የዮሐንስ ወንጌል የጥናት መምሪያና ማብራሪያ
ምልከታ
በኢየሩሳሌም የመቅደስ መታደስ በዓል በሆነ ጊዜ ብርድ ነበረ፤ ኢየሱስም በመቅደስ በሰሎሞን መመላለሻ ይመላለስ ነበር። አይሁድም ከበውት “እስከ መቼ በጥርጣሬ ታቆየናለህ? አንተ ክርስቶስ እንደሆንክ በግልጥ ንገረን” አሉት። ኢየሱስም ነግሬአችኋለሁ ነገር ግን አታምኑም፤ በአባቴ ስም የማደርገው ሥራ ስለ እኔ ይመሰክራል በማለት መለሰላቸው። እናንተ ከበጎቼ ስላልሆናችሁ አታምኑም፤ በጎቼ ግን ድምኄን ይሰማሉ እኔም አውቃቸዋለሁ ይከተሉኛልም አለ። ለእነርሱም የዘላለም ሕይወትን እንደሚሰጣቸው፣ ለዘላለም እንደማይጠፉና ከእጁም ማንም ሊነጥቃቸው እንደማይችል ታላቅ የተስፋ ቃል ተናገረ። አብ ከሁሉ እንደሚበልጥና ከእግዚአብሔር አብ እጅም ማንም ሊነጥቃቸው እንደማይችል በመግለጽ “እኔና አብ አንድ ነን” የሚለውን ታላቅ እውነት አበሰረ። በዚህ ጊዜ አይሁድ ሊወግሩት ድጋሚ ድንጋይ አነሱ፤ እርሱ ግን መልካም ሥራ አሳይቻችኋለሁ ስለ የትኛው ትወግሩኛላችሁ አላቸው። እነርሱም ስለ ስድብ ነው እንጂ ስለ መልካም ሥራ አይደለም አሉት። ኢየሱስም በመጻሕፍት “አማልክት ናችሁ አልሁ” ተብሎ እንደተጻፈ ጠቅሶ ተከላከለ። በመጨረሻም ሊይዙት ቢፈልጉም ከእጃቸው አምልጦ ዮሐንስ መጀመሪያ ያጠምቅበት ወደነበረው ስፍራ ሄደ፤ በዚያም ብዙዎች አመኑ።
ትርጓሜ
ይህ ክፍል አማኝ በክርስቶስ ስላለው የማይናወጥ የደኅንነት ዋስትና የሚያስተምር ድንቅ ክፍል ነው። ኢየሱስ “በጎቼ ድምኄን ይሰማሉ” ማለቱ እውነተኛ እምነት ለጌታ ቃል ካለ ተገዥነትና ከእርሱ ጋር ካለ ጥልቅ ግንኙነት የሚመነጭ መሆኑን ያሳያል። እጅግ የሚደንቀው ደግሞ አማኞች በሁለት እጆች ውስጥ መሆናቸው ነው፤ በክርስቶስ እጅና በአብ እጅ። ይህ የሚያሳየው ደኅንነታችን በእኛ ጥንካሬ ላይ ሳይሆን በእግዚአብሔር ሁሉን ቻይነት ላይ የተመሠረተ መሆኑን ነው። “እኔና አብ አንድ ነን” የሚለው ንግግር ኢየሱስ በአካልም፣ በፈቃድም፣ በባሕርይም ከአብ ጋር እኩል መሆኑን የሚገልጽ መለኮታዊ ምስክርነት ነው።
አይሁድ ይህን ንግግሩን እንደ ስድብ የቆጠሩት ኢየሱስ ራሱን አምላክ ማድረጉን በግልጥ ስለተረዱ ነው። ኢየሱስ መጻሕፍትን ጠቅሶ መከራከሩ የእግዚአብሔር ቃል ለማንኛውም ጥያቄና ክርክር የመጨረሻው ባለሥልጣን መሆኑን ያረጋግጣል። በመጨረሻም ብዙዎች ማመናቸው የእግዚአብሔር ቃል በጠላቶች ተቃውሞ እንደማይታገድና የሚቀበሉት ልቦች ሁልጊዜ እንደሚኖሩ ያሳያል።
💬 ለአነስተኛ ቡድን ውይይት የሚሆኑ ጥያቄዎች
👉በሕይወትህ ውስጥ የሚገጥሙህ ፈተናዎችና የጠላት ጥቃት “ከጌታ እጅ ማንም ሊነጥቀኝ አይችልም” የሚለውን እምነትህን ያናውጡታል?
👉የጌታን ድምፅ ለመስማትና እርሱን ለመከተል በየቀኑ በምታደርገው እንቅስቃሴ ውስጥ ለቃሉ የምትሰጠው ስፍራ ምን ያህል ነው?
👉ደኅንነትህ በእግዚአብሔር ጥበቃ ላይ የተመሠረተ መሆኑን ማወቅህ ከኩራትና ከውድቀት ፍርሃት እንዴት ይጠብቅሃል?
👉”እኔና አብ አንድ ነን” የሚለው የጌታ ምስክርነት ለክርስቶስ የምትሰጠውን አምልኮና ክብር እንዴት ያሳድገዋል?
👉እውነትን በግልጥ ስትናገር ሰዎች ቢቃወሙህና “ድንጋይ ቢያነሱብህ” እንደ ኢየሱስ በቃሉ እውነት የመመከት ድፍረት አለህ?
👉በሕይወትህ ያደረግኸው መልካም ሥራና ምስክርነት ሰዎች ስለ ክርስቶስ ማንነት ጥያቄ እንዲያነሱና እንዲያምኑ ምክንያት ሆኖ ያውቃል?
👉ጌታ ኢየሱስ ከጠላቶች እጅ አምልጦ ወደ ማረፊያ ስፍራ እንደሄደ፣ አንተስ በግርግርና በክርክር መካከል ወደ ጸጥታና ወደ ጌታ መገኘት የመሸሽ ልምድ አለህ?