ኢሳይያስ 7-12

ብዙውን ጊዜ አንድ ክርስቲያን ችግር ሲያጋጥመው የሚወስደው የመጀመሪያ እርምጃ ከሌላ ክርስቲያን ወይም ከጎረቤት ወይም ከወዳጅ እርዳታ መፈለግ ነው፤ ወይም ደግሞ መንግሥት ነገሮችን እንዲያቃናለት ወይም እንዲያስተካክልለት ወደ መንግሥት ፊቱን ያዞራል።

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ችግር ኣጋጥሞህ የነበረበትን ጊዜ ዘርዝር። እርዳታ ፍለጋ የሄድከው ወደ ማን ነበር? ለ) ቤተ ክርስቲያንህ ችግር አጋጥሟት የነበረበትን ጊዜ ዘርዝር። እርዳታ ፍለጋ የሄደችው ወደ ማን ነበር?

ብዙ ክርስቲያኖች ችግር በሚገጥማቸው ጊዜ ወዲያውኑ እርዳታ ፍለጋ ወደ ሌሎች ክርስቲያኖች ወይም ወደ ዘመዶቻቸው ይሄዳሉ። እነርሱ ወይም ቤተ ክርስቲያናቸው ወደ ሕግ ነክ ችግሮች ውስጥ ከገቡ ደግሞ መንግሥት (ፍርድ ቤት) ለእነርሱ እንደሚፈርድላቸው በማሰብ ወደሚመለከተው ክፍል ይሄዳሉ። በዚህ ተፈጥሮአዊ እንቅስቃሴ ውስጥ አንዳችም ስሕተት ባይኖርም እንኳ አደገኛ የሆነ መንፈሳዊ ችግርን የሚያስነሣ ጉዳይ ሊሆን ይችላል። እኛ ወይም ቤተ ክርስቲያናችን ችግር በሚገጥመን ጊዜ ወደ እግዚአብሔር መመለስ አለብን። በችግራችን ጊዜ መጠጊያችንና ረድኤታችን እርሱ ብቻ ሊሆን ይገባል። ረድኤት የምንፈልገው ሁልጊዜ ከሰዎች ከሆነ በእግዚአብሔር ላይ ባለን እምነት ማደግን አንማርም፤ እግዚአብሔር ስለ እኛ ሆኖ ይሠራ ዘንድም አልፈቀድንለትም ማለት ነው።

ኢሳይያስ ከምዕራፍ 7-12 የተጻፈው የይሁዳ ሕዝብና ንጉሥ አካዝ በችግር ውስጥ በነበሩ ጊዜ ነው። የሶርያ ንጉሥ የነበረው ረአሶን የእስራኤል ንጉሥ ከነበረው ፋቁሔ ጋር በመተባበር የይሁዳን ሕዝብ ለመውጋት ዐቀዱ። ንጉሥ አካዝ ምርጫ ነበረው፤ ይኸውም፡- በነቢዩ ኢሳይያስ በኩል የመጣለትን የእግዚአብሔርን ቃል በማመንና በእግዚአብሔር በመታመን ጠላቶቹን ማሸነፍና ዕቅዳቸውን ማክሸፍ ወይም ደግሞ እንደ አሦራውያን ወዳሉ ሌሎች መንግሥታት ዕርዳታ ፍለጋ መሄድ። ብዙዎቻችን ዛሬ እንደምናደርገው፥ በዚህ የችግር ጊዜ አካዝ በእግዚአብሔር ላይ ብቻ መታመን አቃተው፤ ነገር ግን ወደ አሦራውያን ሄዶ ጠላቶቹን በመውጋት እንዲረዱት ጠየቀ። ከጥቂት ጊዜ በኋላ አሦራውያን የእርሱን መንግሥትና ሕዝብ ሙሉ በሙሉ እንደሚያጠፉ አልተገነዘበም ነበር። አካዝ በእግዚአብሔር መታመን ስላልቻለ በሕዝቡ ላይ ከፍ ያለ ችግር አመጣ።

የውይይት ጥያቄ፥ አንተ ወይም ሌላ የምታውቀው ሰው ወይም ቤተ ክርስቲያን በችግር ጊዜ ዕርዳታ ወይም መፍትሔ ፍለጋ ወደ አንድ ስፍራ ሄዳችሁ፥ አስቀድሞ ከነበረው ችግር የላቀ ከባድ ችግር ይዛችሁ የተመለሳችሁበትን ሁኔታ በምሳሌነት ጥቀስ። 

የውይይት ጥያቄ፥ ኢሳይያስ 7-12 አንብብ። ሀ) የኢሳይያስ ልጆች ስሞችን ከነትርጕማቸው ተናገር። ለ) እግዚአብሔር ለንጉሥ አካዝ የሰጠው ምልክት ምን ነበር? ሐ) እግዚአብሔር ለእስራኤልስ ሕዝብ (ኤፍሬም) የሰጠው ተስፋ ምን ነበር? መ) የአሦር ሕዝብ ምን ያደርግ ነበር? ሀ) ንጉሥ ይሆን ዘንድ ላለው ሕፃን የተሰጡትን የተለያዩ ስሞች ዝርዝር (ኢሳይያስ 9፡6-7)። ረ) ከዳዊት ዘር ስለሚመጣው ቅርንጫፍ ወይም ቍጥቋጥ የተሰጡትን ተስፋዎች ዘርዝር (ኢሳይያስ 11)።

ኢሳይያይስ 7-12 የተጻፈው የይሁዳ ሕዝብ በብሔራዊ ችግር ውስጥ ሳለ ነበር። የይሁዳ ሕዝብ በሶርያ (አራም) እና በእስራኤል (ኤፍሬም) ሊደመሰስ የተቃረበበት ጊዜ ነበር። እግዚአብሔር ለኢሳይያስና ለይሁዳ ሕዝብ ስለ መሢሑ መምጣት የሚናገሩ በርካታ አስደናቂ ትንቢቶችን የሰጣቸው በዚህ ጊዜ ነበር።

በኢሳይያስ ምዕራፍ 7፥ እግዚአብሔር ኢሳይያስን ወደ አካዝ እንዲሄድና ብሔራዊ ሰቆቃ ባለበት በዚህ ጊዜ ውስጥ በጌታ ይታመን ዘንድ እንዲያበረታታው ነገረው። ኢሳይያስ የስሙ ትርጒም «ቅራታዎቹ ይመለሳሉ» የሚለውን ልጁን ሸር-ያሹብን አስከትሎ ወደ ንጉሡ ዘንድ ሄደ። ይህ የኢሳይያስ ልጅ ይህንን ስያሜ ያገኘው የይሁዳ ሕዝብ እንደሚጠፉ፥ ነገር ግን እግዚአብሔር አንድ ቀን ወደ ይሁዳ ምድር የሚመልሳቸው ቅሬታዎች እንደሚኖሩ የሚያመለክተውን የኢሳይያስን መልእክት ለማንጸባረቅ ነበር። እግዚአብሔር ለአካዝ የእስራኤልን (የኤፍሬምን) ጦር እንዳይፈራ ነገረው። (የእስራኤል ጦር ኤፍሪም በመባል የሚጠራው በእስራኤል ውስጥ ያለው ዋናው ነገድ የኤፍሪም ነገድ በመሆኑ ነው)። ይልቁንም የሶርያም ሆነ የእስራኤል መንግሥታት በ65 ዓመታት ውስጥ ሊደመሰሱ ነበር። ይህ ትንቢት የሶርያና የእስራኤል መንግሥታት በአሦራውያን ሙሉ በሙሉ በተደመሰሱባቸው በ732ና በ722 ዓ.ዓ. ተፈጽሟል።

እግዚአብሔር ይህ ትንቢት እንደሚፈጸም ለአካዝ ለማረጋገጥ ሲል እውነትነቱን የሚያሳይ ምልክት እንዲጠይቅ ፈቀደለት። ምልክት ብዙ ጊዜ ወደ ፊት የሚፈጸም ትንቢትን እርግጠኛነት ለማሳየት በቅርቡ የሚፈጸም ድርጊት ነው። አካዝ በአሦራውያን እንጂ በእግዚአብሔር መታመን ስላልፈለገ ምልክት ለመጠየቅ ሳይፈቅድ ቀረ፤ እግዚአብሔር ግን ለአካዝ ምልክትን ሰጠው። ምልክቱም አንዲት ድንግል አማኑኤል ተብሎ የሚሰየም ልጅ እንደምትወልድ ነበር።

ስለዚህ ምልክት ምሁራን የተለያየ አሳብ አላቸው። ከአዲስ ኪዳን በግልጥ እንደምንረዳው ይህ ትንቢት ልዩ በሆነ መንገድ በጌታ በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል ተፈጽሞአል። ይህም የሆነው ድንግል ማርያም አምላክ የሆነውን ልጅ በመውለዷ ነው (ማቴዎስ 1፡23)። ነገር ግን ትንቢተ የሚፈጸመው ወደፊት ስለነበረ ምልክቱ አካዝን የሚያበረታታ አልነበረም። ስለሆነም የዚህ ትንቢት አፈጻጸም በሁለት በኩል ሳይሆን አይቀርም። የመጀመሪያው፥ የተፈጸመው በኢሳይያስና በአካዝ ዘመነ መንግሥት ነው። የኢሳይያስ የመጀመሪያ ሚስት የሆነችው የሸአር-ያሹብ እናት ስለሞተች፥ ኢሳይያስ ሌላ ሴት የሚያገባበት ጊዜ ሳይሆን አይቀርም። ስለሆነም ድንግል የሆነች ሴት በማግባትና የምትወልደው ልጅ «አማኑኤል» የሚል ስም እንዲሰጠው በማድረግ እግዚአብሔር ከእነርሱ ጋር ስለነበር የይሁዳ ሕዝብ ሙሉ በሙሉ እንደማይጠፋ አመልክቷል። ልጁ ባደገ ጊዜ አሦራውያን ሶርያንና እስራኤልን ስላሸነፉ የሁለቱ አገሮች ዛቻ አክትሞ ነበር። ምሁራን፥ ይህ አማኑኤል የሚለው ስም «ምርኮ ፈጠነ ብዝበዛ ቸኮላ» የሚል ትርጓሜ የነበረው የኢሳይያስ ሁለተኛ ልጅ ሌላ ስም ስለመሆኑ ይሁን ወይም የሌላ ልጅ ስም የተለያየ አመለካከት አላቸው።

ኢሳይያስ ስለሚመጣው ስለ አሦር መንግሥት ተነበየ። የአሦር መንግሥት ከሶርያና ከእስራኤል ጥቃት የይሁዳን መንግሥት ለጊዜው ማሳረፍ ብቻ ሳይሆን፥ በመጨረሻ በይሁዳ ሕዝብና በዳዊት ቤት ላይ ከፍተኛ ጥፋት እንደሚያመጣ ኢሳይያስ ተንብዮ ነበር።

ኢሳይያስ ምዕራፍ 8 ወደፊት በይሁዳና በአሦር መካከል ስለሚደረገው ጦርነት መተንበዩን ይቀጥላል። አሦር የቅጣት መሣሪያ ትሆን ዘንድ በተለይ በእግዚአብሔር የተመረጠች መሆኑን ኢሳይያስ ተናግሮ ነበር። እርሷ «የእግዚአብሔር በትር» ሆና ነበር። ይህ እንደሚፈጸም ምልክት ይሆን ዘንድ ኢሳይያስ የስሙ ትርጕም «ምርኮ ፈጠነ ብዝበዛ ቸኮለ» የተባለ ሌላ ልጅ ወለደ። ይህ ልጅ፥ ይሁዳ በኃጢአት ምክንያት በአሦር መንግሥት የምትማረክና የምትበዘበዝ መሆንዋን የሚያመለክት ትንቢት ነበር። ይህ ትንቢት በሕዝቡ ዘንድ ባይወደድም፥ ሰውን ሳይሆን እርሱን እንዲፈራው እግዚአብሔር ኢሳይያስን አስጠንቅቆት ነበር (ኢሳይያስ 8፡12-13)። እጅግ አስጨናቂ በሆኑ ጊዜያት እንኳ ኢሳይያስ በእግዚአብሔር ለመታመንና ሕጉንና ምስክርነቱን ለመስማት ወሰነ (ኢሳይያስ 8፡17፥ 20)።

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) አካዝ በእግዚአብሔር ሳይሆን፥ በአሦር ለመታመን ሲወስን ምን ነገር ተፈጸመ? ለ) ከሰው ይልቅ እግዚአብሔርን መፍራት እንዳለበት እግዚአብሔር ለኢሳይያስ የሰጠው ማስጠንቀቂያ ለቤተ ክርስቲያን መሪዎች እጅግ ጠቃሚ ምክር የሚሆነው እንዴት ነው? ሐ) አንድ የቤተ ክርስቲያን መሪ ከእግዚአብሔር ይልቅ ሰውን ሊፈራ የሚችልባቸውን መንገዶች ዘርዝር።

በኢሳይያስ 9-10 ስለ መሢሑ የተነገሩ ትንቢቶችን ቀጥለን እናያለን። የንፍታሌም ነገድና የገሊላ ምድር እንደሚከበሩ ኢሳይያስ ይተነብያል። የንፍታሌም ነገድና የገሊላ ምድር የሚገኙት በእስራኤል ሰሜናዊ ክፍል ሲሆን፥ ብዙ ጊዜ አሕዛብ ይወሩት ነበር። ብዙ ጊዜ በአሕዛብ ቍጥጥር ሥር የሚቆይ ምድር ነበር። ኢሳይያስ ይህን ትንቢት በሚናገርበት ጊዜ፥ ይህ ክፍል የአሦር ሕዝብ ግዛት እንደሆነ ተደርጎ ይቆጠር ነበር። እግዚአብሔር ግን አንድ ቀን በገሊላ ልዩ የሆነ ብርሃን እንደሚበራ ተናገረ። ይህም ብርሃን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው (ማቴዎስ 4፡15-16)። በይሁዳ ሕዝብ ዘንድ ገዥ የሚሆን ልዩ ልጅ እንደሚወለድ ተነገረ። መሢሕ ለሆነው ለጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ የተሰጡትን ስሞች ተመልከት፡-

1. ድንቅ መካር፡- እነዚህ ሁለት ጣምራ ቃላት መሢሑ በንግሥናው ሕዝቦች የሚደነቁበትን ልዩ ተግባር እንደሚፈጽም የሚያሳዩ ናቸው።

2. ኃያል አምላክ፡- ይህ ሕፃን አምላክ ነው፤ ነገር ግን ጠላቶቹን ደምስሶ ለመግዛት የሚችል ኃያልም ነው። 

3. የዘላለም አባት፡- ገዝተው እንደሚሞቱ በጥንት ዘመን እንደነበሩ ነገሥታት ሳይሆን፥ መሢሑና መንግሥቱ ለዘላለም የሚኖሩ ናቸው። እንደ አባት የሕዝቡ ጠባቂና ተንከባካቢ ነው።

4. የሰላም አለቃ፡- በዚያን ጊዜ የይሁዳ ሕዝብ ይኖሩበት እንደነበረው መሢሑ በጦርነት ጊዜ ከመግዛት ይልቅ በምድር ላይ በግለሰቦች ሕይወት፥ በኅብረተሰብ፥ እንዲሁም በሀገሪቱም ሁሉ ዘንድ ሰላምን ስለሚያመጣ ግዛቱ የሰላም ይሆናል።

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ዛሬ በተለያዩ ችግሮች ውስጥ በምንሆንበት ጊዜ እነዚህ የኢየሱስ ስሞች የሚያበረታቱን እንዴት ነው? ለ) የኢየሱስን ባሕርይ የሚወክሉት እነዚህ ስሞች በችግር ውስጥ በምንሆንበት ጊዜ በእርሱ ብቻ እንድንታመን የሚያበረታቱን እንዴት ነው?

የመሢሑ መንግሥት የሚከተሉት ባሕርያት ይኖሩታል፡-

1. ዘላለማዊ ነው።

2. በዳዊት ዙፋን ላይ ይቀመጣል። 

3. መንግሥቱ የፍትሕና የጽድቅ መንግሥት ይሆናል።

የኢሳይያስ ምዕራፍ 9 የመጨረሻ ግማሽና የምዕራፍ 10 የመጀመሪያ ክፍል በይሁዳ ላይ በቅርብ ጊዜ ስለ ሚፈጸመው ጉዳይ በመመለስ፥ በእግዚአብሔርና በገቡት ቃል ኪዳን ላይ በማመፃቸው ስለሚመጣው ፍርድ ይናገራል።

ዳሩ ግን በኢሳይያስ ምዕራፍ 10 መጨረሻ እግዚአብሔር በአሦር ላይ ስለሚመጣው ቅጣትና ፍርድ አስቀድሞ ይናገራል። አሦር፥ ልዑል አምላክ ሕዝቡን ለመቅጣት የተጠቀመባት መሣሪያው ብትሆንም ስለ ጭካኔዋና ትዕቢትዋ በተራዋ እግዚአብሔር ይቀጣታል። ይህ ትንቢት የተፈጸመው ባቢሎን አሦርን በደመሰሰችበት ወቅት ነው፤ ነገር ግን በይሁዳ ቅሬታዎች ይኖራሉ።

ኢሳይያስ ምዕራፍ 11 ስለሚመጣው መሢሕ ወደ መተንበይ ይመለሳል። ይህ ትንቢት በእግዚአብሔር ታላቅነት ላይ ከማተኮር ይልቅ በንጉሥንት ባሕርዩ ላይ ወደማተኮር ያዘነብላል። ይህ መሢሕ ከእሴይ ግንድ የወጣ በትር ወይም ቍጥቋጥ ተብሏል። ይህም መሢሑ በእግዚአብሔር ፍርድ ምክንያት ሊጠፋ ምንም ያህል ካልቀረው ከዳዊት ዘር እንዴት እንደሚመጣ የሚያሳይ ነው። (ለምሳሌ፡- የባሕር ዛፍ ከተቆረጠ በኋላ እንደገና እንደሚያቈጠቍጥ ዓይነት ነው።) 

1. መንፈስ ቅዱስ በእርሱ ላይ ይሆናል። ያም መንፈስ፡-

ሀ) ለመሢሑ በአመራሩ ጥበብንና ማስተዋልን፥ ምክርንና ኃይልን፥ እንዲሁም እውቀትን ይሰጠዋል። 

ለ) እግዚአብሔርን በመፍራት እንዲመላለስ መሢሑን ይረዳዋል። 

2. በእኩልነት፥ በጽድቅና በፍርድ ይበይናል። 

3. ክፉዎችን (በብረት በትር) በኃይል ይቀጣል። 

4. የፍጥረተ ዓለምን ተፈጥሮአዊ ሥርዓት በመለወጥ፥ የእንስሳት ዓለም እንኳ በዔደን ገነት ጊዜ እንደነበረው ዓይነት እንዲሆን ያደርጋል። እንስሳት እርስ በርሳቸው ኣይገዳደሉም፤ እባብም አያስፈራም።

5. ምድር ሁሉ እግዚአብሔርን ታውቃለች፤ ታከብረውማለች።

የአይሁድ ነባር ጠላቶች የሆኑ አሦራውያን፥ ግብፃውያን፥ ኢትዮጵያውያን፥ ባቢሎናውያን፥ እንዲሁም ታዋቂ ጠላቶችና እስከ

ምድር ዳር ድረስ ያሉ ሕዝቦች ሁሉ ሳይቀሩ መሢሑን ያከብራሉ።

6. የእግዚአብሔር ምርጥ ሕዝብ የሆኑት አይሁድ ከተበተኑበት ስፍራ ሁሉ ወደ እስራኤል ይሰበሰባሉ።

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ስለ መሢሑና ስለ መንግሥቱ የተሰጡ እነዚህ የተስፋ ቃሎች በዘመናት ሁሉ የሚኖሩትን ሰዎች ፍላጎት የሚያሟሉት እንዴት ነው? ለ) ክርስቲያኖች በመከራ ውስጥ በሚሆኑበት ጊዜ ተስፋ የሚሆናቸው እንዴት ነው?

ኢሳይያስ ምዕራፍ 12 እግዚአብሔር በመሢሑ በኩል ሊሰጥ ስለገባው የበረከት ቃል ኪዳን የተሰጠ የምስጋና መዝሙር ነው። ኢሳይያስ የኖረበት ዘመን አሦራውያን ባመጡት ጥፋት ምክንያት የቱንም ያህል የጨለመ ቢሆን፥ አንድ ቀን እግዚአብሔር ፍጹም ጽድቅና ትክክለኛ ፍርድ የሞላበት ታላቅ የሆነ ዘላለማዊ መንግሥት በምድር ላይ እንደሚያመጣ በማወቁ ደስ ሊሰኝና ሐሴት ሊያደርግ ቻለ።

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) በእግዚአብሔር ፊት ስለሚኖረን የመንግሥተ ሰማያትና የዘላለም ሕይወት በረከት የተሰጠውን ተስፋ ማወቅ በችግር ጊዜ ውስጥ እንዴት ያበረታታናል? ለ) በክርስቶስ ኢየሱስ በኩል ወደፊት ስለሚያመጣው መንግሥት አሁን ለትንሽ ጊዜ እግዚአብሔርን በምስጋና ስገድለት።

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading