የትንቢተ ዘካርያስ ታሪካዊ ሥረ-መሠረት

አይሁድ በ539 ዓ.ዓ. ከምርኮ በተመለሱ ጊዜ ከፍተኛ መነቃቃትና ደስታ ተሰማቸው። ከሰባ ዓመታት በኋላ ከምርኮ እንደሚመለሱ እግዚአብሔር ለኤርምያስ የሰጣቸው ትንቢቶች እየተፈጸሙ ነበር። እግዚአብሔር በኢሳይያስ፥ በኤርምያስና በሕዝቅኤል የሰጣቸው ሌሎች ትንቢቶችም በቶሎ እንደሚፈጸሙ ያምኑ ነበር (ለምሳሌ፡- ኤርምያስ 30-33፤ ሕዝቅኤል 36-39)። እነዚህ ትንቢተች አይሁድ ወደገዛ ምድራቸው እንደሚመለሱ፥ መሢሑ እንደሚመጣ፥ በአሕዛብ አገዛዝ ሥር መኖራቸው እንደሚያከትም፥ ታላቁ ቤተ መቅደስ እንደገና እንደሚሠራ፥ የእግዚአብሔር መንግሥት እንደሚጀምርና ስራቸው እንደሚያበቃ የሚናገሩ ነበሩ። ስለዚህ በታላቅ ደስታ የሚመጣውን በረከት በሚጠባበቅ ልብ ወደ ኢየሩሳሌም ተመልሰው፥ እግዚአብሔርን ለማምለክ መሠዊያ ከማቆማቸውም የቤተ መቅደሱን ሥራ ጀመሩ።

ነገር ግን እነዚህ ተስፋዎች አለመፈጸማቸውን ለማወቅ ብዙ ጊዜ አልወሰደባቸውም። የቤተ መቅደሱን ሥራ እንደጀመሩ በተለይ ከሳምራውያን በኩል ተቃውሞ ገጠማቸው። ሳምራውያን ከፊል አይሁዳውያን ከፊል አሕዛብ የሆኑ በጥንታዊቷ የእስራኤል ምድር ይኖሩ የነበሩ ናቸው። አይሁድ የቤተ መቅደሱን ሥራ ወዲያውኑ ለማቆም ተገደዱ። ይህም አይሁድ ከአሕዛብ ተጽዕኖ ነጻ እንዳልሆኑና አገራቸው ከቁጥር የማትገባ የፋርስ ንጉሠ ነገሥት ግዛት ክፍለ ሀገር እንደነበረች አረጋገጠላቸው።

አይሁድ በየስፍራው የሚመለከቱት ከ50 ዓመታት በፊት ባቢሎን ኢየሩሳሌምን በደመሰሰች ጊዜ የተረፉትን ፍርስራሾች ነበር። የቤተ መቅደሱ፥ የኢየሩሳሌም ቅጥርና በውስጧ የሚገኙ ቤቶች ፍርስራሽ በአካባቢው ነበር። አይሁድ የቤተ መቅደሱን ሥራ ለማቆም ስለተገደሉ የየራሳቸውን ቤቶች መሥራት ጀመሩ። የእግዚአብሔርን ነገሮች ረስተው፥ ለራሳቸው ፍላጎት ብቻ የሚጠነቀቁ ራስ ወዳዶች ሆኑ። ወዲያውኑ ሁሉን ነገር የሚያጥላሉ ሆኑና እግዚአብሔር የሰጠውን ተስፋ ይፈጽም ይሆንን? የሚል ጥያቄ አቀረቡ። ሌሎች ደግሞ ተስፋ መቁረጥ ጀመሩ። ደግሞም የተመለሱት አይሁድ ቁጥር ጥቂት ስለነበረ ብዙ ሕዝብ አልነበረም፡፡ ድርቅና ራብ አከታትሉ ያጠቃቸው ነበር። የእግዚአብሔር ተስፋዎች የታሉ? እግዚአብሔር በተስፋዪቱ ምድር እንደሚባርካቸው አምነው መመለሳቸው ስሕተት ነበርን? በዚህ ሁኔታ ዓመታት እየተቀጠሩ ሲሄዱ ሕዝቡ የበለጠ ተስፋ እየቆረጡና ለመንፈሳዊ ነገሮች ያላቸው ፍላጎት እየቀነሰ ይሄድ ነበር።

በመካከሉ እግዚአብሔር ሁለት ነቢያትን ጠራ፡፡ በመጀመሪያ ሐጌ እግዚአብሔር ሕዝቡን ያልባረከው በራስ ወዳድነት ተይዘው የየራሳቸውን ፍላጎት ብቻ ለማሟላት ይጥሩ ስለነበር እንደሆነ ነገራቸው። ንስሐ በመግባትና ቤተ መቅደሱን በመሥራት ለእግዚአብሔር መታዘዝ ነበረባቸው። ሁለተኛ፥ ከሁለት ወራት በኋላ እግዚአብሔር ዘካርያስ የተባለ ሌላ ነቢይ ጠራ። አይሁድ ቤተ መቅደሱን መሥራት ከጀመሩ አምስት ወር አልፏቸው ነበር። በዚያኑ ወቅት ተንትናይ የተባለና ሌሎች የፋርስ ባለ ሥልጣናት አይሁድ ቤተ መቅደሱን በመሥራታቸው በፋርስ መንግሥት ላይ በእርግጥ ዓምፀው እንደሆነ ለመመርመር መጡ። እነርሱም የመሪዎችን ስም ጻፉና ወደ ዳርዮስ ደብዳቤ ላኩ። አይሁድ የግንባታውን ሥራ የቀጠሉ ቢሆንም ሥራውን መቀጠል የሚችሉት እስከመቼ እንደሆነ በማሰብ ሳይደነቁ አልቀሩም። ከዚህ ቀደም እንደሆነው ጠላታችን ያስቆሙን ይሆን? ብለው መሥጋታቸው አልቀረም። ስለዚህ ተስፋ መቁረጥ ጀመሩ። እግዚአብሔር ዘካርያስን የጠራው እዚህን ተስፋ የቆረጡ ሕዝብ እንዲያገለግል ነበር። አገልግሎቱ የሕዝቡን መንፈሳዊ ሕይወት እንደገና ማደስ ነበር። ዘካርያስ እግዚአብሔር ከእነርሱ ጋር የገባውን ቃል ኪዳን በማፍረሳቸው ተጠያቂዎች እንደሆኑ በመንገር ሕዝቡን ያስጠነቅቃቸዋል። ሕዝቡ ንስሐ እንዲገቡና ወደ እግዚአብሔር እንዲመለሱ ይነግራቸዋል። እግዚአብሔር የሚባርካቸው ይህ ሲሆን ብቻ ነበር። እግዚአብሔር ከእነርሱና ከመሪዎቻቸው ከዘሩባቤልና ከኢያሱ ጋር እንደሆነ የሰጣቸውም ተስፋ እንደሚፈጸም በመናገር ሕዝቡን ያበረታታል። የቤተ መቅደሱ ሥራ ይጠናቀቃል፤ እግዚአብሔር ሕዝቡን ይጠብቃል፡፡ በመሲሁም መምጣት የእግዚአብሔር ተስፋዎች ይፈጸማሉ፡፡

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) በዚያን ዘመን አይሁድ የነበራቸው ዝንባሌ ዛሬ ብዙ ክርስቲያኖች ካላቸው ዝንባሌ ጋር የሚመሳሰለው እንዴት ነው? ለ) በዘካርያስ ዘመን የእግዚአብሔርን በረከት ለማግኘት የሚያስችሉት ቅድመ-ሁኔታዎች ከዛሬዎቹ ጋር አንድ ዓይነት የሚሆኑት በምን መንገድ ነው? ሐ) እግዚአብሔር ወደፊት ስለሚያደርገው ነገር እኛም እንደ ዘካርያስ በመናገር ክርስቲያኖችን እንዴት ማበረታታት እንችላለን?

ዘካርያስ አገልግሎቱን ለብዙ ዓመታት ቀጥሉ ነበር። ዘካርያስ የአይሁድ ሕዝብ መንፈሳዊ ተሐድሶ በተካሄደና ቤተ መቅደሱ እንደገና በተሠራ ጊዜ ታላቅ ድርሻ እንዳበረከተ ከመጽሐፈ ዕዝራ እናነባለን (ዕዝራ 5፡2)። የቤተ መቅደሱ ሥራ በ516 ዓ.ዓ. ሊጠናቀቅ ዘካርያስ ምስክር እንደነበር አንጠራጠርም። አገልግሎቱን በሚጀምርበት ጊዜ ወጣት የነበረ ይመስላል (ዘካርያስ 2፡4)። ስለዚህ አስቴርን እስካገባው ንጉሥ እስከ ቀዳማዊ አርጤክስስ ዘመነ መንግሥት ድረስ ሳይኖር አልቀረም (465-424 ዓ.ዓ.)።

የውይይት ጥያቄ፥ ስለ ዘካርያስ ከመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት አንብብ። በመዝገበ ቃላት ውስጥ የምታገኛቸውን ጠቃሚ ትምህርቶች ዘርዝር፡

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

የመመዘኛ ጥያቄዎችን ለማግኘት ከታች ያለውን ሊንክ (መስፈንጠሪያ) ይጫኑ፡፡

https://forms.gle/qSVht1qeJ8bbCe3D9

Leave a Reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading