ዘፍጥረት 37-50 የዮሴፍ ታሪክ

የዚህ የኦሪት ዘፍጥረት የመጨረሻ ክፍል ዓላማ የእስራኤል ሕዝብ የከነዓንን ምድር ይወርሱ ዘንድ ቃል የተገባላቸው ሆነው ሳሉ፥ እንዴት ወደ ግብፅ እንደወረዱ ማሳየት ነው። ለኦሪት ዘጸአትም በመግቢያነት የሚያገለግል ነው። ምክንያቱም ኦሪት ዘጸአት እስራኤላውያን በግብፅ 400 ዓመታት ከቆዩ በኋላ ወደ ተስፋይቱ ምድር ለመመለስ እንዴት እንደወጡ የሚያሳይ መጽሐፍ ነው። ታሪኩ የተፈጸመው በሙሴ ዘመን ገደማ ስለሆነ፥ ከሌሎቹ የእስራኤል አባቶች ታሪክ ይልቅ የዮሴፍን ታሪክ በዝርዝር ይነግረናል። በተጨማሪ ኃጢአታቸው የሚያስከትለውን ችግር ጨምሮ እግዚአብሔር በሕዝቡ ሕይወት የሚመጣውን ነገር ሁሉ እየተቆጣጠረ እንዴት ያለማቋረጥ እንደመራቸው እንመለከታለን።

የውይይት ጥያቄ፥ ዘፍጥ. 37-50 አንብብ። ሀ) ዮሴፍ ያያቸውንና የተረጎማቸውን ልዩ ልዩ ሕልሞች ዘርዝር። እያንዳንዳቸው እንዴት ተፈጸሙ? ለ) ዮሴፍ በምሳሌነት ሊቀርብ የሚችል ታላቅ የእግዚአብሔር ሰው የሆነው እንዴት ነው? ሐ) በዮሴፍ ሕይወት ውስጥ የእግዚአብሔር ቁጥጥር የታየባቸውን መንገዶች ዘርዝር። መ) በስደት ውስጥ ይቅርታንና ትዕግሥትን ስለማሳየት ከዮሴፍ ሕይወት የምንማረው ነገር ምንድን ነው? 

ከብዙ ዓመታት በፊት፥ እግዚአብሔር በሌላ ምድር መጻተኞች ሆነው እንደሚኖሩና ለ400 ዓመታት በባርነት እንደሚገዙ ለአብርሃም ተናግሮት ነበር (ዘፍጥ. 15፡13)። በዮሴፍ ታሪክ ይህ ትንቢት መፈጸም ጀመረ። እግዚአብሔር የገባውን ቃል ኪዳንና የሰጠውን ተስፋ እኛ በምንፈልገው ፍጥነት ባይፈጽምም፥ ለሰጠው ተስፋና ቃል ኪዳን ግን ሁልጊዜ ታማኝ ነው።

  1. ዮሴፍ ወደ ግብፅ የሄደበት ምክንያት (ዘፍጥ. 37):- ከዘፍጥረት ምዕራፍ 37 ጀምሮ የእግዚአብሔርን እጅ በሥራ ላይ እናያለን። እግዚአብሔር አንድ ዓይነት ትርጉም ያላቸውን ሁለት ሕልሞች ለዮሴፍ ሰጠው። በመጀመሪያ፥ የወንድሞቹ ነዶዎች ለእርሱ ሲሰግዱ ያያል። በሁለተኛው ሕልም ደግሞ ፀሐይ፥ ጨረቃና አሥራ አንዱ ከዋክብት ለእርሱ ሲሰግዱለት አየ። ይህ ሕልም በወንድሞቹ ላይ ገዥ እንደሚሆንና እነርሱም እንደሚሰግዱለት ማለትም እንደ መሪያቸው ተቆጥሮ እንደሚያከብሩት የተሰጠ ትንቢት ነበር። ይህም ትንቢት ከብዙ ዓመታት በኋላ ዮሴፍ የግብፅ ጠቅላይ ሚኒስትር ሆኖ ወንድሞቹ ምግብ ፍለጋ ወደ እርሱ በመጡ ጊዜ ተፈጸመ።
  2. ትዕማር የይሁዳን ዘር አዳነች (ዘፍጥ. 38)፡- በዮሴፍ ታሪክ አጋማሽ ላይ በሌሉች ወንድሞቹ በተለይም በይሁዳ ሕይወት ኃጢአትና ክፋት መኖሩን የሚያሳይ አሳዛኝ ታሪክ እንመለከታለን። የይሁዳ ትልቁ ልጅ ዔር ትዕማር የምትባል ከነዓናዊት አገባ፤ ነገር ግን አንድም ልጅ ሳይወልድ ሞተ። በዚያ ዘመን በነበረው ወግ መሠረት ይሁዳ የሚቀጥለውን ልጁን አውናንን ከትዕማር ጋር ማጋባት ነበረበት። በባሕሉ መሠረት የሚወለደው የመጀመሪያ ልጅ የሟቹ ወንድም የዔር እንደሆነ ይቆጠር ነበር። የቀሩት ልጆች ደግሞ የአውናን ይሆኑ ነበር። የመጀመሪያው ልጅም የብኩርናን መብት ያገኝ ነበር። በሞተውም ልጅ ምትክ ከአያቱ ርስት ይወርስ ነበር። ይህ ማለት ይሁዳ ለበኩር ልጁ ያወርሰው የነበረው ነገር የመጀመሪያ ልጁ ከሞተ በኋላ የሚተላለፈው ለሁለተኛ ልጁ ሳይሆን ከትዕማር ለተወለደው ለልጅ ልጁ ይሆናል ማለት ነው። አውናን በእግዚአብሔር ላይ ኃጢአት ስላደረገ እግዚአብሔር ቀሠፈው። ባሕሉን ለማክበርና ለወንድሙ ልጅ ለማሳደግ ያልፈለገ ይመስላል። ምናልባት ምንም ልጅ ሳይወልዱ በሞተው ወንድሙ ምትክ የብኩርናን መብት እንደሚወርስ ሳይገምት አልቀረም። አውናን ከሞተ በኋላ ይሁዳ በባሕሉ መሠረት ሦስተኛ ልጁን ለትዕማር ለመዳር ፈቃደኛ ሳይሆን ቀረ። ግዴታውን ለእርሷና ለመጀመሪያ ልጁ ሳይፈጽም ቀረ፤ ስለዚህ እርሷና ልጆችዋ የብኩርና መብት ተጠቃሚ እንዲሆኑ ይሁዳን አታለለችው። ራሷን ሴተኛ አዳሪ አስመስላ በማቅረብ አማችዋ የሆነው ይሁዳ ከእርሱ ጋር እንዲተኛ አደረገችው። ከእርሱም ፋሬስና ዛራ ብላ የጠራቻቸውን መንታ ልጆች ወለደች። ይህን በማድረግዋ የይሁዳን ዘር ከመጥፋት አዳነች። የብኩርናን መብትም በቤተሰቧ በማስቀረት ልጇ ለይሁዳ የተሰጠውን የተስፋ ቃል ወራሽ እንዲሆን አደረገች። የሚያስደንቀው ነገር ንጉሡ ዳዊትና የዳዊት ልጅ ተብሎ የሚጠራው የኢየሱስ ክርስቶስ ዘር የመጣው ከትዕማር ልጅ ከፋሬስ መሆኑ ነው(ማቴ. 1፡3)።
  3. እግዚአብሔር ዮሴፍን በግብፅ ጠብቆ አከበረው (ዘፍጥ. 38-40)።

ሀ. እግዚአብሔር ዮሴፍን በጲጥፋራ ቤት አከበረው፡- ዮሴፍ በዚህ ሰው ቤት ባሪያ ቢሆንም፥ ከእግዚአብሔር ምርጥ ሕዝቦች አንዱ ነበር። እስራኤላውያንን ከራብ በማዳን የተሰጣቸው ቃል ኪዳን ከፍጻሜ እንዲደርስ ለማድረግ በእግዚአብሔር የተመረጠው ሰው ዮሴፍ ነበር። ስለዚህ እግዚአብሔር ዮሴፍን አከበረውና በግብፅ ውስጥ ባለውና መሪ በነበረው በጲጥፋራ ቤት አገልጋዮች ሁሉ አለቃ እንዲሆን አደረገ። ከጲጥፋራ ሚስት ጋር ዝሙት ፈጽሞ ሕይወቱ ሁሉ እንዲበላሽና እንዲጠፋ ለማድረግ ሰይጣን ሞከረ። ዮሴፍ ግን በዚህ መንገድ እግዚአብሔርንና ጲጥፋራን ላለመሳደብ ወስኖ የሰይጣንን ሙከራ ተቃወመ።

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ለዮሴፍ ከጲጥፋራ ሚስት ጋር ዝሙት መፈጸም በጣም ቀላል የነበረው ለምንድን ነው? ለ) በዚህ ዘመን ብዙ ክርስቲያኖች በዚህ ኃጢአት የሚወድቁት ለምንድን ነው? ሐ) ይህንን ፈተና ስለማሸነፍ ከዮሴፍ ሕይወት የምንማረው ነገር ምንድን ነው?

ለ) እግዚአብሔር ዮሴፍን በወኅኒ ቤት አከበረው፡- ምንም ጥፋት ያልነበረበት ንጹሕ የነበረው ዮሴፍ ወደ ወኅኒ ቤት ከገባ በኋላ በዚያ ለብዙ ዓመታት ቆየ። እግዚአብሔር በዚያም ቢሆን ሞገስን ሰጠውና በወኅኒ ቤቱ የእስረኞች አለቃ አደረገው።

የወኅኒ ቤቱ የእስረኞች አለቃ ስለነበር እዚያ ታስረው ከነበሩት ከፈርዖን ጠጅ አሳላፊና የእንጀራ አበዛ ጋር ለመገናኘት ቻለ። እነዚህ ሁለት ሰዎች በግብፅ ቤተ መንግሥት ውስጥ ከፍተኛ ባለሥልጣኖች ነበሩ። ጠጅ አሳላፊው ንጉሡ ወይን ጠጅ ከመጠጣቱ በፊት የሚቀምስለት ሰው ነበር። ይህም ንጉሡን ማንም ሰው በመርዝ ሊገድለው እንዳይችል የተደረገ ዘዴ ነበር። ብዙውን ጊዜ የጠጅ አሳላፊው የንጉሡ ምሥጢረኛና የቅርብ ጓደኛ ነበር። የእንጀራ አበዛውም ንጉሡ ለሚበላቸው ነገሮች ሁሉ ኃላፊነት ስለ ነበረበት በጣም ከፍተኛ ስፍራ የነበረው ሰው ነው። እነዚህ ሁለት ሰዎች በእስር ቤት በነበሩ ጊዜ ዮሴፍ ሊተረጉምላቸው የቻለውን ሁለት ሕልሞች አዩ። የጠጅ አሳላፊው ሕልም ትርጓሜ ንጉሡን ያገለግልበት ወደነበረው ወደ ቀድሞ ሥፍራው መመለሱ ነበር። የእንጀራ አበዛው ሕልም ትርጓሜ ደግሞ የንጉሡን ምሥጢር ስላባከነ በስቅላት እንደሚገደል ነበር። እነዚህ ሕልሞች በኋላ የፈርዖንን ሕልም ለመተርጎም ወደ ቤተ መንግሥት እንዲጠራ ያደረጉት ስለነበሩ በጣም ጠቃሚ ሕልሞች ነበሩ።

  1. እግዚአብሔር ዮሴፍን በፈርዖን ፊት አከበረውና ጠቅላይ ሚኒስትር አደረገው (ዘፍጥ. 40-45)።

ዮስፍ የፈርዖንን ሕልም ከተረጐመ በኋላ እስከ ጠቅላይ ሚኒስትርነት ማዕረግ እንደደረሰ ይታወቃል። እግዚአብሔር በዮሴፍ በኩል ለፈርዖን ሰባት የጥጋብና ሰባት የረሃብ ዓመታት እንደሚመጡ በሕልሙ አሳወቀው። ዮሴፍ ጠቅላይ ሚኒስትር እንደመሆኑ መጠን ለረሀቡ ጊዜ የሚሆነውን እህል በጥጋቡ ጊዜ አዘጋጀ።

እግዚአብሔር ዮሴፍን ያን ወደ መሰለ ከፍተኛ የሥልጣን ቦታ ያመጣው ለምንድን ነው? ሀ) የግብፅን ሕዝብ ከራብ ለማዳን፥ ለ) የተመረጠውን የእስራኤልን ሕዝብ ከራብ ለማዳንና፥ ሐ) ለአብርሃም የገባውን የተስፋ ቃል ለመፈጸም ይችል ዘንድ የእስራኤልን ሕዝብ ወደ ግብፅ ለማምጣት ነው። 

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) እግዚአብሔር ዕቅዱን ለመፈጸም ሲል ዮሴፍን በዚህ ዓይነት ካከበረው፥ ዛሬም ለእኛ እንዴት እንደሚሠራ ይህ ምን ያስተምረናል? ለ) እግዚአብሔር በዮሴፍ ሕይወት እንዳደረገው በአንተ ወይም በሌላው ክርስቲያን ሕይወት ያደረገውን ተመሳሳይ ነገር የሚገልጹ ምሳሌዎችን ዘርዝር።

ዮሴፍ ለባርነት የሸጡትን ወንድሞቹን ለመፈተን በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ እንዲያልፉ አደረጋቸው። እርሱን ለባርነት ስለሸጡበት ኃጢአት በእርግጥ መፀፀታቸውን ማየት ፈለገ። ይሁዳ ራሱን በብንያም ምትክ ለመስጠት የተዘጋጀ መሆኑንና ወንድሞቹም እንደዚያ የተቀጡበት ምክንያት እግዚአብሔር ራሱ ስለቀጣቸው እንደሆነ መቀበላቸውን ሲያይ ከኃጢአታቸው በእርግጥ መመለሳቸውን አወቀ። ከዚያ በኋላ ራሱን ገለጠላቸው።

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ዮሴፍ ወንድሞቹ እንደተለወጡና በእርግጥ ከኃጢአታቸው እንደተመለሱ ማወቅ ለምን አስፈለገው? ለ) ክርስቲያኖች በእውነት ከኃጢአታቸው መመለሳቸውን በምን እናውቃለን?

  1. የያዕቆብ ትውልድና ትንሹ የእስራኤል ጎሳ ወደ ግብፅ መውረድ (ዘፍጥ. 46-50)።

ዮሴፍ ጠቅላይ ሚኒስትር ከሆነ በኋላ ቤተሰቡ ወደ ግብፅ መጥተው እንዲኖሩ አደረገ። የእስራኤል ሕዝብ አባት የሆነው ያዕቆብም ወደ ግብፅ ወረደ። የዮሴፍን ልጆች ጨምሮ ወደ ግብፅ የመጡት እስራኤላውያን ጠቅላላ ቁጥር 70 ነበር። ከ400 ዓመታት በኋላ 70 የነበረው የእስራኤላውያን ቁጥር 2 ሚሊዮን ደርሶ ነበር።

ያዕቆብ ከመሞቱ በፊት ለልጆቹ ለእያንዳንዳቸው በረከቱን አስተላለፈ። እነዚህ በረከቶች የትንቢት መልክ ሲኖራቸው የተሰጡትም በቀጥታ ከእግዚአብሔር እንደመጡ ተደርገው ነበር። የያዕቆብ በረከቶችና ትንቢት የእግዚአብሔር ቃል ነበሩ፤ እግዚአብሔርም ፈጸማቸው።

ሀ) ያዕቆብ የዮሴፍን ሁለት ልጆች ኤፍሬምና ምናሴን ባረካቸው (ዘፍጥ. 48)። ይህንን በማድረግ ያዕቆብ የበኩር ልጅን መብት ለዮሴፍና ለልጆቹ ሰጠ። ደግሞም የብኩርናን መብት ከዮሴፍ ልጆች ለታናሹ ለኤፍሬም ሰጠ። እግዚአብሔር የርስቱን ዕጥፍ ለዮሴፍ ሁለት ልጆች ለኤፍሬምና ለምናሴ ስለሰጠ፥ በእስራኤል ሕዝብ ዘንድ ዮሴፍ የሚባል ነገድ አልነበረም። ይልቁንም በእርሱ ቦታ ኤፍሬምና ምናሴ የሚባሉ ሁለት ነገዶች ነበሩ። 

ለ) ለአሥራ ሁለቱ ልጆች የተሰጠ በረከት (ዘፍጥ. 49) 

ያዕቆብ ልጆቹን እያንዳንዳቸውን ባረካቸው፤ ትንቢትም ተናገረላቸው። ነገር ግን ሦስቱ ልጆቹ ለልዩ ቅጣት ተለዩ። እነዚህም በኩሩ ሮቤል፥ ስምዖንና ሌዊ ናቸው። ሦስቱም የብኩርና መብት አጡ። ሮቤል የአባቱን መኝታ ደፈረ። ይህም በጥንት ባሕል ታላቁ ልጅ የአባቱን ርስት ለመውሰድ መፈለጉን የሚያሳይ ነበር። (ሮቤል አባቱ እስኪሞት ድረስ መጠበቅ አቅቶት ቁባቶቹን ወስዶ ከእነርሱ ጋር በመተኛት የቤቱ ራስ መሆኑን አወጀ። ከዚህ የተነሣ ያዕቆብ ከሮቤል ላይ የበኩር መብት ወሰደበት። ስምዖንና ሌዊ ከነዓናውያን እኅታቸውን በመድፈራቸው የበቀል ሤራ ይወጥኑ ነበሩ። ይህ ዓመፅ የእስራኤል ሕዝብ መሪዎች ለመሆን የነበራቸውን ዕድል አከሸፈባቸው። አብዛኛው በረከት የተላለፈው ለዮሴፍ ቢሆንም የብኩርና መብትና መሪነት ግን ለይሁዳ ተሰጠ። ይሁዳ አራተኛው ልጅ ሲሆን የነገሥታት አባት ሆነ። የያዕቆብ ሦስት ትላልቅ ልጆች እርግማንን እንጂ በረከትን አልተቀበሉም፤ ነገር ግን ዮሴፍና ይሁዳ በረከትን ከተቀበሉ ከያዕቆብ ልጆች ከፍተኛ ድርሻ ተቀብሉአል። በእስራኤል ታሪክ ውስጥ ይህ አስፈላጊ ነበር፤ ምክንያቱም ቢባል በዮሴፍ ልጅ – በኤፍሬም ነገድና በይሁዳ ነገድ መካከል የእስራኤል ነገዶች መሪ ለመሆን ሲባል ብዙ ጊዜ ትግል ይካሄድ ነበር።

የውይይት ጥያቄ፥ በመጨረሻ የኃጢአት ቅጣት የማይቀር ስለመሆኑ እነዚህ ታሪኮች ምን ያስተምሩናል? 

  1. ያዕቆብ በከነዓን ተቀበረ።

ይህ ዋጋ የሌለው ታሪክ ይምሰል እንጂ ሆኖም ግን የሚመስለው ግብፅ የአይሁድ ምድር እንዳልሆነች የሚያሳይ ስለሆነ በጣም አስፈላጊ ነው። በግብፅ መኖር የሚያስፈልጋቸው ለጥቂት ጊዜ ብቻ ነበር። በመጨረሻ የሚመለሱባት ከነዓን ምንጊዜም አገራቸው ነበረች። የያዕቆብ ሬሣ ለቀብር ወደ ከነዓን ተወሰደ። ቆየት ብሎ የዮሴፍ ሬሣም ለቀብር ወደ ከነዓን ተወሰደ፤ (ኢያ. 24፡32)።

አዲስ ኪዳን ይህንን ባይናገርም እንኳ ብዙ ምሁራን ዮሴፍን የክርስቶስ አምሳል አድርገው ያቀርቡታል። ሁለቱም ተሽጠዋል። ዮሴፍ ለባርነት ሲሸጥ፥ ኢየሱስ ደግሞ ከደቀ መዛሙርቱ በአንዱ ተሸጠ (አልፎ ተሰጠ)። ስለ ዮሴፍ በግልጥ የተጠቀሰ ኃጢአት የለም። ኢየሱስም ያለ ኃጢአት ነበር። እግዚአብሔር ኢየሱስንም ዮሴፍንም ሌሎችን ለማዳን ተጠቀመባቸው። እግዚአብሔር እስራኤላውያንን ለማዳን ዮሴፍን ተጠቀመበት። ኢየሱስን ደግሞ በእርሱ የሚያምኑትን ሁሉ ለማዳን ተጠቀመበት።

የውይይት ጥያቄ፥ ከኦሪት ዘፍጥረት ጥናት ስለ እግዚአብሔርና ስለ ሰው ምን መማር ይቻላል?

በኦሪት ዘፍጥረት በግልጥ የተጠቀሱ የእምነት ትምህርቶች

  1. እግዚአብሔር፡-

በኦሪት ዘፍጥረት ውስጥ የእግዚአብሔርን ማንነት ለመረዳት የሚያስችሉን አምስት ዋና ዋና ሥዕላዊ መግለጫዎችን እናገኛለን። እግዚአብሔር መጽሐፍ ቅዱስን ለእኛ የሰጠበት አንዱ ዋና ምክንያት እርሱ ማን እንደሆነ ሊገልጥልንና ከእኛ ምን እንደሚፈልግ ለማስረዳት መሆኑን ልብ በል። የእግዚአብሔርን ማንነት ለማወቅ የምንችለው፥ እርሱ ምን እንደሚመስል እኛ በምናስበው መንገድ ሳይሆን፥ እርሱ ከሚነግረን ነገር ነው።

ሀ. እግዚአብሔር የዓለም ሁሉ ታላቅ ፈጣሪ ነው። አንድ ቃል በመናገር ብቻ ፍጥረታትን ሁሉ እንዲሁም ሰውን ጨምሮ ፈጠረ። 

ለ. እግዚአብሔር ቃል ኪዳን አድራጊ አምላክ ነው። እግዚአብሔር ከእንግዲህ ምድርን በውኃ እንደማያጠፋት ከኖኅ ጋር የገባውን ቃል ኪዳን ተመልክተናል። በኋላም ከአብርሃምና ከዝርያዎቹ ጋር ቃል ኪዳን ገብቶአል። ይህ ቃል ኪዳን እግዚአብሔር ከአይሁድ ጋር ላለው ልዩ ኅብረት መሠረት ነው። አሕዛብ የተባረኩት በዚህ ቃል ኪዳን መሠረት ነው። እግዚአብሔር ምንም ቅድመ ሁኔታ የሌለበትን ቃል ኪዳን አንድ ጊዜ ከገባ፥ ሕዝቡ ባይታዘዙትና ቢያምፁበትም እንኳ ያንን ቃል ኪዳን ለመፈጸም ይተጋል።

ሐ. እግዚአብሔር በኃጢአት ላይ ይፈርዳል። እግዚአብሔር ቅዱስና ጻድቅ ነው፤ ስለዚህ ኃጢአትን ሳይቀጣ አይተውም። በአዳምና በሔዋን፥ በቃየን፥ በኖኅ ዘመን በነበሩ ሰዎች፥ የባቢሎንን ግንብ ለመሥራት በሞከሩ ሰዎች ላይ እንደፈረደ ሁሉ ዛሬም በኃጢአት ውስጥ በሚኖሩ ሰዎች ላይ ለመፍረድ ቃል ገብቷል። 

መ. እግዚአብሔር ኃጢአተኞችንም ይምራል፡- እግዚአብሔር ለኃጢአተኞች የሚገባቸውን ቅጣት በሙሉ ሰጥቶ አያውቅም። እርሱ መሐሪ ነው። አዳምና ሔዋን ኃጢአት ካደረጉ በኋላ እግዚአብሔር ፈለጋቸው። ብዙ ምሁራን እግዚአብሔር የእንስሳ ቆዳ ባለበሳቸው ጊዜ ስለ ኃጢአታቸው የመጀመሪያውን መሥዋዕት እንዳቀረበ ያምናሉ። ከኤድን ገነትም ያስወጣቸው የሕይወትን ዛፍ እንዳይበሉና ለዘለዓለም በኃጢአተኝነት እንዳይኖሩ ብሉ ነው። ይህን የመሰለ ምሕረት የሚገባቸው ባይሆኑም እንኳ ሎጥን ከሰዶም፥ ያዕቆብን ከላባና ከዔሳው እጅ አዳነ። እግዚአብሔር ከአሕዛብ ሁሉ መካከል በመረጠው ጊዜ አብርሃም እንኳ ራሱ ጣዖት አምላኪ ነበር።

ሠ. እግዚአብሔር በምድር ላይ የሚፈጸሙ ድርጊቶችን ሁሉ ይቆጣጠራል። ዓለምን የፈጠረው እርሱ ነው። እግዚአብሔር የጥፋትን ውኃ ላከ። ቋንቋቸውንም በመደበላለቅ ሰዎችን በምድር ላይ በተናቸው። የተመረጡት ሕዝቡን እንዳይጎዱ ወይም ዕቅዱን እንዳያበላሹ የነገሥታትን ሥራ ይቆጣጠራል። እግዚአብሔር ብልጥግናንና ድርቅን የመሳሰለውንም ነገር ወደ ምድር ይልካል።

የውይይት ጥያቄ፥ ዛሬ እነዚህን የእግዚአብሔር ባሕርያት በሕይወታችን የምናየው እንዴት ነው?

ሙሴ የእግዚአብሔርን ባሕርያት ከሚገልጽባቸው መንገዶች አንዱ በኦሪት ዘፍጥረት ውስጥ በጠቀሳቸው በርካታ የእግዚአብሔር ስሞች ነው። አይሁድ ስለ እግዚአብሔር «ስም» በሚነጋገሩበት ጊዜ የሚያተኩሩት በእግዚአብሔር ውጫዊ ስም ላይ ሳይሆን በእግዚአብሔር ባሕርይ ላይ ነበር። ስሙ እግዚአብሔር በእርግጥ ማን እንደሆነ ይገልጥ ነበር። ስለዚህ ሰዎች «የእግዚአብሔርን ስም እናመስግን» ሲሉ «እግዚአብሔርን እናመስግን» ማለታቸው ነበር።

እግዚአብሔር በብሉይ ኪዳን ይጠራባቸው ከነበሩት ስሞች አንዳንዶቹና ትርጉማቸው ቀጥሉ ቀርቦአል። 

  • ኤል (ዘፍ. 35፡7):- የእግዚአብሔር መሠረታዊ ስሙ ሲሆን በእግዚአብሔር ኃይል ላይ ያተኩራል 
  • ኤሎሂም (ዘፍ. 1፡1):- እግዚአብሔር ፈጣሪና ገዥ፥ ኃይልን የተሞላ ግርማዊ ነው። ኤሎሂም በብሉይ ኪዳን በጣም ከታወቁት የእግዚአብሔር ስት አንዱ ነው።
  • ኤል ኤልዩን (ፍ. 14፡18):- እግዚአብሔር ከሁሉ በላይ ወይም ከማንም ጋር መወዳደር የማይችል በአማልክት ሁሉ ላይ አምላክ ነው። 
  • ኤል ሻዳይ (ዘፍ. 17፡1):- እግዚአብሔር ሁሉን ቻይ፥ ሉዓላዊ ገዥ 
  • ኤልሮኢ (ዘፍ. 16፡13):- እግዚአብሔር ሁሉን ያያል ከእርሱ የተሰወረ ነገር የለም 
  • ያህዌ (ጆሆቫ) (ዘፍ. 2፡4):- ልዩና ከሁሉም የበለጠ የተከበረ አይሁዳዊ ስም፥ ለእግዚአብሔር የተሰጠ ስም ሲሆን ፍፁም ታማኝነቱንና የቃል ኪዳን አምላክነቱን ያሳያል። የእግዚአብሔርን የምሕረት፣ የጸጋና የፍቅር ባሕርይ ያካትታል። በብሉይ ኪዳን ከሚታወቁት የእግዚአብሔር ስሞች አንዱ ነው። 
  • ያህዌ ይርኤ (ፍጥ. 22፡14):- በእግዚአብሐር ተራራ ይታያል ማለት እግዚአብሔር ያዘጋጃል።
  • አዶናይ (ፍጥ. 15፡2፣ 8):- እግዚአብሔርን በግል ለማምለክ የሚውል ስም፣ የእግዚአብሔር ጌትነት፥ ታላቅ ባለ ግርማ አምላክ። 
  • አቢር ይስራኤል (ዘፍጥ. 49፡24):- እግዚአብሐር፥ የእስራኤል ኃያል፡፡ 

የውይይት ጥያቄ፥ አምልኮ፥ እግዚአብሔር ስላደረገው ነገር ብቻ ሳይሆን፥ ስለ ማንነቱም ማመስገን ማለት ነው። ከላይ የተዘረዘሩትን ስሞች በመጠቀም ስለማንነቱ እግዚአብሔርን በጸሎት አመስግነው። 

  1. የሰው ልጅ፡

የሰው ልጅ የእግዚአብሔር ፍጥረት ቁንጮ መሆኑን ኦሪት ዘፍጥረት ያሳየናል። የሰው ልጅ በመጨረሻ የተፈጠረ ብቻ ሳይሆን፥ በእግዚአብሔር አምሳል የተፈጠረም ነው። ይህ አምሳል የሰው ልጅ በኃጢአት በመውደቁ ምክንያት እጅግ የተበላሸ ቢሆንም፥ ሙሉ ለሙሉ አልጠፋም። አሁንም የተፈጠርነው በእግዚአብሔር አምሳል ነው፤ ስለዚህ ይህ የሚያሳየው የሰው ልጅ የማያምን እንኳ ቢሆን፥ በእግዚአብሔር ዘንድ ታላቅ ዋጋ እንዳለውና በእኛም ዘንድ ይህ መታወቅ ያለበት እንደሆነ ነው።

እግዚአብሔር ለሰው ትክክለኛ የሆነውንና ያልሆነውን (ማለት ኃጢአትን የማድረግ፣ ያለማድረግ መብት) የመምረጥ ፈቃድ ሰጥቶታል። ሰው የመሆን አንዱ ክፍል የመምረጥ መብት ነው። ስለዚህ ሰው እግዚአብሔርን ለመታዘዝ ወይም ላለመታዘዝ የመምረጥ ፈቃድ አለው። ሰው ምርጫውን መቆጣጠር ቢችልም ውሳኔው የሚያስከትላቸውን ነገሮች ግን መቆጣጠር አይችልም። ለእግዚአብሔር መታዘዝ በረከትን ያስገኛል፤ ለእግዚአብሔር አለመታዘዝ ደግሞ ፍርድን ያስከትላል። የሰው ልጅ ብዙ ጊዜ የሚያሳየው ባሕርይ አለመታዘዝ እንደሆነ ኦሪት ዘፍጥረት ያሳያል። የሰው ልጅ የእግዚአብሔር ፍጡር ቢሆንም፥ እግዚአብሔር በእርሱ ላይ ያለውን የአገዛዝ መብት ግን አልተቀበለም። ለእግዚአብሔር ላለመታዘዝ የመረጡ ሰዎች፥ የውሳኔያቸው ውጤት የሆነውን የእግዚአብሔርን ቅጣት እንደሚቀበሉ የተረጋገጠ ነው። አንድ ሰው እግዚአብሔርን መታዘዝ ከመረጠ፥ እርሱ ያከብረዋል።

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) በኦሪት ዘፍጥረት ውስጥ ይህ ጉዳይ የታየው እንዴት ነው? ለ) ዛሬስ በሕይወታችን የምናየው እንዴት ነው?

ሰዎች ሁሉ ከትንሹ ጀምሮ እስከ ትልቁ፥ በኢስያ ከሚኖሩት ጀምሮ በአውሮፓ እስካሉት። በጣም ከተማሩት ጀምሮ እጅግ ኋላቀር እስከሆኑት ድረስ ያሉት ሁሉ በእግዚአብሔር አምሳል የተፈጠሩ ናቸው። በዚህ መሠረት ነው ክርስቲያኖች በግልጽ ዘረኝነትን፥ ባርያ ፍንገላንና ፅንስ ማስወረድን ስሕተት ነው የሚሉት። የሰው ልጅ ሁሉ አንድ ነው። የሰው ልጆች መጀመሪያ ከአንድ ሰው ከአዳም፥ በኋላም ከኖኅ ተገኙ። የሰው ልጅ ከየትኛውም ዘር ይሁን፥ የትም ይኑር፥ ምንም ያህል ይማር፥ ጾታው ምንም ይሁን የእግዚአብሔር አምሳል ነው። ማንኛውም የጎሰኝነትና የዘረኝነት አመለካከታችን የትዕቢታችንና የኃጢአታችን ውጤት ሲሆን፥ ሁላችንም አንድ እንደሆንን የሚናገረውን የኦሪት ዘፍጥረትን ትምህርት የሚቃረን ነው።

የቤተ ክርስቲያናችን አባሎች ጎሰኝነትን የመቃወም አቋም እንዲኖራቸው ይህንን ትምህርት እንዴት እንጠቀምበታለን? በኢትዮጵያ ውስጥ በዘረኝነት ወይም በጎሰኝነት ላይ የተመሰረተ ጥላቻ እንዴት ይታያል? ክርስቲያኖች እንደመሆናችን መጠን ይህንን ለመቃወም ምን ማድረግ አለብን? 

  1. ኃጢአት፡

ሰዎች ፈጣሪያቸው በሆነው በእግዚአብሔር ሕግ ላይ የማመፃቸው ውጤት ኃጢአት ነው። ይህም በመጨረሻ ሥጋዊ ሞትን ያመጣል። ደግሞም የነፍስ ግድያን፥ የቤተሰብ አባላት መለያየትን፥ ዘረፋን፥ ስርቆትን፥ ሴትን አስገድዶ መድፈርን ወዘተ. ያስከትላል። አዳምና ሔዋን የሠሩት የመጀመሪያው ኃጢአት እጅግ አጥፊ የሆኑ ውጤቶች ነበሩት። በእግዚአብሔርና በሰው፥ በባልና በሚስት መካከል ጠላትነትን አመጣ። ሴትና የመውለድ ችሉታዋ፥ ወንድና ለቤተሰቡ ምግብ የማቅረብ አስፈላጊነት ሁሉ በአሉታዊ ተጽዕኖ ሥር ወደቁ። የሰው ልጅ ሁልጊዜ ከኃጢአት ጋር ይታገል ዘንድ የአዳምና የሔዋን የኃጢአት ባሕርይ ለልጆቻቸው ሁሉ ተላለፈ።

  1. ቃል ኪዳን፡

በእግዚአብሔርና በሰው መካከል የሚደረግ ስምምነት ቃል ኪዳን ይባላል። ከሰው ጋር ቃል ኪዳን ለማድረግ ጀማሪ ሊሆን የሚችለው እግዚአብሔር እንጂ ሰው ስላይደለ ቃል ኪዳን የእግዚአብሔር ጸጋ ምልክት ነው። አንዳንድ ጊዜ ከእርሱ ጋር የቃል ኪዳን ተካፋይ ለሆኑ ሰዎች መመዘኛ ቢያበጅም፥ ብዙ ጊዜ እግዚአብሔር ቃል ኪዳን የሚያደርገው በምንም ቅድመ ሁኔታ ላይ ሳይመሠረት ነው። በታማኝነቱ ላይ የተመሠረተው ተስፋው እርሱ የመረጣቸውን ሰዎች ይመለከታል፤ ስለዚህ የቃል ኪዳኑ አካል የሆኑትን ሁሉ ይቅር በማለት በሕይወታቸው ፈቃዱን ለመፈጸም ያተጋል።

የውይይት ጥያቄ፥ እነዚህ አራቱም የሃይማኖት ትምህርቶች እያንዳንዳቸው ከእግዚአብሔር ጋር ስላለን ግንኙነት ምን ያስተምሩናል?

በኦሪት ዘፍጥረት ውስጥ ስለ ክርስቶስ የተነገሩ ትንቢቶችና ተምሳሌቶች፡- በኦሪት ዘፍጥረት ውስጥ ስለ ጌታ ኢየሱስ የተነገሩ በርካታ ትንቢቶችና ተምሳሌቶች አሉ።

  1. አዳም፡- አዳም የመጀመሪያው ሰው እንደመሆኑ መጠን ከእርሱ ለመጡት የሰው ልጆች ሁሉ ራስና ተወካይ ነው። ኢየሱስም በእምነት የእግዚአብሔር ልጆች ለሆኑትና ለሚሆኑት ሁሉ ራስና ተወካይ ነው (ሮሜ 5፡12-19 ተመልከት)።
  2. ዘፍጥ. 3፡15፡- ይህ የመጀመሪያው የመጽሐፍ ቅዱስ ትንቢት ነው። በሰይጣንና «በሴቲቱ ዘር» መካከል ስለሚኖረው ጦርነት ይተነብያል። ያ ዘር ማን ነው? በብሉይ ኪዳን የእግዚአብሔር ሕዝብ የሆኑትን እስራኤላውያንን ዛሬ ደግሞ ቤተ ክርስቲያንን ያመለክታል (ሮሜ 16፡20)። ከሁሉም ይልቅ ከሴት (ከማርያም) የተወለደውን ኢየሱስ ክርስቶስን ያመለክታል። ሰይጣን «ሰኮናውን ይቀጠቅጣል»። ይህም ሰይጣን ያነሣሣውን የኢየሱስ ክርቶስን የመስቀል ሞት የሚያመለክት ነው፤ ነገር ግን ኢየሱስ ራሱን ይቀጠቅጠዋል። ይህም የሰይጣንን መሸነፍና ሙሉ በሙሉ መጥፋት የሚያመለክት ነው (ራእ. 20፡1-10 ተመልከት)።
  3. እግዚአብሔር እንስሳት ለኃጢአት መሥዋዕት የሚሆኑበትን ተግባር ጀመረ (ዘፍጥ. 3፡21)። ይህም ኢየሱስ ክርስቶስ በመጨረሻ ስለ ዓለም ኃጢአት ሊከፍለው ያለውን መሥዋዕትነት የሚያሳይ ነው፤ (ዕብ. 9፡27-28)። 

የኖኅ መርከብ፡- በመርከቡ ውስጥ የነበሩት ሁሉ እግዚአብሔር በጥፋት ውኃ አማካይነት ካመጣው ፍርድ እንደዳኑ ሁሉ በክርስቶስ ኢየሱስ ያሉት ደግሞ በመጨረሻው ቀን ለማያምኑ ሰዎች ከተጠበቀው ፍርድ ይድናሉ (1ኛ ጴጥ. 3፡20-21)።

  1. መልከ ጸዴቅ፡- መልከ ጸዴቅ፥ ሊቀ ካህንና ንጉሥ እንደ ነበር ሁሉ፥ ኢየሱስ ክርስቶስም ሊቀ ካህንና ንጉሥ ነው፤ (ዘፍጥ. 14፡18-20፤ ዕብ. 6፡20፤ 7)። 
  2. ይስሐቅ፡- ይስሐቅ ብቸኛው (ልዩ) የአብርሃም ልጅ እንደሆነ ሁሉ፥ ኢየሱስም የእግዚአብሔር ልዩ ልጁ ነው። አብርሃም ይስሐቅን እንደሠዋ ሁሉ እግዚአብሔርም ኢየሱስን የኃጢአት መሥዋዕት አድርጎ ሰጥቷል። ይስሐቅ በፍጹም ፈቃደኝነት ራሱን ለመሥዋዕት እንዳዘጋጀ ሁሉ ኢየሱስም ራሱን የኃጢአት መሥዋዕት አድርጎ አቀረበ።
  3. ዮሴፍ፡- ልክ ዮሴፍ ወደ ባርነት እንደተሸጠና ወገኖቹን ከራብ ሁሉ እንዳዳነ ኢየሱስም ለመሠዋትና ሕዝቡን ለማዳን ተሰጠ።

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

1 thought on “ዘፍጥረት 37-50 የዮሴፍ ታሪክ”

Leave a Reply

%d bloggers like this: