የሕይወት እንጀራ

የዮሐንስ ራእይ

አዲስ ሰማይና ምድር እና የክርስቶስ ዳግም ምጽአት ተስፋ (ራእይ 21፡1–22፡21)

፩. አዲስ ሰማይና ምድር (ራእይ 21፡1–22፡6) ስለ መንግሥተ ሰማይና በዚያ ሕይወት ምን እንደሚመስል የበለጠ ብናውቅ ደስ ባለን። ነገር ግን አብዛኛው ነገር ከእኛ የተሰወረ ነው። በዚህ ክፍል ውስጥ መጽሐፍ ቅዱስ መንግሥተ ሰማይ ምን እንደምትመስል በግልጽ ያሳየናል። እግዚአብሔር የተለያዩ ተምሳሌቶችን በመጠቀም የዘላለም ቤታችን ምን ያህል ውብ እንደሆነች እንድንገነዘብና ሕይወታችንን በሚገባ እያዘጋጀን እንድንኖር ያበረታታናል። ዮሐንስ የተለያዩ ምሳሌዎችን በመጠቀም ስለ ዘላለማዊ ቤታችን አንዳንድ ታላላቅ ነገሮችን ይነግረናል፡ ሀ. እግዚአብሔር አዲስ ሰማይና አዲስ ምድርን ይፈጥራል። አሁን ያለ ነው በኃጢአት በተጨማለቀች ምድር ውስጥ ነው። ይሁንና አሁንም ለእኛ ውብ ናት። በኃጢአት ያልተበከሉ አዲስ ሰማይና ምድር ምን ያህል የበለጠ ያምሩ ይሆን! ለ. እግዚአብሔርና ሰው ከመቼውም በበለጠ ቅርበት ኅብረት ያደርጋሉ። እግዚአብሔር ከሰው ጋር አብሮ ለመኖር ሲል ከሰማይ ወደ ምድር እንደሚመጣ በተምሳሌታዊ ቋንቋ ተገልጾአል። በዚህም እንደ ሃያ አራቱ ሽማግሌዎችና አራቱ እንስሳት እግዚአብሔርን ፊት ለፊት ልናመልከው ስለምንችል፥ የቤተ መቅደስም ሆነ የቤተ ክርስቲያን ሕንጻ አያስፈልግም። ይህቺ እዲሲቱ ኢየሩሳሌም በዚህ ምድር ላይ ውድና ተፈላጊ ከሆኑት ነገሮች ሁሉ በላይ የደመቀች ናት። በመሆኑም በዚህ ምድር ላይ ውድ የሆኑት ነገሮች በዚያ ተራ ነገሮች ይሆናሉ። ጎዳናዎች በወርቅ ይነጠፋሉ። በሮች በከበሩ ማዕድናት ይሠራሉ። ሐ. ለሐዘን ሊዳርገን የሚችል ምንም ዓይነት ነገር አይኖርም። እግዚአብሔር የጸጸትንና የሐዘንን እንባዎች ከዓይኖቻችንና ከአእምሮአችን በማበስ ለመቼውም እንዳናስታውሳቸው ያደርገናል። ኃጢአት፥ በሽታ፥ ሞት፥ ስደት፥ ማንኛውም ዛሬ ሥቃይን የሚያስከትልብን ነገር በዚያ አይኖርም። መ. በእግዚአብሔር ላይ የሚያምጹ ሰዎች በዚያ አይኖሩም። ዮሐንስ ከእግዚአብሔር ዘላለማዊ ቤት ውጭ ያደርጉናል ብሎ የዘረዘራቸው ኃጢአቶች በዮሐንስ ዘመን የነበሩ ክርስቲያኖች ስደትን ለመሸሽ የሚፈተኑባቸው መሆናቸው አስገራሚ ነው። ለእምነታቸው ጸንተው ለመቆም ያልቻሉ ፈሪዎች፥ የከርስቶስን መሢሕነት ያልተቀበሉና ከእምነት የራቁ፥ የጠላትን ሐሰተኛ አምልኮ የተቀላቀሉ፥ እንዲሁም ወሲባዊ ኃጢአቶችን የፈጸሙና የጎደፉ ሰዎች ለቅጣት እንደሚጋለጡ ተገልጾአል። ሠ. የክፋት ጨለማ ይወገድና የእግዚአብሔር ዘላለማዊ የመገኘቱ ብርሃን በሕዝቡ ላይ ያበራል። ረ. ከተማይቱ ከማንኛውም አስጊ ነገር የጸዳች በመሆኗ በሮቿ አይዘጉም። ሌቦች ይመጡብናል ብሎ በር መዝጋቱ ያበቃል። ሰ. ለእግዚአብሔር ንጹሕ አምልኮ ስለሚቀርብ በዘላለማዊ መንግሥት ውስጥ ያለ ሰው ሁሉ እግዚአብሔርን ለማምለክ ይመጣል። በኦሮጌዎቹ ሰማይና ምድር እንደነበረው ዐመፃ አይታሰብም። ሸ. ከእግዚአብሔር አብና ወልድ በአዲሲቱ ኢየሩሳሌም ለሚኖሩ አማኞች በረከቶች እንደማያቋርጥ የወንዝ ውኃ ይፈሱላቸዋል። እንዲሁም ከቶውንም የማይወድቅና እንደማይጠወልግ የሕይወት ዛፍ (ፈዋሽ ቅጠሎች ያሉት) የማያቋርጥ፥ ፈውስ ይመጣላቸዋል። ይህ ከበሽታ መፈወስን ሳይሆን፥ አሮጌዎቹ ሰማይና ምድር በሰዎች ላይ ዐመፀኛነቱን ከቀሰቀሱት ክፉ ነገሮች መፈወስን የሚያሳይ ነው። ቀ. የእግዚአብሔር ቤተሰብ ለዘላለም ከእግዚአብሔር አብና ወልድ ጋር ይነግሣሉ።  የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) እነዚህ እስጨናቂ የእግዚአብሔር የተስፋ ቃሎች መንግሥተ ሰማይን እንድትናፍቅ የሚያደርጉህ እንዴት ነው? ለ) እነዚህ የተስፋ ቃሎች ዛሬ ለኢየሱስ ክርስቶስ ታማኞች እንድንሆን የሚያበረታቱን እንዴት ነው? ፪. የክርስቶስ ዳግም ምጽአት ተስፋ (ራእይ 22፡7-21) የዮሐንስ ራእይ የመጽሐፉ መሠረት በሆኑት እውነቶች ይጠናቀቃል። በመጀመሪያ፥ ክርስቶስ በቶሎ እንደሚመለስ ለተከታዮቹ ያስገነዝባቸዋል (ራእይ 22፡7፥ 12)። ስለሆነም፥ ዳግም ምጽአቱን በናፍቆት መጠባበቅ ይኖርብናል። ዮሐንስ፥ መንፈስ ቅዱስና ሙሽራይቱ (ቤተ ክርስቲያን) ዳግም ምጽአቱን በመናፈቅ «ጌታ ኢየሱስ ሆይ፥ ቶሎ ና» ሲሉ ይጸልያሉ። ማናችንም ክርስቶስ መቼ እንደሚመለስ አናውቅም። እስከ ዛሬ ሁለት ሺህ ዓመታት ቢቆጠሩም፥ ጌታ ገና አልተመለሰም። ነገር ግን ለእግዚአብሔር «በቶሎ» ማለት እኛ የምናስበው ዓይነቱ ቶሎ ላይሆን ይችላል። (2ኛ ጴጥ. 3፡8 አንብብ)። ነገር ግን እያንዳንዱ የአማኞች ትውልድ የክርስቶስን ምጽአት ሊጠባበቅና በቶሎ እንደሚደርስ ተስፋ ሊያደርግ ይገባል። ሁለተኛ፥ ክርስቶስ ተከታዮቹ አኗኗራቸውን ከዳግም ምጽአቱ እውነታ አንጻር እንዲያስተካክሉ ያስጠነቅቃል። የዮሐንስ ራእይ የተሰጠው ወደፊት የሚሆነውን ብቻ ሳይሆን፥ በመጽሐፉ ውስጥ የተገለጹትን የትንቢት ቃሎች እንድንጠብቅ ጭምር ነው። እነዚህ በሕይወታችን ውስጥ ተግባራዊ ልናደርጋቸው የሚገቡ እውነቶች ናቸው። የኢየሱስ ክርስቶስ ተከታዮች ልብሳችንን አጥበን ማንጻታችንን ማረጋገጥ አለብን። ይህም በኢየሱስ ክርስቶስ ማመናችንን የሚያመለክት ነው። እንዲሁም እምነታችንን ባለመደበቅ ወይም ባለመካድ፥ ሐሰተኛ አምልኮን ባለመከተልና የዓለማውያንን የተሳሳቱ ልምምዶች ተግባራዊ ባለማድረግ በቅድስና ልንመላለስ ይገባል። እነዚህ ዓለማውያን የእግዚአብሔር በረከቶች ተካፋይ እንደማይሆኑ ግልጽ ነው። ሦስተኛ፥ ለማያምኑ ሰዎች የተሰጠ መልእክት። ክርስቶስ እስከሚመለስና ፍርድ እስከሚጀምር ድረስ እግዚአብሔር መንፈሳዊ ጥማት ላደረባቸው ሰዎች ድነትን (ደኅንነትን) ይሰጣቸዋል። የዘላለም ሕይወት ውኃ ነፃ ነው። ይህን ለማግኘት ሰዎች ዋጋ መክፈል አያስፈልጋቸውም። አንድ ሰው ሊያደርግ የሚገባው ነገር ቢኖር ወደ ክርስቶስ ተመልሶ በእርሱ ማመን ነው። ነገር ግን በእግዚአብሔር ላይ ባላቸው ዐመፀኛነት ቢቀጥሉ፥ በዮሐንስ ራእይ ውስጥ ለተጠቀሱት መቅሰፍቶች ፍርድ ይጋለጣሉ። የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) እነዚህ ሦስት መልእክቶች እግዚአብሔር የሰጠን እጅግ ጠቃሚ መልእክቶች የሚሆኑት ለምንድን ነው? ለ) ቤተ ክርስቲያንህ እነዚህን ሦስት መልእክቶች ለአማኞችና ለማያምኑ ሰዎች እያደረሰች ያለችው እንዴት ነው? ሐ) ከዮሐንስ ራእይ ያገኘሃቸው ሌሎች ጠቃሚ ትምህርቶች ምን ምንድን ናቸው?  (ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

አዲስ ሰማይና ምድር እና የክርስቶስ ዳግም ምጽአት ተስፋ (ራእይ 21፡1–22፡21) Read More »

የክርስቶስ የሺህ ዓመት ንግሥና (ራእይ 20፡1-15)

፩. የክርስቶስ የአንድ ሺህ ዓመት ንግሥና (ራእይ 20፡1-6) ከክርስቶስ ጠላቶች መደምሰስ በኋላ የዮሐንስ ራእይ ስለ ዘላለማዊ መንግሥት አጀማመር ይነግረናል ብለን እንጠብቃለን። ነገር ግን በመጽሐፉ ውስጥ የምናገኘው ክርስቶስ ለአንድ ሺህ ዓመታት በምድር ላይ እንደሚነግሥ የሚያስረዳውን ክፍል ነው። የዮሐንስ ራእይ በተምሳሌቶች የተሞላ መጽሐፍ በመሆኑ፥ ብዙ አማኞች የሺህ ዓመቱ መንግሥት ክርስቶስ በምድር ላይ በአማኞች ልብ ውስጥ፥ በሰማይ ደግሞ በቅዱሳን ሕይወት መንገሡን የሚያመለክት ነው ይላሉ። ነገር ግን ይህ ክፍል መሢሑ ኢየሱስ ክርስቶስ በምድር ላይ ለአንድ ሺህ ዓመታት በቀጥታ የሚነግሥ መሆኑን የሚያሳይ ይመስላል። እግዚአብሔር የዘላለምን መንግሥት ከመጀመሩ በፊት ለሺህ ዓመታት በምድር ላይ ለመግዛት የፈለገበትን ምክንያት አናውቅም። ነገር ግን ሁለት ሊሆኑ የሚችሉ ምክንያቶች አሉ። በመጀመሪያ፥ በብሉይ ኪዳን ነቢያት የተነገሩና እንደ ዳዊት ካሉ ሰዎች ጋር የተደረጉ አብዛኞቹ ቃል ኪዳኖች ክርስቶስ በምድር ላይ የሚነግሥ መሆኑን ያሳይሉ። ስለሆነም፥ እግዚአብሔር በተለይ ለአይሁዶችና በአጠቃላይ ለሰዎች ሁሉ እነዚህን የተስፋ ቃሎች ለማሟላት የክርስቶስን የምድር ላይ መንግሥት ይመሠርታል። ሁለተኛ፥ እግዚአብሔር የሰዎችን ልብ ክፋት ለማሳየት ይፈልጋል። ብዙውን ጊዜ ሰዎች ክፋትን የሚማሩት ከእነርሱ ውጭ የሆነ ነገር ወደ ከፋት ስለሚመራቸው ነው ብለን እናስባለን። ሰዎች ከወላጆቻቸው፥ ከባህላቸው፥ ወዘተ… ክፋትን ይማራሉ ብለን እናስባለን። ነገሮች ሁሉ መልካም ቢሆኑ፥ በምድር ላይ እውነተኛ ፍቅር ቢኖር፥ ሰዎች ሁሉ ቢማሩ፥ ሰዎች እግዚአብሔርን በማክበር በትክክለኛው መንገድ ይኖራሉ ብለን እናስባለን። ይህ ግን እውነት አይደለም። የሰው ልብ ክፉ ስለሆነ ሁልጊዜም የእግዚአብሔርን አገዛዝ ይቃወማል (ኤር. 17፡9)። ይህም በዚህ ክፍል ውስጥ በግልጽ ተመልክቷል። ምንም ዓይነት ባህላዊ፥ ወላጃዊ ወይም ማኅበራዊ ክፋቶች ለማማሃኛነት ሊጠቀሱ በማይችሉበት ሁኔታ ውስጥ (ክርስቶስ በጽድቅ ነግሦ ሳለ) ሰዎች አሁንም በእግዚአብሔር ላይ ያምጻሉ። ምናልባትም ታላቁን መከራ ካለፉት ክርስቲያኖች የተወለዱ ልጆች ከዚሁ የክርስቶስ የሺህ ዓመታት መንግሥት ፍጻሜ ላይ ማመጽ ይጀምራሉ። ወዲያውኑ ሰይጣን እንደ ተፈታ ከእርሱ ጋር በመተባበር ከእግዚአብሔር ጋር ይዋጋሉ። የሰው ልጅ ምንኛ ክፉ ነው!  የውይይት ጥያቄ፡- የእግዚአብሔር ልጅ ብትሆንም እንኳን የልብህን ክፋት እንዴት እንደተመለከትህ ግለጽ። ይህ ስለ እግዚአብሔር ምሕረት ታላቅነት ምን ያስተምረናል? ዮሐንስ የተለያዩ ቡድኖችንና ክርስቶስ በምድር ላይ ለመግዛት ከሰማይ በሚመለስበት ጊዜ በእነርሱ ላይ ስለሚሆኑት ነገሮች ያብራራል። ሀ) ሰይጣንና ተከታዮቹ አጋንንት ሺህ ዓመታት ወደ ጥልቁ ወርደው ይታሰራሉ። ይህም ጥልቁ ጉድጓድ ክፉ መናፍስት የሚታሰሩበት ነው። በዚያም በእስር ቤት ሰዎች ኃጢአትን እንዲሠሩና በመሢሃቸው ላይ እንዲያምጹ ሊያደርጉ አይችሉም። ለ) የተሠዉ አማኞችና በዘመናት ሁሉ የኖሩ ክርስቲያኖች ከሞት ተነሥተው የትንሣኤን አካል ይለብሳሉ። በታላቁ መከራ ጊዜ ያልሞቱና በሕይወት ያሉ አማኞችም ተለውጠው ከእነዚሁ ክርስቲያኖች ጋር ይሆናሉ (1ኛ ቆሮ. 15፡51-54)። አማኞቹ በእግዚአብሔር ተከብረው ከክርስቶስ ጋር በምድር ላይ ይነግሣሉ። (ማስታወሻ፡ በዮሐንስ ራእይ ውስጥ ሁሉ ዮሐንስ በሰማዕትነት ባለፉት አማኞች ላይ አጭር ማስታወሻ ይሰጣል። ይህንንም ያደረገው አማኞች በቆራጥነት ስደትን እንዲጋፈጡና ያለ ፍርሃት ለእምነታቸው እንዲሞቱ ለማበረታታት ነው። መከራን የሚቀበሉ ክርስቲያኖች እግዚአብሔር እንደሚያከብራቸው ማስታወስ ይኖርባቸዋል። ምንም እንኳ ለጊዜው ክፉ ሰዎች ሁኔታዎችን በመቆጣጠር ላይ ቢሆኑም፥ እነዚህ መከራን የተቀበሉ አማኞች የሚነግሡበት ቀን ይመጣል። ከሌሎች የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች በግልጽ እንደሚታየው፥ አማኞች ሁሉ ከሞት ተነሥተው ከክርስቶስ ጋር ይነግሣሉ (1ኛ ተሰ. 4፡13-18፤ 2ኛ ጢሞ. 2፡12፥ ራእይ 5፡9-10)። ከክርስቶስ ትምህርት እንደምንመለከተው፥ በዚህ ምድራዊ ንግሥና እያንዳንዱ አማኝ የሚኖረው ሥልጣን አሁን እርሱን በምናገለግልበት ጊዜ ባለን ታማኝነት ላይ ይመሠረታል (ማቴ. 25፡14-30)። ዮሐንስ የአማኞችን ትንሣኤ የመጀመሪያው ትንሣኤ ሲል ይጠራዋል። ወደ ሲዖል መውረድን ደግሞ ሁለተኛው ሞት ሲል ይጠራዋል። ክርስቶስን በታማኝነት የሚከተሉ ሰዎች የዚህ የመጀመሪያው ትንሣኤ አካል ከመሆናቸው በተጨማሪ፥ በሁለተኛው ሞት ወደ ሲዖል እንደማይወርዱም ተገልጾአል። ሐ) በሁሉም ዘመን የሞቱ ሰዎች ገና ከሞት አይነሡም። ፪. የሰይጣን መፈታትና የሰው ልጆች ዐመፅ (ራእይ 20፡7-15) ሁላችንም የአዳምንና የሔዋንን ታሪክ እናውቃለን። በምርጥ ስፍራ ሲኖሩ ሳለ ሰይጣን በፈተናቸው ጊዜ ለማመጽ መርጠዋል። እኛ ግን ክርስቶስ በመካከላችን ቢኖር እንዲህ ዓይነት ኃጢአት እንፈጽምም ብለን ልናስብ እንችላለን። ይሁንና ኃጢአት መፈጸማችን የማይቀር ነው። ዮሐንስ የሰው ልጅ እንዴት ሁልጊዜም በእግዚአብሔር ላይ እንደሚያምጽ ያሳያል። ሰይጣን ከእስራቱ ከተፈታ በኋላ በቀላሉ የዓለም ሰዎች እንዲያምጹ ያደርጋል። እነዚህ ሰዎች ለሕይወት የሚያስፈልጉ ቁሳዊ በረከቶች ሁሉ በተሟሉባት የክርስቶስ የጽድቅ መንግሥት ውስጥ ይኖሩ ነበር። ይሁንና አሁንም ሰይጣንን ለመከተል መረጡ። ክርስቶስ የንግሥናው መዲና አድርጎ ወደ መረጣት ወደ ኢየሩሳሌም ከተማ እየገሰገሰ ሳለ ክርስቶስ በራእይ 19 ጠላቶቹን እንዳሸነፈ ሁሉ በቀላሉ ያሸንፋቸዋል። የሚገርመው እነዚህ ሰዎች ከአንድ ሺህ ዓመታት በፊት ከተገለጸው የክርስቶስ ኃይል አለመማራቸው ነው። ዮሐንስ የዘላለም መንግሥት ከመጀመሩ በፊት ለእነዚህ የተለያዩ ቡድኖች ስለሚሆነው ሁኔታ ይገልጻል፡ ሀ) ሰይጣን ወደ እሳት ባህር ይወረወራል። እዚያም ለዘላለም ስለሚታሰር ከእንግዲህ ሰዎች በእግዚአብሔር ላይ እንዲያምጹ የሚያደርግበትን ዕድል አያገኝም። ይህ የእሳት ባህር ወይም ሲዖል የእግዚአብሔር ጠላቶች ለዘላለም የሚቀጡበት ስፍራ ነው። ለሲዖል በመጽሐፍ ቅዱስ ከምንመለከታቸው ነገሮች ምን ያህሎቹ ተምሳሌታዊ ምን ያህሎቹ ደግሞ ቀጥተኛ እንደሆኑ እናውቅም። ነገር ግን አራት ነገሮችን እናውቃለን። 1. ሲዖል ለዘላለም የሚቀጥል ነው። ይህ ሰዎች ከኃጢአታቸው ጸድተው የሚወጡበት የመቆያ (ፐርጋቶሪ) ስፍራ አይደለም። 2. ሰዎች ወደ ምንምነት ወይም አዕምሮአቸውን ወደማያውቁበት ሁኔታ ውስጥ አይሆኑም። ሕይወት ያላቸውና ያሉበትን ሁኔታ የሚያውቁ ይሆናሉ። 3. ይህ ጥልቅ ሥቃይና መከራ የሚበዛበት ስፍራ ነው። እዛ ያሉት ሁሉ በጣም ይሠቃያሉ። 4. ሲዖል ምንም ዓይነት የእግዚአብሔር በረከት የሌለበት ስፍራ ነው። ከእግዚአብሔር ምሕረትና ፍቅር ደስታ የሚያመልጡልን ነገሮች ሁሉ በዚያ አይኖሩም። ለ) ሙታን ከሞት ተነሥተው በታላቁ ነጭ ዙፋን ፊት ይቆማሉ። ምሁራን እነዚህ እነማን ናቸው በሚለው ጉዳይ ላይ ይከራከራሉ። የክርስቶስ የፍርድ ወንበርና ታላቁ ነጭ ዙፋን አንድ ናቸው ወይስ የተለያዩ? አንድ ከሆኑ፥ ይህ ታላቁ የነጭ ዙፋን ፍርድ ለአማኞችም ለማያምኑ ሰዎችም መሆኑ ነው። የተለያዩ ከሆኑ፥ ይህ ፍርድ የሚሰጠው ለማያምኑ ሰዎች ብቻ ይሆናል። በራእይ 20፡5 የተገለጸው ትንሣኤ (ሌሎች የአዲስ ኪዳን ክፍሎች የሚጠቅሱት) አማኞችን ሁሉ የሚያካትት ከሆነ፥ ሌሎችም የአዲስ ኪዳን ክፍሎች እንደሚጠቁሙን በነጭ ዙፋን ፊት የቆሙት ቀደም ሲል ለሕይወት ያልተነሡ ዓለማውያን ሊሆኑ ይችላሉ። (ማስታወሻ፡ ይህ እውነት ከሆነ፥ ከዚህ ቀደም ብሎ የአማኞች የምድር ላይ ሕይወት የሚገመገምበትና ሰማያዊ ሽልማት የሚያገኙበት ጊዜ ይኖራል። ጳውሎስ ይህንን የክርስቶስ የፍርድ ወንበር ሲል ይጠራዋል። 1ኛ ቆሮ. 3፡11–15 አንብብ። ይህ ፍርድ ድነትን (ደኅንነትን) የሚመለከት አይደለም። ነገር ግን የአንድ አማኝ ሕይወት በማይጠቅሙ ነገሮች ለምሳሌ፡- ገለባ፥ እንጨት፥ ወይም በሚጠቅሙ ነገሮች ለምሳሌ፡- ወርቅ፥ ብር፥ የከበሩ ድንጋዮች መሟላቱን ለማረጋገጥ የተሰየመ ችሎት ነው። ለእግዚአብሔር የምናደርገው ነገር ጠቃሚ መሆን አለመሆኑ የሚወሰነው ክርስቶስን በምናገለግልበት ጊዜ ባለን ዓላማና አመለካከት ላይ ነው። በዙፋኑ ላይ የተቀመጠው እጅግ ታላቅ፥ ኃያልና ቅዱስ በመሆኑ፥ በተምሳሌታዊ አገላለጽ ፍጥረት ሁሉ ከፊቱ ሊቆም አይችልም። ፈራጁ እግዚአብሔር አብና ወልድ ይመስላል (ራእይ 22፡1፥3)። የፍርዱ መሠረት ምንድን ነው? ፍርዱ የሚሰጠው በሁለት መጻሕፍት ላይ ተመሥርቶ ነው፡– ሀ. የሕይወት መጽሐፍ፡ ይህ የሰማይ ዜጎችን ስም የሚዘረዝር መጽሐፍ ነው። በዚህ መጽሐፍ ውስጥ የሚገኘው በዘመናት ሁሉ ያመኑት ሰዎች ስም ብቻ ነው። በዚህ መጽሐፍ ውስጥ ስማቸው የተጻፈላቸው ሰዎች የመንግሥተ ሰማይ ነዋሪነትና የዘላለም ሕይወት ይሰጣቸዋል። በዚህ መጽሐፍ ውስጥ ስማቸው ያልተጻፈላቸው ሰዎች ወደ ሲዖልና ዘላለማዊ ሞት ይላካሉ። ለ. የሰዎችን ተግባራት የሚገልጹ መጻሕፍት፡ አንድ ሰው በምድር ላይ በኖረበት ሁኔታ ላይ ተመሥርቶ በሰማይ ለአማኞች የሚሰጡ ሽልማቶች በደረጃ እንደሚለያዩ ሁሉ፥ ለኃጢአተኞችም በምድር ላይ ሳሉ በፈጸሟቸው ተግባራት ላይ የተመሠረቱ የተለያዩ ፍርዶች የሚሰጡ ይመስላል። እንደ ሂትለር ሰይጣን የላቀ ክፋት ለመፈጸም የተጠቀመባቸው ሰዎች ክርስቶስን አልከተልም እያለ ዳሩ ግን መልካም ሕይወት ከመራ ሰው የባሰ ቅጣት ይጠብቃቸዋል። ነገር ግን መልካም ሕይወት መምራቱ ብቻ ሰውን ስሙ በመንግሥተ ሰማይ ዜጎች መዝገብ ውስጥ እንዲሰፍር አያስችለውም።

የክርስቶስ የሺህ ዓመት ንግሥና (ራእይ 20፡1-15) Read More »

የክርስቶስ ምጽአት (ራእይ 19:1-21)

፩) በሰማይ ያሉት ለባቢሎን ውድመት የሰጡት ምላሽ (ራእይ 19፡1-10) በራእይ 18 ዮሐንስ ዓለማውያን ለባቢሎን መደምሰስ የሰጡትን ምላሽ ገልጾል። ለእነርሱ ይህ የሐዘን ጊዜ ነበር። ምክንያቱም የወደዷቸው ነገሮች፥ ኃይልና ክብራቸው ሁሉ ወድሟልና ይህም ቁሳዊ ሀብት የሚያመጣው ነው። በራእይ 19፡1-10 ግን በሰማይ ለባቢሎን መደምሰስ የተሰጠው ምላሽ ተገልጾአል። ዮሐንስ በተለያዩ ሰዎች እግዚአብሔር በባቢሎን ተምሳሌትነት ለተገለጸው የዓለም ላይ ክፋት ፍርዱን ስለገለጸ ደስ ተሰኝተው ያመሰግኑታል። ሀ) በሰማይ የታዩ እጅግ ብዙ ሕዝብ ቀደም ሲል በራእይ 7፡9-17 የተገለጹት አማኞች ናቸው። በእነዚህ ውስጥ ቀደም ሲል ታላቁ መከራ ተብሎ በሚጠራው የመከራ ጊዜ የሞቱ አማኞች ይገኛሉ። እነዚህ ሰዎች ለእምነታቸው በሰማዕትነት ያለፉ ናቸው። ለሞት አሳልፈው የሰጧቸው ክፉ ሥርዓቶች (ፖለቲካዊ፥ ሃይማኖታዊ፥ ኢኮኖሚያዊ) ሲወድሙ በማየታቸው አማኞቹ ደስ ተሰኝተው እግዚአብሔርን ያመሰግኑታል። ይህ በተጨማሪም ራሳቸውን በንጽሕና የጠበቁና የዓለም ፍቅር እንዳይቆጣጠራቸው ያደረጉ እውነተኛ አማኞች ሁሉ የሚሰጡት ምላሽ ምልክት ነው። ፍትሕ ሊሰፍን ደስ ይሰኛሉ። «ሃሌሉያ» የሚለው ቃል ከአይሁድ የአምልኮ ሥርዓት ተወስዶ ሳይተረጉም በአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የተቀመጠ ነው። የቃሉ ትርጉም «ጌታ ይመስገን» የሚል ነው። የቀድሞይቱ ቤተ ክርስቲያን ያልተለመደ ደስታ ሲገጥማት ወይም በአምልኮ ጊዜ ይህንን ቃል ትጠቀም ነበር። በኢትዮጵያ ውስጥ የሚገኙ ክርስቲያኖች ይህንን ቃል በተደጋጋሚ ይጠቀማሉ። ይህ ቃል የመንፈሳዊነት ወይም የልዩ ኃይል ምልክት የሆነ ይመስል ደጋግመን እንጠቀምበታለን። ምንም እንኳን ለአማኞች ትርጉሙን ካወቅነው ይህንን ቃል መጠቀሙ መልካም ቢሆንም፥ እነዚህ ቃላት የመንፈሳዊነት ምልክቶች ወይም በጸሎት ጊዜ ልንጠቀምባቸው የሚገቡ ምትሃታዊ ቃላት እንደሆኑ ማሰብ የለብንም። የደስታ ስሜታችን በተፈጥሯዊ መንገድ ሃሌሉያ ወይም እልል በማለት ራሱን ከገለጸ መልካም ነው። ይሁንና፥ ተራ አገላለጽ ተጠቅመው «ጌታ ይመስገን» ለማለት የሚመርጡትን ሌሎች አማኞች መኮነን የለብንም። የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) አንዳንድ ሰዎች በተደጋጋሚ ሃሌሉያ እያሉ የሚጮሁት እንዴት ነው? ለ) ሰዎች ይህንን ቃል የሚጠቀሙት ትርጉሙን ተረድተውና አግባብነትን ጠብቀው ነው ወይስ የበለጠ መንፈሳዊ ወይም ለጸሎታቸው ኃይል እንደሚሰጥ በማሰብ? ለ) ሃያ አራቱ ሽማግሌዎችና አራቱ እንስሶችም እግዚአብሔርን ላከናወነው ተግባር ያመሰግኑታል። ሐ) ሁለተኛው እጅግ ብዙ ሕዝብ። ይህ ሕዝብ ምናልባትም በዘመናት ሁሉ ድነትን (ደኅንነትን) ያገኙ ሰዎች ክምችት ሳይሆን አይቀርም። እነርሱም እግዚአብሔርን ያመሰግኑታል። የደስታቸውም ምንጭ ሁሉን ቻይ የሆነው አምላክ መንገሡ ነው። ከእንግዲህ በሰማያት ያሉ ጠላቶች (ሰይጣን) አገዛዙን አይዋጉም። በምድር ላይም ያሉ ቢሆን አገዛዙን የሚቃወሙ (ለምሳሌ፥ መንግሥታት) ጠላቶች አይኖሩም። በሰማይና በምድር ያለው ነገር ሁሉ ለእግዚአብሔር አገዛዝ በመስገድ ትክክለኛ ሚናቸውን ይጫወታሉ። ይህ ሕዝብ የሚደሰትበት ሌላው ምክንያት ደግሞ የበጉ ሠርግ መቅረቡና ሙሽራይቱም ራሷን ማዘጋጀቷ ነው። መጽሐፍ ቅዱስ ብዙውን ጊዜ በብሉይም ሆነ በአዲስ ኪዳን ውስጥ የነበሩትን የእግዚአብሔርን ሕዝብ ከሙሽራ ጋር ያነጻጽራል (ሆሴዕ 2፡19-20፤ 2ኛ ቆሮ. 11፡2)። አይሁዶች የመሢሑ መንግሥት የሚጀምረው በታላቅ ግብዣ እንደሆነ ያምኑ ነበር (ማቴ. 25፡1-13)። ዮሐንስ ይህንኑ ምሳሌ በዚህ ስፍራ ይጠቀማል። ነገር ግን ዮሐንስ ቤተ ክርስቲያን ገና ለክርስቶስ እንደ ታጨች እንጂ እንዳገባችው አልገለጸም። ክርስቶስ በመስቀል ላይ ከሞተበት ጊዜ ጀምሮ እስከ አሁን ድረስ ጋብቻው አልተፈጸመም። ቤተ ክርስቲያን ለጋብቻ እየተዘጋጀች እንዳለች ሙሽራ ነች። ነገር ግን እግዚአብሔር ባቢሎንን ሲያጠፋና ክርስቶስም መግዛት ሲጀምር፥ በክርስቶስና በቤተ ክርስቲያን መካከል ያለው ግንኙነት ይበልጥ ንጹሕና የጠለቀ ይሆናል። በተምሳሌታዊ መልኩ ክርስቶስ ሙሽራ፥ ቤተ ክርስቲያን ሙሽራይቱ፥ እንዲሁም በመካከላቸው ያለው ግንኙነት እግዚአብሔር እንዳቀደው ንጹሕ ይሆናል። በሕይወታችን ውስጥ የኃጢአት መሰናክል ሳይኖር ክርስቶስን ፊት ለፊት እናየዋለን። ያ የጋብቻ ሥርዓት ጊዜ በምድር ላይ ከተደረጉት ከየትኞቹም የጋብቻ ባህሎች የላቀ ይሆናል። ዮሐንስ አማኞች ዛሬ ለዚሁ ጋብቻ መዘጋጀት እንዳለባቸው ያስገነዝበናል። ቀጭንና ነጭ የተልባ እግር መልበስ ይኖርብናል። ይህ ተምሳሌት ሁለት ጠቃሚ እውነቶችን ያመለክታል። በመጀመሪያ፥ በኢየሱስ ክርስቶስ በማመናችን እግዚአብሔር ጻድቃን ናችሁ ብሎናል። ለዚህም ነው ሰዎች የተልባ እግሩን ራሳቸው ያላዘጋጁትና ከእግዚአብሔር ዘንድ የተቀበሉት። ሁለተኛ፥ ዮሐንስ ድነንት (ደኅንነትን) እንዳገኙ ሰዎች እንዴት መመላለስ እንዳለብን ያስጠነቅቀናል። በሕይወታችን ውስጥ ካለው ክፋት ሁሉ ተላቅቀን ለእጮኛችን ለኢየሱስ ክርስቶስ ክብርን የሚያመጡትን ነገሮች ማድረግ ይኖርብናል። በዮሐንስ ራእይ መጨረሻ አካባቢ ዮሐንስ ሁለት ጊዜ መላእክትን ሊያመልክ ሲሰግድና ዳሩ ግን ይህንኑ እንዳያደርግ ሲከለክል እንመለከታለን (ራእይ 19፡10፤ 22፡8-9)። በቀድሞዎቹ አብያተ ክርስቲያናት ውስጥ ከተስፋፉት ሐሰተኛ ትምህርቶች አንዱ መላእክትን ማምለክ ነበር (ቆላ. 2፡18) አንብብ። ይህም ዛሬ በአንዳንድ አብያተ ክርስቲያናት ውስጥ የሚታይ ሁኔታ ነው። ነገር ግን እግዚአብሔር መላእክት ማን እንደሆኑና መላእክትን ማምለኩ ለምን ትክክለኛ ተግባር እንዳልሆነ እንድንገነዘብ ይፈልጋል። መላእክት በእግዚአብሔር ዓይኖች ፊት ከእኛ የበለጡ አይደሉም። ነገር ግን መላእክት ከእኛ በተለየ መንገድ የተፈጠሩ ፍጥረታት ናቸው። መላእክትም ሆኑ ሰዎች ሁላችንም የእግዚአብሔር አገልጋዮች ነን። እንዲያውም እግዚአብሔር ለመላእክት ከሰጣቸው ዐበይት ተግባራት አንዱ የኢየሱስ ክርስቶስን ምስክርነት የሚጠብቁትን አማኞች እንዲረዱ ነው። ቅዱሳንን ማምለክ አያስፈልግም። ማርያምን ማምለክ አያስፈልግም። አያት ቅድመ አያቶቻችንንም ማምለክ የለብንም። ልናመልከውና ልንሰግድለት የሚገባው እግዚአብሔር ብቻ ናቸው።  የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) አንዳንድ ክርስቲያኖች ለመላእክት፥ ለቅዱሳን፥ ለአያት ቅድመ እያቶቻቸው፥ ለማርያም፥ ወዘተ… የሚሰግዱት ለምንድን ነው? ለ) እነዚህ ክርስቲያኖች ከእግዚአብሔር ጋር ስላለን ግንኙነት ያልተገነዘቡት ነገር ምንድን ነው? ሐ) እነዚህ ሰዎች ስለ መላእክትና ታላላቅ ክርስቲያኖች የያዙት የተሳሳተ ግንዛቤ ምንድን ነው?  ፪) ባቢሎን የወደመችበትን ሁኔታ የሚያሳይ ገለጻ (ራእይ 19፡11-21) ራእይ 16:17-18፡24 ባቢሎን በተለያዩ መልኮች እንደ ወደመች ያሳያል። ነገር ግን እነዚህ ራእዮች ክፋት እንዴት ሊጠፋ እንደ ቻለ በግልጽ አያሳዩም። ራእይ 19፡11-21 ክፉ ፖለቲካዊና መንግሥታዊ ሥርዓቶች እንዴት እንደ ወደሙ ያሳየናል። በዚህም ጊዜ ክርስቶስ የበላይ ሆኖ መንገሡን እንመለከታለን። ይህ ክርስቶስ በሚመለስበት ጊዜ በቀጥታ የሚሳተፍበት ተግባር ነው። ዮሐንስ ታላቁ ሰማያዊ ተዋጊ የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ ከሰማይ ወደ ምድር ሲመጣ ያሳየናል። በዚህ ክፍል ውስጥ የተጠቀሱትን ነገሮች ከዚህ በታች ተመልከት፡- ሀ) ተዋጊው ክርስቶስ የታመነና እውነተኛ ነው። እርሱ በተከታዮቹ የታመነ ሲሆን፥ በበቀል የገደሏቸውን ሰዎች ይቀጣል። እርሱ የሚናገራቸውን ነገሮች ሁልጊዜም ስለሚፈጽም እውነተኛ ነው። ለሰው ልጆች ስለ ዘላለማዊ ፍርድ የሰጠው ማስጠንቀቂያ ደግሞ ይፈጸማል። ለ) የእሳት ነበልባል የሆኑት ዓይኖቹ በጽድቅ ቁጣና በፍርድ የተሞሉ ናቸው። ሐ) ማንም የማያውቀው ስሙ እርሱ ከማንም እንደሚበልጥ፥ ባሕሪውንና እንደ አምላክ ታላቅነቱን መረዳት ከሰዎች አእምሮ በላይ መሆኑን ያሳያል። መ) ልብሱ በደም ተጨማልቋል። ምንም እንኳ ይህ ክርስቶስ ሰዎችን ለማዳንና በሰይጣን ላይ ለመፍረድ ሥልጣን ያገኘበትን የመስቀል ላይ ሞቱን ሊያመለክት ቢችልም፥ አማኞችን መቅጣቱን በበለጠ የሚያሳይ ይመስላል። ይህም የአንድ ተዋጊ ወታደር ልብሶች በጠላቶቹ ደም እንደሚበላሽ ማለት ነው። ሠ) የሰማይ ሠራዊት ይከተሉታል። እነዚህ መላእክትና ከሰማይ ወደ ምድር ተከትለውት የሚመጡ አማኞች ናቸው። ከእርሱ ጋር የሚመጡት በውጊያው ለማገዝ ሳይሆን፥ ድሉን አብረውት ለማክበር ነው። ምክንያቱም ወደ ኋላ እንደምንመለከተው ክርስቶስ ጠላቶቹን ሁሉ በአንድ ትእዛዝ ቃል ብቻ ያጠፋቸዋል። ረ) የጦርነቱ መሣሪያ የክርስቶስ የትእዛዝ ሰይፍ ነው። እርሱ እጅግ የሚበልጥ በመሆኑ ውጊያው በእኩልነት ላይ የተመሠረተ አይደለም። (የኃይል ሚዛኑ አይመጣጠንም)። ክርስቶስ እርሱን ለመውጋት የተሰበሰቡትን ክፉ ገዢዎችም አይፈራም። ጦርነቱ የሚጠናቀቀው በሰይፍ በመጨፋጨፍና የኋላ ኋላም ጠላት ድልን በመንሣቱ ሳይሆን፥ በክርስቶስ ኃይለኛ የትእዛዝ ቃል ነው። የክርስቶስ ኃይል እንዲህ ነው። ሰ) እርሱ የነገሥታት ንጉሥና የጌቶች ጌታ ነው። ክርስቶስ ሁሉንም ነገሥታትና ጌቶች በሰማይም ሆነ በምድር ይቆጣጠራል።  የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ከእነዚህ ጥቅሶች ስለ አዳኛችን ኃይል ምን እንማራለን? ለ) ይህ ከሰይጣን፥ ከክፋት፥ እንዲሁም በምድር ላይ ካሉት ክፉ ሰዎች ጋር በምናደርገው ጦርነት ውስጥ ማበረታቻን የሚሰጠን እንዴት ነው?  ዮሐንስ ክርስቶስ ለተለያዩ የሕዝብ ቡድኖች የሰጠውን ትእዛዝ ውጤት ይገልጻል፡- ሀ) ክርስቶስ በሕይወታቸው ውስጥ እንዲገዛ የማይፈቅዱትን ሰዎች ከመሪዎች እስከ ዝቅተኛ ባሪያዎች፥ ከታላላቆች እስከ ታናናሾች ድረስ በኃያል ትእዛዙ ይገድላቸዋል። ለዚህም ነው አሞራዎች የወደቁትን ሰዎች እንዲበሉ የተጠሩት። ይህ ክፉዎች አካላዊ ሞት እንደሚጠብቃቸውና የመቀበርም ዕድል እንደማያገኙ ያሳያል። ውድመታቸው ከፍጻሜ ይደርስና ለታላቅ

የክርስቶስ ምጽአት (ራእይ 19:1-21) Read More »

የባቢሎን ጥፋት (ራእይ 17:1-18:24)

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ዘፍጥ. 11፡1-9 አንብብ። ባቢሎን በመባል በምትታወቀው ሰናዖር ላይ ምን ተከሰተ? ለ) ከመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት ስለ ባቢሎን የተጻፈውን አንብብና ስለ ባቢሎን ታሪክ በተለይም ከእግዚአብሔር ሕዝብ ጋር ስላላቸው ግንኙነት ማጠቃለያ ጻፍ። ሐ) ራእይ 17-18ን አንብብ። ስለ ባቢሎን የተጻፈውን ገለጻና እግዚአብሔር ባለው መሠረት የተፈጸመውን አሳብ ዘርዝር። ራእይ 17-18 በባቢሎን ላይ ሊሆን ስላለው ነገር በሁለት አቅጣጫ ይጽፋል። ራእይ 17 ከሃይማኖታዊ እይታ አንጻር ስለጠፋችው ባቢሎን ይናገራል። ራእይ 18 ደግሞ የንግድ ማዕከል በነበረችው ባቢሎንና ለኑሮአቸውና ለብልጽግናቸው ሲሉ የተደገፏት ሕዝብ በሚሰጡት ምላሽ ላይ ያተኩራል።  ባቢሎን ግን ማንን ትወክል ይሆን? ዮሐንስ በብሉይ ኪዳን ዘመን በኤፍራጥስ ወንዝ አካባቢ የጥንት ሥልጣኔ ማዕከል የነበረችውን ነባራዊዋን ባቢሎንን እየገለጸ ነው? ወይስ ተምሣሌታዊ ገጽታ ስላላው ሌላ ነገር እየተናገረ ነው? ተመራማሪዎች ሦስት የተለያዩ አመለካከቶች አሉአቸው? አንደኛ፥ ዮሐንስ ስለ ነባራዊዋ ባቢሎን እንደተናገረ የሚያምኑ ጥቂት ተመራማሪዎች አሉ። የባቢሎን ከተማ የረጅም ጊዜ ታሪክ ያላት ናት። ለመጀመሪያ ጊዜ የተጠቀሰችው በዘፍጥ. 11፡1-9 ሰናዖር በሚለው ስሟ ነው። ይህቺም ከተማ ከጥፋት ውኃ በኋላ ሰዎች ስማቸውን ለማስጠራት እስከ ሰማይ የሚደርስ ግንብ የገነቡባት ስፍራ ናት። በዚህም ምክንያት እግዚአብሔር ቋንቋቸውን በመለወጥ በምድር ዙሪያ ሁሉ በተናቸው። ወደ በኋላ ባቢሎን ኢየሩሳሌምንና መቅደሱን በማፍረስ ብዙ አይሁዶችን በ586 ዓ.ዓ ወደ ምርኮ በመውሰዷ የአይሁዶች ዋነኛ ጠላት ሆናለች። ከዚያም በኋላ ለአንድ መቶ ዓመታት ያህል አስፈላጊ ብትሆንም፥ በኋላ የሜዶንና የፋርስ መንግሥታት አሸንፈዋታል። በዚህም ምክንያት በኢሳይያስ በተነገረው ትንቢት መሠረት ፈራረሰች (ኢሳ. 13)። በአዲስ ኪዳን ዘመን ባቢሎን በአካባቢዋ ከሚኖሩ ጥቂት መንደርተኞች በስተቀር የፈራረሰች ከተማ ነበረች። የሆነ ሆኖ ግን፥ በመጨረሻው ዘመን የክርስቶስ ተቃዋሚ ከተማይቱን መልሶ በማቋቋም የግዛቱ ማዕከል እንደሚያደርጋት የሚያምኑ አንዳንዶች አሉ። ይህ እውነት ከሆነ ራእይ 17–18 የሚገልጸው የክርስቶስ ተቃዋሚን የግዛቱን ዋና ከተማ ጥፋት ነው ማለት ነው። ሁለተኛ፥ ባቢሎን በአዲስ ኪዳን ዘመን የነበረችውን ሮምን በተምሳሌትነት የምታመለክት ናት ብለው የሚያምኑ ጥቂት ሰዎችም አሉ። በአዲስ ኪዳን ዘመን በነበሩት ሌሎች የአይሁዶችና የክርስቲያን ሥነ ጽሑፎችም ውስጥ ባቢሎን የሮም ተምሳሌት ነበረች። ሮም የአይሁዶች ጠላት ስትሆን፥ በ70 ዓ.ም ኢየሩሳሌምንና መቅደሱን አፍርሳለች፡፡ ይህም ባቢሎን በኢየሩሳሌምና በቤተ መቅደሱ ላይ ካደረገችው ጋር ተመሳሳይነት አለው። በተጨማሪም እርሷ የእግዚአብሔር ሕዝብ የሆኑትን አይሁድንና ክርስቲያኖችን ያሳደደች መንግሥት ናት። ከዚያም በኋላ በ1ኛ ጴጥሮስ 5፡13 ጴጥሮስ ባቢሎን የሚለውን ስም የተጠቀመው ሮምን ለማመልከት ሳይሆን አይቀርም። ስለሆነም፥ ብዙ ምሁራን ዮሐንስ የሮምን ውድመት እያመለከተ መሆኑን ይናገራሉ። ሦስተኛ፥ በይበልጥ፥ ባቢሎን እግዚአብሔርን የሚቃወሙትን ሁሉ በተምሳሌትነት የምታመለከት ይመስላል። በሰይጣን ቁጥጥር ሥር ውሎ ሰዎችን የሚያታልለውን የትኛውንም ሃይማኖት ትወክላለች። እውነትንና የእግዚአብሔርን ሕዝብ የሚቃወም መንግሥት የሚኖርባትን (እንደ ሮም ያለች) ከተማ ታመለክታለች። በዚህ መልኩ ሮም በአንድ በኩል ባቢሎን መሆኗን እንመለከታለን። ነገር ግን ከሁሉም የከፋችው ባቢሎን ዓለም በሙሉ እግዚአብሔርን እንዲዋጋ የሚያስተባብረው ሐሳዊ መሢሕ መንግሥት ትሆናለች። ስለሆነም ዮሐንስ ባቢሎን እንደምትወድቅ ሲገልጽ፥ በእግዚአብሔርና በመንገዶቹ ላይ የሚያምጹ ሁሉ እንደሚወድሙ መግለጹ ነው። ይህም ማለት የውሸት ሃይማኖቶች፥ ክፉ የመንግሥት ሥርዓቶች፥ ቁሳዊ ኢኮኖሚዎች፥ ወዘተ… ይጠፋሉ ማለት ነው። የሐሳዊ መሢሕ የመጨረሻው መንግሥት ዓለም እስከ አሁን አይቶት የማያውቀው ክፉ በመሆኑ፥ በዚህ ስፍራ በቀዳሚነት የተጠቀሰው ባቢሎን ይኸው ነው። ብዙ ምሁራን ዮሐንስ ሁለት ተምሳሌታዊ ከተሞችን እያነጻጸረ ነው ይላሉ። አንደኛዋ የክፋት ተምሳሌት የሆነችው ባቢሎን ናት። ይህች ከተማ በሰይጣን ቁጥጥር ሥር ውላ ሁልጊዜም የእግዚአብሔርን መንገድ እየተቃወመች የሰዎችን መንገድ ከፍ ከፍ ታደርጋለች። ሌላዋ እግዚአብሔር የሚቆጣጠራቸውና እርሱን የሚያከብሩ ነገሮች ሁሉ ተምሳሌት የሆነችው አዲሲቱ ኢየሩሳሌም ነች። አዲሲቱ ኢየሩሳሌም እግዚአብሔር በንግሥና የሚገዛባትና ሰዎች እርሱን እየታዘዙ የሚያከብሩባት ከተማ ነች። ለዘላለም የምትኖረው ይህቺው ኢየሩሳሌም ናት። ዮሐንስ ቀደም ሲል ስለ ባቢሎንና ስለሚደርስባት ፍርድ ሁለት ጊዜያት ጠቅሷል (ራእይ 14፡8፤ 16፡19)። የመጨረሻው የጽዋ ፍርድ ስለ መውደሟ ይናገራል። ራእይ 17–18 ስለ ታላቂቱ ባቢሎንና እግዚአብሔር ስለሚያመጣባት ውድመት ተጨማሪ ገለጻዎችን ያቀርባል።  ፩. ሃይማኖታዊዋ ባቢሎን፡ ከአውሬው ላይ የተቀመጠችው ሴት (ራእይ 17)  የውይይት ጥያቄ፡- ሃይማኖትና መንግሥታት በእግዚአብሔር ሕዝብ ላይ ስደት ለማምጣት እንዴት አብረው ሲሠሩ እንደተመለከትክ ግለጽ። ቀደም ሲል እንደተመለከትነው፥ ብዙውን ጊዜ ሐሰተኛ ሃይማኖትና ክፉ መንግሥታት እግዚአብሔርና ሕዝቡን ለመውጋት አብረው ይሠራሉ። ዮሐንስ ይህንን እውነት የአንዲትን ጋለሞታ ሴት ተምሳሌታዊ ራእይ በማቅረብ ያብራራል። ይህች ሴት ጋለሞታ የተባለችው ሰዎችን ከእውነተኛ ፍቅርና ለእግዚአብሔር ታማኝ ከመሆን ስለምትመልስ ነው። ይህቺ ሴት በብዙ ውሆች ላይ ትቀመጣለች። ይህም በሁሉም አገር ውስጥ እንደምትገኝ ያመለክታል። ሴቲቱ የተቀመጠችበት ቀይ አውሬ የስድብ ስሞች የሞሉበት፥ ሰባት ራሶችና አሥር ቀንዶች ያሉት ነው። ሃይማኖታዊዋ ባቢሎን ከፖለቲከኛዋ ባቢሎንና ከዘንዶው ጋር የጠበቀ ቁርኝት አላት። ሁሉም ተመሳሳዮች ናቸው። ይህቺ ጋለሞታ የሐሳዊ መሢሕን ያህል ሥልጣንና ኃይል አላት። ሴቲቱ እንደ ዘንዶው ማለትም እንደ ሰይጣን ናት። ዘንዶው ወይም ሰይጣን ከእግዚአብሔር ጋር በሚያደርገው ውጊያ እንድታግዘው ባሕሪውንና ኃይሉን ይሰጣታል። ይህቺ ሴት በሐምራዊ፥ በወርቅና በከበሩ ድንጋዮች አጊጣለች። ይህም ይህቺ ሴት የተከበረችና እንደ ንግሥት የምትታይ መሆኗን ያመለክታል። ከተከታዮቿ ባገኘችው ሀብት በልጽጋ ነበር። (አብዛኞቹ የሐሰተኛ ሃይማኖት መሪዎች ወደ ብልጽግናው ያደላሉ። ይህ ሐሰተኛ ሃይማኖት እንደ አብዛኞቹ ሐሰተኛ ሃይማኖቶች ሁሉ ውጭው ሲታይ የተከበረ ይመስላል። በውስጡ ግን ታላቅ ክፋት ተሰውሯል። ይህንን አክራሪ ሙስሊሞች እነርሱ የሚፈልጉትን ነገር የማያደርጉትን በሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ከሚገድሉበት ወይም ክርስትና የመንግሥት ሃይማኖት በመሆን በመሪዎቹ አማካኝነት የተለየ አሳብ የሚይዙትን ሰዎች ከሚገድልበት (እንደ መስቀል ዘመቻ ዘመን) ሁኔታ ጋር የሚመሳሰል ነው። ይህ ሃይማኖት ምንም ዓይነት ስም ይኑረው ለክርስቶስ ምስክርነት የሚሰጡትን ቅዱሳን ደም የሚያፈስ የእግዚአብሔር ሕዝብ ጠላት ነው። መልአኩ ጋለሞታይቱ ከተቀመጠችበት አውሬ ጀምሮ ራእዩን ያብራራል። ዮሐንስ ስለ አውሬው የሚናገረውን ሁሉ መረዳቱ አስቸጋሪ ነው። ምክንያቱም ተምሳሌቱ መንግሥትንም ሰውንም ያመለክታልና ነው። እንዲሁም ተምሳሌቱ በዮሐንስ ዘመን የሮምን መንግሥት፥ እንዲሁም በሐሳዊ መሢሕ ፍጻሜውን ወደሚያገኝበት የመጨረሻው ዘመን የሚያመለክት ይመስላል። የዚህ ራእይ አያሌ ገጽታዎች ከዚህ በታች ቀርበዋል። ሀ) “አስቀድሞ ነበር፥ አሁንም የለም፥ ከጥልቁም ይወጣ ዘንድ አለው። ወደ ጥፋትም ይሄዳል።” አንዳንድ ሰዎች ይህ ክፋት በሃይማኖትና በመንግሥታት ውስጥ የሚኖር መሆኑን ያሳያል ይላሉ። ሰዎች ምንም ያህል ክፋትን ለማጥፋት ቢታገሉም፥ ሁልጊዜም ተመልሶ ይመጣል። ክፋት ሙሉ በሙሉ የሚደመሰሰው በክርስቶስ ዳግም ምጽአት ብቻ ነው። ይህ ምናልባትም በራእይ 13 እንደ ሞተና ከዚያም ነፍሰ እንደ ዘራ የተመለከትነውን ከባህር የወጣ አውሬ ወይም ሐሳዊ መሢሕን የሚያመለክት ይሆናል (ራእይ 13:3-4)። ለ) ሰባቱ ራሶች ሰባት ኮረብቶችና ሰባት ነግሥታት ናቸው። ከሰባቱ ነገሥታት አምስቱ ቀደም ሲል ሞተዋል። አንዱ በሥልጣን ላይ ነው። ሌላኛው ደግሞ ገና ወደ ፊት ይመጣል። ከዚያም ከሰባተኛው ንጉሥ የሚመጣው ስምንተኛው ንጉሥ ሐሳዊ መሢሕ ይሆናል። የሮሜ ከተማ መጀመሪያ በሰባት ኮረብታዎች ላይ እንደ ተመሠረተች ከታሪክ እንረዳለን። ይህም በዚህ ስፍራ የተገለጸችው ሮም እንደሆነች የሚያመለክት ይመስላል። ይህ አስቸጋሪ ገለጻ ምሁራን የተለያዩ አመለካከቶችን እንዲይዙ አድርጓቸዋል። አንዳንዶቹ ዮሐንስ ከእርሱ በፊት ስለነበሩት አምስት ነገሥታት፥ በዘመኑ ስለነበረው አንድ ንጉሥና ከእርሱ በኋላ ስለሚመጡ ሁለት ነገሥታት፥ በአጠቃላይም ስምንት የሮም ነገሥታት እየተናገረ ነው ይላሉ። ሌሎች ሰባት ነገሥታት ከምድር የሚነሡ ዓለማዊ መንግሥታት መሆናቸውን ይናገራሉ። እነዚህም ከዮሐንስ ዘመን በፊት አምስቱ (እንደ ግብጽ፥ አሶር፥ ባቢሎን፥ ሜዶንና ፋርስ፥ ግሪክ)፥ የሮም መንግሥት እንዲሁም የሐሳዊ መሢሕ መንግሥት የሚመነጭበት ሌላ መንግሥት ናቸው። አሁንም ሌሎች ዮሐንስ በተምሳሌታዊ መልኩ የክፋትን ኃይል እያመለከተ ነው የሚሉ አሉ። ክርስቶስ በመስቀል ላይ በሞተ ጊዜ የክፋትን ኃይል አሸንፎአል። አማኞችም ለክርስቶስ በመታዘዛቸው ምክንያት ነፍሳቸውን አሳልፈው እየሰጡ ክፋትን ያሸንፋሉ (ራእይ 12፡11)። በዮሐንስ ዘመን ግን ክፋት አሁንም በሮም መንግሥት ውስጥ ነግሦ አማኞችን በማሳደድ ላይ ነበር። ነገር ግን ወደፊት የሚኖረው አንድ የክፋት ራስ ብቻ ነበር። ይህም የሐሳዊ መሢሕ መንግሥት ነው።

የባቢሎን ጥፋት (ራእይ 17:1-18:24) Read More »

ሰባቱ የጽዋ ፍርዶች (ራእይ 15:1-16:21)

የዘፍጥረት መጽሐፍ ትልቅ ውበትን በመግለጽ ይጀምራል። እግዚአብሔር በብርሃን፥ በእንስሳትና በሰዎች፥ እንዲሁም በአትክልት ስፍራ የተዋበች ዓለም ፈጥሯል። ከዚህም በላይ እግዚአብሔር በተደጋጋሚ የኤድን ገነት ነዋሪዎች ከሆኑት ወንድና ሴት ጋር እየተገናኘ ይወያያል። በመካከላቸውም ምንም ዓይነት መጋረጃም ሆነ ኃፍረት አልነበረም። ያ ሁሉ ውበት አዳምና ሔዋን እግዚአብሔር በሕይወታቸው ላይ የነበረውን ቁጥጥር በመቃወማቸው ከመቅጽበት ተናደ። በዚህም ጊዜ ያ ሁሉ ውበት በኃጢአት ቆሸሸ። ይህም እሾሆች፥ ላብ ጠብ የሚያደርግ ብርቱ ሥራ፥ የወሊድ ምጥና ሞት፥ ግድያ፥ ወሲባዊ ኃጢአት፥ ጦርነቶች፥ ወዘተ… እንዲስፋፉ አደረገ። በሕይወት ውስጥ የሚያጋጥሙን ችግሮች ሁሉ የመነጩት በዘፍጥረት ውስጥ ከተከሰተው ዐመፅ ነው። የዮሐንስ ራእይ የዘፍጥረት መጽሐፍ ከተጀመረበት ሁኔታ ጋር በሚቃረን መልኩ ይጠናቀቃል። ራእይ የሚጀምረው በኃጢአት፥ ዐመፅ፥ ጦርነቶች፥ የተፈጥሮ አደጋና በታሪክ በማንኛውም ስፍራ ከታየው ሁሉ በላቀ ክፋት ነው። ነገር ግን ያ ሁሉ ይወገዳል። እንዲሁም በድጋሚ አንድ ጊዜ፥ ውበትና ግልጽ የሆነ ግንኙነት ከአምላካችን ጋር እናደርጋለን። ማንኛውም የሥቃይ ስሜት የሚያመጣብን ምድራዊ ነገር ሁሉ ይወገዳል። ይህ አዲስ ሰማይና ምድር ምን እንደሚመስል ወይም የመጀመሪያዋን ምድር የምትመስል ትሁን ወይ ሌላ ሙሉ ለሙሉ አናውቅም። ነገር ግን እኛ ከምንገምተው ከማናቸውም ነገሮች በላይ ውብ እንደምትሆን እናውቃለን። አሁን የምንኖርባት ምድር እንኳን በኃጢአት ከተበከለችበት ሺህ ዓመታት በኋላ እንኳን ውብ ናት፥ ፈጽሞ የምትታደሰው አዲሲቱ ምድር ምን ልትመስል እንደምትችል እስኪ አስብ! ምንም ሥቃይ የሌለበት ዓለም ምን ይመስል ይሆን? ከሁሉ በላይ ደግሞ ከእግዚአብሔር ጋር ያለ ምንም የኃጢአት ጋሬጣና ግድግዳ እንዲሁም ያለ አንዳች እፍረት ፊት ለፊት የምንገናኝበት ዓለም ምን ሊመስል እንደሚችል ገምት። ወንድሞችና እኅቶች፥ ዮሐንስ ስለ አዲሲቱ ሰማይና ስለ አዲሲቱ ምድር እንድናስታውስ ይፈልጋል። ምክንያቱም ያ ቋሚ መኖሪያችን ነው። በዚህን ሰዓት በእምነት ጉዞ ላይ እንገኛለን። እውነት ነው በአሁኑ ዓለም ውስጥ በኃጢአትና በበሽታ ምክንያት እንቸገራለን። በተጨማሪም የክፉ መሪዎችና የአስጨናቂ ሃይማኖቶች ጊዜ ይሆናል። ነገር ግን በታማኝነት ክርስቶስን ብንከተልና ብንጸና፥ አንድ ቀን ይህ ሁሉ ችግር ልንገልጸው እስከማንችል ድረስ ወደ ክብር ይለወጣል።  የውይይት ጥያቄ፡– ራእይ 15-16 አንብብ። እግዚአብሔር በምድር ላይ በመጨረሻው ጊዜ ላይ የሚያመጣውን የመጨረሻ ፍርድ ግለጽ።  የመጨረሻው የፍርድ ጊዜ ፍጻሜ በደጅ ነው። ታላቁ መከራም በመጠናቀቅ ላይ ነው። ከዚህ በኋላ በምድር ላይ የሚመጣው አንድ ቀጣይነት ያለው ታላቅና መጥፎ የፍርድ ጊዜ ብቻ ነው። የዮሐንስ ራእይ የእግዚአብሔር ዙፋን ወዳለበት ሰማያዊ ክፍል ይመለሳል። በዚያም ሕዝብ በዙፋኑ ፊት ቆሞ ያያል። አማኞች አሸናፊዎች ናቸው። ሰይጣን ሐሰተኛው ነቢይና ሐሳዊው መሢሕ እምነታቸውን ለማስጣል ካመጡባቸው ፈተናዎች በተቃራኒ ታማኝ ሆነው በመቆማቸው ምክንያት አሸንፈዋል። ክርስቲያኖች ለማመቻመችና እንደ ምስል ላሉ ለማናቸውም ነገሮች ላለመስገድ ወስነዋል። የአውሬውን ምልክት በመቀበል የዓለም ሥርዓትን አስተናግደው ለዓለም ታማኝነታቸውን ለማሳየት አልፈለጉም። እነዚህ ቅዱሳን ስደትና የኑሮ ጉድለት አጎሣቁሏቸው ነበር። አሁን ግን በእረፍት ላይ ናቸው። ይህም እግዚአብሔር የሚበቀልበት፥ የክርስቶስን ጠላቶች የሚያጠፋበትና መንግሥቱን የሚመሠርትበት ጊዜ ነው። የእግዚአብሔር መንገዶች ትክክል በመሆናቸው ምክንያት አማኞች በታላቅ የውዳሴ ዝማሬ እግዚአብሔርን ያመልኩታል። ከዐመፅና ከመከራ ውስጥ ውበትን ማውጣት የሚችል እግዚአብሔር ብቻ ነው። እነዚህ ክርስቲያኖች አሁን እግዚአብሔር በሁሉም ዘንድ ክብርን እንደሚያገኝ ያውቃሉ። ዐመፅ ይቆማል። «የምስክሩ ማደሪያ» ከሚባለው ዙፋንም የመጨረሻዎቹ የእግዚአብሔር የቁጣ ጽዋዎች ፍርዶች ለሰባት መላእክት ተሰጡ። ከእነዚህ ፍርዶች መካከል አንዳንዶቹ ከመለከት ፍርዶችና በሙሴ ዘመን በግብጽ ምድር ላይ ከወረዱት መቅሠፍቶች ጋር ይመሳሰላሉ። እነዚህ ፍርዶች በቅደም ተከተል ደረጃ ከመምጣት ይልቅ ከመቅጽበት አንዱ በአንዱ ላይ እየተደራረበ ይመጣል። የመጀመሪያ ጽዋ፡- የአውሬው ምልክት ባለባቸው ሰዎች ላይ የሚመጣ ቁስል። እንደ ግብጹ መቅሠፍት ሁሉ (ዘጸ 7-11)፥ አንዳንዶቹ ፍርዶች ማኅተም ያለባቸውን የእግዚአብሔር ልጆችና የአውሬውን ምልክት የተቀበሉትን ያላመኑ ሰዎች ለመለየት እንደሚያገለግሉ ዮሐንስ ያሳየናል። በዚህ ቁስል የሚመቱት የእግዚአብሔር ተቃዋሚዎችና የአውሬውን ምልክት የተቀበሉት የሰይጣን ግብረ አበሮች ብቻ ናቸው። ሁለተኛዋ ጽዋ፡- የባሕር ውኃ ሁሉ ወደ ደም መለወጥ። አስቀድመን የባሕር ሲሶ በፍርድ ውስጥ መመረዙን አይተናል። ይህም 2/3ኛው ለሰው ልጆች ተስማሚ እንደነበር ያሳየናል። አሁን ግን እግዚአብሔር በባሕር ውስጥ ያሉትን ፍጥረታት በሙሉ ያጠፋል። ከዚያ በኋላ በባሕር ላይ የመርከብ ላይ ጉዞ አይኖርም። በባሕር ዳርቻ ላይ ለሚኖሩም ከባሕር ውስጥ የሚገኝ ምግብ አይኖርም። ሦስተኛው ጽዋ፡- የማንኛውም ንጹሕ ውኃ ወደ ደም መቀየር። ይህም መቅሠፍት ልክ እንደ ሁለተኛው ጽዋ ሁሉ ከመለከት ፍርዶች የከፋ ነበር። ምክንያቱም መለከት ፍርድ ላይ 1/3ኛው ንጹሕ ውኃ ብቻ ሲበከል፥ አሁን ግን በጽዋው ፍርድ የውኃ ዘር የተባለ ሁሉ ይበከላል። መልአኩም ይህንን ፍርድ ተስማሚ ፍርድ ይለዋል። እርኩሳን የእግዚአብሔርን ሕዝብ ደም አፍስሰዋል። አሁን ግን በእግዚአብሔር ፍርድ አማካኝነት ደሙን እንደ ውኃ ይጠጣሉ። አራተኛው ጽዋ፡- የፀሐይ ሰዎችን ማቃጠል። በአንድ በሆነ ምክንያት የፀሐይ ኃይል በብዛት ይጨምርና ሰዎችን ማቃጠል ይጀምራል። (ማስታወሻ፡- እነዚህ እግዚአብሔር ለሰው ልጆች የሚሰጣቸው የመጨረሻ ማስጠንቀቂያዎች ሲሆኑ ከመጨረሻው ጊዜ በፊት የሚሆን የንስሐ ዕድል ነው። ነገር ግን ሰዎች ምላሽ የሚሰጡት በምን መንገድ ይሆን? ከእርኩሰታቸው ተመልሰው እግዚአብሔርን ያመልኩት ይሆን? በጭራሽ፥ የተነገረን እነዚህ ፍርዶች የመጡት ከእግዚአብሔር ዘንድ መሆኑን እያወቁ እግዚአብሔርን እንደሚራገሙ ነው።) አምስተኛው ጽዋ፡- ጨለማና ሥቃይ። የክርስቶስ ተቃዋሚ እግዚአብሔር ነኝ ብሎ ይኩራራል። ሰዎችም ያመልኩት ዘንድ ያስነግራል። የሁሉም ነገሮች ተቆጣጣሪ እንደሆነም ያውጃል። ሆኖም ግን የእግዚአብሔር ሰዓት ሲደርስ የእግዚአብሔር ፍርድ በክርስቶስ ተቃዋሚ፥ በቤተ መንግሥቱና በግዛቱ ሁሉ ላይ ይወድቃል። በመንግሥቱ ሁሉ ላይ ጨለማ ሲከብድ፥ በዚያ ውስጥ የሚኖሩ ሰዎች የመጀመሪያው የጽዋ ፍርድ ቁስል ይሰማቸዋል። እንደገናም ሕዝቡ ንስሐ ገብቶ ወደ እግዚአብሔር እንደማይመለስ ተነግሮናል። የሰው ልብ ምንኛ ጠንካራ ነው! ስድስተኛ ጽዋ፡- ለአርማጌዶኑ ጦርነት የተደረገ የሕዝብ ስብሰባ። በእግዚአብሔር ትእዛዝ ክፉ መናፍስት ከዘንዶው፥ ከአውሬውና ከሐሰተኛው ነቢይ አፎች ውስጥ ይወጣሉ። እነርሱም ከእግዚአብሔር ጋር የሚዋጉበት ሰዓት እንደ ደረሰ ያውቃሉ። እነዚህም እንቁራሪት መሣይ ክፉ መናፍስት የምድር ነገሥታትና እርኩሳት መናፍስትን ሁሉ አርማጌዶን ለተባለው ጦርነት እንዲሰበሰቡ ያሳምናሉ። አንዳንድ ተመራማሪዎች አርማጌዶን፥ የእግዚአብሔርን ቀንና እግዚአብሔር ከጠላቶቹ ጋር የሚያደርገውን የመጨረሻ ጦርነት በተምሳሌትነት ብቻ እንደሚያሳይ ያምናሉ። ሌሎች ተመራማሪዎች ግን አርማጌዶን በሰሜን እስራኤል የሚገኝና የመጨረሻውም ጦርነት በትክክል የሚካሄድበት ስፍራ እንደሆነ ያስባሉ። ሰባተኛው ጽዋ፡- እግዚአብሔር በሰው ዘር ሁሉ ላይ ታላቅ የመሬት መንቀጥቀጥንና በረዶን ያመጣል። (ማስታወሻ፡- ይህ ሰባተኛው ፍርድ እንደ ፍርድ የተገለጠበት የመጀመሪያ ጊዜ ነው።) እግዚአብሔር «ተፈጸመ» ብሎ ሲናገር፥ ይህንን የታላቅ ፍርድ ጊዜ ወደ ፍጻሜው አመጣለሁ ማለቱ ነው። በዓለም ታሪክ የምናውቀው የሰዎች የበላይነት አሁን ፍጻሜውን አገኘ። አሁን ጊዜው፥ ኢየሱስ የሚመለስበትና መንግሥቱንም የሚመሠርትሰት ነው። አሕዛብ፥ ቅኝ ግዛቶችና «የታላቂቱ ባቢሎን» ተምሣሌቶች የሆኑት የዓለም ከተማዎች ሁሉ ጠፍተዋል። እስከ መጨረሻው ድረስ የሰው ዘር ለንስሐ ማመፅና በተስፋ ቢስ ቁጣ እግዚአብሔርን መራገምን ተያይዞታል። የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ሰዎች ለመጨረሻው የእግዚአብሔር ፍርድ ከሚሰጡት ምላሽ በመነሣት ስለ ሰዎች የልብ ድንዳኔ ምን ልንማር እንችላለን? ለ) እግዚአብሔር ሰዎች ወደ እርሱ እንዲመለሱ በፍርዶች አማካኝነት ሲያስጠነቅቃቸው አብዛኛዎቹ ሰዎች ለምን ንስሐ እንደማይገቡ ግለጽ? (ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

ሰባቱ የጽዋ ፍርዶች (ራእይ 15:1-16:21) Read More »

በመንፈሳዊ ውጊያ ውስጥ የሚሳተፉ ቁልፍ ግለሰቦች (ራእይ 12:1-14:20) 

የውይይት ጥያቄ፡– ራእይ 12-14 አንብብ። ሀ) በዚህ ክፍል በቀረቡት ራእዮች ውስጥ የተገለጹትን እያንዳንዳቸውን ገጸ ባሕርያት ዘርዝር። እያንዳንዳቸው እንዴት የተለዩና ከሌሎች ጋር ግንኙነት ያላቸው መሆናቸውን ግለጽ። ለ) ይህ ክፍል ስለ እግዚአብሔር አብና ወልድ ምን ያስተምረናል? ሐ) ስለ አማኞች ምን እንማራለን? ዛሬ በምድር ላይ የሚፈጸሙትን ነገሮች ማለትም እንደ ስደት፥ ረሃብና ጦርነት የመሳሰሉትን እንዴት ልንረዳቸው ይገባል? ክርስቶስ ሊመለስ ሲል በዓለም ላይ የሚሆነው ሁኔታ ምን ይመስላል? ዮሐንስ እግዚአብሔር ወደ ምድር ስለሚልካቸው የመጨረሻዎቹ ተከታታይ ፍርዶች ከመግለጹ በፊት፥ ወደ ፊት ቁልፍ ሚና በሚጫወቱ ግለሰቦች ላይ ያተኩራል። ነገር ግን የእነዚህ ግለሰቦች ባሕርያት ሙሉ በሙሉ በመጨረሻው ዘመን የሚታይ ቢሆንም፥ አሁንም በመጠኑ እየታየ መሆኑ ግልጽ ነው። ፩. በሴቲቱና በዘንዶው መካከል የተደረገ ጦርነት (ራእይ 12) ዮሐንስ ይህንን ራእይ «ታላቅ ምልክት» ሲል ይጠራዋል። ምልክት ከክስተት ወይም ከራእይ በስቲያ ያሉትን አስደናቂ ክስተት ወይም ራእይ ነው። ለምሳሌ ያህል፥ ብዙዎቹ የኢየሱስ ክርስቶስ ተአምራት ምልክቶች ተብለው ይጠራሉ። ለዚህም ምክንያቱ እነዚህ ነገሮች ምን እንደ ተከሰተ የሚያሳዩ ታሪኮች ብቻ ሳይሆኑ፥ ክርስቶስ እንደ ሞት ባሉት ነገሮች ላይ መለኮታዊ ኃይል እንዳለው የሚያሳዩና መሢሕነቱን የሚገልጹ መሆናቸው ነው (ዮሐ 6፡30)። በዚህ የራእይ ምልክት ዮሐንስ ሴቲቱና ልጁ ከዘንዶው ጋር ያደረጉትን ትግል ያመለክታል። ዮሐንስ በዚህ ራእይ ላይ ባለ 12 ከዋክበት አክሊል የደፋች እርጉዝ ሴት ይመለከታል። ይህች ዙፋን የሚወርስ ወንድ ልጅ ልትወልድ ያለች ሴት ማን ነበረች? ሦስት አመለካከቶች አሉ። መጀመሪያ፥ አንዳንዶች ይህቺ ሴት የክርስቶስ እናት የሆነችው ማርያም ናት ይላሉ። ሁለተኛ፥ ሌሎች ደግሞ የአማኞች ማኅበረሰብና መንፈሳዊት እስራኤል የሆነችው ቤተ ክርስቲያን ናት ይላሉ። ሦስተኛ፥ አሁንም ሴቲቱ መሢሑ የመጣባት እስራኤል ናት የሚሉ አሉ። ትክክለኛው አመለካከት ሁለተኛው ወይም ሦስተኛው ይመስላል። ሴቲቱ ልትወልድ ስትል አንድ ታላቅ ቀይ ዘንዶ መጣባት። ይህ ዘንዶ የእግዚአብሔርና የልጆቹ ጠላት የሆነው ሰይጣን ነው። ዘንዶው ከከዋክብት ሲሶዎቹን ወደ ምድር ጣለ። ይህ ምናልባትም ሰይጣን በኃጢአት የወደቀበትን ሁኔታ የሚያመለክት ሊሆን ይችላል። ሰይጣን ከመላእክቱ ሲሶዎቹን (አንድ ሦስተኛ) ይዞ ወድቋል። ሌሎች ደግሞ ይህ ሰይጣን ብዙ አማኞችን ለመግደል መሞከሩን ያሳያል ይላሉ። ዘንዶው ሰባት አክሊሎች ያሉባቸው ሰባት ራሶችና አሥር ቀንዶች ነበሩት። ይህ ምናልባትም የዘንዶውን ታላቅ ኃይልና ሥልጣን የሚያመለክት ሊሆን ይችላል። ዘንዶው ከሴቲቱ የሚወለደውን የመንግሥት ወራሽ የሆነ ልጅ ለመዋጥ ፈልጎ ከአጠገቧ ቆመ። ወንዱ ልጅ ኢየሱስ ክርስርቶስን ያመለክታል። ሰይጣን ኢየሱስ ክርስቶስን በኃጢአት ፈተናና በመስቀል ላይ ሞት ሊያጠፋው ሞክሯል። ነገር ግን የኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤ ድል ነሺነቱን ያመለክታል። ከዚያም እግዚአብሔር ኢየሱስ ክርስቶስን ከሰይጣን ጥቃት አርቆ ወደ መንግሥተ ሰማይ ወስዶታል። ኢየሱስ ክርስቶስ በእግዚአብሔር መንግሥት ላይ እንዲገዛ የተሰጠውን መብት ማንም አይወስድበትም። ዘንዶው ሴቲቱን ሊያጠፋት ሲፈልግ (ሴቲቱ እስራኤል ወይም ቤተ ክርስቲያን ትሆናለች) እግዚአብሔር ለአንድ ሺህ ሁለት መቶ ስልሳ ቀናት (ዘመን፥ ዘመናትና የዘመን እኩሌታ) በምድረ በዳ ውስጥ ይሸሽጋታል። (ማስታወሻ፡ አንድ ሺህ ሁለት መቶ ስልሳ ቀናት፥ ሦስት ዓመት ተኩል ጊዜን ያመለክታሉ። ይህ ደግሞ ሁለቱ ምስክሮችና ይኼኛው ክስተት በእኩል የጊዜ ርዝመት የሚፈጸሙ መሆናቸውን ያመለክታል።) ዘንዶው ሴቲቱን ሊያጠፋ በሚፈልግበት ጊዜ የተፈጠረች ምድር እንኳን ከእግዚአብሔር ጋር ተባብራ ትረዳታለች። ይህ በሰይጣንና በእስራኤላውያን መካከል የሚካሄደውን ጦርነት የሚያመለክት ከሆነ፥ እግዚአብሔር በመጨረሻው የታላቁ መከራ ዘመን ሰይጣን የእስራኤልን ሕዝብ እንዳይጨርስ የሚከላከል መሆኑን ያሳያል። ሴቲቱ ቤተ ክርስቲያን ከሆነች፥ እግዚአብሔር ሕዝቡን በምድር ላይ ሙሉ ለሙሉ ከመውደም የሚጠብቃቸው መሆኑን ያሳያል። ከሌሎች የዮሐንስ ራእይ ክፍሎች ለመረዳት እንደሚቻለው፥ አማኞች ለእምነታቸው የሚገደሉ መሆኑ ግልጽ ነው። ነገር ግን ሰይጣን ቤተ ክርስቲያንን በአጠቃላይ ሊያጠፋት አይችልም። ምክንያቱም እግዚአብሔር ዛሬም ሆነ በታሪክ ሁሉ፥ እንዲሁም ሐሳዊ መሢሕ አማኞችን ለማጥፋት በሚፈልግበት በመጨረሻው ዘመን ሕዝቡን ይጠብቃል። ዘንዶው ሴቲቱን ለማጥፋት ባለመቻሉ ልጇን ለማጥፋት ይሞክራል። ይህ እስራኤላውያን ወይም የቤተ ክርስቲያን አማኞችን ሊያመለክት ይችላል፥ በአመዛኙ ሁሉንም አማኞች ይወክላል። ዮሐንስ እንዴት እንደሚገልጻቸው ልብ ብለህ ተመልከት። አማኞች የእግዚአብሔርን ትእዛዛት የሚከተሉ ናቸው። መጽሐፍ ቅዱስ የእግዚአብሔር ልጆች ሁልጊዜም እግዚአብሔርን ለመታዘዝ እንደሚተጉ ያስባል። እነዚህ አማኞች የኢየሱስ ክርስቶስን ምስክርነት ይጠብቃሉ። አማኞች በወንጌሉ ላይ ያላችውን ንጹሕ እምነት በመጠበቅ ከስደት ሁሉ ባሻገር ስለ ክርስቶስ ይመሰክራሉ። ሰይጣን የሴቲቱን ልጅ ለማጥፋት የሞከረው እንዴት ነበር? በራእይ 13 ሰይጣን ሌሎች ሁለት ዓይነት ሰዎችን እንደሚጠቀም ተገልጾአል። ከባህር እንደሚወጣ አውሬ የተገለጸው የመንግሥት መሪ አለ። ይህም ሐሳዊ መሢሕ ነው። ከምድር እንደሚወጣ የተገለጸው ደግሞ ሃይማኖታዊ መሪ መሆኑን እንመለከታለን። በምድር ላይ በሰይጣንና በእግዚአብሔር ሕዝብ መካከል ከሚካሄደው ጦርነት በስተጀርባ ሌላ ታላቅ ጦርነት አለ። (በራእይ ምዕራፍ 13 እንደምንመለከተው፥ ሰይጣን የመንግሥትና የሃይማኖት መሪዎችን በመጠቀም ጦርነትን ያካሂዳል።) ይህ በሰይጣንና በኃይሎቹ፥ እንዲሁም በእግዚአብሔርና በኃይሎቹ መካከል የሚካሄድ ታላቅ ጦርነት ነው። የእግዚአብሔር ሠራዊት መሪ የሆነው ሊቀ መልአኩ ሚካኤል ሰይጣንና መላእክቱን ከሰማይ ወደ ምድር ይወረውራቸዋል። ይህ ራእይ መቼ እንደ ተፈጸመ አናውቅም። ነገር ግን ይህ በክርስቶስ መስቀል ላይ የተካሄደውን ጦርነት የሚያመለክት ሊሆን ይችላል። ሀ) ክርስቶስ በሞት ጊዜ የተካሄደ ጦርነት። ክርስቶስ በመስቀል ላይ በሚሞትበት ጊዜ ሰይጣን ድል ያገኘ መስሎት ነበር። ክርስቶስ ከሞት ሲነሣ ግን ሰይጣን በሰው ነፍሶች ላይ ያለውን ኃይል በማጥፋት ድል ነሥቶታል (ቆላ. 2፡15 አንብብ)። ለ) በአመዛኙ ይህ የመጨረሻው ዘመን እጅግ ክፉ የሚሆንበትንና የእግዚአብሔር ሕዝብ ለእምነታቸው የሚሞቱበትን ምክንያት የሚያስረዳ ይመስላል። ፍጻሜው እየተቃረበ በሚመጣበት ጊዜ እግዚአብሔር ሰይጣን ከመንግሥተ ሰማይ እንዲርቅ ያደርገዋል። (ሰይጣን በእግዚአብሔር ዙፋን ፊት እንደሚቀርብ ለመመልከት ኢዮብ 1-2 አንብብ።) ስለዚህ በምድር ላይ ብቻ እንዲሠራ ይገደባል። ሰይጣን አጭር ጊዜ ብቻ እንደቀረው ስለሚገነዘብና እንቅስቃሴዎቹም በምድር ላይ ብቻ በመወሰናቸው፥ የእግዚአብሔርን ዕቅዶችና ሕዝብ ለማጥፋት የሚችለውን ሁሉ ያደርጋል። ነገር ግን የሰይጣን ወደ ምድር መምጣት የፍጻሜው መጀመሪያ ሊሆን፥ ክርስቶስ በሁሉም ላይ የሚነግሥስት ጊዜ መምጣቱን የሚያሳይ ነው። ዮሐንስ በራእይ 12፡10-12 ባቀረበው ታላቅ መዝሙር የሁሉም ዘመን አማኞች በሰይጣን ላይ ድል መቀዳጀት እንዳለባቸው ይናገራል። ይህ በተለይም ሰይጣን የእግዚአብሔርን ሕዝብ ለማጥፋት ተግቶ በሚሠራበት በመጨረሻው ዘመን አስፈላጊ ነው። ለመሆኑ አማኞች ሰይጣንን የሚያሸንፉት እንዴት ነው? ድምጻቸውን ጮክ አድርገው በመጸለይ ይሆን? ወይስ ከአካባቢያቸው እንዲርቅ በመገሠጽ ነው? ወይስ ወደ ጥልቁ እንዲወርድ በማዘዝ? ዮሐንስ ድል የሚያስገኙትን ሦስት ነገሮች ይጠቅሳል። ሀ) የበጉ ደም፡ ሰይጣንን የምናሸንፈው የእግዚአብሔር ልጆች፥ የመንግሥቱ አካሎች በመሆንና በኢየሱስ ክርስቶስ ደም (በክርስቶስ ሞት) በመታመን ነው። በመልካም ሥራችን ድነትን (ደኅንነት) ልናገኝ አንችልም። ነገር ግን የድነትን ነፃ ስጦታ በእምነት እንቀበላለን። ይህም ከሰይጣን መንግሥት አውጥቶ በኢየሱስ ክርስቶስ መንግሥት ውስጥ ያኖረናል። አማኞች ሆነን ኃጢአት ስንፈጽምና ሰይጣን ሲከስሰን፥ የኢየሱስ ክርስቶስ ደም ለኃጢአታችን እንደ ተከፈለና እግዚአብሔርም በነፃ እንዳሰናበተን ልንነግረው እንችላለን። ከእግዚአብሔር ጋር ያለንን ግንኙነት ለማደስ ኃጢአታችንን እንናዘዛለን። ለ) የምስክርነታችን ቃል፡ ስደት ክርስቲያኖች እምነታችንን እንድንደብቅ፥ አፋችንን እንድንዘጋና ምስክርነታችንን እንድናቆም ያደርገናል። ይህ በሚሆንበት ጊዜ ሰይጣን አሸናፊ ይሆናል። ዮሐንስ ሰይጣንን የምናሸንፍበት መንገድ የእግዚአብሔርን ቃል በማወቅና እምነታችንን ለዓለማውያን በማካፈል መሆኑን ይናገራል። ሐ) ለእምነታችን ለመሞት በመፍቀድ፡ ሕይወታችንን በምንወድበት ጊዜ ሰይጣን በብዙ መንገዶች ሊያሸንፈን ይችላል። ገንዘብን በመጠቀም የዓለምን ነገሮች እንድንፈልግ ይማርከናል። የአመራር አገልግሎታችንን በተዛባ መልኩ እንድንጠቀም ያደርገናል። ፈርተን እምነታችንን እንድንደብቅ ስደትን ይጠቀማል። እነዚህ ሁሉ ራስን የመውደድ ምሳሌዎች ናቸው። ነገር ግን ድል የሚገኘው ለእግዚአብሔርና ለመንግሥቱ በመኖር ነው (ማቴ. 6፡33)። ለራሳችን የራስ ወዳድነትና የትዕቢት ፍላጎቶች በምንሞትበት ጊዜ ሰይጣን ሊያሸንፈን አይችልም። በስደት ጊዜ ጸንተን ስንቆምና ለእምነታችን ስንሞት ሰይጣን ሊያሸንፈን አይችልም። ነገር ግን ሊያገኘን ወደማይችልበት ሰማይ ይልከናል። ክርስቶስ በመስቀል ላይ በመሞትና በመነሣት ሰይጣንን እንዳሸነፈ ሁሉ፥ እኛም ሰይጣንን የምናሸንፈው ለክርስቶስ በታማኝነት እየኖርን በመሞትና ለዘላለም ከሞት በመነሣት ነው። የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ብዙውን ጊዜ እኛ ሰይጣንን እናሸንፋለን ብለን የምናስብባቸውን መንገዶች ዮሐንስ ከገለጻቸው ሰይጣንን

በመንፈሳዊ ውጊያ ውስጥ የሚሳተፉ ቁልፍ ግለሰቦች (ራእይ 12:1-14:20)  Read More »

የእረፍት ጊዜ (ራእይ 10፡1-11፡14) እና የሰባተኛው መለከት ፍርድ (ዋይታ 3) ራእይ 11፡15-19

ከበደ ተወልዶ ያደገው በክርስቲያን ቤተሰብ ውስጥ ነው። ነገር ግን የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪ በነበረበት ወቅት ጀርባውን ለክርስቶስ ሰጥቶ እንደ እግዚአብሔር ሕጎች ላለመመላለስ ወሰነ። የዐመፀኝነት መንፈሱን ካሳየባቸው መንገዶች መካካል አንዱ ወሲባዊ ኃጢአቶችን መፈጸም ነበር። በትምህርት ቤት ከተለያዩ ሴት ተማሪዎች ጋር ያመነዝር ነበር። ገንዘብ ሲኖረው ደግሞ ወደ ሴተኛ አዳሪዎች ጎራ ማለቱን ተያያዘው። ብዙውን ጊዜ ይህ ባህሪው የጨብጥ በሽታ ያስከትልበት ነበር። ይህም ከተግባሩ እንዲታቀብ እግዚአብሔር ያስተላለፈለት ማስጠንቀቂያ ነበር። እርሱ ግን የእግዚአብሔርን ማስጠንቀቂያ ለመስማት አልፈለገም። ጊዜው እየገፋ ሲሄድ ከበደ የበሽታ ምልክቶች ይታዩበት ጀመር። መድኃኒት ሲወስድ ትንሽ ይቀልለዋል። ወዲያውኑ ደግሞ ይነሣበታል። ክብደትም መቀነስ ጀመረ። አንድ ጊዜ ሐኪም ቤት ሄዶ ሲመረመር የኤድስ ቫይረስ በደሙ ውስጥ እንዳለበትና በቅርብ ጊዜ እንደሚሞት ተነገረው። አሁንም እግዚአብሔር ለከበደ ስለፈጸማቸው ተግባራት ማስጠንቀቂያ በመስጠት ንስሐ የሚገባበትን ዕድል ሰጠው። እርሱ ግን ወደ እግዚአብሔር እንደ መመለስ የቁጣ ስሜት አደረበት። በእግዚአብሔር ላይ ስለ ተቆጣ ንስሐ ለመግባት አልፈለገም። እንዲሁም አኗኗሩን ለመለወጥ አልፈለገም። ይባስ ብሎ ከሌሎች ሰዎች ጋር ወሲባዊ ግንኙነቶችን በመፈጸም ይህንኑ መድኃኒት የሌለው በሽታ ወደ ተለያዩ ሴቶች ማስተላለፉን ተያያዘው። ከእርሱ ጋር የተኙት ሴቶች ደግሞ የበሽታውን ቫይረስ ለሌሎች ወንዶች ማስተላለፍ ጀመሩ። ከበደ እግዚአብሔር የሰጠውን ማስጠንቀቂያ ለመስማት ቸል ብሎ ሕይወቱን አጥቷል። የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) እግዚአብሔር ሰዎችን አለማመናቸውና ዐመፀኝነታቸው ስለሚያስከትሉባቸው ውጤቶች የሚያስጠነቅቅባቸውን ሌሎች መንገዶች ግላጽ። ለ) ብዙ ሰዎች የእግዚአብሔርን ማስጠንቀቂያ ሰምተው ንስሐ የማይገቡት ለምንድን ነው? ሐ) እግዚአብሔር ሰዎችን ለማስጠንቀቅ አደጋን በመጠቀሙ ስለ ባሕሪው ምን እንማራለን? መ) አደጋ በሚመጣበት ጊዜ ወደ እግዚአብሔር ለመመለስ ካለመፈለጋቸው ስለ ሰዎች ልብ ምን እንማራለን? ከዮሐንስ ራእይ አብዛኛው ክፍል እግዚአብሔር በተለይም በመጨረሻው ዘመን ወደ ምድር በሚልካቸው የተፈጥሮና ሰው ሠራሽ አደጋዎች ፍርዶች ላይ አጽንኦት ይሰጣል። እነዚህ አደጋዎች ሰዎችን ለመቅጣት የታሰቡ ናቸው። እንዲሁም አደጋዎቹ ሰዎች ንስሐ ባይገቡ ዘላለማዊ ሞት እንደሚጠብቃቸው ለማስጠንቀቅ የታሰቡ ናቸው። እግዚአብሔር በምሕረቱ ሁልጊዜም ሰዎች ንስሐ እንዲገቡ እንጂ እንዲሞቱ አይፈልግም (ሕዝ. 18፡21-23 አንብብ)። ነገር ግን የሰዎች ልብ እጅግ ክፉ ከመሆኑ የተነሣ ብዙ ሰዎች አደጋ በሚመጣበት ወቅት ወደ እግዚአብሔር አይመለሱም (ኤር 17፡9)። ነገር ግን ያለ እግዚአብሔር እርዳታ አደጋውን ለማሸነፍና በዐመፀኛነታቸው መንገዳቸው ለመቀጠል ይፈልጋሉ። ሞት በሚመጣበት ጊዜ ንስሐ የምንገባበትን ዕድል እናጣለን። ከዚህ በኋላ የሚጠብቀን ዘላለማዊ ሞትና ሲዖል ይሆናል። ሰዎች ሥራቸው ስለሚያስከትሏቸው ውጤቶች ልናስጠነቅቃቸው አይገባምን? ከዚህ ታላቅ መከራ ለማምለጥ ብቸኛ መንገድ ስለሆነው ክርስቶስ ለሰዎች ልንነግራቸው ይገባል። የውይይት ጥያቄ፡– ራእይ 10–11 አንብብ። ሀ) እግዚአብሔር ለዮሐንስ የሰጠው የመጽሐፍ ጥቅልሉ ጠቀሜታ ምንድን ነው? ለ) ስለ ሁለቱ ምስክሮችና በእነርሱ ላይ ስለተፈጸመው ሁኔታ ግለጽ። ፩. የእረፍት ጊዜ (ራእይ 10፡1-11፡14)   በብዙ መንገዶች የዮሐንስ ራእይ የሠርግ ፎቶ ይመስላል። በአንድ ሰው ሠርግ ላይ ካልተገኘህ፥ በዚያን ጊዜ የተነሣቸው ፎቶግራፎች ስለ ሠርጉ ብዙ መረጃዎችን ይሰጡሃል። ነገር ግን የክስተቶቹን ቅደም ተከተል አያሳዩህም። የዮሐንስ ራእይ በተለይም መካከለኛው ክፍል (ራእይ 10-18)፣ በመጨረሻው ዘመን ታላላቅ ሚናዎች የሚጫወቱትን ሰዎች የሚገልጽ ይመስላል። ነገር ግን ራእዮቹ የድርጊቶቹን ቅደም ተከተል አያሳዩንም። ዮሐንስ አሁንም ገለጻውን አቋርጦ የተለያዩ ነገሮችን ይመለከታል። ይህንንም ያደረገው ስለ መጨረሻው ዘመን የተሻለ ግንዛቤ ሊሰጠን ስለፈለገ ነው። ሀ) መልአኩና ትንሿ መጽሐፍ (ራእይ 10)። በመጀመሪያ የተገለጸው ለዮሐንስ ትንሿን መጽሐፍ እንዲበላት የሰጠው መልአክ ነው። ይህ ዮሐንስ በእስትንፋሰ እግዚአብሔር ከተጻፈው የእግዚአብሔር ቃል ጋር ያለውን ግንኙነት ያመለክታል። በተጨማሪም፥ ዛሬ ከእግዚአብሔር ቃል ጋር ያለንን ግንኙነት ያሳያል። ዮሐንስ ወደ ምድር የተመለሰ ሲሆን፥ ወዲያውኑ አንድ ታላቅ መላእክ ከሰማይ ሲወርድ ያየዋል። መልአኩ በምድር ሁሉ ላይ ሥልጣን እንዳለው ለማሳየት በባህርና በመሬት ላይ ይቆማል። በእጁ ትንሽ መጽሐፍ ይዟል። ክርስቶስ ከእግዚአብሔር አብ ከወሰዳት መጽሐፍ በተቃራኒ፥ ይህቺኛዋ መጽሐፍ በመጠን አነስ ያለች ስትሆን፥ በጽሑፍ መሞላቷም አልተገለጸም። ይህም እግዚአብሔር በታሪክ ውስጥ ከሚፈጸመው ተግባር ጥቂቱን ብቻ እንደገለጸልን ያሳያል። የተገለጸልን ግን የእግዚአብሔርን እውነት፥ የድነት (ደኅንነትን) መንገድ፥ እንዲሁም በመጨረሻው ዘመን ምን እንደሚከሰት ለመገንዘብ በቂያችን ነው። መልአኩ ለዮሐንስ ትንሿን መጽሐፍ ከመስጠቱ በፊት በታላቅ ድምጽ ይጮሃል። በዚህም ጊዜ ሰባት ነጎድጓዶች ምላሽ ይሰጣሉ። ዮሐንስ እነዚያ ሰባት ነጎድጓዶች በፍርድ የተናገሩትን ሊጽፍልን ፈልጎ ሳለ መልአኩ ግን እንዳይጽፍ ከልክሎታል። ይህ ራእይ እግዚአብሔር በታሪክና በመጨረሻው ዘመን ስለሚፈጸመው ነገር ጥቂቱን ብቻ እንደገለጸልን ያሳያል። የሚከሰተውና የሚከሰትበትም ምክንያት በአብዛኛው በእግዚአብሔር ምሥጢራት ውስጥ የተደበቀ ነው። ይህም ለሰው ልጆች ያልተገለጸ መሆኑን እንመለከታለን። በታሪክ የመጨረሻዎቹ ቀናት የሚከሰተው ነገር አልተገለጸም። ነገር ግን እግዚአብሔር ነገሮችን ሁሉ እንደሚቆጣጠር ለማወቅ የሚያስችል በቂ መረጃ ተሰጥቶናል። መጪዎቹ ጊዜያት ክፉዎችና አስቸጋሪዎች ቢሆኑም፥ ኢየሱስ ክርስቶስ ጠላቶቹን ሁሉ (ሰዎችም ሆኑ ሰይጣን) ያሽንፋል። ዮሐንስ የበላት ትንጂ መጽሐፍ እግዚአብሔር ለዮሐንስና በእርሱም በኩል ለእኛ የሰጠንን መለኮታዊ ቃል በተምሳሌትነት ታሳያለች። በእግዚአብሔር ቃል ውስጥ የዮሐንስ ራእይ ተጠቃልሎ እንመለከታለን። መለኮታዊው ትንቢት ኃጢአተኛ ሰዎች ከእግዚአብሔር ጋር እንዴት ኅብረት ሊያደርጉ እንደሚችሉ ስለሚናገር፥ ጣፋጭ ነው። እንዲሁም የኢየሱስን ዘላለማዊ መንግሥትን ክብር ይገልጻል። ይህም ብቻ አይደለም። ለማመን በማይፈልጉ ሰዎች ላይ እግዚአብሔር የሚያመጣቸውን ፍርዶች ስለሚገልጽ መራራም ነው። ዛሬ ጣፋጩም ሆነ መራራው የእግዚአብሔር ቃል ለሰዎች ሁሉ መነገር አለበት። ዳቦ በምንበላበት ጊዜ በሰውነታችን ሁሉ ተሰራጭቶ ይገነባናል። በተመሳሳይ ሁኔታ፥ መልአኩ ዮሐንስ ትንሿን መጽሐፍ እንዲበላት ነግሮታል። ይህም የእግዚአብሔርን ቃል ለሌሎቹ ከማጋራታችን በፊት በማጥናት፥ በማሰላሰልና በመታዘዝ የሕይወታችን አካል ልናደርገው እንደሚገባ ያሳያል። ብዙ ሰባኪዎችና አስተማሪዎች የመጽሐፍ ቅዱስን እውነት ከሕይወታቸው ጋር ሳያገናዝቡ ለምእመናን ያስተላልፋሉ። የቤተ ክርስቲያን አባላት ይህንን ግብዝነት በሚመለከቱበት ጊዜ ለአገልጋዮቻቸው አክብሮት ማጣት ብቻ ሳይሆን፥ የእግዚአብሔርን ቃል ብቻ ሳይሆን የእነዚህኑ መሪዎች ምሳሌነት ይከተላሉ።  የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) የእግዚአብሔር ቃል በተለይም የዮሐንስ ራእይ እንዴት ጣፋጭም መራራም ሊሆን እንደቻለ ግለጽ። ለ) ዮሐንስ መጽሐፉን በተቀበለ ጊዜ እንዳደረገው ሁሉ እኛስ ከእግዚአብሔር ቃል ጋር ባለን ግንኙነት ምን ልናደርግ ይገባል? ሐ) ሰባኪዎችና አስተማሪዎች መጀመሪያ ከራሳቸው ሕይወት ጋር ሳይዋሃዱ የእግዚአብሔርን እውነት ለሰዎች ሲያስተላልፉ የተመለከትከው እንዴት ነው? ይህ በግላሰቡና በቤተ ከርስቲያን ላይ የሚያስከትለው አደጋ ምንድን ነው? ለ) ሁለቱ ምስክሮች (ራእይ 11፡1-14)። ሁለተኛዎቹ ምድቦች ሁለት ምስክሮች ናቸው። ይህ በራእይ ውስጥ ለመተርጎም እጅግ ከሚያስቸግሩ ምንባቦች አንዱ ነው። በዚህ ምንባብ ላይ የምሁራኑ አስተሳሰብ በሁለት ዐበይት ቡድኖች የተከፈለ ነው። በመጀመሪያ፥ አንዳንዶች ይህ ትንቢት በታላቁ መከራ ጊዜ በእስራኤል ላይ የሚከሰተውን ሁኔታ ለመግለጽ በሚያስችል መልኩ በቀጥታ መተርጎም አለበት ይላሉ። እነዚህ ምሁራን በመጨረሻው ዘመን አይሁዶች ቤተ መቅደላቸውን እንደገና ገንብተው እዚያው ውስጥ እንደሚያመልኩ ይናገራሉ። ከዚያ በኋላ ግን ሐሳዊው መሢሕ ተነሥቶ ከአይሁዶች እግዚአብሔርን እንዳያመልኩ ይከለክላቸዋል። ብዙ አይሁዶችንም ይገድላል። ነገር ግን እግዚአብሔር ታማኝ አይሁዶች ሙሉ በሙሉ በሐሳዊ መሢሕ እንዳይደመሰሱ ይጠብቃቸዋል። እንዲሁም እግዚአብሔር ሁለት አይሁዶችን መርጦ ቃሉን እንዲናገሩና እንዲመሰክሩ ኃይልን ይሰጣቸዋል። ሁለተኛ፥ ራእዩ ቤተ ክርስቲያንን በተምሳሌትነት የሚያቀርብ ነው የሚሉ ምሁራን አሉ። እግዚአብሔር ለቤተ ክርስቲያን የመመስከርና ሰዎችን የማስጠንቀቅ (ወንጌልን በመስበክ) ኃላፊነት እንደ ሰጣት ይገልጻሉ። እንዲሁም እግዚአብሔር እርሱን ለማምለክ እንዲያስችለንና በውስጣችን በኃይል እንዲሠራ መንፈስ ቅዱስን ሰጥቶናል። እግዚአብሔር ቤተ ክርስቲያንን ከአጠቃላይ ውድመት ቢጠብቃትም፥ አንዳንድ አማኞች በስደት መጎዳታቸው የማይቀር ነው። ነገር ግን በትንሣኤ አማካኝነት ድሉ የራሳችን ስለሆነ ልንጨነቅ አይገባም። የዚህ ራእይ ቁልፍ ተምሳሌቶች የሚከተሉት ናቸው፡- የቤተ መቅደስ ውጫዊ ክፍል፥ የመሠዊያውና የማምለኪያዎቹ መለካት፡- በዚህ ራእይ ውስጥ ዮሐንስ አንድ መልአክ የእግዚአብሔርን ቤተ መቅደስ ሲለካ ተመልክቷል። በብሉይ ኪዳን ዘመን፥ መላእክት አንድን ነገር የሚለካበት ታላቅ በረከት (ኤር. 31፡38-40፤ ዘካ 1፡16) ወይም ጥፋት (አሞፅ 7፡7-9) እንደሚመጣ ለማሳየት ነው። የቤተ መቅደስ ውስጣዊ ክፍል መለካቱ እግዚአብሔር እውነት ተከታዮቹን ለማወቅና ሙሉ ለሙሉ እንዳይወድሙ ለመጠበቅ መፈለጉን የሚያሳይ ይመስላል። ለዚህ ራእይ የሚሰጡ ሁለት ዐበይት አተረጓጎሞች

የእረፍት ጊዜ (ራእይ 10፡1-11፡14) እና የሰባተኛው መለከት ፍርድ (ዋይታ 3) ራእይ 11፡15-19 Read More »

ሰባት የመለከት ፍርዶች (ራእይ 8፡2-11፡19)

ሰባቱ የማኅተም ፍርዶች የመጨረሻውን ዘመን ባሕርያት የሚገልጹ ሲሆን፥ ሰባቱ የመለከት ፍርዶች እና ሰባቱ የጽዋ ፍርዶች ክርስቶስ ሊመለስ ሲል ስለሚሆኑት ሁኔታዎች ዝርዝር ማብራሪያ ያቀርባሉ። በራእይ 6፡9-11፥ ሰማዕት አማኞች፥ እግዚአብሔር በገደሏቸው ሰዎች ላይ ፍትሕንና በቀልን መቼ እንደሚያመጣ ሲጠይቁ እንመለከታለን። አሁን በቅዱሳን ጸሎት ምክንያት በሚገለጹት ሰባት የመለከት ፍርዶች አማካኝነት እግዚአብሔር በኃጢአተኞች ላይ ፍትሕንና በቀልን ሲገልጽ እንመለከታለን። እግዚአብሔር በፍርድ ለሰው ልጅ የሰጣቸውን የተፈጥሮ ስጦታዎች መልሶ መውሰድ ይጀምራል። ሰዎች ለእነዚህ ስጦታዎች እግዚአብሔርን አላመሰገኑም ነበር። እንዲሁም እግዚአብሔር ቀደም ሲል ገድቦ የያዘውን የሰይጣን ኃይል በመልቀቅ ሰይጣን በምድር ላይ ባሉት ኃጢአተኞች ላይ ሥቃይን እንዲያበዛ ያደርጋል። ከእነዚህ ፍርዶች አብዛኞቹ እግዚአብሔር በሙሴ ዘመን በግብጽ ላይ ያወረዳቸውን መቅሰፍቶች የሚመስሉና ነገር ግን ከዚያ የከበዱ ናቸው። ዮሐንስ ስለ ሰባት የመላከት ፍርዶች በሚያቀርበው ገለጻ በተለይ በስድስተኛውና አምስተኛው መለከቶች ላይ ትኩረት ያደርጋል።  ሀ) የመጀመሪያው መለከት፡ እግዚአብሔር የምድርን አንድ ሦስተኛ (ሲሶ) በእሳት ያጠፋል። ይህም ዛፎችንና ሣርን የሚያጠቃልል ሲሆን፥ ሰዎች እህል ዘርተው የሚበሉበትን ሁኔታ በከፍተኛ ደረጃ ይቀንሳል። ምሁራን ይህ ሲሶ የተባለው አሃዝ ቀጥተኛ ወይም ተምሳሌታዊ በመሆኑ ላይ ይከራከራሉ። በይበልጥ ግን ዮሐንስ አብዛኛው የመሬት ክፍል ሰብል የማምረትና አትክልቶችን የማብቀል አቅም እንደሚያጥረው የገለጸ ይመስላል። ብዙዎች ይህ ራእይ ምንን እንደሚያመለክት የተለያዩ አሳቦችን ያቀርባሉ። ይህ የምድርን አብዛኛውን ክፍል የሚያጠፋ መለኮታዊ ፍርድ ይሆን? ወይስ እንደ አካባቢያዊ ብክለት ወይም የኒኩለር ጦርነት ያለ በእግዚአብሔር ቁጥጥር ሥር የሚከናወን የሰው ልጅ የተግባር ውጤት ይሆን? ይህ ምንን እንደሚያመለክት በትክክል ባናውቅም፥ መልእክቱ ግልጽ ነው። እህልን የሚያበቅል ሰፊ መሬት በማይኖርበት ወቅት እግዚአብሔር ለብዙ ሰዎች ሕይወትን አስቸጋሪ እንደሚያደርግ እንመለከታለን። ለ) ሁለተኛው መለከት፡ እግዚአብሔር የባህርን ሲሶ በባህር ውስጥ የተለያዩ ነገሮች የሚሸከሙትን መርከቦች ሲሶ፥ እንዲሁም በባህር ውስጥ የሚገኙትን ነገሮች ሲሶ ያጠፋል። በአብዛኞቹ ደሴቶችና በባህር ዳርቻዎች አካባቢ የሚኖሩ ሰዎች ምግባቸውን የሚያገኙት ከባህር ነው። በተጨማሪም የብዙ አገሮች ኢኮኖሚ ከአንድ አገር ወደ ሌላው አገር ምርቶችንና ቁሳቁሶችን በሚያጓጉዙ መርከቦች ላይ የተመሠረተ ነው። ስለሆነም፥ ይህ ፍርድ የብዙ አገሮችን የምግብ ፍጆታና ኢኮኖሚ ይጎዳል። ሐ) ሦስተኛው መለከት፡ እግዚአብሔር በምድር ላይ ለመጠጥነት ከሚያገለግለው ውኃ ሲሶውን ያጠፋዋል። ሬቶ የተባለው ኮከብ እንደ ስሙ መራራ ነው። ይህ ኮከብ መርዛማ ባይሆንም፥ የአንድን ነገር ጣእም በከፍተኛ ደረጃ ይለውጣል። እግዚአብሔር የሰውና የእንስሳት ሕይወት የተመሠረተበትን ውኃ ያስወግዳል። ወይም አንዳንድ ምሁራን እንደሚሉት፥ ይህ እግዚአብሔር በምድር ላይ ከሚያመጣው ፍርድ የተነሣ በሰዎች ሕይወት ላይ የሚደርሰውን ምሬት የሚያሳይ ነው። መ) አራተኛው መለከት፡ እግዚአብሔር በምድር ላይ ብርሃን የሚያመጡትን ነገሮች ያጠፋል። የፀሐይ፥ የጨረቃና የከዋክብት ሲሶ ብርሃኑን ያጣል። ይህ በምድር ላይ ብርሃን የሚታይበት ጊዜ እንደሚቀንስና የጨለማው ሰዓት እንደሚጨምር የሚያመለክት ሊሆን ይችላል። ሠ) አምስተኛው መለከት (ዋይታ )። ይኼኛውና ቀጣዩ ፍርድ በጣም የጠነከሩ በመሆናቸው፥ ሁለቱም የዋይታ ፍርዶች በመባል ይታወቃሉ። ይህ ራእይ ሰይጣንና አጋንንቱ ምድርን ለማጥፋት ተጨማሪ ኃይል ማግኘታቸውን ያሳያል። ከሰማይ የወደቀው መላእክት አብዶን ወይም አጶሊዎን የሚባለው (ትርጉሙ አጥፊ) ሰይጣን ሳይሆን አይቀርም። እግዚአብሔር አሁን ጥልቁን ጉድጓድ እንዲከፍት ሥልጣን ይሰጠዋል። ይህም እስከዚህ ጊዜ ድረስ እግዚአብሔር ብዙ አጋንንትን አስሮ ያቆየበት ስፍራ ነው። እነዚህ አጋንንት በምድር ዙሪያ በመዟዟር የእግዚአብሔር ማኅተም የሌለበትን ሰው ሁሉ እንዲያሠቃዩ ሥልጣን ተሰጥቷቸዋል። በመሆኑም አማኞችን የመግደል ሳይሆን የማሠቃየት ሥልጣን አላቸው። የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ይህ ራእይ እግዚአብሔር፥ በሰይጣንና በአማኞች መካከል ያለውን ግንኙነት ለመረዳት የሚያግዘው እንዴት ነው? ለ) ይህ ብዙ ሰዎች ስለ ሰይጣን አሠራር ከሚያውቁት የሚለየው እንዴት ነው? በዚህ ፍርድ ውስጥ በጣም አስፈላጊ የሆነ እውነት እንመለከታለን። እግዚአብሔር ሁልጊዜም ሰይጣንን በመቆጣጠር ላይ ነው። እርሱ ሰይጣን የትና እንዴት ሊሠራ እንደሚገባ ዳርቻውን ይወስንለታል። ከእግዚአብሔር ፈቃድ እስካላገኘ ድረስ ሰይጣን በሕይወታቸው ውስጥ የመንፈስ ቅዱስ ማኅተም ያለባቸውን አማኞች ሊነካ አይችልም። ሊፈትነን ቢችልም፥ የእግዚአብሔር ልጆች እንደ መሆናችን እግዚአብሔር ካላጸደቃቸው ከማናቸውም ጥቃቶች የተጠበቅን ነን። ረ) ስድስተኛው መለከት (ዋይታ 2)፡ በእግዚአብሔር ትእዛዝ አራት መላእክት ከኤፍራጥስ ወንዝ ይለቀቃሉ። በእነዚህ መላእክትና ሁለት መቶ ሚሊዮን ፈረሶችና ጋላቢዎች ባሉበት ሠራዊታቸው አማካኝነት የሰዎች ሲሶ ይገደላል። እነዚህ ታላቅ ሠራዊት ማንን እንደሚያመለክቱ ምሁራን በሚሰጡት ትንታኔ ይለያያሉ። አንዳንዶች ሰዎችን ማሠቃየት ብቻ ሳይሆን የመግደልም ሥልጣን የተሰጣቸው የአጋንንት ሠራዊት ናቸው ይላሉ። ሌሎች ደግሞ ይህ ታላቅ የዓለም ጦርነት የተገለጸበት ክፍል ነው ሲሉ ያስተምራሉ። ይህን አመለካከት የሚከተሉ ሰዎች የእስያ በተለይም የቻይና ሠራዊት የኤፍራጥስን ወንዝ ተሻግሮ ወደ ተስፋይቱ ምድር እንደሚመጣ ይናገራሉ። እሳት፥ ጭስና ድኝ፥ የቦንቦችና የታንኮች ወይም የኑክሌር ጦርነት ውጤቶች ሊሆኑ ይችላሉ። ይህም ታላቅ ጦርነት የሰዎችን ሲሶ (ወይም አብዛኛውን ሕዝብ) ይጨርሳል። እነዚህ ፈረሶችና በፈረሶቹ ላይ የተቀመጡት እነማን እንደሆኑ ላናውቅ ብንችልም፥ ውጤቱ ግን በግልጽ የሚታይ ነው። እግዚአብሔር ሰይጣንን ስላላስቆመው፥ ሞት ዓለምን ይሸፍናል። ከአምስተኛው የመለከት ፍርድ በተቃራኒ፥ እግዚአብሔር አማኞችን ከሞት እንደሚታደግ የሚያመለክት ነገር አይገለጽም። በዚህ ክፍል ዮሐንስ ስለ መናፍስት ዓለም አንዳንድ አስገራሚ ነገሮችን ያስተምራል። ከእግዚአብሔር ታላላቅ ምሕረቶች አንዱ ሰይጣንና አጋንንት የሚፈልጉትን ክፋት ሁሉ እንዳይፈጽሙ መገደቡ ነው። ሰይጣንና አጋንንቱ ነፍሰ ገዳዮች ናቸው (ዮሐ. 8፡44)፡፡ ለመጉዳት፥ ለመግደልና ለማጥፋት ይፈልጋሉ። ነገር ግን እግዚአብሔር የሚፈልጉትን ሁሉ እንዲያደርጉ አይፈቅድላቸውም። ኃይላቸውን ይገድበዋል። ነገር ግን አንድ ቀን እግዚአብሔር ከሰይጣን ላይ የቁጥጥር እጁን በማንሣት ሰዎች ከዚህ በፊት ታይቶ በማይታወቅ ሁኔታ እንዲሠቃዩና በሚሊዮን የሚቆጠሩት ደግሞ ለሞት እንዲጋለጡ ያደርጋል። በአንድ በኩል እነዚህ የመለከት ፍርዶች እግዚአብሔር በሰዎች አለማመንና ኃጢአት ላይ ያመጣቸው ፍርዶች ናቸው። በሌላ በኩል ደግሞ እነዚህ የእግዚአብሔር የምሕረቱ ምልክቶች ናቸው። ሰዎች በዐመፀኛነታቸው ሳይቀጥሉ ወደ እርሱ ተመልሰው ምሕረቱንና ይቅርታውን እንዲቀበሉ ለማበረታታት ፍርዱን በመሣሪያነት ይጠቀማል። የሚያሳዝነው ግን ሰዎች ወደ እግዚአብሔር ከመመለስ ይልቅ በዐመፃቸውና በክፉ ሥራቸው ይቀጥላሉ። የተሳሳተው አምልኳቸው በአጋንንት ቁጥጥር ሥር የሚካሄድ ነው። እንዲሁም ስርቆት፥ ግድያና ወሲባዊ ኃጢአቶች ይፈጽማሉ። በአንድ አገር ላይ አደጋ በሚደርስበት ጊዜ ይህንኑ አደጋ የሚቆጣጠረው እግዚአብሔር ነው። እግዚአብሔር በዚሁ አደገኛ ሁኔታ (ለምሳሌ፥ ጦርነት፥ ረሀብ፥ ኤድስ) አማካኝነት ለመፈጸም ከሚፈልጋቸው ነገሮች መካከል አንዱ ሕዝቡ ወደ ምሕረቱ እንዲመለስ፥ ይህ ካልሆነ ግን ወደፊት ከዚህ የከፋ ቅጣት እንደሚጠብቃቸው ለማስገንዘብ ነው። የውይይት ጥያቄ፡– ሀ) በኢትዮጵያ ላይ ስለ ተከሰተ አንድ አደጋ ግለጽ። እግዚአብሔር በዚህ አደጋ አማካኝነት ለሕዝቡ ለማስተላለፍ የፈለገው መልእክት ምን ይመስልሃል? ለ) ብዙ ሰዎች የእግዚአብሔርን ማስጠንቀቂያ ችላ ብለው በዐመፀኝነታቸው የሚገፉት ለምን ይመስልሃል? ሀ) እነዚህ ጥቅሶች ስለ እግዚአብሔር ኃይል፥ ተቆጣጣሪነትና ምሕረት ምን ያስተምሩናል? (ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

ሰባት የመለከት ፍርዶች (ራእይ 8፡2-11፡19) Read More »

ሰባት የማኅተም ፍርዶች (ራእይ 6፡1-8፡1)

የውይይት ጥያቄ፡– ራእይ 6-9 አንብብ። ሀ) ስድስቱን የማኅተም ፍርዶች ዘርዝር። ለ) በአንድ መቶ አርባ አራት ሺህዎቹ ላይ ምን እንደሚደርስ ግለጽ። ሐ) በሰማይ የታዩትን እጅግ ብዙ ሕዝብ ግለጽ። መ) ስድስት የመለክት ፍርዶችን ዘርዝር። ሀ) እግዚአብሔር አሁንም ሆነ ወደፊት በምድር ላይ የሚከናወኑትን ነገሮች ስለ መቆጣጠሩ እነዚህ ምዕራፎች ምን ያስተምሩናል? ረ) እነዚህ ምዕራፎች ስለ መጨረሻው ዘመን ባሕርይ ምን ያስተምሩናል? እግዚአብሔር ለልጆቹ በሰማይና በምድር የሚከናወኑ ተግባራት በእርሱ የተወሰኑ መሆናቸውን ለማሳየት ይፈልጋል። በራእይ 4-5፥ እግዚአብሔር ለዮሐንስ በሰጠው ራእይ አማካኝነት የሰማይን የዙፋን ክፍል ያሳየናል። በዚያ ዙፋን አካባቢ ነገሮች ከቁጥጥር ውጪ በመሆናቸው ምክንያት የፍርሃት ምልክት ሲከሰት አንመለከትም። ሰይጣን ሊያደርግ የማይገባውን በማድረጉ ወይም በማሸነፉ ምክንያት የታየ ጭንቀት አልተጠቀሰም። በቤተ ክርስቲያን ድክመት ምክንያት ነገሮች ከቁጥጥር ውጪ መሆናቸውም አላሳሰበም። ነገር ግን ዙፋኑ በኃይል፥ በሥልጣን፥ በቁጥጥርና በልበ ሙሉነት የተሞላ ነው። እግዚአብሔር ነገሮችን ሁሉ ሙሉ በሙሉ የሚቆጣጠር ፍጹማዊ ገዢ በመሆኑ ፍጥረታት ሁሉ ያመሰግኑታል። ለመሆኑ ታላቁ አምላክ አገዛዙን የሚያከናውነው እንዴት ነው? ዮሐንስ እግዚአብሔር አብ ለወልድ የታሪክን ጥቅልል በመስጠት በምድር ላይ የሚከናወኑትን ነገሮች ሁሉ እንዲቆጣጠር ማድረጉን ያሳየናል። በራእይ 6-19፥ እግዚአብሔር በምድር ላይ ነገሮችን የሚቆጣጠር ማን እንደሆነ ብቻ ሳይሆን፥ በመጨረሻው ዘመን የሰውን ልጅ ታሪክ ከፍጻሜው ለማድረስና የኢየሱስ ክርስቶስን ዘላለማዊ መንግሥት ለመመሥረት እንዴት ተግባሩን እንደሚያከናውንም ያሳየናል። ምሁራን እነዚህ ፍርዶች መቼ እንደሚፈጸሙ በሚያቀርቧቸው አሳቦች ይለያያሉ። አንዳንዶች ራእይ 6–19 ታላቁ መከራ የተባለውንና ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ምድር ሊመለስ ሲል የሚፈጸመውን የሰባት ዓመታት የመከራ ክፍለ ጊዜ ያመለክታል ይላሉ። እነዚህ ምሁራን በዚህ ክፍለ ጊዜ ውስጥ የእግዚአብሔር ጽኑ ፍርድ በምድር ላይ እንደሚወርድ አማኞች ታይቶ የማይታወቅ ስደት እንደሚደርስባቸውና በእነዚህ ራእዮች እንደተገለጸው ሐሳዊ መሢሕ በምድር ላይ እንደሚገዛ ይናገራሉ። ሌሎች ምሁራን ደግሞ እነዚህ ክርስቶስ ወደ ምድር ሊመለስ ሲል በምድር ላይ የሚከሰቱ ፍርዶች መሆናቸውን ቢገልጹም፥ የጊዜ ገደቡን አይወስኑም። እነዚህ እውነቶች አሁን በምድር ላይ ረሃብና ስደት በእኛ ላይ ሐዘንን በሚያስከትሉበት ወቅት በሰማይ ላይ ስለሚከሰቱት ነገሮች የሚያሳዩ ናቸው ብሎ መቀበሉ የሚሻል ይመስላል። ነገር ግን እነዚህ ነገሮች ኢየሱስ ክርስቶስ ሊመለስ ሲል ሙሉ በሙሉ ይፈጸማሉ። ፩. ስድስት የማኅተም ፍርዶች (ራዕይ 6) በጥንት ዘመን ደብዳቤ ወይም ጠቃሚ ሰነድ በማኅተም ይታተም ነበር። ይህም የሚሆነው በመጽሐፉ ጥቅልል ጫፍ ላይ ሰም በመጨመርና ከሰሙ ላይ ደብዳቤውን የጻፈው ግለሰብ ቀለበት እንዲያርፍ በማድረግ ነበር። በዚህም ጊዜ አንድ ሰው ያለ ፈቃድ ደብዳቤውን መክፈቱ በቀላሉ ይታወቅ ነበር። ክርስቶስ የተቀበለው የመጽሐፍ ጥቅልል እጅግ ጠቃሚ በመሆኑ በሰባት ማኅተሞች ታትሟል። አንዳንድ ምሁራን ይህ እያንዳንዳቸው መጻሕፍት በአንዳንድ ማኅተሞች የታተመበትን ሁኔታ ያሳያል ይላሉ። እያንዳንዱ የማኅተም ፍርድ በአንዳንድ ጥቅልል ላይ እንደ ተጻፈና ክርስቶስም እያንዳንዱን ፍርድ በሚያመጣበት ጊዜ ይህንኑ ጥቅልል እንደሚያነብ ይናገራሉ። ዮሐንስ የሚናገረው ይህንኑ ይሁን ወይም ሰባት ማኅተሞች ያረፉባት አንድ ትልቅ የመጽሐፍ ጥቅልል በትክክል ለማወቅ ያስቸግራል። የማኅተም ፍርዶች የመጨረሻውን ዘመን ባሕሪ በሰፊው ይገልጻሉ። ዮሐንስ ክርስቶስ በጥቅልሉ ላይ ያለውን ማኅተም በከፈተና የተጻፈውን መልእክት ባነበበ ቁጥር ምን እንደሚከሰት ይገልጻል፡- ሀ) የመጀመሪያው ማኅተም፡ በነጭ ፈረስ የሚጋልበው ሰው ድል እንዲነሣ ሥልጣን ተሰጠው። ምሁራን ይህ ፈረሰኛ ማን እንደሆነ ይከራከራሉ። ጋላቢው ጠላቶቹን ድል የሚነሣው ክርስቶስ ይሆን? ወይስ ዓለምን እንዲያሸንፍ መብት የተሰጠው ሐሳዊ መሢሕ? በአመዛኙ ግን አንዱ አገር ሌላውን ለማሸነፍ በሚፍጨረጨርበት ጊዜ የሚታየው የጦርነትና የማሸነፍ መንፈስ ነው። ይህ ሌላውን የማሽነፍ መንፈስ በመጨረሻው ዘመን እያየለ ይሄዳል። ለ) ሁለተኛው ማኅተም፡ በቀይ ፈረስ ላይ የተቀመጠው ጋላቢ ትልቅ ሰይፍ ተሰጠው። ይህ ሰዎች እርስ በርስ መገዳደላቸውን ያሳያል፡፡ የመጀመሪያው ማኅተም አገሮች እርስ በርሳቸው እንደሚዋጉ የሚያመለክት ሲመስል፥ ይሄኛው ግን በእያንዳንዱ አገር ውስጥ የሚከሰተውን የእርስ በርስ ውጊያ የሚያሳይ ይመስላል። በዚህም ጊዜ ከጥቂት ዓመታት በፊት በሩዋንዳ እንደተከሰተው በአገሪቱ ውስጥ የሚገኙ ጎሳዎች እርስ በርሳቸው ይጨፋጨፋሉ። ምንም እንኳ ይህ ታሪክ ሁሉ የተለመደ ችግር ቢሆንም፥ ወደ መጨረሻው ዘመን አካባቢ የአገር ውስጥ ዐመፆችና የጎሳዎች መዋጋት እየጨመረ ይሄዳል። በዚህም ብዙ ሰዎች ይገደላሉ። ሐ) ሦስተኛው ማኅተም፡ በጥቁር ፈረስ ላይ የተቀመጠው ሰው ምግብን ለመመዘን ሚዛን ይዟል፡፡ ይህ ፈረስ ረሀብን ያመለክታል። ከጦርነትና ከእርስ በርስ ግጭት፥ እንዲሁም ከአየር መዛባት የተነሣ በዓለም ላይ ረሃብ ይከሰታል። ይህ ራእይ አነስተኛ ስንዴ (ብዙ ሰዎች የሚመገቡት የምግብ ዓይነት) ለማግኘት ብዙ ገንዘብ እንደሚጠይቅ ያስረዳል። አንድ ሰው ብቻ ሊመገብ የሚችለውን ስንዴ ለማግኘት ሙሉ ቀን መሥራት ያስፈልጋል። ብዙዎች የማይወዱትን ማሽላ ለማግኘት ደግሞ የአንድ ቀን ትጋትን ይጠይቃል። ይህም ጥቂት ሰዎች ላሉበት ቤተሰብ የአንድ ቀን ምግብ ይሆናል። መ) አራተኛ ማኅተም፡ ሞት የተባለ ጋላቢ ከገረጣ ፈረስ ላይ ይቀመጥና ሲዖል ይከተለዋል። ከጦርነት፥ ከእርስ በርስ ግጭቶች፥ ከረሃብ፥ ከበሽታና ከሌሎችም መቅሰፍቶች የተነሣ፥ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ሰዎች ይሞታሉ። በዚህ ስፍራ ሲዖል የሚያመለክተው የዘላለምን ፍርድ ሳይሆን፥ እስከ ፍርድ ጊዜ ድረስ ኃጢአተኞች የሚቆዩበትን ጊዜያዊ ስፍራ ነው። ሠ) አምስተኛው ማኅተም፡ በሰማዕትነት ያለፉ የታማኝ አማኞች ነፍሳት፡፡ ይህ ማኅተም በዚህ ጊዜ በእግዚአብሔር ሕዝብ ላይ የሚደርሰውን ሁኔታ እንጂ እግዚአብሔር በዓለም ላይ የሚያመጣውን ፍርድ አይገልጽም። ይህ ታላቅ ስደት የሚከሰትበት ወቅት በመሆኑ በእግዚአብሔር ቃልና ለምስክርነታቸው (ስለ ክርስቶስ በመመስከራቸውና የተቀደሰ ሕይወት በመኖራቸው) ይገደላሉ። እግዚአብሔር አማኞች በምድር ላይ ቀላል ሕይወት እንደሚያሳልፉ ቃል አልገባላቸውም። ነገር ግን ለእምነታችን እንድንሞት ጠርቶናል። ስለሆነም በታማኝነት ለመጽናት መቁረጥ አለብን። ከኃጢአተኞች ጋር በሲዖል ከመኖር ይልቅ እነዚህ ነፍሶች ወደ እግዚአብሔር ቀርበው እንመለከታለን። እነርሱ የነበሩበት የሰማይ መሠዊያ ከእግዚአብሔር ዙፋን ፊት የሚገኝ ነው። ሞት አማኞችን ወደ እግዚአብሔር አምጥቷቸዋል። እነዚህ በሰማዕትነት ያለፉ አማኞች እግዚአብሔርን «እስከ መቼ?» እያሉ ይጠይቁታል። ይህም የአሳደዷቸው ሰዎች ላይ እግዚአብሔር መቼ ፍርዱን እንደሚሰጥ መጠየቃቸውን ያመለክታል። እግዚአብሔር ግን እንዲጠብቁ ይነግራቸዋል። የእግዚአብሔር የታሪክ ዕቅድ ከፍጻሜው ከመድረሱ በፊት ገና ብዙ አማኞች ይሞታሉ። ይህ ዛሬ ተወዳጅነት ያለው መልእክት አይደለም። ነገር ግን በብዙ የአዲስ ኪዳን መልእክቶችና በተለይም በዚሁ በዮሐንስ ራእይ ውስጥ እንደተመለከትነው እግዚአብሔር ልጆቹ ለእምነታቸው እንዲሞቱ ይጠይቃቸዋል። ለእርሱ ታማኞች ሆነን በመቆም ታማኝነታችንንና ፍቅራችንን እንድንገልጽለት ይፈልጋል። እግዚአብሔር የልጆቹን ሞት በፍጥነት አይበቀልም። ነገር ግን በራእይ 17-19 እንደምንመለከተው እግዚአብሔር የኋላ ኋላ ጠላቶቹን (ጠላቶቻችንን) በሙሉ ይቀጣቸዋል። ረ) ስድስተኛው ማኅተም፡ ምድርን ብቻ ሳይሆን ሰማይን ጭምር ያናወጠ ታላቅ የምድር መንቀጥቀጥ። ክርስቶስ ሊመለስ ሲል ምድር በደም መፍሰስና በሞት ከመሞላቷ ባሻገር ፍጥረት ሁሉ ይናወጣል። ይህን ሁሉ ሲመለከቱ ነገሮችን ሁሉ ልንቆጣጠር እንችላለን የሚሉት ታላላቅ መሪዎች ሳይቀሩ የምድር ነዋሪዎች ሁሉ በፍርሃት ይወጣሉ። የእግዚአብሔርን ኃይለኛ ፍርድ ከመቀበል ይልቅ የተፈጥሮ አደጋ ቢደርስባቸው ይመርጣሉ። የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ክርስቶስ ሊመለስ ሲል የሚከሰተው የመጨረሻ ዘመን ሁኔታ ምን እንደሚመስል ጠቅለል ባለ መልኩ ግለጽ፡፡ ለ) ዛሬ በሚኖሩት አማኞች ውስጥ እነዚህ እውነቶች ምን ለውጥ ሊያመጡ ይገባል? ሐ) አንድ ያልተጠበቀ አደጋ በሚደርስበት ጊዜ የአማኞች እምነት ሲናጋ የተመለከትከው እንዴት ነው?  ያልተጠበቁ ችግሮች በሚደርሱብን ጊዜ በአብዛኛው ግራ መጋባትና ጥርጣሬ ይወርሩናል፡፡ እግዚአብሔር በምድር ላይ ከማንኛውም ዓይነት ስደትና መከራ እንደሚጠብቀን የሚያስተምሩ ሰዎች አሉ። ምንም እንኳን አንዳንድ ጊዜ እግዚአብሔር ከመከራ ቢጠብቀንም፥ ብዙውን ጊዜ በመከራና ስደት ውስጥ እንድናልፍ ይፈቅዳል። እግዚአብሔር በዮሐንስ አማካኝነት ልጆቹ በአብዛኛው መከራ የሚቀበሉ መሆናቸውን ያስገነዝበናል። ይህም ያለምንም ግራ መጋባት፥ ፍርሃትና ጥርጣሬ ስደትንና መከራን ለመቀበል እንድንዘጋጅ ያደርገናል። ዛሬ ብዙ ክርስቲያኖች ይህንን እውነት ባለመረዳታቸው ችግር በሚደርስባቸው ጊዜ ግራ ይጋባሉ። የቤተ ክርስቲያን መሪዎች እግዚአብሔር ሕዝቡን ከስደትና መከራ እንደሚታደግ ብቻ ሳይሆን፥ በዚሁ መከራ ውስጥ እንዲያልፉ የሚፈቅድ መሆኑን ጭምር ማስተማር ያስፈልጋቸዋል።  ፪. የእረፍት ጊዜ (ማቋረጫ) (ራእይ 7፡1-8፡1) ዮሐንስ ሰባተኛውን ማኅተምና ቀጣዮቹን የመለከት ፍርዶች ከመግለጹ በፊት፥ የመጨረሻውን ዘመን ሁለት ሌሎች ባሕርያት ለማሳየት ሲል የእግዚአብሔርን ሕዝብ ሁለት

ሰባት የማኅተም ፍርዶች (ራእይ 6፡1-8፡1) Read More »

እግዚአብሔር በዙፋኑ ላይ ተቀምጦ የሚታይበት ራእይ (ራእይ 4:1-5:14)

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) በሰዎች ላይ ተስፋ መቁረጥና ስጋት ሊፈጥሩ የሚችሉትን የዓለም ክስተቶች ዘርዝር። ለ) ክርስቲያኖች ክርስቶስን በመከተላችን ምክንያት የምንሠቃይባቸውን መንገዶች ዘርዝር። ሐ) መከራን በምንቀበልበት ጊዜ የመከራውን ዓላማ ማወቃችን እንዴት እንደሚረዳን ግለጽ። በዓለም ላይ እጅግ ታላላቅ የሆኑት ሰዎች ስለ ዕቅዶቻቸው ሲነጋገሩ የመስማት ዕድል ገጥሞናል እንበል። አዲስ አበባ በሚገኘው ቤተ መንግሥት ገብተው ጠቅላይ ሚኒስቴሩ በአንተ እና በሌሎችም ኢትዮጵያውያን ላይ ተጽዕኖ ስለሚያሳድሩ ነገሮች የሚወስዷቸውን እርምጃ ዎች ብትሰማ ምን ታደርጋለህ? ወደ ኋይት ሐውስ ገብተህ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ለዓለምና ለአገራቸው ስለሚያከናውኗቸው ተግባራት የወጠኗቸውን ዕቅዶች ብታውቅስ? ወይም የሩሲያ፥ የኬንያ፥ የእንግሊዝ፥ የጀርመን፥ የፈረንሳይ መሪዎች የወጠኗቸውን ዕቅዶች ብታውቅስ? ይህ ተጨማሪ ግንዛቤ በሕይወትህ ውስጥ የሚያመጣው ለውጥ ምንድን ነው? በዚህ ጊዜ በዓለም ላይ የሚከሰቱ ነገሮች ለአንተ የተለየ ትርጉም የሚሰጡት እንዴት ነው? መሪዎች ውሳኔያቸውን የሚሰጡባቸውን ምክንያቶች ማወቁ ብዙ ተስፋ መቁረጥን ሊያስከትል ይችላል። እንደዚህ ከሆነ፥ ለምን ቀረጥ እንከፍላለን? ለምን ወደ ጦርነት እንሄዳለን? የተወሰኑ አገሮች ለአገራችን ገንዘብ የሚያበድሩት ለምንድን ነው? እንዲህ ዓይነት ውሳኔዎች የሚተላለፉባቸውን ምክንያቶች ብናውቅ፥ በሕይወታችን ላይ ተጽዕኖ የሚያስከትሉትን ውሳኔዎች ለመቀበል ይቀልለናል። ነገር ግን በበለጠ የሚያሳስቡን ሌሎች ጉዳዮች አሉ። ረሀብ የሚነሣው ለምንድን ነው? እግዚአብሔር ኤድስ ብዙ ወጣቶችን እንዲፈጅ የፈቀደው ለምንድን ነው? እግዚአብሔር ልጆቹ ስደትን እንዲጋፈጡ እና ለእምነታቸው እንዲሞቱ የሚፈቅደው ለምንድን ነው? ታላላቅ አገሮች በሚያካሂዷቸው ጦርነት ሳቢያ ዓለም በኒውክሌር ቦንብ ትጠፋ ይሆን? ለእነዚህ ጥያቄዎች መልሶችን የምናገኘው ወይም ቢያንስ እግዚአብሔር እነዚህን ነገሮች እንደሚቆጣጠር የምናውቀው እንዴት ነው? ራእይ 4-19 እጅግ ወደላቀው የአመራር ስፍራ እንድንገባ በር ይከፍትልናል። እግዚአብሔር በሰማይ ወደአለው ዙፋኑ እንድንቀርብና ውሳኔዎቹን እንድንሰማ ፈቅዶልናል። እነዚህ ውሳኔዎች በምንኖርባት ዓለም ላይ የሚያስከትሉትን ተጽዕኖ እንድንገነዘብ እስችሎናል። እግዚአብሔር ከኢትዮጵያ፥ ከአሜሪካ፥ ወይም ከሩሲያ መሪዎች የበለጠ ታላቅ አምላክ ነው። እርሱ የነገሥታት ንጉሥና የጌቶች ጌታ፥ እንዲሁም በምድር ላይ የሚወሰኑትን ውሳኔዎች ሁሉ የሚቆጣጠር አምላክ ነው። በዮሐንስ ዘመን፥ እግዚአብሔር በምድር ላይ ባሉት ሕዝቡ ላይ በቅርቡ ታላቅ ስደት እንደሚነሣ ያውቅ ነበር። እንዲሁም በአንድም ሆነ በሌላ መንገድ ስደት በአብዛኞቹ ዘመናት ውስጥ የሚቀጥል ነበር። የእግዚአብሔር ልጆች ታሪክን እንዲረዱ እና ወደፊት ሊሆን ስላለው ጨረፍታውን እንዲመለከቱ በማገዝ፥ የዮሐንስ ራእይ እግዚአብሔር አጽናፈ ዓለሙን የሚገዛበትን ሁኔታ ወደ መንግሥተ ሰማይ ቀርበን እንድንመለከት ይጋብዘናል። እግዚአብሔር ነገሮችን እንደሚቆጣጠር መመልከቱ በምድር ላይ መከራ በምንቀበልበት ጊዜ እጅግ ያበረታታናል። የየትኛውም ንጉሥ አገዛዝ፥ ውሳኔ፥ የትኛውም የተፈጥሮ አደጋ ሁሉ በዙፋኑ ላይ ባለው አምላክና የታሪክን ጥቅልል በያዘው አንበሳና በግ በሆነው ልጁ ቁጥጥር ሥር የሚከናወን ነው። እግዚአብሔር አምላካችን ይነግሣል! የተፈጥሮ አደጋ በሚመታን ጊዜም እርሱ ንጉሥ ነው። ጦርነት ቢነሣም፥ ስለ እምነታችን ስንሰደድም፥ እርሱ በዙፋኑ ላይ ነው። በዮሐንስ ራእይ ውስጥ በተገለጡት እውነቶች አማካኝነት ዓይኖቻችን (የእምነት) ወደ ታላቁ የመንግሥተ ሰማይ ዙፋን እንዲመለከቱ ልንፈቅድ ይገባል። እንዲሁም በዙፋኑ ላይ ለተቀመጠው ምሥጋና ልናቀርብለት ይገባል። ከዚህ በኋላ እግዚአብሔር በታሪክ ውስጥ እንደሚሠራ በማወቅ በልበ ሙሉነት ልንመላለስ እንችላለን።  የውይይት ጥያቄ፡- ራእይ 4-5 እንብብ። ሀ) ስለ እግዚአብሔር አብ የተሰጡትን ስምና ገለጻዎች ዘርዝር። ከእነዚህ ራእዮች ስለ እግዚአብሔር አብ ኃይልና አገዛዝ ምን እንማራለን? ለ) ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ የተሰጡትን ስሞችና ገለጻዎች ዘርዝር። ከእነዚህ ራእዮች ስለ ኃይሉ እና ስለ አገዛዙ ምን እንማራለን? ሐ) እነዚህን ሁለት ራእዮች በምንመለከትበት ጊዜ ምን ዓይነት ስሜት ሊሰርጽብን ይገባል?  በራእይ 4-5፥ የዮሐንስ መገለጦች ከዮሐንስ ዘመን ወደፊት ይገሰግሳሉ። እግዚአብሔር ለዮሐንስ ከራሱ ዘላለማዊ ዙፋን ላይ ተቀምጦ የሚሰጠውን አገዛዝና ለልጁ ለኢየሱስ ክርስቶስ የሚያስተላለፈውን የታሪክ ቁጥጥር ሥልጣን ያሳየዋል። ይህም የሰው ልጅ ታሪክ እግዚአብሔር በወሰነው መልኩ የሚፈጸም ነው። ከራእይ 6–22 ድረስ እግዚአብሔር ለልጆቹ ወደ ፊት የሚፈጸሙትን ነገሮች ያሳያል። እግዚአብሔር በዚህ ክፍል ውስጥ የገለጻቸው አብዛኞቹ ነገሮች ክርስቶስ ጠላቶቹን ለማሸነፍና ለመንገሥ ሊመለስ ሲል የሚከሰቱ ይሆናሉ። ነገር ግን እነዚህ ራእዮች ዛሬም እንኳን በሰማይ ላይ የሚከናወኑትን አንዳንድ ነገሮች እንድንገነዘብ ያግዙናል። የወደፊትን ዘመን የሚቆጣጠረው እግዚአብሔር እርሱ የዛሬንም ዘመን ይቆጣጠራል። ክርስቲያኖች ሁሉ በምድር ላይ የሚፈጸሙ ነገሮች በክፉ መሪዎች ቁጥጥር ሥር አለመሆናቸውን መገንዘብ ይኖርባቸዋል። የእነዚህ ነገሮች ተቆጣጣሪ ሰይጣንም አይደለም። ነገር ግን በምድር ላይ የሚሆነውን ሁሉ የሚቆጣጠረው እግዚአብሔር አብና ልጁ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። አብና ወልድ በሰማይ ሆነው ሁሉንም ይቆጣጠራሉ።  የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) እግዚአብሔር ሁኔታዎችን እንደሚቆጣጠር ሳንረዳ ወይም ሳናምን ስንቀር በሕይወታችን ውስጥ ምን ይከሰታል? ለ) ለአማኝ እግዚአብሔር በሕይወቱ ውስጥ ያሉትን ነገሮች፥ እንዲሁም በአገሩ እና በዓለም ሁሉ የሚካሄዱትን ነገሮች እንደሚቆጣጠር ማወቁ ለምን ያስፈልጋል? በራእይ 4፡2፥ ዮሐንስ «ወደዚህ ቦታ ውጣ» ተብሎ ሲጠራ እንመለከታለን። በዚህም ጊዜ በተምሳሌታዊ በር በኩል ወደ ሰማይ ተወስዶ እግዚአብሔር የሚቀመጥበትንና ታሪክን ሁሉ የሚቆጣጠርበትን ዙፋን ተመልክቷል። አንዳንድ ክርስቲያኖች ይህን ጥቅስ በመጠቀም ክርስቲያኖች በዚህ ጊዜ እንደሚነጠቁ ይናገራሉ። ነገር ግን ይህ ለዮሐንስ እንጂ ለቤተ ክርስቲያን ምእመናን ሁሉ የቀረበ ጥሪ አለመሆኑን መገንዘቡ ጠቃሚ ነው። ዮሐንስ በሰማይ የተመለከተው ምን ነበር?  ፩. የእግዚአብሔር አብ ራእይ (ራእይ 4) ዮሐንስ ወደ ሰማይ ሲደርስ መጀመሪያ የተመለከተው የእግዚአብሔር አብን ዙፋን ነው። ይህ የአጽናፈ ዓለሙ እምብርት ነው። እግዚአብሔር ሁሉንም ነገር የሚቆጣጠረው ከዚህ ሆኖ ነው። በተቀረው የዮሐንስ ራእይ ክፍል በምድር ላይ የሚፈጸሙ ነገሮች ሁሉ ከዚህ ዙፋን እንደሚመነጩ እንመለከታለን። ዮሐንስ እግዚአብሔር አብን በግልጽ ሊያብራራልን አልቻለም። ይህም የሆነው ምናልባትም እግዚአብሔር አብ ከምናውቀው ነገር ሁሉ በላይ የላቀ እና የተለየ በመሆኑ ሙሉ ለሙሉ መረዳት አስቸጋሪ በመሆኑ ይሆናል። እንዲሁም እግዚአብሔር አብ እጅግ ቅዱስና ታላቅ በመሆኑ፥ ለፍጥረቶቹ ሙሉ በሙሉ ተገልጾ አያውቅም። (1ኛ ጢሞ. 6፡16 አንብብ።) ዮሐንስ ሊያደርግ የቻለው ነገር ቢኖር በእግዚአብሔር አብ ዙሪያ የነበሩትን አስገራሚ ቀለሞችና ኃይል መግለጽ ነበር። ዮሐንስ የጠቀሳቸው የከበሩ ድንጋዮች እና ቀስተ ደመና አረንጓዴ፥ ቀይ፥ ነጭ እና ሌሎችንም ልዩ ቀለሞች ያመለክታሉ። መብረቅ እና ነጎድጓድ በዘፋኑ ላይ የተቀመጠውን አምላክ ታላቅነትና ኃይል ያሳያሉ። ዮሐንስ በእግዚአብሔር እና በፍጥረቶቹ መካከል የብርጭቆ ባህር ተመልክቷል። ይህም እግዚአብሔር አብ ምን ያህል ቅዱስና የተለየ እንደነበር ያሳያል። ዮሐንስ በዚህ ራእይ ነገሮችን ሁሉ በሚቆጣጠረው በእግዚአብሔር አብ ብቻ ሳይሆን፥ በዙፋኑ ዙሪያ ባሉትና እነዚህም በዙፋኑ ዙሪያ ያሉት ፍጥረታት ከእግዚአብሔር አብ ጋር ባላቸው ግንኙነት ላይ አጽንኦት ሰጥቷል። ዮሐንስ የሚጠቅሳቸውን የሚከተሉትን ፍጥረታት ተመልከት። ሀ) በ24 ዙፋናት ላይ የተቀመጡ 24 ሽማግሌዎች፡ አንዳንድ ምሁራን እነዚህ የሰማይ መማክርት የሆኑ ገዢ መላእክት እንደሆኑ ያስባሉ። ነገር ግን እነዚህ ፍጥረታት ጠቅላላውን የእግዚአብሔር ሕዝብ በተምሳሌትነት የሚያመለክቱ ይመስላል። የብሉይ ኪዳን አይሁዶች በ12 ነገዶች፥ የአዲስ ኪዳን ቤተ ክርስቲያን ደግሞ በ12 ሐዋርያት በተምሳሌትነት ተወክለዋል። ለ) ሰባቱ የእግዚአብሔር መናፍስት የሆኑ ሰባቱ መቅረዞች፡ «ሰባት መናፍስት» የሚሉ ቃላት «ሰባት እጥፍ መንፈስ» ተብለው ሊተረጎሙ ይችላሉ። ይህም ፍጹም ንጹሕ የሆነውን መንፈስ ቅዱስ በተምሳሌትነት ያሳያል። በእግዚአብሔር አብ ተልዕኮ ዕቅዱን ተግባራዊ ለማድረግ እየተጠባበቅ ከዙፋኑ ፊት ይቆማል። የዮሐንስ ወንጌል እንደሚለው እግዚአብሔር አብና እግዚአብሔር ወልድ መንፈስ ቅዱስ ዕቅዳቸውን ተግባራዊ ያደርግ ዘንድ ወደ አማኞች ይልኩታል (ዮሐ 14፡26፤ 15፡26 አንብብ)። ሐ) አራቱ እንስሶች፡ በሕዝቅኤል 1፡6–14 እንደተጠቀሱት ኪሩቤል፥ እነዚህ የእግዚአብሔርን ትእዛዛት የመፈጸም ኃላፊነት ያለባቸው ኃያላን መላእክትና የእግዚአብሔር አብ የቅድስና ጠባቂዎች ሳይሆኑ አይቀሩም። እነዚህ ፍጥረታት ዓይኖች የሞሉዋቸው መሆናቸው ተገልጾአል። ይህም እየሆነ ያለውን ሁሉ ለማየት የሚችሉ መሆናቸውን ያሳያል። ስድስት ክንፎቻቸው የእግዚአብሔርን ዕቅዶች በፍጥነት እንዲያከናውኑ ያስችሏቸዋል። እነዚህ እንስሳት እንደ አንበሳ፥ በሬ፥ ንሥርና ሰው ያሉ ናቸው። እነዚህ ሁሉ የፍጥረትን ሥርዓት የሚገዙ ናቸው። አንበሳ የዱር አራዊት ንጉሥ ነው፥ በሬ የቤት እንስሳት ንጉሥ ነው፥ ንሥር የአእዋፍ ንጉሥ ነው፥ እንዲሁም ሰው የፍጥረት ሁሉ ንጉሥ ነው። የዮሐንስ ራእይ ባለማቋረጥ ለእግዚአብሔር በሚቀርበው አምልኮ ላይ አጽንኦት ይሰጣል። ሕያዋን ፍጥረታት «ቅዱስ፥ ቅዱስ፥ ቅዱስ» እያሉ ቀንና ሌሊት

እግዚአብሔር በዙፋኑ ላይ ተቀምጦ የሚታይበት ራእይ (ራእይ 4:1-5:14) Read More »