ላይ ለመፍረድና የእግዚአብሔር ሰው የሆነው ኖኅ በአዲስ መልክ እንዲጀምር ለማድረግ ነበር። ልክ እንደ አዳም ኖኅ የሰው ዘር ሁሉ ራስ ሆነ። ዛሬ በምድር ላይ ያሉ ሰዎች በሙሉ የተገኙት ከኖኅ ነው።

ሠ. ከዘፍ. 10-11 ክፍል ክፋት በጥፋት ውኃ ሊጠፋ እንዴት እንዳልቻለ እናያለን። ኖኅ የእግዚአብሔር ሰው ቢሆንም፥ እርሱና ቤተሰቡ የክፋት ባሕርይ ነበረባቸው። በመጀመሪያ፥ ኖኅ ጠጥቶ ሰከረና ጨዋነት በጎደለው መንገድ እራቁቱን ሆነ። ከዚያም የኖኅ ልጆች ከነበሩት አንዱ የሆነው ካም የአባቱን እርቃነ-ሥጋ አየ። ከዚህ የተነሣ የካም ልጅ የነበረውና የእስራኤል ሕዝብ ጠላት የሆኑት የከነዓናውያን አባት ከነዓን በኖኅ ተረገመ። 

** (ማስታወሻ፡- አንዳንድ ሰዎች የተረገመው ከነዓን እንጂ ካም ስላልሆነ ከነዓንም በኖኅ ላይ ኃጢአት ሠርቷል የሚል አስተሳሰብ አላቸው። በምንም ሁኔታ ይሁን ኖኅ በነቢይነት የከነዓን ዘር የሴምና የያፌት ዘሮች ባሪያ እንደሚሆን አስቀድሞ ተናገረ፤ ነገር ግን ይህን ታሪክ ነጮች ጥቁሮችን ለመግዛት ሊጠቀሙበት አይገባም)።

ሁለተኛ፡- የኖኅ ዝርያዎች በሙሉ ብዙ ሳይቆዩ በኃጢአት ውስጥ ተዘፈቁ። በትዕቢታቸውና ሐሰተኞች አማልክትን ለማምለክ በመፈለጋቸው የባቢሎንን ግንብ ለመሥራት ተነሡ። ይህም ምድርን እንዲሞሉ ያዘዛቸውን እግዚአብሔር በተዘዋዋሪ መንገድ አንታዘዝም ማለት ነበር፤ ዳሩ ግን ለመበታተን አልፈለጉም ነበር (ዘፍ. 9፡7፤ 11፡4 ተመልከት)። አሁን ደግሞ እግዚአብሔር ቋንቋቸውን ደባልቆ እንዲበተኑ በማድረግ በሰው ልጆች ላይ ፈረደባቸው። በዘፍ. 10 በምድር የሚገኙ የሰው ዝርያዎች ሁሉ ከየት እንደመጡ ተጽፏል። ነጮችና የምሥራቅ ሰዎች የመጡት ከያፌት ዘር ነው። ዓረቦችና አይሁድ የመጡት ከሴም ዘር ነው። አፍሪካውያን ደግሞ የመጡት ከካም ዘር ነው። 

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ኃጢአት በኖኅና በቤተሰቦቹ የመቀጠሉ እውነታ ኃጢአት ከትውልድ ወደ ትውልድ ስለ መተላለፉ ምን ይነግረናል? ለ) ዛሬ የኃጢአት ባሕርይ ከወላጆች ወደ ልጆች የመተላለፉን እውነታ እንዴት እናየዋለን? 

፪. ከአዳም እስከ አብርሃም ያለው እግዚአብሔርን የሚፈራው ትውልድ። 

የእነዚህ ምዕራፎች ሁለተኛ ዓላማ ደግሞ የአብርሃምን የዘር ሐረግ ወደ ኋላ በመመለስ እስከ መጀመሪያው ሰው እስከ አዳም ድረስ ማሳየት ነው። በዘፍጥረት 5 ሙሴ አሥር ትውልዶችን በመዘርዘር ከአዳም እስከ ኖኅ ድረስ ያለውን የትውልድ አመጣጥ አሳይቷል። በዘፍ. 11፡10-32 ደግሞ ሙሴ የአዳምን የዘር ሐረግ የኖኅ ልጅ እስከሆነው እስከ ሴም ከዚያም እስከ አብርሃም ድረስ ያሳያል። እርሱም የተመረጡና እሥራኤል ተብሎ የተጠራው የእግዚአብሔር ሕዝብ ራስ ነው። «አባት» የሚለው የዕብራይስጥ ቃል አያትን ወይም ቅድመ አያትን የሚያሳይ ስለሆነ እነዚህ ቁጥሮች አሥር ትውልዶችን ይሁን ወይም አንዱ የሌላው ዘር መሆኑን ብቻ የሚያሳዩ ይሆኑ የመጽሐፍ ቅዱስ ምሁራን ከስምምነት ላይ መድረስ አልቻሉም።

፫. የዓለምን መንገድ ለመከተል እምቢ ያሉና ጻድቃን የሆኑ ሰዎች ምሳሌ፡፡

አብዛኛው የዚህ ክፍል ታሪክ ትኩረት በዓለም ላይ ኃጢአት እየተስፋፋ ስለመምጣቱ ቢሆንም፥ ስለ ኃጢአትና ፍርድ በሚናገሩ ታሪኮች ውስጥ የተለዩ ሕዝቦች ታሪኮች ተሰውረው እናገኛለን። እነዚህም ሦስት የተለያዩ ሰዎች በብዙኃኑ ሕዝብ መካከል ያለውን ኃጢአት ተቋቁመው በእግዚአብሔርም ፊት የጽድቅን ሕይወት የኖሩ ናቸው።

የመጀመሪያው ሄኖክ ነበር። ስለ ሄኖክ ሕይወት የተጻፈልንና የምናውቀው ነገር «አካሄዱን ከእግዚአብሔር ጋር ማድረጉ» ነው፤ ስለዚህም እግዚአብሔር ሞትን ሳያይ ወደ ሰማይ ወሰደው። እርሱም ሞትን ሳያይ ወደ መንግሥተ ሰማያት የተወሰደ የመጀመሪያ ሰው ነው።

ሁለተኛ፥ ኖኅን እናገኛለን። ስለ ኖኅ «በትውልዱ ጻድቅ ፍጹምም ሰው ነበር» ተብሎላታል (ዘፍ. 6፡9)። ስለሆነም ቀሪውን የሰውን ዘር በሙሉ ካጠፋው ውኃ እግዚአብሔር እርሱንና ቤተሰቡን አድኖአል። የጥፋት ውኃንና እግዚአብሔር ኖኅን እንዴት እንደጠበቀው የሚናገረውን ታሪክ ከዘፍጥረት 6-9 ባለው ክፍል እናገኛለን። በታሪኩ ውስጥ የሚከተሉትን ነገሮች ተመልከት፡-

  1. የኖኅ መርከብ መጠን 140 ሜትር ርዝመት 23 ሜትር ስፋትና 13.5 ሜትር ከፍታ ያለው ነበር። ይህም ማለት ርዝመቱ ከእግር ኳስ ሜዳ ከፍታውም ሦስት ፎቅ ካለው ሕንጻ የሚበልጥ ነበር። ሦስት ወለሉች ወይም ፎቆች ነበሩት። መርከቡ አንድ በርና አንድ መስኮት ብቻ ነበረው። እስከ 1900 ዓ.ም. ድረስ ሰዎች እንዲህ ዓይነት ትልቅ መርከብ መሥራት አለመጀመራቸውን ማወቅ የሚያስገርም ነው። በአሁኑ ጊዜ በውቅያኖስ ላይ ዕቃ ጫኝ ተሽከርካሪዎችን የሚሸከሙ መርከቦች መጠናቸው ከዚያ የሚተካከል ነው። ኖኅ መርከቡን ለመሥራት 120 ዓመታት ፈጅቶበታል። ኖኅ ምንም ዝናብ ባያይና በሐይቅ (በባሕር) አካባቢ ካለመኖሩ የተነሣ ብዙ ውኃ ምን እንደሚመስል ባያውቅም እንኳ እግዚአብሔር እንዲሠራ ያዘዘውን ነገር በታማኝነት በመፈጸም መርከቡን ሠራ። 

የውይይት ጥያቄ፥ እግዚአብሔር አንድን ነገር እንድናደርግ የጠየቀን ለምን እንደሆነ ባልተረዳንበት ሰዓት እንኳ እርሱን በመፍራት ልንታዘዘው እንደሚገባ የኖኅ ተግባር እንዴት ጥሩ ምሳሌ ይሆነናል?

  1. የመርከቡ መሠራት ዓላማ በጥፋት ውኃ ጊዜ የኖኅን ቤተሰብና (8 ሰዎች) በምድር ላይ ከነበሩ እንስሳት በሙሉ አንድ አንድ ለማዳን ነበር። ሳይንቲስቶች ዛሬ በምድር ላይ ካሉ እንስሳት ሁሉ አንድ አንድ ቢገቡ መርከቡ ሊይዛቸው እንደሚችል አረጋግጠዋል። በአዲስ ኪዳን መርከቡ እግዚአብሔር ልጆቹን የመቤዠቱ ምሳሌ ነው (ዕብ. 11፡7፤ 2ኛ ጴጥ. 2፡5)። ደግሞም የጥምቀት ምሳሌ ነው (1ኛ ጴጥ. 3፡20-2)። 
  2. ኖኅና ቤተሰቡ በመርከቡ ውስጥ ለ377 ቀናት ቆዩ። (ከአንድ ዓመት በላይ ማለት ነው)። በእነዚህ ሁሉ ጊዜያት እግዚአብሔር ለእርሱና ለእንስሳቱ ሁሉ የሚያስፈልጋቸውን ነገር ይሰጣቸው ነበር። 
  3. ውኃው ምድርን ሁሉ ሸፍኖ ነበር። አንዳንድ ክርስቲያኖች የጥፋት ውኃው በመስጴጦምያ አካባቢ ብቻ በመሆን በዚያን ጊዜ በታወቀው ዓለም የነበሩትን ነገሮች ብቻ እንዳጠፋ አድርገው ቢያስቡም እንኳ ውኃው የሸፈነው ምድርን በሙሉ እንደሆነ ከታሪኩ በግልጥ እንመለከታለን። በጥንት ዘመን በሁሉም አህጉር ታላቅ ጥፋትን ያስከተለ ውኃ እንደነበር የሚያሳዩ ምልክቶች መገኘታቸው የሚያስገርምና የዚህን ታሪክ እውነተኛነት የሚያረጋግጥ ነው። የመጽሐፍ ቅዱስን ታሪክ ባያውቁም እንኳ በዓለም ላይ የሚገኙ በርካታ ሕዝቦች በባሕላቸው፥ ዓለም እንዴት በውኃ እንደጠፋች የሚናገር ታሪክ አላቸው። 
  4. በጥፋት ውኃው መጨረሻ ላይ እግዚአብሔር ከኖኅ ጋር ቃል ኪዳን አደረገ። ቃል ኪዳኑን ከመስጠቱ በፊት አንዳንድ ትእዛዛትን ሰጠው (ዘፍ. 9፡ 17)። 

ሀ. ምድርን ለመሙላት መባዛት ነበረባቸው፤ 

ለ. እንስሳት ሁሉ ለሰው ልጅ ለምግብነት ተሰጡት፤ 

ሐ. ኖኅ ደም እንዳይበላ ታዘዘ፤ 

መ. የሌላውን ሰው ነፍስ በግድየለሽነት የሚያጠፉ ሁሉ ይገደሉ ነበር።

ነገር ግን እግዚአብሔር ከሰው ልጆችም ጋር ተስፋንና ቃል ኪዳንን አድርጓል። ያም ቃል ኪዳን እግዚአብሔር እንደገና ምድርን በጥፋት ውኃ እንደማያጠፋ የሚናገር ነበር። ቀስተ ደመና እግዚአብሔር ከዚህ በኋላ ምድርን በውኃ ላለማጥፋት የገባውን ቃል ኪዳን እንደሚጠብቅ የሚያሳይ ምልክት ነበር። 

የውይይት ጥያቄ፥ 2ኛ ጴጥ. 3፡3-7 አንብብ። ምድር ወደፊት የምትጠፋው እንዴት ነው?

ማስታወሻ፡- አንዳንድ ሰዎች የኖኅን መርከብ በቱርክና በሩሲያ ድንበር ላይ በአራራት ተራራ ጫፍ አግኝተናል ቢሉም እስካሁን ድረስ ግን እውነትነቱ አልተረጋገጠም።

ሦስተኛ፥ የምናገኘው ሰው አብርሃም ነው። እርሱም በመስጴጦምያ ይኖር በነበረ ጊዜ እግዚአብሔር እርሱ ወደሚያሳየው ምድር ይወጣ ዘንድ ያዘዘው ሰው ነበር። ዘፍ. 12-25 በዚህ ልዩ የእግዚአብሔር ሰው ላይ ያተኩራል።

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) እግዚአብሔርን ከሚፈሩ ሰዎች ሕይወት በክፋት ዓለም ውስጥ ስለመኖር ምን የምንማረው ነገር አለ? ለ) በእኛስ ፊት ይኸው ምርጫ እንዴት ነው? ሐ) ለእኛም የተዘጋጀው ተመሳሳይ ሽልማት ምንድን ነው?

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

%d bloggers like this: