የመጽሐፈ ሩት ዋና ዋና ትምህርቶች 

በመጽሐፈ ሩት ውስጥ በተደጋጋሚ የተጠቀሱ ሁለት ቁልፍ ቃላት ይገኛሉ። እነርሱም የመጽሐፉን ዋና ዋና ትምህርቶች የያዙ ናቸው።

  1. መዋጀት፡- በዚህ ታሪክ መዋጀት የሚለውን ትርጉም የሚሰጠውን የዕብራይስጥ ቃል በተለያየ መልኩ 23 ጊዜ እናገኘዋለን። በመጽሐፈ ሩት «መዋጀት» የሚለው ቃል በተለይ ያገለገለው የአይሁድን የመቤዥት ባሕል ለመግለጥ ነው። ተቤዢው ለሟች ዘመዱ ወራሽ የሆነ ልጅ ለማሳደግ፥ ወይም ለችግረኛ ዘመዱ በችግር ምክንያት የሸጠውን መሬቱን ከፍሉ ለማስመለስ፥ ወይም በባርነት ሊወድቅ ላለ ዘመዱ ዋጋ ከፍሉ ከባርነቱ ለማስቀረት ወዘተ ፈቃደኛ የሆነ ነው። ቦዔዝ ለሩትና ለኑኃሚን ተቤዢ ሆነ።

ቦዔዝ የእግዚአብሔርና የሕዝቡ የእስራኤል ግንኙነት ተምሳሌት ነበር። ቦዔዝ ኑኃሚንና ሩትን በድህነት ምክንያት ከነበረባቸው ባርነት ዋጃቸው (ተቤዣቸው)። ፍላጎታቸውን አሟላ። ልክ እግዚአብሔር እስራኤልን ከግብፅ ባርነት ነፃ እንዳደረገ ዓይነት ማለት ነው። እርሱ የእስራኤላውያንን ፍላጎት ሁሉ ያሟላ አምላክ ነው።

ቦዔዝ የክርስቶስ ኢየሱስ ተምሳሌት ነው። ኢየሱስ ክርስቶስ ሰው ሆነ፥ በመሆኑም የእኛ ዘመድ ሆነ። እንደ ዘውድነቱ በመስቀል ላይ በመሞቱ፥ እያንዳንዳችንን ከኃጢአት ባርነት ዋጀን፤ (የሐዋ. 20፡28)፤ በዚህም የተቤዢነቱን ዓላማ አሟላ። ተቤዢያችን ክርስቶስን እኛን ከባርነት፥ ከመንፈሳዊ ጉስቁልና ለመዋጀት የሚከፈለውን ዋጋ ከፈለ። በዚህም የእግዚአብሔር ቤተሰብ አባላት አደረገን።

የትኩረት ነጥብ፥ የተቤዠህን ክርስቶስን ለማመስገን ጊዜ ይኑርህ።

  1. በፍቅር የተሞላ ቸርነት፡- አይሁድ «ሂሴድ» የሚል ልዩ ቃል ነበራቸው። ይህ ቃል በብዙ ልዩ ልዩ መንገዶች ሊተረጎም ይችላል። አንዳንድ ጊዜ ለቃል ኪዳኑ ታማኝነት፥ አንዳንድ ጊዜ ርኅራኄ፥ ሌላ ጊዜ ፍቅር መሆን ይችላል።

የሩት ታሪክ እንዲህ ዓይነቱን በፍቅር የተሞላ ርኅራኄ ይገልጣል። ሩት እውነተኛ ተስፋ ባይኖርም እንኳ በፍቅር የተሞላ ርኅራኄና ቸርነት ለኑኃሚን ገለጠች። የኑኃሚንን ጉስቁልና በመካፈል በታማኝነት ለኑኃሚን የሚያስፈልገውን ነገር ሁሉ ለማድረግ ከእርሷ ላለመለየት መቁረጧን ገለጠች (2፡11-12)። ቦዔዝ ሩትን በእርሻ ስፍራው በመርዳት፥ ወራሾቹን አደጋ ላይ የሚጥል ቢሆንም እንኳ፥ እርሷን ለማግባት በመፍቀድ እንዲህ ዓይነቱን በፍቅር የተሞላ ቸርነትና ርኅራኄ ለሩትና ለኑኃሚን ገለጠ።

ከሁሉም በላይ ግን በታሪኩ ውስጥ የእግዚአብሔርን በፍቅር የተሞላ ቸርነትና ርኅራኄ እንመለከታለን (2፡20)። ከዚህ ታሪክ የምንመለከተው፥ እግዚአብሔር በእርሱ የሚታመኑትን ፍቅርን በተሞላ ቸርነትና ርኅራኄ እንደሚመለከታቸው ነው። በመጽሐፈ ሩት ውስጥ እግዚአብሔር በተለያዩ ስውር መንገዶች ለሕዝቡ ጥቅም ሲሠራ እንመለከታለን። ሩትን ወደ ቦዔዝ እርሻ መራት፤ ቦዔዝም እንዲራራላት አደረገ፤ ቦዔዝና ሩት እንዲጋቡም አደረገ። ቦዔዝ፥ ሩትንና ኑኃሚንን የታላቁ የእስራኤል ንጉሥ የዳዊት አያት በሆነ ልጅ ባረካቸው።

ምንም እንኳ የእግዚአብሔርን እጅ ሁልጊዜ በሥራ ላይ ባናየውም፥ እግዚአብሔር በማይታይ መንገድ ለእርሱ ታማኝ የሆኑ ሕዝቦችን ሁልጊዜ እንደሚረዳ እንመለከታለን። የሩት ታሪክ ሮሜ 8፡28ን ይገልጣል። «እግዚአብሔርንም ለሚወዱት እንደ አሳቡም ለተጠሩት ነገር ሁሉ ለበጎ እንዲደረግ እናውቃለን።»

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ሆነህ መከራን በምትቀበልበት ጊዜ፥ ይህ እውነት እንዴት ያጽናናሃል? ለ) ለእግዚአብሔርና ለሌሎች ባለህ ግንኙነት ታማኝ ስለመሆን አስፈላጊነት ይህ ታሪክ ምን ያስተምርሃል?

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading