ከጥንት መምህራን አንዳንዶቹ የሳባሊዮስን የሐሰት አስተምህሮ ቢቃወሙም ራሳቸው ወደ ባሰ ስሕተት መውደቃቸው አልቀረም። እነርሱም ያቀርቡት የነበረው ክርክር እዚአብሔር አንድ ከሆነ፥ ወልድ እብን ካልሆነ፥ እንግዲያውስ ወልድ ከአብ ያንሳል፥ ወልድ የእግዚአብሔር አምሳያ ነው የሚል ነበር። አርዮስ የተባለ አንድ መምህር በዚህ ትምህርቱ ታዋቂ ሆኖ ነበር። ይህ ሰው ሲያስተምር አብ ከወልድ በፊት ነበር፥ አብ ወልድን ፈጥሮታል፥ በተጨማሪም ወልድ በሕልውና ያልነበረበት ጊዜ ነበር ይላል። እንደዚሁም እርሱ እንደሚያምነው ወልድ እግዚአብሔር ከፈጠራቸው ፍጥረታት የመጀመሪያውና ዋናው ነው። ቀጥሎም አብ ወልድን ካፈጠረ በኋላ በእርሱ አማካይነት ሌሎችን ፍጥረታት ሁሉ ፈጥሮአል ብሎ ያስተምር ነበር። አርዮስና ተከታዮቹ በቆላስይስ 1፡5 ላይ፥ «እርሱ የፍጥረት ሁሉ በኩር ነው» የሚለውን ጥቅስ በራሳቸው መንገድ በመተርጎም ወልድ መጀመሪያ አለው፥ ስለዚህም በአብ ተፈጥሮአል ብለው ሊያስተምሩ ችለዋል። እንደዚሁም ኢየሱስ በዮሐንስ 14፡28 ላይ፥ «አብ ከእኔ ይበልጣል» ያለውን ሐረግ በመምዘዝ፥ ኢየሱስ ከእግዚአብሔር አብ የሚያንስ መሆኑን ራሱ ተናግሯል ሲሉ ይከራከራሉ።
ጥያቄ፡- ሀ) አርዮስ ስለ እግዚአብሔር ልጅ ምን ሊል አስተማረ? ቢያንስ ሦስት ነጥቦችን ጻፉ። ) አርዮስ ትምህርቱን የሚደግፉ የትኛችን ጥቅሶች ተጠቀመ?
ጥያቄ፡- ዮሐንስ 14፡28 አንብቡ። ይህ ጥቅስ ስለ አብና ወልድ ምንን የሚያስተምር ይመስላችኋል?
አርዮስ በትምህርቱ ወልድ የእግዚአብሔር ኣምሳያ እንጂ ራሱ ኣብ አልነበረም ሲል አስተምሮአል። እንደዚሁም ወልድ በህልውና ያልነበረበት ጊዜ ነበር፥ የተፈጠረውም በአብ ሲሆን የፍጥረታት ሁሉ በኩር ነው። ፍጥረታት ሁሉ በእርሱ አማካይነት ተፈጥረዋል ብሎ አስተምሯል። ለዚህም አርዮስ አሳቤን ይደግፉኛል ብሎ የጠቀሰው ቆላስይስ 1፡15 እና ዮሐንስ 14፡28 ናቸው።
ዮሐንስ 14፡28 በእርግጥ የሚያስተምረው ለምንድን ነው? በዮሐንስ 14 ውስጥ ጌታ ኢየሱስ ደቀ መዛሙርቱን ትቶአቸው የሚሄድ በመሆኑ ያጽናናቸዋል። አብ ወዳለበት ወደ ሰማይ ቤቱ እንደሚመለስ ነግሮአቸው ነበር። የእርሱ መኖሪያ ወደሆነውና ወደ ምድር ከመምጣቱ በፊት ወደነበረው ክብር፥ እንዲሁም አብ ወዳለበት የክብር ስፍራ ይመለሳል። ስለዚህ ኢየሱስ የአብን ክብር ወልድ በምድር ላይ በነበረበት ጊዜ ከነበረው ክብር ጋር ያመዛዝናል። እርሱ በምድር ላይ በነበረበት ጊዜ የአብ ክብር፥ ከእርሱ ክብር በጣም የላቀ ነበር። ስለዚህ እዚህ ላይ ኢየሱስ «አብ ከእኔ ይበልጣል» ሲል፥ እኔ እግዚአብሔር አይደለሁም ማለቱ አይደለም። መግለጽ የፈለገው እርሱ በምድር ላይ በነበረበት ጊዜ አብ የነበረውን ክብር ነው።
እንደዚሁም በትምህርት አንድ ውስጥ በቆላስይስ 1፡5 እንደተመለከትነው ኢየሱስ የመጀመሪያው ፍጡር አይደለም። «እርሱ የፍጥረት ሁሉ በኩር ነው» የሚለው ኢየሱስ በጊዜ የመጀመሪያው ነው ማለት ሳይሆን ከፍጥረታት ሁሉ በላይ ነው ለማለት ነው። እንደዚሁም ቆላስይስ ምዕራፍ 1 ኢየሱስ በእግዚአብሔር ባሕርይ የተሞላ የፍጥረታት ሁሉ ፈጣሪና የእግዚአብሔርም መገለፃ ነው በማለት ያስተምራል። በተጨማሪም ቆላስይስ ምዕራፍ 1 ኢየሱስ ራሱ እግዚአብሔር እንጂ የእግዚአብሔር አምሳል ብቻ አለመሆኑን ያረጋግጣል።
ጥያቄ፡- ሀ) በዛሬይቱ ኢትዮጵያ የአርዮስን የተሳሳተ ትምህርት የሚከተሉ ምን ቡድኖች አሉ? ስለ እነዚህ ሰዎች የምታውቁትን ጻፉ። ለ) ከአጠናናቸው ጥቅሶች የትኞቹ የእነዚህ ቡድኖች አስተምህር ሐሰት መሆኑን ያጋልጣሉ?
ዛሬ በኢትዮጵያ ውስጥ በብዛት ይህን የሐሰት የአርዮስ ትምህርት የሚከተሉት የይሖዋ ምስክሮች ናቸው። ልክ እንደ አርዮስ እነርሱም ወልድ የእግዚአብሔር ኣምሳል ነው። ስለሆነም እግዚአብሔር አይደለም ይላሉ። ዮሐንስ 1፥ ፊልጵስዩስ 2፥ ቆላስይስ 1 እና ሌሎችም በትምህርት አንድ ላይና ቀደም ሲል በዚህ ትምህርት ያጠናናቸው ጥቅሶች ወልድ ከእግዚአብሔር አምሳል በላይ መሆኑንና እርሱ ራሱ አምላክ መሆኑን ያረጋግጣሉ። ሆኖም ግን የይሖዋ ምስክሮች የራሳቸው ትርጉም የሆነ የእንግሊዝኛ መጽሐፍ ቅዱስ አላቸው። ታዲያ አብዛኛዎቹ የተማሩት እነዚህ ጥቅሶች እንደተጻፉት አለመሆናቸውን ነው። እግዚአብሔር አንድም ሦስትም ሆኖ ሊገኝ አይችልም፥ ሲያስቡትም አይሆንም ይላሉ። እነዚህን የይሖዋ ምስክሮች ወደ ክርስቶስ ለማምጣት እነዚህን የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅሶች ይዞ ከእነርሱ ጋር መከራከር ኣያስፈልግም፥ ነገር ግን እኛ ማድረግ የሚገባን በዕለታዊ ኑሮአችን ውስጥ የክርስቶስን ፍቅር ለእነርሱ ማሳየት ነው።
ጥንታዊት ቤተ ክርስቲያን የአርዮስን አስተምህሮ አጥብቃ አውግዛለች። በ325 ዓ.ም የቤተ ክርስቲያን መሪዎች በኒቂያ ጉባዔ አድርገው የክርስትና እምነት መግለግ አዘጋጅተዋል። የእምነት መግለጫው ከመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በተውጣጡ ክፍሎች ላይ የተመሠረተ ሆኖ በተለይ የአርዮስን አስተምህሮ የሚቃወም ነው። መግለጫውም፥ «ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ ነው፤ ከሁሉ በላይ የላቀ፥ የተወለደ እንጂ ያልተፈጠረ፥ ከአብ ጋር እኩል የሆነ» ይላል። ምንም እንኳን የአርዮስ ትምህርት የተሳሳተ መሆኑ ቢታወቅም፥ ቤተ ክርስቲያን ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ ማንነት ትክክለኛው ግንዛቤ እንዲኖራት በማድረግ ረገድ ረድቷታል። እርሱ የእግዚአብሔር አምሳል ብቻ አልነበረም። ራሱ አምላክ ነበር። ከእግዚአብሔርም ጋር ህልውናው አንድ ነው።
ጥያቄ፡- የኒቃያው ጉባዔ የአርዮስን ትምህርት እንዴት አወገዘው?
በዚህ በኒቂያ ጉባዔ ጊዜ ኢየሱስ ክርስቶስን በሚመለከቱ አንዳንድ እውነቶች ረገድ ቤተ ክርስቲያን በጣም ግልጽ ነበረች። ኢቢዮናዊነትን፥ ኖስቲካዊነትን ሞናርካዊነትን፥ እና አርዮሳዊነትን ኣውግዘዋል። ልክ እንደ እግዚአብሔር አብ፥ ኢየሱስም ፍጹም አምላክ እንደ ሆነ አምነዋል። በመለኮትነቱ፥ ከእግዚአብሔር አብ ጋር በአካል አንድ እንዳልሆነ፥ ነገር ግን በባህሪ ኣንድ እንደ ሆነ ያምናሉ። ፍጹም ሰው እንደሆነና፥ ነገር ግን ያለ ኃጢአት እንደ ሆነ ያምናሉ። ይሁን እንጂ፥ ኢየሱስ እንዴት ሊሆን ነው በአንድ ጊዜ በአንድ አካል አምላክም ሰውም የሚሆነው? የጥንቷ ቤተ ክርስቲያን በዚህ አስቸጋሪ ጉዳይ ላይ ለመወሰን ሞክራለች። በሚቀጥለው ሳምንት ጥንታዊት ቤተ ክርስቲያንና የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ስለ ክርስቶስ አምላክነትና ሰብአዊነት ጥምረት ለመግለጽ እንዴት ሙከራ እንዳደረጉ እንመለከታለን።
ምንጭ፡- “አስተምህሮ ክርስቶስና ደኅንነት”፤ ጽሑፍ፣ በዶ/ር ስቲቭ ስራውስ፤ ትርጉም በኃይሉ ልመንህ