የመጽሐፈ ነህምያ መግቢያ

እንደ ዕዝራ ሁሉ ነህምያም የእግዚአብሔርን ሕዝብ እንደገና ስለ ማነጽ የሚናገር ታሪክ ነው። ምናልባት ስለ መልካም የቤተ ክርስቲያን አስተዳደር በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ከሚገኙ እጅግ ግልጽ ከሆኑ ምሳሌዎች አንዱ ይህ ነው። የእግዚአብሔር ሕዝብ እርሱ የሰጣቸውን ሥራ ውጤታማ በሆነ መንገድ እንዲያከናውኑ እንዴት ማደራጀት እንደሚቻል ያሳያል።

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) እግዚአብሔር ሕዝቡ እንዲሠሯቸው የሚፈልጋቸውን ነገሮች ውጤታማ በሆነ መንገድ ለመሥራት ይቻል ዘንድ ጥሩ አደረጃጀት የሚጠይቁ ሥራዎችን ዘርዝር። ለ) በቤተ ክርስቲያን መሪዎች ዘንድ ጥሩ የሆነ አደረጃጀት ወይም አስተዳደር ባለመኖሩ በቤተ ክርስቲያንህ ውስጥ በሚገባ ያልተሠሩ ሥራዎች የትኞቹ ናቸው? 

የውይይት ጥያቄ፥ ነህምያን ከመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት ተመልከት። ስለ መጽሐፈ ነህምያ የተጠቀሱ አንዳንድ ጠቃሚ ነገሮችን ጥቀስ። 

መጽሐፍ ቅዱስን በቅደም ተከተል እያጠናህ ከሆነ ከዚህ ቀደም ብለን የመጽሐፈ ዕዝራና ነህምያ የመጀመሪያ ዘገባዎች የተጻፉት በዕዝራና በነህምያ እንደሆነ ተመልክተናል። እነዚህ ዘገባዎች ተጠናቅረውና ወደ ይሁዳ ስለተመለሱት ምርኮኞች የሚናገረው ታሪክ ታከሉባቸው ዕዝራ-ነህምያ ወደሚል አንድ መጽሐፍ ተጠቃለሉ። የዕብራይስጡ መጽሐፍ ቅዱስ ወደ ግሪክ ቋንቋ በተተረጎመበት ጊዜ ግን ይህ መጽሐፍ በሁለት ክፍል ተከፈለ።

መጽሐፈ ህምያ ስያሜውን ያገኘው የመጽሐፉ ዋና ገጸ ባሕርይ ከሆነው ከነህምያ ነው። እርሱም የይሁዳ ገዥ በመሆን የኢየሩሳሌምን ቅጥሮች እንደገና በበላይነት ይቆጣጠር ነበር። 

የነህምያ ዘመን

ነህምያ በምርኮ ዘመን በምርኮ አገር የተወለደ አይሁዳዊ ነው። እግዚአብሔር በፋርስ መንግሥት ውስጥ ከፍተኛ ሥልጣን እንዲያገኝ አደረገው። ነህምያ የንጉሡ ጠጅ አሳላፊ ነበር። ይህ ከፍተኛ የሥልጣን ስፍራ ባይመስልም፥ ጠጅ አሳላፊነት በጥንት ዘመን የንጉሡ ወዳጅ ለሆነና በከፍተኛ ደረጃ ታማኝነት ላለው ሰው የሚሰጥ ሥራ ነበር። ጠጅ አሳላፊ ታማኝ መሆን የነበረበት ሰዎች ንጉሡን የመግደል ሙከራ የሚያደርጉበት አንዱ መንገድ በሚበላው ወይም በሚጠጣው ነገር ላይ መርዝ በመጨመር ስለ ነበር ነው፤ ስለዚህ ይህ ማለት ነህምያ የፋርስ ንጉሥ የቅርብ አማካሪ ከሆኑት ሰዎች አንዱ ነበር ማለት ነው። ነህምያ በመንግሥት ዘንድ በጣም ጥሩ ሥራ ያለውና ጥሩ ኑሮን የሚኖር ቢሆንም፥ ወገኖቹንና ጨርሶ አይቷት የማያውቃትን ኢየሩሳሌምን አልረሳም። ነህምያ እግዚአብሔርን የሚወድ፥ ስለ እግዚአብሔር ክብርና ስለ ሕዝቡ በጣም የሚገደው ሰው ነበር። የኢየሩሳሌም ቅጥር ባለመሠራቱ የእግዚአብሔር ስም ተነቅፍ ስለ ነበረና ሕዝቡም ለጠላት ጥቃት ተጋልጠው ስለ ነበር ነህምያ ስለ ደኅንነታቸው ገደደውና የኢየሩሳሌምን ቅጥር በመሥራት እርሱን ይጠቀምበት ዘንድ እግዚአብሔርን ለመነ።

ነህምያ አብሮት ይሠራ የነበረው የፋርስ ንጉሥ አርጤክስስ በመባል ይታወቃል። በሥልጣን ላይ የቆየው ከ464-425 ዓ.ዓ. ነበር። አርጤክስስ በዘመነ መንግሥቱ መጀመሪያ ላይ አይሁድን ስደት እንዲደርስባቸው ያደረገ ቢሆንም፥ ለዕዝራ ግን የተለየ ርኅራኄ በማሳየት በ458 ዓ.ዓ. ዕዝራንና አንዳንድ አይሁድን ወደ አገራቸው እንዲመለሱ አድርጓል። ከ13 ዓመታት በኋላ ደግሞ ነህምያ ሌላ ቡድን እየመራ ወደ አገሩ እንዲሄድ አርጤክስስ ፈቅዶለታል። ነህምያ ወደ ኢየሩሳሌም አገሩ ከተመለሰ በኋላ ለ12 ዓመታት (444-432 ዓ.ዓ.) የይሁዳ ገዥ በመሆን አገልግሏል። ከ12 ዓመታት በኋላ ግን ወደ ፋርስ በመመለስ በአርጤክስስ መንግሥት ውስጥ እንደገና አገልግሏል። ከዚያ በኋላ በፋርስ ምን ያህል እንደቆየ ባናውቅም፥ በመጨረሻ ወደ ኢየሩሳሌም በመመለስ የይሁዳ ገዥ እንደሆነ እንመለከታለን። ለሁለተኛ ጊዜ ገዥ የሆነበት ዘመን ምን ያህል እንደሆነ አናውቅም።

ነህምያ ገዥ ሆኖ ስለሠራበት ጊዜ ብዙ የምናውቀው ነገር የለም። ከነህምያ 1-12 የሚገኘው ታሪክ በአብዛኛው የተፈጸመው ነህምያ በኢየሩሳሌም ባገለገለባቸው በመጀመሪያዎቹ ዓመታት ነው።

የነህምያ የመጀመሪያ አገልግሎት የኢየሩሳሌምን ቅጥር እንደገና መሥራት ነበር። ይህ ነገር በጣም አስፈላጊ የሆነው ለምንድን ነው? ሁለት ዋና ዋና ምክንያቶች ነበሩ፡፡ የመጀመሪያው፥ በጥንት ዘመን ሕዝቦች ድንገት ከሚመጣ የጠላት ጦርና ከሚዘርፍ ወራሪ የሚከላከሉበት ዋናው መንገድ የከተማ መከለያ ቅጥር ነበር፤ ስለዚህ በኢየሩሳሌም ከተማ ዙሪያ ቅጥር እስከሌለ ድረስ የእግዚአብሔር ሕዝብ ሰላም ሊኖራቸውና የደኅንነት ዋስትና ሊያገኙ አይችሉም ነበር። ይልቁንም በማያቋርጥ ፍርሃት መኖር ዕጣ ፈንታቸው ነበር። ልክ ቅጥሩ እንደተሠራ ሕዝቡ በመንፈሳዊ ሕይወታቸው ላይ በማተኮር የእግዚአብሔርን ቃል ለመስማትና ለመታዘዝ የነበራቸውን ፈቃደኝነት ማየት የሚያስገርም ነው።

ሁለተኛ፡- የኢየሩሳሌም ቅጥሮች የእግዚአብሔር ሕዝብ ያሉበት መንፈሳዊ ሁኔታ ምልክት ነበሩ። ቅጥሮቹ እስካልተሠሩ ድረስ እግዚአብሔር ስሙን ሊያኖርባትና ሊመለክባት ተስፋ ለሰጣት ለዚህች ከተማ በቂ ትኩረት እንደሌለ የሚያሳይ ነበር። እግዚአብሔር ሊመለክበት ባለው ስፍራ ስሙን ለማኖር ቃል ገብቶ ነበር። የእግዚአብሔር ከተማ የነበረችው የኢየሩሳሌም ውጫዊ ሁኔታ የእግዚአብሔርን ሕዝብ የልብ መንፈሳዊ አቋም የሚያንጸባርቅ ነበር።

የውይይት ጥያቄ፥ የአብያተ ክርስቲያናቶቻችን ውጫዊ ሁኔታ ብዙ ጊዜ መንፈሳዊ ሁኔታቸውን የሚያመለክተው እንዴት ነው?

የነህምያ አስተዋጽኦ

  1. የነህምያ የመጀመሪያ አስተዳደር(1-12)

ሀ. ነህምያ ስለ ኢየሩሳሌም ሰማ (1) 

ለ. ነህምያ ወደ ኢየሩሳሌም ተጓዘ (2)

ሐ. በኢየሩሳሌም ቅጥር ይሠሩ የነበሩ ሰዎች ዝርዝር (3) 

መ. የኢየሩሳሌም ቅጥር ሥራ የገጠመው ተቃውሞ (4) 

ሠ. የኢየሩሳሌም ቅጥር ሥራን ያስቆሙ ውስጣዊ ችግሮች (5) 

ረ. የቅጥሩ ሥራ ተፈጸመ (6) 

ሰ. ወደ ይሁዳ የተመለሱ ምርኮኞች ዝርዝር (7) 

ሸ. በዕዝራ አመራር ሥራ የተነሣ መንፈሣዊ መነቃቃት (ተሐድሶ)(8-10) 

ቀ. በኢየሩሳሌም የሚኖሩ ሰዎች ተመረጡ (11) 

በ. የካህናት ዝርዝርና የቅጥሩ መመረቅ (12) 

  1. የነህምያ ሁለተኛ አስተዳደር፥ መንፈሳዊ ተሐድሶ (13) 

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading