የኦሪት ዘሌዋውያን ዓላማ እና ቁልፍ ሃሳቦች

የኦሪት ዘሌዋውያን ዓላማ

የኦሪት ዘሌዋውያን ዋና ዓላማ «ቅዱስ» በሚለው ቃል ተጠቃሏል። በመጽሐፉ ውስጥ ቅዱስ የሚለው ቃል ከ90 ጊዜ በላይ ተጠቅሶአል። ጌታ ራሱ ቅዱስ እንደሆነ ይገልጻል። ሕዝቡም በእርሱ ፊት ቅዱስ ይሆኑ ዘንድ ይነግራቸዋል። ቅድስና በአንድ ሰው ሕይወት ውስጥ የማይነካው ነገር የለም። እግዚአብሔርን ለእስራኤል ሕዝብ እንዴት የተቀደሱ ሕዝብ እንደሚሆኑና የማያቋርጥ በረከት እንደሚያገኙ ነግሮአቸዋል። ያ ቅድስናቸው የሚያተኩረው በሁለት ዋና ዋና ነገሮች ላይ ነበር። በመጀመሪያ፥ በእርሱ ዘንድ ተቀባይነት ባለው መንገድ እግዚአብሔርን እንዴት ማምለክ እንደሚቻል ይናገራል።

ዛሬ በዓለም ላይ በርካታ የሃይማኖት ሰዎች አሉ። እግዚአብሔር ግን አምልኮአቸውን አይቀበልም። ለምን? ምክንያቱም እግዚአብሔርን የሚያመልኩት፥ እርሱ በሚመራቸው መንገድ ስላልሆነ ነው። እርሱ በሚቀበለው መንገድ እንዴት ልናመልከው እንደምንችል ሊነግረን የሚችል እግዚአብሔር ብቻ ነው። በብሉይ ኪዳን፥ ሰዎች መሥዋዕት በመሠዋት እንዴት እደሚያመልኩት ገልጾላቸዋል። በአዲስ ኪዳን ደግሞ ሰዎች እግዚአብሔርን ሊያመልኩ የሚችሉበት ብቸኛ መንገድ፥ በመጨረሻው መሥዋዕት በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል ነው።

የውይይት ጥያቄ፥ ዮሐ. 14፡6 አንብብ። ሀ) ይህ ጥቅስ እግዚአብሔርን ስለምናመልክበት ብቸኛ መንገድ ምን ይነግረናል? ለ) ይህ ጥቅስ በዓለም ዙሪያ ስላሉና፥ በኢየሱስ ክርስቶስ ስለማያምኑት ሰዎች ምን ያስተምረናል?

በሁለተኛ፥ ደረጃ የተቀደስን የእግዚአብሔር ሕዝብ እንደመሆናችን መጠን በቅድስና እንዴት መኖር እንዳለብን ያሳያል። በኢየሱስ ላይ ያለን እምነት እውነተኛ ከሆነ፥ ወንጌል ሕይወታችንን መለወጥ አለበት። የሚለውጠው አምልኮአችንን ብቻ ሳይሆን፥ ከጎረቤቶቻችን ጋር ያለንን አኗኗር፥ አሠራራችን ወዘተ. ሁሉንም ነው። ኦሪት ዘሌዋውያን የተሰጠው፥ ሕዝቡ የእግዚአብሐር ቅዱስ ሕዝብ ሆነው እንዴት መኖር እንዳለባቸው ዝርዝር የሕይወት ሁኔታዎችን ለማሳየት ነው።

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ክርስቲያን ከሆንክ ጀምሮ ሕይወትህ እንዴት እየተለወጠ ነው? ለ) አንተና ሌሎች የቤተ ክርስቲያንህ አባሎች የተቀደሰ ሕይወት የምትኖሩት እንዴት ነው? ምሳሌዎችን ጥቀስ። 

በኦሪት ዘሌዋውያን ውስጥ የሚገኙ ቁልፍ አሳቦች

ኦሪት ዘሌዋውያን ከኦሪት ዘጸአት ቀጥሎ መምጣቱ በጣም ትክከለኛ ነው። በኦሪት ዘጸአት የእስራኤል ሕዝብ እግዚአብሔርን የሚያመልኩበትን የመገናኛውን ድንኳን እንዴት እንደሠሩ ተመልክተን ነበር። በተጨማሪም የአምልኮ መሪዎች የሆኑት ካህናትና ሊቀ ካህናት በመገናኛው ድንኳን ውስጥ በሚደረገው አምልኮ ስለሚኖራቸው ዝግጅትም ተነግሮናል። አሁን ደግሞ በኦሪት ዘሌዋውያን በመገናኛው ድንኳን ውስጥ፥ አምልኮው ስለሚፈጸምበት መንገድ የተሰጠ መግለግጫ እናገኛለን። ደግሞም ቅዱሱን እግዚአብሔር በመገናኛው ድንኳን ውስጥ ለማምለክ የተፈቀደላቸው ሰዎች መንፈሳዊ ሁኔታም ተገልጦ እናያለን። የሚከተሉት በኦሪት ዘሌዋውያን ውስጥ ከሚገኙ ዋና ዋና ትምህርቶች ጥቂቶቹ ናቸው፡

  1. ቅድስና

ብዙ ክርስቲያኖች ምን ማለት እንደሆን ባያውቁም እንኳ፥ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ካሉ እጅግ በጣም አስፈላጊ ቃላት አንዱ «ቅድስና» ነው። ኦሪት ዘሌዋውያን እግዚአብሔርን ደስ ማሰኘትና እርሱ በሕይወታችን ውስጥ ሳያቋርጥ በመገኘቱ ሐሴት እንድናደርግ ሁለት ነገሮችን ማድረግ አለብን ይላል። በመጀመሪያ፥ ተገቢ የሆነ ወይም የተቀደሰ አምልኮ መፈጸም ነው። ሁለተኛው ደግሞ፥ የተቀደሰ አኗኗር ነው። ስለዚህ ቅድስና ምን ማለት እንደሆነ መረዳት አስፈላጊ ነው።

«ቅድስና» የሚለው ቃል በመሠረቱ «መለየት» ማለት ነው። በብሉይ ኪዳን ቅድስና ስለ ሁለት ዓይነት መለየት ይናገራል። በመጀመሪያ፥ የእግዚአብሔር ካልሆነ ከማንኛውም ነገር መለየት ነው። እስራኤል «የተቀደሰ» ሕዝብ የተባለው ከአሕዛብ ተለይቶ፥ የእግዚአብሔር ስለሆነ ነው። እስራኤላውያን ከአሕዛብና ከተግባራቸው በመለየት በአኗኗራችው የተቀደሱ መሆን ነበረባቸው፤ ምክንያቱም አሕዛብ ለእግዚአብሔር የተለዩ አልነበሩምና። ለአምልኮ የተለዩ እንስሳት እንኳ የተቀደሱ ይባሉ ነበር። በኦሪት ዘሌዋውያን ውስጥ ትኩረት የተሰጠው አብዛኛው ነገር ከተለመዱ ነገሮች በመለየት ቅዱስ መሆንን የሚመለከት ነው። እግዚአብሔር ልዩ በመሆኑ ቅዱስ ነው። ከተፈጠሩ ነገሮች ሁሉ የተለየና የላቀ ነው። እንደ እርሱ ያለ ማንም የለም፤ እርሱን የሚመስል ማንም የለም።

ሁለተኛው፥ ከክፉ ሥነ-ምግባር መለየት ነው። የሥነ-ምግባር ቅድስና ከኃጢአት መራቅን የሚያመለክት ነው። እግዚአብሔር ኃጢአት ስለማያደርግና ሊያደርግም ስለማይችል ሥነ-ምግባር የተቀደሰ ነው። ኃጢአታችንን ስንናዘዝና የክርስቶስ ደም ከኃጢአታችን ሁሉ ሲያነጻን በሥነ-ምግባር የተቀደስን እንሆናለን። ለእግዚአብሔር ሕግ በታዛዥነት ስንኖርና ኃጢአት ሕይወታችንን እንዳይቆጣጠር ጸንተን ስንቃወም በሥነ-ምግባር የተቀደሰ ሕይወት እንኖራለን።

በአዲስ ኪዳን፥ እኛ ክርስቲያኖች በሁለቱም መንገዶች የተቀደስን ነን። እግዚአብሔር ስለመረጠንና ከዓለም ስለተለየን የተቀደስን ነን። ነገር ግን ኃጢአትን ድል የመንሣት ሕይወት በመኖር ደግሞ በቅድስና መመላለስ አለብን። በሕይወታችን የሚኖር ማንኛውም ኃጢአት በኢየሱስ ክርስቶስ ደም ሲታጠብ በእግዚአብሔር ፊት ብቁ ሆኖ ወደሚገኘው ወደ ቅድስና ደረጃችን እንደገና ሊመልሰን ይችላል። 

የውይይት ጥያቄ፥ ሕይወትህን መርምር። ሀ) በመጀመሪያው መንገድ የተቀደስከው እንዴት ነው? ለ) በሁለተኛው መንገድስ የተቀደስከው እንዴት ነው? ሐ) በሕይወትህ ያልተቀደስህባቸው ክፍሎች ካሉ {አሁን ተናዘዝና ከእነዚህ ኃጢአቶች ተመለስ። 

  1. ንጹሕና እርኩስ

አብዛኛው የኦሪት ዘሌዋውያን ክፍል ንጹሕ ስለሆኑና ስላልሆኑ ነገሮች፥ እንዲሁም ሰውን ንጹሕ ስለሚያደርጉና ስለማያደርጉ ነገሮች ይናገራል። ይህ ለእኛ እንግዳ ስለሆነ ለብዙዎቻችን ይህንን ሐሳብ መረዳት በጣም አስቸጋሪ ነው። በኦሪት ዘሌዋውያን ውስጥ የሚገኙትን፥ አብዛኛዎቹን ሕግጋት ለመረዳት የእግዚአብሔርን ዓላማዎችና የአይሁዳውያንን አስተሳሰብ መረዳት ያስፈልጋል።

በብሉይ ኪዳን፥ እግዚአብሔር ውጫዊ የሆኑ የአካል ጉድለቶችን የኃጢአት ተጽዕኖዎች ገላጭ ማስተማሪያዎች አድርጎ ሲጠቀምባቸው እናያለን። የአካል ጉድለት በራሱ ኃጢአት አይደለም። ነገር ግን አካሉ ጎዶሎ መሆን ኃጢአተኝነትን ያመለክት ነበር። ለምሳሌ፡- በሥጋው ምንም ዓይነት ጉድለት ያለበትን፥ ወይም ጤናማ ያልሆነ ሰው በክህነት እንዳያገለግል እግዚአብሔር አግዶታል (ዘሌ. 21፡17-21)። ለምን? ያ ካህን ኃጢአተኛ ነውን? አይደለም። ነገር ግን ጤናማ አለሆኑ፥ በዓለም ላይ ኃጢአት መኖሩን የሚያሳይ ማስረጃ ነው። ስለዚህ እግዚአብሔር በኃጢአት ላይ ያለውን ጥላቻ ለእስራኤል ሕዝብ በግልጽ ለማሳየትና ከታወቀ ኃጢአት የመራቃቸውን አስፈላጊነት ለመግለጥ፥ አካለ-ጎዶሉ የሆን ካህን በተቀደሰው በእግዚአብሔር ፊት እንዲያገለግል አልፈቀደም። በዘሌዋውያን ውስጥ ላሉ አብዛኛዎቹ ሕግጋት ይህ መመሪያ የሚሠራ ነው። ጤነኛ ያልሆኑ፡- እንደ የሴት የወር አበባ ወይም በሽታ ያሉቱ የኃጢአት ውጫዊ ምልክቶች ነበሩ፤ ስለዚህ ለመንጻት መሥዋዕት ይፈልጉ ነበር።

አይሁድ ነገሮችን ሁሉ በሁለት ክፍሎች ይከፍሉ ነበር። የመጀመሪያው «ቅዱስ» ወይም የተለየ የሚባለው ክፍል ሲሆን፥ ሁለተኛው ደግሞ፥ «የተለመደ» የሚባለው ክፍል ነው። እንስሳትም ሆኑ ሰዎች ከሌሎች ተለይተው ለእግዚአብሔር ሲሰጡ ቅዱስ (የተለዩ) ይሆናሉ (ለምሳሌ፡- ዘሌ. 21፡7-8)። ቅዱስ የነበሩ ነገሮች በሰዎች ዘንድ በማይገባ መንገድ ለተለመዱ ነገሮች አገልግሎት ሲውሉ፥ ቅዱስ መሆናችው ይቀርና የተለመዱ ይሆናሉ። ለምሳሌ፡- አንድ ሰው ከመንጋዎቹ መካከል አንድን ጠቦት ለመሠዋት ቃል ቢገባ፥ ያ ጠቦት ቅዱስ ይሆናል። ለእግዚአብሔር የተለየ ይሆናል። ቅዱስ የሚሆነው በሥነ-ምግባር አልነበረም። ለእግዚአብሔር ተመርጦ በመለየቱ ብቻ ነው። ልክ እንደዚሁ፥ ሳምሶን በሥነ – ምግባር የወደቀ ወይም የተበላሸ ሕይወት ቢኖረውም፥ ለአንድ ለተለየ አገልግሎት በእግዚአብሔር በመመረጡ ብቻ የተቀደሰ ነበር። የተለመዱ (ተራ) የሆኑ ነገሮች፡ በሥነ ምግባር የሚፈተኑ አልነበሩም፤ ነገር ግን ለእግዚአብሔር ዓላማ ተመርጠው የተለዩ ሊሆኑ ይችላሉ። 

«ንጹሕ የመሆንና ያለመሆን» አሳብ የሚጎለብተው ከዚህ ነው። በእግዚአብሔር ፊት ጤናማ የሆኑ ነገሮች ንጹሐን ናቸው። ሣር የሚበሉና ሸሆናቸው የተሰነጠቀ እንስሳት ጤናማ ስለሆኑ፥ ንጹሐን እንስሳት ናቸው። ምንም ዓይነት አካላዊ ጉድለትና በሽታ የሌለባቸው ሰዎች ጤናማና የተለመዱ ስለሆኑ፥ ንጹሐን ናቸው፤ ነገር ግን ከተለመደው ነገር ውጭ የሆነ ማንኛውም ነገር «ንጹሕ አይደለም»። ንጹሕ ያልሆነ ነገር ሁሉ የኃጢአት ምልክት ስለሆነ፥ ወደ እግዚአብሔር ፊት ሊቀርብ ወይም ለእግዚአብሔር ሊሰጥ አይገባም ነበር። ለምሳሌ፡- አንድን ጠቦት በመሥዋዕትነት ለእግዚአብሔር በመስጠት ቅዱስ ማድረግ ይቻላል፤ ነገር ግን አንድ አካሉ ጉድለት ካለው (አንድ ዓይኑ ዕውር ቢሆን፥ ወይም ሽባ ቢሆን፥ ወዘተ.) ንጹሕ ስላይደለ፥ ለእግዚአብሔር ሊሠዋ አይገባም ወይም አንድ ሰው ያልተለመደ በሽታ ካለው ርኩስ ነበር። ከበሽታው ለመፈወሱና ንጹሕም ለመሆኑ ሁለንተናውን በማጠብ ካሳየና መሥዋዕት ካቀረበ እንደገና እንደቀሩት እስራኤላውያን እግዚአብሔርን ማምለክ ይችላል።

በኦሪት ዘሌዋውያን ውስጥ ያሉትን ሕግጋት በምታጠናበት ጊዜ የሚከተሉትን ነገሮች አስተውል፡-

  1. ቅዱስ ለመሆን፥ ሰው ወይም ሌላ ነገር ተቀባይነት ባለው መንገድ ለእግዚአብሔር ይለያል። ይህ ካልሆነ የተለመደ ወይም ተራ ነገር ነውና ለማንኛውም ተራ አገልግሎት ብቻ ይውል ነበር።
  2. አንድ ነገር ንጹሕ ለመሆን አካሉ ሙሉ መሆን ነበረበት። አካለ-ጎዶሎ የሆነ ነገር ንጹሕ ሊሆን አይችልም፤ ምክንያቱም ጤናማ ያልሆነ ነገር የሚያመለክተው ኃጢአትን ነውና። 
  3. አካለ ጎዶሎ የሆነ ነገር ሁሉ እርኩስ ነበር። ኃጢአት ባይሆንም እንኳ ኃጢአትን ስለሚወከል እንደገና ንጹሕ ይሆን ዘንድ መሥዋዕት ሊቀርብለት ያስፈልግ ነበር። 

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ንጹሕ ስለ መሆንና አለመሆን የተሰጠው ትምህርት እግዚአብሔር በኃጢአት ላይ ስላለው ጥላቻ ምን ያስተምረናል? ለ) ይህ ስለተገለጠው የኃጢአት ተጽዕኖ ምን ያስተምረናል? ሐ) በእግዚአብሔር ዘንድ ተቀባይነትን ለማግኘት ስለ ግላዊ ቅድስና አስፈላጊነት ይህ ምን ያስተምረናል?

በአዲስ ኪዳን እግዚአብሔር ንጹሕ መሆንና አለመሆንን በሚመለከት በውጫዊ ነገሮች ላይ አላተኮረም። ይልቁንም ሰውን የሚያረክሱት ውስጣዊ የሆኑ ወይም በሰው ልብ ውስጥ የሚፈጸሙ ነገሮች ናቸው። ምክንያቱም ግልጽ የሆነ ክፋትና ኃጢአት የሚገለጠው በሚታዩ መንገዶች (በጥላቻ፥ በቁጣ፥ በመግደል፥ በምንዝር፥ ወዘተ.) ሲሆን የሚመነጨውም ከልብ ነው (ማቴ. 15፡8-20 ተመልከት)።

አዲስ ኪዳን እኛ የተወለድነው «በኃጢአት» ነው ይላል። ምክንያቱም ሁላችንም የአዳምን የኃጢአት ባሕርይ ወርሰናል (ሮሜ 5፡12-14)። የምንቀደሰው በመስቀል ላይ በተሰቀለው በኢየሱስ ሞትና ለድነት (ደኅንነት) በእርሱ ላይ በምንታመንበት ጊዜ ለልባችን እርሱ በሚሰጠን መንጻት ብቻ ነው (1ኛ ቆሮ. 6፡9-11)። 

  1. ንጉሡ እግዚአብሔር ስለ ሕይወታችን አቅጣጫ ሁሉ ይገደዋል፡፡ ብዙ ጊዜ ክርስቲያኖች እግዚአብሔር የሚገደው በቤተ ክርስቲያን ስለምናደርገው ወይም በመንፈሳዊ ሕይወታችን ስለሚሆነው ነገር ብቻ እንደሆነ በማሰብ ይሳሳታሉ። ሥጋዊ ናቸው የምንላቸው ነገሮች እጅ ሥራን እንደ መሥራት፥ ከሰዎች ጋር መነጋገር፥ ትምህርት ቤት መሄድ፥ ወዘተ፥ እግዚአብሔርን ብዙ የሚያሳስበው አይደሉም ይላሉ፤ ዳሩ ግን እግዚአብሔር እስራኤላውያንን ያስተማረው ስለ ማንኛውም የሕይወታቸው ክፍል ዝርዝር ጉዳይ ሁሉ እንደሚገደው ነው። ንጉሣቸው እንደመሆኑ መጠን እግዚአብሔር እስራኤላውያን እንዲታዘዙትና እንዲያከብሩት የሚፈልገው በሁሉም የሕይወታቸው አቅጣጫ ነው።

ስለዚህ በኦሪት ዘሌዋውያን ውስጥ ሁሉንም የሕይወት አቅጣጫ የሚነኩ ሕግጋትን እናገኛለን። እግዚአብሔርን እንደ ማምለክ ያሉ ሃይማኖታዊ ጉዳዮች የሚመለከቱ ሕግጋት አሉ። ደግሞም እስራኤላውያን የእግዚአብሔር ሕዝብ እንደመሆናቸው መጠን እርስ በርሳቸው እንዴት መኖር እንዳለባቸው የሚናገሩ ሕግጋትም አሉ። ግላዊ ስለሆኑ ነገሮች (ለምሳሌ፡- በሽታ ወዘተ) የሚናገሩ ሕግጋት ደግም አሉ። እግዚአብሔር በእነዚህ ነገሮች ሁሉ ላይ ያለውን ፍላጎትና ቁጥጥር ለማሳየት ትእዛዛትን ሰጠ።

የውይይት ጥያቄ ፥ 1ኛ ቆሮ. 10፡31 አንብብ። ሀ) ይህ ጥቅስ ይህንን እውነት የሚገልጸው እንዴት ነው? ለ) እግዚአብሔር ደስ የሚሰኝባቸውንና እኛ የምናደርጋቸውን አንዳንድ የተለመዱ ነገሮች ጥቀስ። ሐ) እነዚህን ነገሮች ለእግዚአብሔር ክብር በማያመጣ መንገድ ልንጠቀምባችው የምንችለው እንዴት ነው? መ) እነዚህን ነገሮች ለእግዚአብሔር ክብር በሚያመጣ መንገድ ልንጠቀምባቸው የምንችለውስ እንዴት ነው? 

  1. መሥዋዕቶች

በብሉይ ኪዳን፥ ሰው እግዚአብሔርን የሚቀርበውና የሚያመልከው መሥዋዕትን በማቅረብ ነበር። በአጠቃላይ አምስት ዓይነት የተለያዩ መሥዋዕተች ነበሩ። የሚቃጠል መሥዋዕት፥ የእህል ቁርባን፥ የድነት (ደኅንነት) መሥዋዕት፥ የበደል መሥዋዕትና የኃጢአት መሥዋዕት ናቸው። እነዚህ መሥዋዕቶች ሁሉ የየራሳቸው ዓላማ ያላቸው ቢሆንም የሚቀርቡበት ግን ሁለት ዋና ዋና ምክንያቶች አሉ፡

1) አንዳንድ መሥዋዕቶች ለእግዚአብሔር ምስጋናንና ክብርን ለመግለጥ የሚቀርቡ ናቸው።

2) ሌሎች መሥዋዕቶች ደግሞ ከእግዚአብሔር ዘንድ የኃጢአት ይቅርታን ለመቀበል የሚቀርቡ ናቸው። 

የውይይት ጥያቄ፥ ዘሌ. 17፡ 11ና ዕብ. 9፡22 አንብብ። የመሥዋዕት ዓላማ መሠረታዊ ግንዛቤ ምን ነበር? አብዛኛዎቹ የብሉይ ኪዳን መሥዋዕቶች የእንስሳት ደም የሚፈስባቸው ነበሩ። ስለመሥዋዕቶች ልናውቃቸው የሚገቡ በርካታ መሠረታዊና ጠቃሚ የሆኑ ነገሮች አሉ።

  1. የእንስሳው ደም የእንስሳውን ሕይወት የሚወክል ነው። ስለዚህ ብሉይ ኪዳንና አዲስ ኪዳን የእንስሳት ደም የኃጢአት ስርየትን ያስገኛል ሲሉ፥ እርቅን የሚያስገኘው በደሙ የተወከለው የእንስሳው ሞት ነው ማለት ነው። እንደዚሁም እኛ ስለ ክርስቶስ ደምና ስላለውም ኃይል ስንናገር፥ ስለ ሞተና በእርሱም ስለተገኘው ውጤት መናገራችን ነው።
  2. የመሥዋዕት መሠረት ምትክ የመሆን ሐሳብ ነው። በብሉይ ኪዳን አንድ ሰው አንድን እንስሳ ለመሥዋዕት እንዲሆን ሲያቀርብ፥ በእንስሳው ራስ ላይ እጁን ይጭናል። ይህን ሲያደርግ ጥፋተኛ ስለሆነ ሞት ይገባዋል ብሎ ማወጁ ነበር። ነገር ግን የእንስሳው ሕይወት ለኃጢአተኛው ሕይወት ምትክ ሆኖ የቀረበ ነው። በአዲስ ኪዳንም እንደዚሁ፥ የኢየሱስ ክርስቶስ ሕይወት ለኃጢአተኛው ሕይወት ምትክ ሆኗል። የኃጢአትን ዕዳ ለመክፈል እያንዳንዳችን መሞት ሲገባን፥ በእኛ ፈንታ ኢየሱስ ሞተ።
  3. የመሥዋዕቱ ውጤት ኃጢአትን ማስተሰረይ ነው። 

የውይይት ጥያቄ፡ ሀ) «ማስተስረይ» የሚለው ቃል በመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት ውስጥ ተመልከት። ቃሉ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ያለውን ሙሉ ትርጉም ጻፍ። ለ) ይህ ቃል እግዚአብሔር በኢየሱስ የክርስቶስ በኩል ስላደረገልን ነገር የሚገልጸው እንዴት ነው?

«ማስተሰርይ» የሚለው ቃል በብሉይ ኪዳን በተደጋጋሚ ያገለገለ ሲሆን፥ በግሪኩ አዲስ ኪዳን ግን አንድ ጊዜ ብቻ እናገኘዋለን (ሮሜ 5፡11)። ማስትሰረይ እግዚአብሔር ለኃጢአተኛ ሰው ይቅርታን እንዲያገኝና ከራሱ ጋር እንዲታረቅ የሠራው ሥራ ነው። በብሉይ ኪዳን የቃሉ ትርጉም «ማጥፋት»፥ «መሸፈን»፥ «ማስወገድ»፥ ወይም «መጥረግ» ማለት ነው። ኃጢአተኛው በሚያቀርበው መሥዋዕት ከእግዚአብሔር ይቅርታን ለመግዛት አይሞከርም። ይልቁንም እግዚአብሔር ለኃጢአተኛው፥ በጸጋው ከእርሱ ጋር ሊታረቅ የሚችልበትን መንገድ ሰጠው። የእርቅ መሠረታዊ አሳብ፥ በሌላ እንስሳ መሠዋት እግዚአብሔር የኃጢአተኛው ኃጢአት እንዲሸፈን ያደርግ ነበር። ልክ እንደዚሁ፥ እግዚአብሔር ጻድቃን አድርጎ ይቀበለን ዘንድ፥ የኢየሱስ ክርስቶስ ሞት ኃጢአታችንን ይሸፍናል። 

  1. መሥዋዕቱ ራሱ ኃጢአተኛውን የሚያድን ወይም ይቅርታ የሚያስገኝለት አይደለም። መሥዋዕቱ ውጫዊ ማስረጃ ሲሆን የኃጢአተኛው ውስጣዊ ዝንባሌ ማለትም ንስሐ መግባቱንም የሚያሳይ ነበር። ንስሐ ለመግባት የተዘጋጀ ልብ ከሌለና ለእግዚአብሔር ታዛዥ ለመሆን ይችል ዘንድ የሰውየው ሕይወት ካልተለወጠ፥ መሥዋዕቱ አንዳችም ዋጋ የለውም ፤(1ኛ ሳሙ. 15፡22-23፤ መዝ. (50፡16-17፤ ሚክ. 6፡6-8 ተመልከት)። 

የውይይት ጥያቄ፥ በዚህ ዘመን ለሚኖረን አምልኮ የዚህ እውነትነት እንዴት ነው? 

  1. የመሥዋዕት ዓላማዎች የሚከተሉት ነበሩ፡

ሀ. የእግዚአብሔርን ቅድስናና እርሱ ኃጢአትን እንዴት እንደሚጠላ፥ ደግሞም ሁልጊዜ ኃጢአትን በሞት እንደሚቀጣ ለማስተማር ነው። በብሉይ ኪዳን በኃጢአተኛው ምትክ እንስሳ ይገደል ነበር። በአዲስ ኪዳን ደግሞ የኃጢአት ቅጣት የተከፈለው በኢየሱስ ሞት ነው። 

ለ. የሰውን ኃጢአተኛነት ለማስተማር ነው። ሰው መሥዋዕት ባቀረበ ቁጥር ኃጢአተኛ መሆኑን ይመሰክራል፡፡ ደግሞም የኃጢአት ደመዎዝ የኃጢአተኛው ወይም የእንስሳው ሞት መሆኑንም ያሳያል፤ (ሮሜ 6፡23)። 

ሐ. ይቅርታ የሚገኘው የኃጢአተኛውን ኃጢአት ለመሸፈን በሚፈጸም የምትክ ሞት መሆኑን ለማሳየት ነው።

መ. አንድ ኃጢአተኛ፥ በእግዚአብሔር ፊት ሕይወቱን በንጽሕና የመጠበቅ ኃላፊነት እንዳለበትና ኃጢአት ከሠራም ለመንጻትና እንደገና ከእግዚአብሔር ጋር ኅብረት ለማድረግ ንስሐ መግባት እንዳለበት ለማስተማር ነው። 

ሠ. የእግዚአብሔርን ምሕረትና ጸጋ ለማሳየት ነው። እግዚአብሔር እያንዳንዱ ኃጢአተኛ በግል ስለ ኃጢአቱ እንዲሞት መጠየቅ ይችል ነበር። ነገር ግን እርሱ እንደዚያ ቢያደርግ ኖሮ ሁላችንም ኃጢአተኞች ስለሆንን ማንም ሰው በሕይወት አይቀርም ነበር፤ ነገር ግን እግዚአብሔር፥ ኃጢአተኛን ሰው ከራሱ ጋር የሚያስታርቅበትንና ይቅርታ የሚሰጥበትን መንገድ ሁልጊዜ ማዘጋጀቱ ምሕረቱንና ጸጋውን ያሳያል። ቅዱስ ስለሆነ፥ ኃጢአትን ሳይቀጣ አይተውም፤ ስለዚህ እግዚአብሔር በኃጢአተኛ ምትክ የሌላን ሰው ወይም የሌላን ነገር ሞት ጠየቀ። ነገር ግን መሐሪ ስለሆን፥ ሰው ይቅርታ በመቀበል ከእግዚአብሔር ጋር የሚታረቅበትን መንገድ አዘጋጀ። 

  1. የብሉይ ኪዳን መሥዋዕቶች እግዚአብሔር ለኃጢአተኞች የሠዋውን የእግዚአብሔር በግ የሆነውን ኢየሱስ ክርስቶስን የሚያመላክቱ ተምሳሌቶች ናቸው (ዮሐ. 1፡29-31፤ ሮሜ 5፡6-11፤ ዕብ. 10፡10-12 ተመልከት)።
  2. የብሉይ ኪዳን መሥዋዕቶች ክርስቲያኖች ዛሬ ለእግዚአብሔር የሚያቀርቡትን መሥዋዕት የሚያመላክቱ ናቸው። 

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) 1ኛ ጴጥ. 2፡5፤ ፊልጵ. 4፡18፤ ዕብ. 13፡15-18፤ ራእ. 5፡8፤ ሮሜ 15፡16-17፤ ሮሜ 12፡1፤ ፊልጵ. 2:17፤ 2ጢሞ. 4፡6 አንብብ። ክርስቲያኖች ለእግዚአብሔር ማቅረብ የሚገባቸውን መሥዋዕቶች ዘርዝር። ለ) እነዚህን መሥዋዕቶች በሕይወትህ እንዴት እየሠራህ ነው? ምሳሌዎችን ስጥ። 

  1. በብሉይ ኪዳን ሳይታሰብ ለተሠሩ ኃጢአቶች የሚቀርቡ መሥዋዕቶች ብቻ ነበሩ። አንድ ሰው ግን አውቆ በእግዚአብሔር ላይ በሚያምፅበት ጊዜ ምንም መሥዋዕት ማቅረብና ይቅርታን መቀበል አይችልም ነበር። 

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

%d bloggers like this: