የሕይወት እንጀራ

ወደ ፊልጵስዩስ ሰዎች

ጢሞቴዎስና አፍሮዲጡ፣ ወደር የማይገኝለት ጥንድ (ፊልጵስዩስ 2፡19-30) 

በሳን በርናዲኖ ካሊፎርኒያ ውስጥ፥ አንድ ጋዜጠኛ ተዘዋዋሪ በሚበዛበት መንገድ አጠገብ ከሚገኝ ቦይ ውስጥ አንዱን ሰው ሕመምተኛ አስመስሉ እንዲተኛ አደረገ። ታዲያ በመቶ የሚቆጠሩ ሰዎች በአጠገቡ ይለፉ እንጂ፥ አንዳቸውም ቆመው ሊረዱት ይቅርና የሐዘን ፊት እንኳን አላሳዩትም ነበር።  ከጥቂት ዓመታት በፊት ጋዜጦች አንድ ከዳር እስከዳር የተናኘ ዜና አውጥተው ነበር። ይኸውም አንድ ሰው እያደባ ሴትየዋን ሲቀርባትም ሆነ በመጨረሻም በጩቤ ሲወጋት ሠላሳ ስምንት ተመልካቾች ቢያዩም አንዳቸውም ፖሊስ ለመጥራት ስልክ አለመደወላቸውን የሚገልጽ ነበር።  እንደዚሁም ሁለት ወጣቶች በዲትሮይት ውስጥ ሲሄዱ በስልክ መደወያ ጎጆ ውስጥ አንዲት ሴት በልብ ድካም በሽታ ስትሰቃይ ያገኙአታል። እነርሱም ቅርብ ወደሆነው ቤት ተሸክመዋት በመሄድ፥ ባለቤቱ በሩን ሲከፍትላቸው እርዳታ ጠየቁ። ያገኙት መልስ ግን «ከበረንዳዬ ላይ ዘወር በሉ – እርሷንም የምታደርሱበት አድርሷት» የሚል ነበር።  አንድ የከንታኪ ሐኪም በሽተኛውን ለመጠየቅ በመኪና በመጓዝ ላይ እንዳለ አንድ አደጋ ሲደርስ አየ። ቆመና ለተጎዳው ሰው እርዳታ ካደረገለት በኋላ ወደ በሽተኛው ቤት አመራ። ሆኖም ያ የረዳው ሰው ከጥቂት ቀናት በኋላ ክስ አቀረበበት።  ታዲያ በዛሬው ጊዜ «መልካሙን ሳምራዊ» መሆን ይቻላል? እያንዳንዱስ ሰው ራሱን ለመጠበቅ ሲል ልቡን ማደንደን አለበት ማለት ነው? ምናልባት «መሥዋዕትና አገልግሉት» ጥንታዊ ልማድ ስለሆኑ እኛ ዘመናዊ ሥልጣኔ ብለን ከምንጠራው ጋር ሊስማሙ አይችሉም ይሆናል። እንዳውም እርስ በእርስ መረዳዳት በጳውሎስ ጊዜ እንኳን ያልተለመደ ለመሆኑ አያጠያይቅም። በሮም ያሉ ክርስቲያኖች በፊልጵስዩስ ስላለው ችግር ግድ የላቸውም ነበር። ጳውሎስ ወደ ፊልጵስዩስ ፈቃደኛ ሆኖ የሚሄድለት አንድም ሰው አላገኘም (2፡19-21)። ጊዜው ብዙም አልተለዋወጠም ማለት ነው።  ጳውሎስ በዚህም አንቀጽ፥ አሁንም ቢሆን ስለ ትሑት አእምሮ እያስረዳን ነው። ኢየሱስ ክርስቶስን ምሳሌ በማድረግ ለትሑት አእምሮ መግለጫ ሰጥቶናል (2፡1-11)። ከእራሱ ልምምድ በመነሣት የትሑት አእምሮ እንዴት እንደሚሠራ ቀደም ሲል ያሳየን ነው (2፡ 12-18)። አሁን በአገልግሎቱ ጊዜ ከረዱት ሰዎች መሀል ሁለቱን ያስተዋውቀናል፣ ጢሞቴዎስንና አፍሮዲጡን፣ እና ይህንንም ያደረገው ያለ ምክንያት አልነበረም። በእርግጥ አንባቢዎቹ የሚከተለውን ምክንያት እንደሚያቀርቡ ያውቃል፥ «እኛ እንደ ክርስቶስና እንደ ጳውሎስ ይህን መሰሉቹን ምሳሌዎች ለመከተል አይቻለንም። መቼም ኢየሱስም የእግዚአብሔር አንድያ ልጁ ነው ጳውሎስም የተመረጠ ሐዋርያ፥ ትልቅ መንፈሳዊ ልምምድ ያለው ነው! » ሲሉ ምክንያት ይሰጣሉ። ከዚህም የተነሣ ነው ጳውሎስ ሐዋርያ ወይም በጣም የሚያስደንቅ ተአምር የሚሠሩትን ሳይሆን ሁለቱን «ተራ ቅዱሳን» የሚያስተዋውቀን። እንድናውቅ የሚፈልገውም ትሑት አእምሮን ጥቂት የተመረጡ ሰዎች ብቻ የሚታደሉት ስጦታ አለመሆኑን ነው። ይህ ስጦታ ማንኛውም ክርስቲያን ደስታን ያገኝ ዘንድ የሚያስፈልገው ነው። በመሆኑም ዕድሉ ለሁሉም አማኞች ተሰጥቷቸዋል።  ጢሞቴዎስ (2፡19-24)  ጳውሎስ በመጀመሪያ የወንጌል አገልግሎት ጉዞው ላይ ጢሞቴዎስን በድንገት አገኘው (ሐዋ. 16፡6 ጀምሮ)፥ ምናልባትም በዚያን ጊዜ ወጣቱ ተለውጦ ሊሆን ይችላል (1ኛ ቆሮ. 4፡17)። በመጀመሪያም ክርስትናን የተቀበሉት የጢሞቴዎስ እናትና አያት ነበሩ (2ኛ ጢሞ. 1፡3-5)። እርሱም በእናቱ የአይሁድ በአባቱም የአሕዛብ ልጅ ነበር፥ ነገር ግን ጳውሎስ ሁልጊዜ በእምነት የራሱ «የተወደደ ልጅ» አድርጎ ይቆጥረዋል (2ኛ ጢሞ. 1፡2)። ወጣቱ ጢሞቴዎስ የጳውሎስ ረዳት መሆን የጀመረው ጳውሎስ ወደ ልስጥራንና ደርቤን ለሁለተኛው ጊዜ በተመለሰበት ወቅት ነው(የሐዋ. 16፡1-4)። በአንድ በኩል፥ ጢሞቴዎስ በኋላ ማርቆስ በመባል የሚታወቀውን ዮሐንስን ተክቷል። ይኸውም ጳውሎስ በዚህ በጉዞው ላይ ማርቆስን ይዞ ለመሄድ ባለመፈለጉ ነው። ለዚህም ምክንያቱ ማርቆስ ከዚህ ቀደም ሲል ኃላፊነቱን ለመሸከም ፈቃደኛ ባለመሆኑ ነው (ሐዋ. 13፡13፤15፡36-41)።  ከዚህ ከጢሞቴዎስ ልምምድ ውስጥ የምንማረው ትሑት አእምሮ በአንድ አማኝ ሕይወት ውስጥ ከመቅፅበት የሚታይ ወይንም ትኩረት ሳንሰጠው የሚከሰት ነገር አለመሆኑን ነው። ጢሞቴዎስ ለማደግና ለመጎልበት «የክርስቶስን አሳብ» ያዘ። አገልጋይ መሆን የተፈጥሮው አልነበረም። ነገር ግን የጌታን ፈለግ በመከተሉና ከጳውሎስ ጋር በቅርብ በመሥራቱ፥ ጳውሎስ የሚተማመንበትና እግዚአብሔር የሚባርከው ዓይነት አገልጋይ ለመሆን በቃ። የዚህን ወጣት ሰው ባሕርይ ተመልከት። እርሱ የማገልገል አሳብ ነበረው (2፡19-21)  መጀመሪያ ነገር፥ ጢሞቴዎስ በተፈጥሮው ለሰዎች ጥንቃቄ የሚያደርግ ስለሚያስፈልጋቸውም ነገር የሚጨነቅ ነበር። እርሱ «ጓደኞቹን በማሸነፍና ሰዎችን በመጫን» አይደሰትም ነበር፤ እርሱ ከልቡ የሚደሰተው በሚያገለግላቸው ሰዎች አካላዊና መንፈሳዊ ደኅንነት ነበር። ጳውሎስ ስለፊልጵስዩስ ቤተ ክርስቲያን ጭንቀት አድሮበት ነበር። በመሆኑም ጭንቀቱን የሚገልጽለትና በዚያም የሚያየውን ሁሉ ሳይደብቅ የሚነግረው አንድ ሰው መላክ ፈልጎ ነበር። በሮም ውስጥ በመቶ የሚቆጠሩ ክርስቲያኖች ነበሩ (በሮሜ ከተማ ውስጥ ጳውሎስ ለ26ቱ በስማቸው ሰላምታ አቅርቧል)፤ ሆኖም አንዳቸውም ይህንን ጉዞ ለማድረግ ፈቃደኞች አልነበሩም። «ሁሉ የራሳቸውን ይፈልጋሉና፥ የክርስቶስ ኢየሱስን አይደለም» (ፊልጵ. 2፡21)። ከዚህ የምንረዳው ሁላችንም ብንሆን በፊልጵ. 1፡21 ወይም በፊልጵ. 2፡21 ውስጥ መኖራችንን ነው!  ነገር ግን ጢሞቴዎስ በተፈጥሮው ለሌሎች በጎ ለማድረግ የሚጨነቅ ነበር። ስለዚህ የአገልጋይ አሳብ ያለው ሰው ነበር። በሮም ውስጥ ያሉ አማኞች ግን በራሳቸው ጉዳይ ብቻ የተጠመዱና በውስጣዊ ጭቅጭቃቸው የተያዙ በመሆናቸው (1፡15-16) ለዚህ ዓይነቱ ጠቃሚ ለሆነው የጌታ አገልግሉት ጊዜ አልነበራቸውም። በአሁኑም ጊዜ ቢሆን የቤተ ክርስቲያን ዓቢዩ ችግር አባሎቹ ጊዜያቸውንና ኃይላቸውን አላስፈላጊ በሆኑ ጉዳዮች ላይ ማዋላቸው ነው። ጢሞቴዎስ አንዱን ወገን የማጠናከር ወይም ሌላውን የመከፋፈል ፍላጎትም ምኞትም አልነበረውም። እርሱ በእግዚአብሔር ሰዎች መንፈሳዊ ሁኔታ ብቻ ደስተኛ ነበር። ይህም በተፈጥሮው የተቀዳጀው ጸጋ ነበር። ሆኖም ይህ ጸጋ እንዴት ነው ሊበለፅግና ለሌሎችም አገልግሎት ሊውል የሚችለው? መልሱን በሚቀጥለው በወጣቱ ሰው ባሕርይ ውስጥ እናገኛለን።  ሌሎችን ለማገልገል የሠለጠነ ነበረ (2፡22)  ጳውሎስ ጢሞቴዎስን ክርስቶስን እንደተቀበለ ወዲያውኑ የ«ቡድኑ» አባል አላደረገውም። ጳውሎስ እንዲህ ዓይነቱን ስህተት ላለመፈጸም የሚጠነቀቅ ሰው ነበር። መጀመሪያ ላይ በልስጥራንና ደርቤን ውስጥ የቤተ ክርስቲያን ተራ አባል በመሆን እንዲያገለግል ትቶት ሄደ። ከዚያም በዚያ ኅብረት በመንፈሳዊ ነገሮች አደገ፥ ጌታንም እንዴት እንደሚያገለግል ተማረ። ጳውሎስ ከጥቂት ዓመታት በኋላ ወደዚያ አካባቢ ሲመለስ ስለ ወጣቱ ጢሞቴዎስ «ወንድሞች ሲመሰክሩለት» በመስማቱ ደስ አለው (ሐዋ. 16፡2)። ጳውሎስም ከዓመታት በኋላ ለጢሞቴዎስ ሲጽፍለት፥ አዲስ የተለወጠ ሰው ለአገልግሎት ብቁ ከመሆኑ በፊት ማደግና መሠልጠን እንደሚያሻው ገልጦለታል (1ኛ ጢሞ. 3፡6-7)።  አንድ ታዋቂ የምሽት ክበብ ተጫዋች ወደ አንድ መጋቢ በመሄድ መዳኑንና ጌታን ለማገልገል መፈለጉን አስታወቀው «ከዚህ ቀጥዩ ምን ማድረግ ይገባኛል?» በማለትም ጠየቀው።  «እኔ የማሳስብህ፥ ከአንድ ጥሩ ቤተ ክርስቲያን ጋር ተገናኝተህ ማደግ እንድትጀምር ነው» ብሉ መጋቢው ከመለሰለት በኋላ፥ ከዚያም «ሚስትህ ክርስቲያን ናት?» ሲል ጠየቀው።  «አይደለችም» አለ ሙዚቀኛው፥ «ሆኖም በእኔ አማካይነት እንደምትለወጥ ተስፋ አደርጋለሁ» ካለ በኋላ «ግን እኮ እርሷ ለመለወጥ እፈልጋለሁ እስከምትለኝ መጠበቅ የለብኝም! ማለቴ አሁኑኑ ለእግዚአብሔር አንድ ነገር ማድረግ አለብኝ» አለ።  «አዎን፤ ስለ ጌታ ለመመስከር መጠበቅ አያስፈልግህም። የቤተ ክርስቲያን አባል በመሆን ተሰጥዖህን ለክርስቶስ ተጠቀምበት» ሲል መከረው።  «ነገር ግን እኔን አላወቅከኝም» ብሉ ሙዚቀኛው ተቃወመ፥ «እኔ እኮ ሁሉም ሰው የሚያውቀኝ ትልቅ ተጫዋች ነኝ። የራሴ የሆነም ድርጅት መጀመር እፈልጋለሁ የሙዚቃ ሸክላዎችን ማሳተም፥ በብዙ ሕዝብ መሀልም መታየት እፈልጋለሁ»።  መጋቢው በማስጠንቀቅ፥ «በጣም በርቀትና በፍጥነት ከሄድክ እራስህንና ምስክርነትህን ልትጎዳ ትችላለህ። ሰዎችን መማረክ የሚጀመርበት ቦታ ከቤት ውስጥ ነው። እግዚአብሔር የአገልግሎትን ቦታ የሚከፍትልህ እንደተዘጋጀህ ሲያይ ነው። እስከዚያው ድረስ መጽሓፍ ቅዱስህን አጥና፥ እራስህን ለማሳደግ ዕድል ስጠው» አለው።  ሰውየው የመጋቢውን ምክር አልተቀበለም። በእርሱ ምትክ ግን የራሱ የሆነ ድርጅት ከፍቶ በራሱ ኃይል ለማደግ ጀመረ። ሆኖም ሥራው «የተሳካለት። ከዓመት ላነሰ ጊዜ ብቻ ነበር። ከባዱን ኃላፊነቱን ለመወጣት በቂ ጥንካሬ ስላልነበረው ምስክርነቱን ብቻ ሳይሆን፥ በማያቋርጥ ጉዞው የተነሣም ከሚስቱና ከቤተሰቡ ጋር እንደ ባዕድ መተያየት ጀመረ። ከዚያም እንግዳ ከሆነ ቡድን ጋር በመግጠሙ ከሕዝባዊ አገልግሎቱ ላይ ተሰወረ፥ በመጨረሻም የተበላሸና የከሰረ ሰው ሆነ።  መጋቢውም ሰለ ሰውየው ሁኔታ ሲተች «የጠለቀ ሥር በመስደድ ምትክ፥ ቅርንጫፎቹን ለማንሰራፋት የፈለገ ሰው ነበር። ይህን የሚያደርግ ሰው መጨረሻው ውድቀት ይሆናል» አለ።  ጳውሎስ ይህን መሰሉን ስሕተት በጢሞቴዎስ ላይ አልፈጸመም። ወደታች ሥር እንዲሰድ ጊዜ ሰጥቶት ነበር። ከዚያም ወጣቱን ሰው በወንጌል ሥራ ካስገባው በኋላ አብረው ይሠሩ ነበር። ለጢሞቴዎስ ቃሉን ማስተማር

ጢሞቴዎስና አፍሮዲጡ፣ ወደር የማይገኝለት ጥንድ (ፊልጵስዩስ 2፡19-30)  Read More »

የክርስትና ሕይወት በዝርዝር ሲታይ (ፊልጵስዩስ 2፡12-18)

ማርክ ትዌይን፥ «በጥሩ ምሳሌ መማረክን የመሰለ ከባድ ነገር የለም» ሲል ጽፏል። ምናልባትም ስለጥሩ ምሳሌ ሊሰማን የሚችል ቅሬታ ቢኖር፥ በምሳሌው ውስጥ የተገለጠውን ዓይነት መልካም ባሕርይ በዚህ ሕይወታችን ውስጥ ልንለማመድ ባለመቻላችን መሆን አለበት። በትልቅ ሰው መደነቅ እኛን ሊያነሳሳን ይችላል፤ ነገር ግን እኛን ትልቅ ለመሆን አያስችለንም። በእኛ ሕይወት ሰውየው ካልገባና ችሎታውን ካላካፈለን፥ እኛ ወደ እርሱ ከፍ ያለ የሥራ ውጤት መድረስ አንችልም። ላይ ላዩን ሲያዩት እንደ ምሳሌው ለመሆን ቀላል ይመስላል፤ ዳሩ ግን ባለ በሌለው ውስጣዊ ኃይላችን መጠቀም በግድ ያሻናል።  ጳውሎስ፥ የትሑት አእምሮን ልምምድ በማስመልከት ኢየሱስ ክርስቶስን ታላቁ ምሳሌ በማድረግ አቅርቦልናል። እኛም አንብበነው በእርሱ አሳብ እንስማማ ይሆናል፤ ነገር ግን ትልቁ ጥያቄ፥ «ወደ ልምምድ የምንሸጋገረው እንዴት ነው?» የሚለው ነው። ሌላው ጥያቄ ደግሞ «ደካማው የሰው ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ የፈጸመውን ለመፈጸም እንደ ምን ተስፋ ለማድረግ ይችላል?» የሚል ነው። ይህን ለመሞከር እንኳን ጨርሶ የማይቻል ይመስላል። እኛ ግን ትሕትናን ለመለማመድና ለማሳደግ፥ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስን ለመምሰል በድፍረት በመነሳሳት በኩራት እየታበይን ነው።  እንደ እውነቱ ይህን ለማሟላት ያን ያህል አስቸጋሪ አይደለም። ጳውሎስ የማይቻለውን «ዘላችሁ ከከዋክብት ላይ ድረሱ» ሲል አልጠየቀንም። እርግጥ የእኛ ግብ ከዚህም የበለጠ ነውና በበኩላችንም በዚያው መጠን ጥረት ልናደርግ ይገባናል። ጳውሎስም የሚያሳስበን በትሑት አእምሮ በመመራት እንዴት የእግዚአብሔርን ትእዛዛት ልናሟላ እንደምንችልና በእርሱም ፈለግ መጓዝ እንደሚኖርብን ነው። «በእናንተ የሚሠራ እግዚአብሔር ነውና» (2፡13)። በማስመሰል ሳይሆን ግን ሥጋችንን በመልበሱ «ክርስቶስ ግን በእኔ ይኖራል»(ገላ. 2፡20) ለማለት እንድንችል ነው። የክርስትና ሕይወት ገባ ወጣ ወይንም የሚፈራረቅ አይደለም። በምትኩ በማይቃረን ሁኔታ «በውስጣችንና በውጪም» የሚሠራ ኃይል ነው። እግዚኣብሔር ከውስጥ ይሠራል እኛ ደግሞ ከውጭ እንሠራለን። ትሕትና የተሞላ አእምሮን የምናሳድገው እግዚአብሔር ለእኛ በመለኮታዊ መንገድ ለሚያዘጋጅልን ነገሮች ምላሽ በመስጠት ነው።  ለመፈጸም ዓላማ አለን (2፡12፥ 14-16)  «የራሳችሁን መዳን ፈጽሙ» (ቁ. 12) ማለት «ለራሳችሁ መዳን ሥሩ» ማለት አይደለም። መጀመሪያ ነገር፥ ጳውሎስ ሲጽፍ በቅድሚያ «ቅዱሳን» (1፡1) ለሆኑ ሰዎች ነው፥ ይህም ማለት እነርሱ በክርስቶስ አምነዋልና ለራሱ የለያቸው ናቸው። «ፈጸመ» የሚለው ግሥ የያዘው ትርጉም «ሥራን ሙሉ በሙሉ አከናወነ» ወይም በሒሳብ ቋንቋ ቀመሩን በትክክል አስቀመጠ እንደማለት ነው። በጳውሎስ ጊዜ ቃሉን «ለማዕድን ሥራ» ይጠቀሙበት ነበር። ይኸውም የተለያዩ ማዕድናትን ከአፈርና ከድንጋይ ውስጥ አንጥሮ ማውጣትን ያመለክታል። እንደዚሁም «በእርሻ ሥራ» ላይ ብዙ መከር ለማግኘት የሚደረገውን ጥረት ለመግለጥ ያገለግል ነበር። የእግዚአብሔር ፍላጎት እኛ ክርስቶስን ለመምሰል በምናደርገው ጥረት ከግብ እንድንድረስ ነው። «የልጁን መልክ እንዲመስሉ» (ሮሜ 8፡29)። በሕይወት ውስጥ ችግሮች አሉ፥ ግን እግዚአብሔር «እንድንወጣቸው» ይረዳናል። የእኛ ሕይወት እንደ ማዕድኑና እንደ እርሻው በከፍተኛ ሊበለጽግ የሚችል ነው፥ እና እርሱም ይህን እንድንፈጽም ሊረዳን ይፈልጋል።  ሲንዲ ከዩኒቨርስቲ ከቤተሰቦችዋ ጋር በዓልን ለማሳለፍ ቤት ስትደርስ የተደሰተች አትመስልም። ወላጆችዋ ያልተለመደ ባሕሪዋን አውቀዋል፤ ግን እርሷ እራሷ ችግሯን እስክታካፍላቸው ድረስ ይጠብቋታል። ከእራት በኋላ እንዲህ ሆነ።  «እናቴ፥ አባቴ ሆይ፤ እስቲ አንድ ነገር ልነግራችሁ እፈልጋለሁ፤ ግን እንድታዝኑብኝ አልፈልግም» አለች። «በልብሽ ያለውን ንገሪን» ብሎ አባቷ አደፋፈራት፤ «እኛ እንረዳሻለን፥ ምንም ነገር ይሁን ካንቺ ጋር ስለ ችግሩ እንጸልያለን»። «መቼም እንደምታስታውሱት ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት እያለሁ ነርስ እንደምሆን ብዙ ጊዜ አወራ ነበር፤ ምክንያቱ እናቴ ነርስ ስለሆነች እና እናንተም የእርሷን ፈለግ እንደምከተል ሳትገምቱ ባለመቅረታችሁ ነው። ነገር ግን በዚህ ዓላማዬ ለመቀጠል አልቻልኩም። ጌታ ነርስ እንድሆን አልፈለገም» አለቻቸው።  እናቷ ፈገግ ብላ የሲንዲን እጅ ያዘችና «ውዴ፥ አባትሽና እኔ የምንፈልገው የእግዚአብሔር ፈቃድ በሕይወትሽ ውስጥ እንዲመራሽ ነው። ከዚህ ውጭ ሌላ ነገር ብትሠሪ ግን ሁላችንም አንደሰትም።» አለቻት።  ሲንዲ የወሰደችው የድፍረት እርምጃ ነበር። ይኸውም የእግዚአብሔርን ፈቃድ በመጠበቅ ለራሷ መዳን ለመሥራት ፈለገች፡ የራሷን ክርስትና ሕይወት ተከተለች እንጂ ሌላ ሰው እንድትሆን የመከራትን ለመሆን አልፈለገችም። ክርስቲያን የመሆን አንዱ አስደናቂ ነገር እግዚአብሔር በእኛ ሕይወት ያለውን ፈቃድ ለማወቅ መቻላችንና ፈቃዱን ለክብሩ ሲል እንድንፈጽመው እንደሚረዳን መገንዘባችን ነው (ኤፌ. 2፡10)። እግዚአብሔር በምንም ነገር የማይወሰን ፈጣሪ አምላክ ነው። ሁለት አበቦች አንድ አይደሉም፥ ሁለት የሱፍ ዘለላዎች አንድ አይደሉም፤ ታዲያ ሁለት ክርስቲያኖች ለምን አንድ መሆን ይገባቸዋል? ሁላችንም ክርስቶስን መምሰል አለብን፥ ግን እኛ ደግሞ ራሳችንን መሆን አለብን።  «የራሳችሁን መዳን ፈጽሙ» የሚለው ሐረግ ምናልባት በተለይ በፊልጵስዩስ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ላለው ልዩ ችግር የተጻፈ መረጃ ይሆናል፤ ዓረፍተ-ነገሩ ግን ለእያንዳንዱ ክርስቲያን ይሠራል። እኛ የሌሎች ሰዎች ቅጂ መሆን አይገባንም። በተለይም የታላላቅ ክርስቲያኖች ግልባጮች መሆን አይገባንም። እኛ መከተል ያለብን በሕይወታቸው ውስጥ የምናየውን የክርስቶስ ባሕርያት ብቻ ነው። «እኔ ክርስቶስን እንደምመስል እኔን ምሰሉ» (1ኛ ቆሮ. 11፡1)። እያንዳንዱ «ታላቅና ቅዱስ ነኝ ባይ» ደካማ ጎን አለው፤ እና ውሉ አድሮ ተስፋ ሊያስቆርጠን ይችላል። ኢየሱስ ክርስቶስ ግን ፈጽሞ ለውድቀት አይዳርገንም።  በቁጥር 14 እና 15 ውስጥ ጳውሎስ የአማኝን ሕይወት በዓለም ከሚኖሩ ሰዎች ጋር ያነጻጽራል። ያልዳኑ ሰዎች ያማርራሉ፥ በሌሉች ላይ አቃቂር ለማውጣት ይጥራሉ፤ ክርስቲያኖች ግን በደስታ ይሞላሉ። በዙሪያችን ያለው ኅብረተሰብ «የተወሳሰበና የተዛባ» ነው። ክርስቲያኖች ግን ቀጥ ብለው ይቆማሉ ምክንያቱም ሕይወታቸው የሚለካው በእግዚአብሔር ቃል በመሆኑ ነው። እርሱም ፍጹም መለኪያ ነው። ዓለም ጨለማ ነው ክርስቲያኖች ግን እንደ ደማቅ ብርሃን ይበራሉ። ዓለም የምትሰጠው ምንም ነገር የላትም፥ ክርስቲያን ግን በክርስቶስ በማመን የሕይወት ቃል የሆነውን የደኅንነት መልእክት ይሠጣል። በሌላ አነጋገር እግዚአብሔር በእኛ ሕይወት ሊያሟላ የሚፈልገውን እንዲሠራ ከፈቀድንለት፥ እኛም በተራችን በዓለም ውስጥ ተስፋ ለቆረጡትና ክርስቶስ ለሚያስፈልጋቸው ምስክሮች እንሆናለን። እነዚህ ባሕሪያትን ከኢየሱስ ጋር ስናነጻጽር እርሱ በዚህ ፍጹም ባልሆነ ዓለም ፍጹም የሆነ ኑሮ እንደኖረ እናያለን።  ከልብ ልናጤነው የሚገባው ነገር ደግሞ ይህ ግብ «በዚህ በመጥፎና በጠማማ ትውልድ መካከል» እንኳን ሊሳካ መቻሉን ነው። ጳውሎስ ከምንኖርበት ዓለም ተገልለን፥ ሕይወታችንን ሙሉ በምነና እንድናውለው አይመክረንም። እንደ እውነቱ ክርስቶስን ይበልጥ መምሰል የምንጀምረው በዕለት ኑሮአችን ላይ ችግሮች ሲገጥሙንና ፈተናዎችን በድል ስንወጣ ብቻ ነው። ፈሪሳውያን በጣም የተለዩ እና ከእውነት የራቁ ከመሆናቸውም፥ የራሳቸው የሆነ ሰው-ሰራሽ ጽድቅ በማስፋፋት እግዚአብሔር እንዲኖራቸው ከሚፈልገው ጽድቅ የራቁ ነበሩ። በመሆኑም ፈሪሳውያን ሃይማኖታቸውን በግዳጅ ተቀባይነት እንዲኖረው ለማድረግ ይጥራሉ። እናም በሰዎች ላይ ባርነትን ይጭናሉ (ማቴ. 23 አንብብ)። ኢየሱስን የሰቀሉበትም ምክንያት ይህንን ዓይነት ሃይማኖት በመቃወም በድፍረት ስለተናገረ ነው። የእግዚአብሔርን ዓላማ በሕይወታችን ለመፈጸም የምንችለው ራሳችንን ከዓለም በማግለል ሳይሆን ሌሎችን በማገልገል ነው።  የምንቀበለው ኃይል አለ (2፡13)  ጳውሎስ የጻፈው መመሪያ፥ እግዚአብሔር በእኛ ተጠቅሞ ከመሥራቱ በፊት በእኛ ውስጥ መሥራት አለበት የሚል ነው። ይህ መመሪያ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በምናገኛቸው እንደ ሙሴ፥ ዳዊት፥ ሐዋርያት እና ሌሎች ሰዎች ሕይወት ውስጥ እንደሠራ እናያለን። እግዚአብሔር ለእያንዳንዱ ሰው ሊፈጽመው ያለ ልዩ ዓላማ አለው። በመሆኑም እያንዳንዱ ሰው ልዩ ነው እንጂ አንዱ ሌላውን ሰው ሊሆን አይችልም። ለምሳሌ እግዚአብሔር ሙሴን የእስራኤልን ሕዝብ ወዳዘጋጀው ቦታ እንዲመራ ለማዘጋጀት ለአርባ ዓመታት ታግሦ ጠብቋል። ሙሴ በእነዚያ አርባ ዓመታት የበጎች እረኛ በመሆን ቢያገለግልም እግዚአብሔር በእርሱ ውስጥ ይሠራ ነበር። ዝግጅቱም እግዚአብሔር በእርሱ አማካይነት የሚሠራበት ቀን እስከሚደርስ ነበር። እግዚአብሔርም ከሥራው ይበልጥ በሠራተኛው ይደሰታል። ሠራተኛው ትክክለኛ ሰው እስከሆነ፥ ሥራውም የሰመረ ይሆናል።  በጣም ብዙ ክርስቲያኖች በውስጣቸው ባለው ኃይል ገፋፊነት ሳይሆን ከውጪ በሚያድርባቸው ተጽዕኖ የተነሳ ለእግዚአብሔር ይታዘዛሉ። ጳውሎስ የፊልጵስዩስ ሰዎችን ሲያስጠነቅቅ እርሱ ከእነርሱ ጋር ባይሆንም፥ ትልቁ ቁም ነገር ግን እግዚአብሔርን ለመታዘዝና ለማስደሰት ፍላጎት እንዲኖራቸው መሆኑን ገልጦላቸዋል (1፡27፤ 2፡12)። ሕይወታቸውን በጳውሎስ ላይ መመሥረት አይችሉም። ምክንያቱም እርሱ ከእነርሱ ጋር ለሁልጊዜም አብሯቸው የሚቆይ ባለመሆኑ ነው። በመሪዎች ለውጥ ምክንያት አንዳንድ የቤተ ክርስቲያን አገልግሎቶች ሲደክሙ ወይም ሲፈርሱ ሳይ አዝናለሁ። ሰዎችን የማስደሰት ፍላጎት አለን፥ እንደዚሁም የሌሎችን አድናቆት ለማግኘትም ስንል ብቻ ለእግዚአብሔር የምንታዘዝበት ጊዜ አለ፤ ነገር ግን ልቦናችንን ለእግዚአብሔር

የክርስትና ሕይወት በዝርዝር ሲታይ (ፊልጵስዩስ 2፡12-18) Read More »

ትሕትናን ከክርስቶስ መማር (ፊልጵስዩስ 2፡1-11) 

አንድ የካርቱን ፊልም ገጸ ባሕርይ እንዲህ አለ፥ «ለመውደዱ እንኳ መላውን የሰው ዘር እወድ ነበር፤ ሆኖም ሰዎችን በግል ልቀርባቸው አልሻም!»  ሰዎች ደስታችንን ሊቀሙን ይችላሉ። ጳውሎስ ከሰዎች የተነሳ በሮም (1፡15-18) ችግር ገጥሞታል። በተለይም በፊልጵስዩስ ያሉት ነበሩ የበለጠ ችግር ያደረሱበት። አፍሮዲጡን ከፊልጵስዩስ ቤተ ክርስቲያን ወደ ጳውሎስ ብዙ ስጦታንና ስለ ጳውሎስ መልካም ወሬ አመጣ። በዚያውም መጠን በቤተ ክርስቲያኗ ውስጥ ያለውን መከፋፈል የሚያረዳም ክፉ ወሬ ይዞ መጥቶ ነበር። የቤተ ክርስቲያኗን አንድነት ከሁለት አቅጣጫ የተቃጣ ጥቃት በሥጋት ላይ የጣላት ይመስላል፤ ይኸውም ከውጭ የሚመጡ የስሕተት አስተማሪዎች (3፡1-3) እና በውስጥ ያሉት አባሎች አለመስማማት (4፡1-3) ነበር። ኤዎድያን («መዓዛ») እና ሲንጤኪ («ዕድለኛዋ») በምን የተነሣ እንደሚከራከሩ ጳውሎስ አልጠቀሰውም። ምናልባት ሁለቱም የሚፈልጉት የሴቶች ማኅበር ወይም የመዝሙር ቡድን ፕሬዚዳንት ለመሆን ይሆናል።  ጳውሎስ የሚያውቀውን ያህል፥ በዛሬ ጊዜ የሚገኙት አንዳንድ የቤተ ክርስቲያን ሠራተኞች አያውቁም። በአንድነትና በተመሳሳይነት መካከል ያለውን ልዩነት እንኳን የማይረዱ ብዙዎች ናቸው። እውነተኛ መንፈሳዊ አንድነት ከውስጥ የሚመጣ ነው፤ ይኸውም ከልብ የሚመነጭ ነው። ተመሳሳይነት ከውጪ ከሚመጣ ጠላት የተነሣ የሚዳብር የአንድነት ስሜት ነው። ለዚህም ነው መግቢያ ጽሑፉን መንፈሳዊ መነቃቃትን ለማስገኘት ዓላማ ያዋለው (2፡1-4)። በፊልጵስዩስ ያሉ አማኞች «በክርስቶስ ውስጥ» የሚኖሩ እንደመሆናቸው ይህ በራሱ በመከፋፈልና በመፎካከር ምትክ በፍቅርና በአንድነት እንዲሠሩ ሊያበረታታቸውም በተገባ ነበር። ጳውሎስም አክብሮት በተሞላ መንገድ ለቤተ ክርስቲያኗ እንዲህ አለ፥ «የእናንተ አለመስማማት የሚያሳየው በኅብረታችሁ ውስጥ መንፈሳዊ ችግር እንዳለ ነው። ለዚህም በሕግ ወይም በማስፈራራት መፍትሔ ማግኘት አይቻልም። ለእነዚህ መፍትሔ ማግኘት የሚቻለው ልባችሁን ለክርስቶስ ስታስገዙና እርስ በርሳችሁ በፍቅር ስትተያዩ ነው» ። ጳውሎስ ለማሳየት የፈለገው ለችግሩ ዋናው ምክንያት ራስ ወዳድነት መሆኑን ነው። የራስ ወዳድነት መነሻው ኩራት ነው። በክርስትና ሕይወት ውስጥ ራስን ከሌሉች በላይ በማድረግ ምንም ደስታ ማግኘት አይቻልም።  ተቃራኒ ሁኔታዎች ቢያጋጥሙም ደስታን ለመቀዳጀት ምሥጢሩ በአንድ አሳብ መጽናት ብቻ ነው። ሰዎች ቢቃወሙንም አሁንም ደስታ የማግኛው ምሥጢር የአእምሮ ትሕትና ነው። ዋናው ጥቅስ፥ «ለወገኔ ይጠቅማል በማለት ወይም በከንቱ ውዳሴ ምክንያት አንድ እንኳ አታድርጉ፥ ነገር ግን እያንዳንዱ ባልንጀራው ከራሱ ይልቅ እንዲሻል በትሕትና ይቁጠር» ይላል (2፡3)። በምዕራፍ 1 «ክርስቶስ መጀመሪያ» እንደተደረገ ያየነው ሲሆን በምዕራፍ 2 «ሌሉች ሁለተኛ» መሆናቸውን እንመለከታለን። እንደዚሁም በምዕራፍ 1 ውስጥ የነፍሳት ማራኪ የነበረው ጳውሎስ በምዕራፍ 2 ውስጥ አገልጋይ ሆኖ እናገኘዋለን።  በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ «ትሕትና» ምን ማለት እንደሆነ መረዳቱ በጣም ጠቃሚ ነው። ትሑቱ ሰው ስለራሱ ብቻ የሚያስብ አይደለም፤ እንዳውም ስለእራሱ ጨርሶ አይጨነቅም። ትሕትና፥ አንድ ነገር እንዳለን እያወቅን፥ የለንም ለማለት የሚያስችለን ጸጋ ነው። በእውነቱ ትሑት የሆነ ሰው ራሱን ያውቃል፥ ደግሞም ራሱን ይቀበላል (ሮሜ 12፡3)። የክርስቶስ አገልጋይ አድርጎ ራሱን ይሰጣል፥ እርሱነቱንም ሆነ ያለውን ሁሉ ለእግዚአብሔር ክብርና ለሌሎችም ጥቅም ያውላል። በዚህ ምዕራፍ (ቁ. 3-4) ውስጥ «ሌሉች» የሚለው ዋና አሳብ ነው፤ የአማኞች ዓይን በራሳቸው ላይ ከማተኮር ይልቅ በሌሎች ፍላጎት ላይ ያርፋል ማለት ነው።  «ትሑት አእምሮ» የሚያመለክተው ሁሉም ሰው እንደፈለገ የሚያዘውን ወይም ሁሉም ሰው የሚጠቀምበትን «መንፈሰ ደካማ» የሆነ አማኝ አይደለም! አንዳንዶች ብዙ ጓደኞችን ለማፍራትና የቤተ ክርስቲያንን አንድነት ለመጠበቅ ሲሉ፥ ለማንኛውም ሰው ምኞትና ፍላጎት ተገዢዎች ይሆናሉ። ጳውሎስ እንደዚህ ዓይነት አሳብ በፍጹም አላቀረበም በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በግልጽ የሰፈረው «ስለ ኢየሱስም ራሳችንን ለእናንተ ባሪያዎች እናደርጋለን» (2ኛ ቆሮ. 4፡5) የሚል ነው።  በምዕራፍ 1 ውስጥ በስፋት የተብራራው «አንድ አሳብ» እስካለን በምዕራፍ 2 ያለውን «ትሑት አእምሮ» ለማዳበር ችግር አይገጥመንም።  ጳውሎስ ስለ ትሑት አእምሮ አራት ምሳሌዎችን ሰጥቶናል፡ እነርሱም ኢየሱስ ክርስቶስ (ቁ. 1-11)፣ ጳውሎስ ራሱ (ቁ. 12-18)፥ ጢሞቴዎስ (ቁ. 19-24) እና አፍሮዲጡን (ቁ. 25-30) ናቸው። በእርግጥ ትልቁ ምሳሌ ኢየሱስ ሲሆን፥ ጳውሎስም የሚጀምረው በእርሱ ነው። ትሑት አእምሮ ያለው ሰው የሚኖሩት አራት ባሕርያት በኢየሱስ ክርስቶስ ውስጥ እንደሚከተለው ይንጸባረቃሉ።  ለሌሎች ያስባል፥ ለራሱ አይደለም (2፡5-6)  የክርስቶስ «አሳብ» ማለት ክርስቶስ የሚያሳየው «ጠባይ» ማለት ነው። «በክርስቶስ ኢየሱስ የነበረው ይህ አሳብ በእናንተም ዘንድ ደግሞ ይሁን» (ቁ. 5)። ያም ሆነ ይህ አመለካከታችን ውጤቱን ይወስናል። አመለካከታችን ራስ ወዳድነት ከሆነ ድርጊቶቻችን አውዳሚ ይሆናሉ። ያዕቆብ ይህንኑ ዓይነት ነገር ተናግሯል (ያዕ. 4፡1-10 ተመልከት)።  እነዚህ በፊልጵስዩስ መልእክት ውስጥ ያሉት ጥቅሶች እኛን ወደ ቀድሞው ዘለዓለማዊነት ይወስዱናል። «የእግዚአብሔርን መልክ» በቅርጽ ወይም በመጠን ለመግለጽ አይቻልም። እግዚአብሔር መንፈስ ነው (ዮሐ. 4፡24)፥ እና እንደዚህ ያለውን አሳብ በሰው አነጋገር መግለጽ አይቻልም። በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ «የጌታ አይኖች» ወይም «የጌታ እጅ» የሚል ብንመለከትም፥ ይህ ግን እግዚአብሔር የሰው ቅርጽ አለው ማለት አይደለም። መለኮታዊ ሁኔታዎችን (የእግዚአብሔር ባሕርይ) እና ድርጊቶችን፥ በሰው አነጋገር ለመግለጽ የተደረገ ሙከራ ነው። «ምስል» የሚለው ቃል የውስጣዊውን ተፈጥሮ በውጭአዊ ገለጻ የሚያቀርብ ነው። ይህም ማለት በቀድሞው ዘላለማዊነት ውስጥ፥ ኢየሱስ ክርስቶስ፥ እግዚአብሔር ነበር ማለት ነው። ጳውሎስ እንደተናገረው እርሱ «ከእግዚአብሔር ጋር እኩል» ነው። በሌላ ጥቅሶች ላይ ደግሞ፥ ለምሳሌ በዮሐ. 1፡1-4፣ ቆላ. 1፡15 እና ዕብ. 1፡1-3፥ ኢየሱስ ክርስቶስ እግዚአብሔር እንደሆነ በግልጥ ሰፍሯል።  ስለዚህ ኢየሱስ ክርስቶስ እንደ እግዚአብሔርነቱ ምንም ነገር ባላስፈለገውም ነበር! ክብርና ምስጋና ሁሉ በሰማይ አለው። ከአባቱና ከመንፈስ ቅዱስ ጋር በዓለማት ላይ ይነግሣል። በቁጥር 6 ላይ እንደተጠቀሰው የሚያስደንቀው እውነት ከእግዚአብሔር ጋር መተካከሉን መግለጥ «እንደራስ ወዳድነት» እንዳይቆጠር በመፈለጉ አልተጠቀመበትም። ኢየሱስ ስለእራሱ አያስብም፤ የሚያስበው ለሌሎች ነው። የእርሱ አመለካከት (ፍላጎት) ለሌሎች ራስ ወዳድነት የሌለበት አሳቢነቱን ማሳየት ነው። እንግዲህ «የክርስተስ አሳብ» ማለት «ያለኝን መብቶች ለእራሴ ብቻ አልይዝም፥ የምጠቀምባቸውም ለሌሉች ነው። እና ይህን ለማድረግ በደስታ እነርሱን ትቼ የሚያስፈልገውን ዋጋ ሁሉ እከፍላለሁ» የሚል አስተሳሰብ ነው።  አንድ ጋዜጠኛ፥ በመቶ የሚቆጠሩ ሰዎችን በየሙያቸው ለማስቀጠር ለቻሉ አንድ የሥራ አማካሪ ቃለ መጠይቅ አቅርቦላቸው ነበረ። እርሳቸውም የጠየቅከኝ ይህ እንዴት እንደተሳካልኝ እንዳብራራልህ ነው በማለት ሲገልጡ፥ «በእውነት አንድ ሠራተኛ ምን ይመስላል ብለህ ለማወቅ እስከፈለግህ፥ ኃላፊነትን ሳይሆን መብትን ስጠው። ብዙ ሰዎች ኃላፊነት የሚይዙት በቂ ገንዘብ ሲከፈላቸው ነው። ነገር ግን እውነተኛ መሪ መብቱን ለመያዝ ቅድሚያ ይሰጣል። መሪውም በመብቱ የሚጠቀመው ሌሎችን ለመርዳት፥ ድርጅቱን ለማስፋፋት ነው። አስተሳሰቡ አነስተኛ የሆነ ሰው ግን በሚያገኘው መብት ራሱን ለማበልጸግ ይሽቀዳደማል» በማለት ደምድመዋል። ኢየሱስም በሰማዩ መብቱ የሚጠቀመው ለሌሉች ማለትም እኛን ለመርዳት ነው።  የክርስቶስን ሁኔታ ከሉሲፈር (ሰይጣን) (ኢሳ. 14፡12-15) ጋር እና ከአዳም (ዘፍ. 3፡1-7) ጋር ማነጻጸር የሚገባ አይደለም። ብዙ የመጽሐፍ ቅዱስ ተማሪዎች እንደሚያምኑት የሉሲፈር አወዳደቅ የሚገልጸው የሰይጣንን አወዳደቅ ነው። አንድ ጊዜ ከመላእክት ፍጥረት ሁሉ ታላቅ፥ ለእግዚአብሔር ዙፋን የቀረበ ነበር (ሕዝ. 28፡11-19)። ነገር ግን የእርሱ ፍላጎት በእግዚአብሔር ዙፋን ላይ ለመቀመጥ ሆነ። ሉሲፈር «አደርጋለሁ» ሲል በድፍረት ይናገራል፥ ኢየሱስ ግን «ፈቃድህ ይሁን …» ይላል። ሉሲፈር ፍጡር በመሆኑ አይረካም፤ እርሱ የሚፈልገው ፈጣሪ መሆን ነው። ኢየሱስ በፈቃዱ ሰው ሆነ እንጂ ፈጣሪ ነው። የክርስቶስ ትሕትና የሰይጣንን ኩራት ይገሥጸዋል።  ሉሲፈር እራሱ ዐመፀኛ መሆኑ ስላላረካው ወደ ኤደን ገነት ጣልቃ በመግባት ሰውንም ዐመፀኛ እንዲሆን ገፋፋው። አዳም የሚያስፈልገው ሁሉ ነበረው፤ በእውነቱ እርሱ እግዚአብሔር በፈጠረው ላይ ሁሉ «ንጉሥ» ነበር («ይግዙ» ዘፍ. 1፡26 ይላል)፤ ነገር ግን ሰይጣን «እንደ እግዚአብሔር ትሆናላችሁ» አለ። ሰው በድንገት አሁን ከነበረበት ደረጃ በላይ የጨበጠ መሰለው፥ እና ውጤቱም የሰውን ዘር በሙሉ ወደ ኃጢአትና ሞት ጣለ። አዳምና ሔዋን የሚያስቡት ለራሳቸው ብቻ ነው፤ ኢየሱስ ክርስቶስ ግን ለሌሎች ያስባል።  ያልዳኑ ሰዎች ራስ ወዳድና ስስታም ስለ መሆናቸው ለእኛ አዲስ ነገር አይደለም፤ ሆኖም ግን የክርስቶስን ፍቅር ከተለማመዱና የመንፈስ ኅብረት (ፊልጵ. 2:1-2) ካላቸው ክርስቲያኖች ይህንን አንጠብቅም። በአዲስ ኪዳን ከሃያ ጊዜ በላይ «እርስ በርሳችን» ተፋቅረን እንድንኖር እግዚአብሔር አዝዞአል። እርስ በርሳችሁ ተከባበሩ (ሮሜ 12፡10)፥ እርስ በርሳችሁ ተመካከሩ (1ኛ ተሰ. 5፡11)

ትሕትናን ከክርስቶስ መማር (ፊልጵስዩስ 2፡1-11)  Read More »

ደስታችንን እንዴት እንጨምራለን (ፊልጵስዩስ 1፡1-11)

ኅብረት የሚለው ቃል ለብዙ ሰዎች የተለያየ ትርጉም ይሰጣል። ምናልባትም ለአንዳንድ ሰዎች ልክ እንደ አረጀ ሳንቲም ያህል፥ ማሳየት የሚገባውን እውነተኛ መልክ አጥቷአል ለማለት ይቻላል። እንዲህ ከሆነ የቃሉን ትክክለኛ ትርጉም ለማቆየት አንዳንድ እርምጃዎችን ብንወስድ ይሻላል። ለነገሩ፥ እንደ ኅብረት ያለው መልካም የመጽሐፍ ቅዱስ ቃል በመካከላችን ብዙ ጊዜ ሊዘወተር ይገባዋል።  ጳውሎስ በሮም እስረኛ በነበረበት ጊዜ አስቸጋሪ አጋጣሚዎች ቢደርሱበትም ደስተኛ ነበር። የደስታውም ምሥጢር አንድ አሳብ ነው፤ እርሱ የሚኖረው ለክርስቶስ እና ለወንጌል ነው። (በምዕራፍ አንድ «ክርስቶስ» 18 ጊዜ እና «ወንጌል» ደግሞ 6 ጊዜ ተጠቅሷል)። «ለእኔ ሕይወት ክርስቶስ ሞትም ጥቅም ነውና» (ፊል. 2፡2)። ስለዚህ «አንድ አሳብ» ስንል ምን ማለት ነው? ለዚህ ትክክለኛው መልስ፥ «ክርስቶስ ይክበር፥ ወንጌል ለሌሉች ይዳረስ እንጂ በእኔ ላይ ምንም ቢደርስብኝም ለውጥ አያመጣም» የሚል ነው። ጳውሎስ በችግር ውስጥ ቢሆንም ደስተኛ ነው። ምክንያቱም ሁኔታዎቹ የወንጌል ኅብረትን አጠነከሩለት (1፡1-11)፥ ወንጌልን አስፋፋ (1፡12-26)እና የወንጌልንም እምነት ጠበቀ(1፡27-30)።  ኅብረት የሚለው ቃል «በጋራ አለን» ማለት ነው። እውነተኛ የክርስቲያን ኅብረት አብሮ ከመብላትና ከመጠጣት፥ ከመጫወትም በላይ ሥር የሰደደ ነው። በጣም ብዙ ጊዜ «ኅብረት» የሚለው ቃል ለእኛ የሚያስታውሰን፥ ግንኙነትን (ትውውቅ) ወይም ጓደኝነትን ነው። ከአንድ ሰው ጋር በጋራ የምንካፈለው ከሌለን ኅብረት ማድረግ አንችልም፥ እናም ለክርስቲያኖች ኅብረት፡ ማለት የዘላለም ሕይወትን በልብ መያዝ ማለት  ነው። አንድ ሰው ክርስቶስን እንደ አዳኙ ካልታመነ ስለ «ወንጌል የሆነ ኅብረት» ምንም አያውቅም። በፊልጵ. 2፡1 ውስጥ ጳውሎስ ስለ «መንፈስ የሆነ ኅብረት» ጽፏል። ምክንያቱም አንድ ሰው ዳግም በተወለደ ጊዜ የመንፈስን ስጦታ ይቀበላል (ሮሜ 8፡9)። ደግሞም «በመከራውም እንድንካፈል» የሚል ቃል አለ (ፊልጵ.3፡10)። ያለንን ከሌሎች ጋር በምንካፈልበት ጊዜ ይህም ደግሞ ኅብረት ነው (4፡15)።  ስለዚህ፥ እውነተኛ የክርስቲያን ኅብረት በቤተ ክርስቲያን ስምን ከማስጠራትና በየጉባኤው ከመገኘት በብዙ የተለየ ነው። ሰዎችን በአካል አጠገባቸው ሆኖ በመንፈስ ግን ብዙ ኪሎ ሜትር መራቅ ይቻላል። አንደኛው የክርስቲያን የደስታ ምንጭ አማኞች በኢየሱስ ክርስቶስ ያላቸው ኅብረት ነው። ጳውሎስ በሮም ነበረ፥ ጓደኞቹም ደግሞ ብዙ ኪ.ሜ. ርቀው ፊልጵስዩስ ነበሩ፥ ነገር ግን መንፈሳዊ ኅብረታቸው ተጨባጭ እና የሚያረካ ነበረ። አንድ አሳብ በሚኖራችሁ ጊዜ፥ ስለ አጋጣሚዎች አታማርሩም፤ ምክንያቱም አስቸጋሪ አጋጣሚዎች የወንጌልን ኅብረት እንደሚያጠናክሩት ስለምታውቁ ነው።  ጳውሎስ በ1፡1-11 ሦስት አሳቦችን ተጠቅሞ የክርስቲያንን እውነተኛ ኅብረት አስረዳ፡- አስታውሳችኋለሁ (ቁ. 3-6)፡ በልቤ ትኖራላችሁ (ቁ. 7-8) እጸልይላችኋለሁ (ቁ. 9-11)።  አስታውሳችኋለሁ (1፡3-6) ጳውሎስ ስለራሱ ማሰብ ትቶ ለሌሎች ማሰቡ የሚያስደንቅ አይደለምን? ጳውሎስ በሮም ፍርዱን እየጠበቀ አሳቡን በፊልጵስዩስ ወዳሉት አማኞች በመመለስ እያንዳንዱ የሚያስታውሰው ነገር ደስታን ይሰጠው ነበር። የሐዋርያት ሥራ 16ን አንብቡ፤ ይህንን ስታነቡ ጳውሎስ በፊልጵስዩስ ከተማ ስለደረሰበት በደል ማወቅ ትችላላችሁ፥ ይህ ትውስታ ሐዘንን የሚፈጥር ነው። አግባብ ያልሆነ እስራትና ድብደባ ደረሰበት፥ ከግንድ ጋር አጣብቀው አስረውት ነበር፥ በሰዎችም ፊት ተዋርዶ ነበር፤ ነገር ግን እነዚህን ሲያስታውስ እንኳን ለጳውሎስ ደስታ ይሰጠዋል፥ ምክንያቱም በዚህ መከራ ውስጥ በማለፍ ነበር የወህኒ ጠባቂው ክርስቶስን ለማግኘት የቻለው! ጳውሎስ ሊዲያንና ቤተሰቧን ያስታውሳል፥ በአጋንንት ተይዛ የነበረችውን ድሀ ልጅ፥ እንዲሁም በፊልጵስዩስ ያሉ ውድ ክርስቲያኖችን እና ሌሎችም የሚያስታውሳቸው ነገሮች የደስታው ምንጭ ነበሩ። (እንዲህ ብለን እራሳችን መጠየቅ የሚገባን ነው «ለመሆኑ መጋቢዩ ስለእኔ በሚያስብበት ጊዜ እውነተኛ ደስታን የማስገኝለት ዓይነት ክርስቲያን ነኝን?»)።  ቁጥር 5 እነርሱ (የፊልጵስዩስ ሰዎች) ከጳውሎስ ጋር ስለነበራቸው ገንዘብ-ነክ ኅብረት ሊያወራ ይችላል፥ ይህን አርእስት በድጋሚ በ4:14-19 አንስቶታል። የፊልጵስዩስ ቤተ ክርስቲያን የጳውሎስን አገልግሎት ለማገዝ ከጳውሎስ ጋር ኅብረት ያደረገች ብቸኛ ቤተ ክርስቲያን ነበረች። በቁጥር 6 ላይ «መልካም ሥራ» ብለን የምንመለከተው ያላቸውን ነገር እንደሚከፋፈሉ ነው፤ ይህም የተጀመረው በጌታ እንደመሆኑ ጳውሉስም ጌታ በዚሁ እንደሚቀጥልና ከፍጻሜ እንደሚያደርሰው እርግጠኛ ነበር።  ነገር ግን እነዚህን ጥቅሶች ለድነታችንና (ለደኅንነታችንና) ለክርስቲያናዊ ኑሮአችን ዋስትና እንደሚያስገኙልን አድርገን መውሰዱ ወደ ስህተት ሊያመራን አይችልም። እኛ የዳንነው በመልካም ሥራችን አይደለም (ኤፌ. 2፡8-9)። ድነት (ደኅንነት) ማለት በልጁ ስናምን እግዚአብሔር በእኛ የሚሠራው መልካም ሥራ ነው። በፊል. 2፡12-13 እንደሚናገረን እግዚኣብሔር በእኛ የጀመረውን ሥራ በመንፈሱ በኩል ይቀጥላል በሌላ አነጋገር፥ ድነት በአጠቃላይ ሦስት አቅጣጫ ያለው ነው።  – እግዚአብሔር ለእኛ የሠራው – መዋጀት  – እግዚአብሔር በእኛ ውስጥ የሚሠራው – መቀደስ  – እግዚአብሔር በእኛ አማካኝነት የሚሠራው – አገልግሎት  ይህ ሥራ ክርስቶስን እስከምናየው ድረስ የሚቀጥል ሲሆን ከዚያ በኋላ ግን ሥራው ይፈጸማል «ቢገለጥ እርሱ እንዳለ እናየዋለንና እርሱን እንድንመስል እናውቃለን» (1ኛ ዮሐ. 3፡2)።  እግዚአብሔር በፊልጵስዩስ ባሉ አማኝ ጓደኞቹ ሕይወት ውስጥ እስካሁን መሥራቱን ማወቅ ለጳውሎስ የደስታው ምንጭ ነበር። በእርግጥም እውነተኛ መሠረት ያለው ደስተኛ የክርስቲያን ኅብረት አለ ለማለት የምንችለው እግዚአብሔር በየቀኑ ኑሮአችን ውስጥ ሲሠራ ነው።  በልቤ ውስጥ ትኖራላችሁ (ፊል 1፡7-8) አሁን ደግሞ ትንሽ ጠለቅ ወዳለ አስተሳሰብ እንተላለፍ፤ ሌሎችን በአእምሮአችን ልናስታውሳቸው ብንችልም እንደ እውነቱ ግን በልባችን ውስጥ ላይኖሩ ይችላሉ። (አንድ ሰው እንደ ታዘበው፥ በዛሬው ጊዜ ብዙ ሰዎች፥ «አንጄቴን ቆርጠኃል!» በሚለው ገለጻ መጠቀማቸው የተለመደ ሆኗል።) ጳውሎስ ለጓደኞቹ ያለው ቅን የሆነ ፍቅር ግን የተሰወረ ወይም እንዳስመሳይ አልነበረም።  የክርስቲያን ፍቅር «የሚያስተሳስር» ነው። ፍቅር ተድነታችን (የደኅንነታችን) ማስረጃ ነው «እኛ ወንድሞችን የምንወድ ስለሆንን ከሞት ወደ ሕይወት እንደተሸጋገርን እናውቃለን» (1ኛ ዮሐ. 3፡14)። ጨው አልጫ ውስጥ ቢገባ ወጡን እንደሚያጣፍጠው ሁሉ ፍቅር የማኅበራዊ ጉዳዮችን የኑሮ እንቅስቃሴ ያለምንም እንቅፋት በሰላማዊ መንገድ እንዲጓዝ ይረዳል። ጳውሎስ ሲጽፍ «ሁላችሁም» የሚለውን ሐረግ ብዙ ጊዜ እንደተጠቀመበት አስተውላችኋል? በዚህ መልእክት ቢያንስ ቢያንስ ዘጠኝ ጊዜ ጠቅሶት ነበር። ስለሁሉም ሰው በማሰብ አንድም ሰው እንኳን ቢሆን እንዲገለልበት አይፈልግም (አንዳንድ ትርጉሞች «እኔ በልብህ ውስጥ አለሁ» ይላሉ። ለምሳሌ በቁጥር 7 ውስጥ ተመልከት፤ ሆኖም ግን መሠረታዊው እውነት ኣንድ መሆኑን ልብ በል።)  ጳውሎስ ፍቅሩን እንዴት ነበር ያሳያቸው? አንዱ ነገር፥ እርሱ ስለ እነርሱ መከራ ይቀበል ነበር። እስራቱም ፍቅሩን ያረጋግጣል። እርሱ «አሕዛብ ስለሆናችሁ ስለእናንተ የክርስቶስ እስረኛ ነበር» የተባለለት ሰው ነው (ኤፌ. 3፡1)። ጳውሎስ ለፍርድ በመቅረቡ ምክንያት፥ ክርስትና በሮም ባለሥልጣኖች ፊት በአግባቡ መታየት ጀመረ። ፊልጵስዩስ በሮም ቅኝ ግዛት ሥር ስለነበረች፥ በዚያ ያሉትን አማኞች ውሳኔው ጎድቷቸዋል። የጳውሎስ ፍቅር እንደው ለአፍ ያህል የሚናገረው ሳይሆን የተለማመደው ነገር ነበር። ለእርሱ አስቸጋሪ ሁኔታዎች ቢያጋጥሙትም፥ ዳሩ ግን ያንን አጋጣሚ ወንጌልን ለመጠበቅና እውነት መሆኑን ለማስረዳት ጥሩ ዕድል አድርጎ ቆጥሮታል። በዚህም በየቦታው ያሉት ወንድሞቹ ተጠቅመውበታል።  ታዲያ ይህን ዓይነቱን ፍቅር ለመለማመድ ክርስቲያኖች እንዴት መማር ይችላሉ? «እኔ ካልዳኑት ዘመዶቼ ይልቅ ከዳኑት ጎረቤቶቼ ጋራ መኖር የበለጠ ይቀለኛል» ብሎ አንድ ሰው ለመጋቢው አጫወተውና በመቀጠልም «ምናልባትም አንድ ቢላዋ ስለት እንዲያወጣ በሌላ ቢላዋ መሞረድ ያሻዋል እንደሚሉት ዓይነት ለእኔም ተመሳሳይ እርዳታ ሳያስፈልገኝ አይቀርም» ሲል አከለበት። የክርስቲያን ፍቅር እኛ የምንሠራው ነገር ሳይሆን እግዚአብሔር በእኛ ውስጥ እና በእኛም አማካይነት ለሌሉች የሚሠራው ነገር ነው። ጳውሎስ ከጓደኞቹ ተለያይቶ በመቆየቱ «በክርስቶስ ኢየሱስ እንደምናፍቃችሁ» ሲል ጽፏል (ቁ. 8)። ይህም ማለት የጳውሎስ ፍቅር በክርስቶስ አማካይነት ተገልጿል ማለት ሳይሆን፥ በዚያ ምትክ ግን የክርስቶስ ፍቅር በጳውሎስ አማካይነት ተላለፈ ማለት ነው። «በተሰጠን በመንፈስ ቅዱስ አማካይነት የእግዚአብሔር ፍቅር በልባችን ስለ ሞላ ተስፋው አያሳፍረንም» (ሮሜ 5፡5 አዲስ ትርጉም)። እግዚአብሔር «መልካሙን ሥራ» በእኛ ውስጥ እንዲያከናውን ስንፈቅድ፥ እርስ በርሳችን በፍቅር እናድጋለን።  በእውነት ከሌላው ክርስቲያን ጋር በፍቅር መተሳሰራችንን እንዴት መናገር እንችላለን? አንደኛ ነገር፥ እኛ ለሌሎች ማሰባችን ነው። በፊልጵስዩስ ያሉ አማኞች ለጳውሎስ ስለሚያስቡ አፍሮዲጡን እንዲያገለግለው ላኩለት። ጳውሎስም ደግሞ በተለይ አፍሮዲጡን በህመሙ ምክንያት መልሶ ለመላክ ባቃተው ጊዜ (2፡25-28) በፊልጵስዩስ (ስላሉት) ወዳጆቹ በጣም ያስብ ነበር። «ልጆቼ ሆይ፥ በሥራና በእውነት እንጂ በቃልና በአንደበት አንዋደድ» (1ኛ ዮሐ. 3፡18)።  እርስ በርስ ይቅር ለመባባል ፈቃደኛ መሆን ሌላው የክርስቲያን ፍቅር መግለጫ ነው። «ፍቅር

ደስታችንን እንዴት እንጨምራለን (ፊልጵስዩስ 1፡1-11) Read More »

እጸልይላችኋለሁ (ፊል 1፡9-11) 

“ፍቅራችሁ በጥልቅ እውቀትና በማስተዋል ሁሉ በዝቶ እንዲትረፈረፍ እጸልያለሁ። ይኸውም ከሁሉ የሚሻለውን ለይታችሁ እንድታውቁ፣ እስከ ክርስቶስም ቀን ድረስ ንጹሓንና ነቀፋ የሌለባችሁ እንድትሆኑ፣ ለእግዚእብሔር ክብርና ምስጋና በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል በሚገኘው የጽድቅ ፍሬ እንድትሞሉ ነው።” ጳውሎስ በፊልጵስዩስ ላሉት ወዳጆቹ የሚያድግ ፍቅር ስለነበረው ሲያስታውሳቸው ደስተኛ ይሆናል። በጸሎት ወደ ጌታው የጸጋ ዙፋን በቀረበ ጊዜ ሁሉ እነርሱን በፊቱ እያስታወሰ ደስተኛ ነበር። በብሉይ ኪዳን ጊዜ ሊቀ ካህኑ በልቡ ላይ የሚደርበው ኤፉድ የተባለ ልዩ ልብስ ነበረው። በዚህም ላይ በእያንዳንዱ የእስራኤል ነገዶች ስም በከበረ ድንጋይ የተቀረጹ አሥራ ሁለት ድንጋዮች ይገኛሉ (ዘጸ. 28፡15-29)። ጳውሎስም እንደሚያደርገው ሁሉ እርሱም በፍቅር ለሕዝቡ ያለውን ፍቅር በልቡ ይሸከም ነበረ። ምናልባትም በዚህ ሕይወታችን የምንለማመደው ከፍተኛው ክርስቲያናዊ ሕብረትና ደስታ የሚገኘው፥ ከጸጋ ዙፋኑ ሥር በፍቅር አብረን ስንጸልይና አንደኛችን ለሌላው ስንጸልይ ነው።  ይህ ጸሎት አማኞች በመንፈሳዊ ሕይወታቸው ብስለት እንዲያገኙ ነው፤ ጳውሎስ ይህንን የጀመረው በፍቅር ነው። ያም ሆነ ይህ የክርስቲያን ፍቅራችን እንደሚገባ ከሆነ የቀሩት ነገሮች ሁሉ ይከተሉናል። የሚለማመዱት ፍቅር የሞላ ፍቅርና ቀናዒ ፍቅር እንዲሆንላቸው ይጸልያል። የክርስቲያን ፍቅር እውር ፍቅር አይደለም! ልብና አሳብ አብረው ስለሚሠሩ ልንወደውና ልንጠላው የሚገባንን ለይተን እናውቃለን። ጳውሎስ ወዳጆቹ በዚህ ዓይነቱ ፍቅር በሙላት እንዲያድጉ ይፈልጋል፥ ይኸውም «የተለያዩ ነገሮችን መለየት» እንዲችሉ ነው።  የመለየት ችሎታ የማደግ ምልክት ነው። አንድ ሕፃን ለመናገር በሚለማመድበት ጊዜ አራት እግር ያለውን እንሰሳ ሁሉ «ውው.. ውው» እያለ ይጣራል። በኋላ ግን ድመቶች፥ ውሾች፥ አይጦች፥ ላሞች እና ሌላ ባለአራት እግር ፍጥረቶች እንዳሉ ይገነዘባል። ለሕፃን ልጅ አንድ መኪና ከሌላው መኪና ጋር አንድ ነው፥ ግን ወደ ጎልማሣነቱ ሲቃረብ ወላጆቹ ከሚጠሩት የመኪና ስም ፈጥኖ የሞዴሉን ልዩነት እንኳን ይናገራል። እርግጠኛ የሆነ የማደግ ምልክቶች አንደኛው መለየት የሚችል ፍቅር ነው።  ጳውሎስ ደግሞ ለክርስቲያኖች «ቅንና አለነውር» የሆነ ባሕርይ እንዲኖራቸው ይጸልያል። ከግሪክ ቃል የተተረጎመው ቅን የሚለው ቃል የተለያየ ትርጉም አለው። አንዳንዶቹ «በፀሐይ ብርሃን የተፈተነ» ብለው ይተረጉሙታል። ቅን የሆነ ክርስቲያን በብርሃን መቆም አይፈራም። አንድ ሰው ለታላቁ እንግሊዛዊ ሰባኪ፥ ለቻርልስ ስፐርጀን የሕይወት ታሪክህን ለመጻፍ እፈልጋለሁ ሲል ይነግረዋል። ስፐርጀን ግን «የእኔን ሕይወት ታሪክ በደመና ላይ መጻፍ ትችላለህ። ምንም የተደበቀ ነገር የለኝም» ሲል መልሶለታል።  ሌሎች ደግሞ፥ ቅን ማለት «በወንፊት ውስጥ ተንገዋልሉ» መውጣትን ያመለክታል ይላሉ፡ ይህም አሳብ ገለባን ከማስወገድ ወይም ከማበራየት ዘዴ ጋር የተያያዘ ነው። በሁለቱም ትርጉሞች ላይ እውነቱ አንድ ነው፤ ጳውሎስ ለወዳጆቹ ፈተናን ማለፍ የሚችል የዚህ ዓይነቱ ባሕርይ እንዲኖራቸው ይጸልይላቸዋል።  ጳውሎስ የሚጸልይላቸው የበሰለ የክርስቲያን ፍቅር እና ባሕርይ እንዲኖራቸው እና «ለክርስቶስ ቀን ያለ ነውር እንዲሆኑ» ነው (ቁ. 10)። ይህም ማለት የእኛ ሕይወት ለሌሉች መሰናከያ ምክንያት እንዳይሆንና ኢየሱስ ሲመለስ በክርስቶስ የፍርድ ወንበር ፊት ለመቅረብ ዝግጁ እንዲሆን ነው (2ኛ ቆሮ. 5:10 እና 1ኛ ዮሐ. 2:28 ተመልከት)። እኛ መንፈሳዊነትን መለየት እንድንለማመድ መከተል የሚገባን ሁለት መፈተኛ መንገዶች እንደሚከተለው ቀርበዋል፡- (1) ለሌሉች መሰናክል የሆንኩበት ጊዜ አለን? (2) ኢየሱስስ ሲመጣ አፍር ይሆንን?  ከዚህ በተጨማሪም ጳውሎስ የበሰለ የክርስቲያን አገልግሎት እንዲኖራቸው ይጸልያል። ሕይወታቸው የጽድቅ ፍሬ የተሞላ እንዲሆን ይፈልጋል (ቁ. 11 አዲስ ትርጉም)። የእርሱ ፍላጎት «በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት» ውስጥ በምናደርገው ተሳትፎ የተወሰነ አይደለም፥ ግን ከክርስቶስ ጋር በምናደርገው ኅብረት በምናስገኘው የመንፈስ ፍሬ ዓይነት ላይ ጭምርም ነው። «በእኔ ኑሩ እኔም በእናንተ። ቅርንጫፍ በወይኑ ግንድ ባይኖር ከራሱ ፍሬ ሊያፈራ እንዳይቻለው፥ እንዲሁ እናንተ ደግሞ በእኔ ባትኖሩ አትችሉም» (ዮሐ. 15፡4)። ብዙ ክርስቲያኖች በክርስቶስ ከመኖር እና ፍሬን ለማግኘት ሕይወታቸውን ከመስጠት ይልቅ «ውጤት ለማግኘት» በራሳቸው ጥረት ይሞክራሉ።  እግዚአብሔር በሕይወታችን ማየት የሚፈልገው «ፍሬ» ምንድን ነው? በእውነት እርሱ የሚፈልገው «የመንፈስ ፍሬ» (ገላ. 5፡22-23) ማስገኘታችንን ነው። የክርስቲያን ባሕርይ እግዚአብሔርን ያስከብራል። ጳውሎስ የጠፋውን ነፍስ ለክርስቶስ ማዳንን ፍሬ ከማፍራት ጋር ያመሳስለዋል (ሮሜ 1፡13)። እና «ቅድስናን» ደግሞ እንደ መንፈስ ፍሬ ይጠራዋል (ሮሜ 6፡22)። «በበጎ ሥራ ሁሉ ፍሬ አፍሩ» (ቆላ. 1፡10) ብሎ አጥብቆ ያሳስባል። በዕብራውያን ላይ ደግሞ የእኛ ምስጋና «የከንፈራችን ፍሬ» (13፡15) መሆኑን ያስታውሰናል። የፍሬ ዛፍ ፍሬ በሚያፈራበት ጊዜ አንዳችም ዓይነት ጩኸት አያሰማም፤ ሕይወት በውስጡ እንዲሠራ ብቻ ይፈቅዳል፤ ውጤቱም ፍሬው ራሱ ነው። «እኔ የወይን ግንድ ነኝ እናንተ ቅርንጫፎች ናችሁ። ያለ እኔ ምንም ልታደርጉ አትችሉምና በእኔ የሚኖር እኔም በእርሱ፥ እርሱ ብዙ ፍሬ ያፈራል» ( ዮሐ. 15፡5)።  በመንፈስ ፍሬ እና በሰው «የሃይማኖት አገልግሎት» መሀል ያለው ልዩነት ለኢየሱስ ክርስቶስ ክብር በሚያመጡት ፍሬ ላይ ነው። ምንጊዜም አንድን ነገር በራሳችን ኃይል ስንሠራ፥ እኛ ስለሠራነው የመመካት ፍላጎት ይኖረናል። እውነተኛ የመንፈስ ፍሬ እጅግ ያማረ እና ግሩም ነው። ክብሩ ወደ እግዚአብሔር ብቻ እንጂ ማንም ሰው ለራሱ «ዋጋ ይገባኛል» አይልም።  እውነተኛ የክርስቲያን ኅብረት ከተራ ወዳጅነት ያለፈና ያለንን በጋራ ለመካፈል የሚያስችል ጥልቅ መተሳሰብ መሆን አለበት። «አስታውሳችኋለሁ … በልቤ ውስጥ ትኖራላችሁ … እጸልይላችኋለሁ አላቸው»። እንዲህ ዓይነት ኅብረት ደስታን ያስገኛል፥ ይህን ኅብረት ለማግኘት ደግሞ አንድ አሳብ መሆን ነው።  አንድ ሰው ወደ ኒውዮርክ ከተማ ለልዩ ቀዶ ጥገና ሕክምና መሄድ ግድ ቢሆንበትም እርሱ ግን ርቆ መሔዱን አልወደደውም ነበር። «ለምንድን ነው የዚህ ዓይነቱ ሕክምና በአካባቢያችን የማይሰጠው?» ብሉ ሐኪሙን ጠየቀው። «በዚያ በግር ግር በተሞላ ታላቅ ከተማ ውስጥ አንድ ሰው እንኳ አላውቅም» አለው። ነገር ግን ባለቤቱና እርሱ ከሆስፒታሉ ሲደርሱ እነርሱን ለመገናኘት የመጣ አንድ መጋቢ አገኙ። ከተማውን እስኪለማመዱትም በእርሱ ቤት እንዲቀመጡ ጋበዛቸው። ቀዶ ጥገናው አስጊ ስለነበረ በሆስፒታሉ ውስጥ ለመቆየት የነበረው ዕድል ረጅምና አስቸጋሪ ነበር፤ ነገር ግን የባለቤቱና የመጋቢው ኅብረት ደስታን አስገኘለት። እኛም እነዚህን መሰሎቹ አጋጣሚዎች ለወንጌል ኅብረት ማጠናከር መንገድ እንደሚከፍቱ እስካመንበት ድረስ ሁኔታዎች ደስታችንን ሊነጥቁን እንደማይችሉ እርግጠኞች እንሆናለን።  በተግባር ላይ እናውለው!  እስቲ በዚህ ሳምንት ውስጥ ሁኔታዎች ሁሉ ወደ ክርስቲያን ወዳጆችህ እንድትቀርብ እንዲያደርጉህ ሞክር። አንድ አሳብ ብቻ ካለህ – ማለትም የምትኖረው ለክርስቶስና ለወንጌል እስከሆነ፥ ያለምንም ጥርጥር ከዚያ በኋላ መከራዎችህና ችግሮችህ የወንጌልን ኅብረትን እንደሚያጠነክሩ ትገነዘባለህ፥ ያም ኅብረት ከፍተኛ ደስታን ያጎናጽፍሃል። በ1966ዓ.ም፥ በሰዓት በ90 ማይል ፍጥነት የሚበር መኪና ገጭቶኝ በአስጊ ሁኔታ ላይ እገኝ ነበር። ሆኖም በዚያ ሳቢያ የመሠረትኩት መልካም ኅብረት ውጤት የደረሰብኝን ሕመምና ችግር ሁሉ የሚያስረሳ ነበር። ያም አጋጣሚ ነበር ወደ እግዚአብሔር ሕዝብ እንድቀርብ ያስቻለኝ።  «ለእኔ ሕይወት ክርስቶስ፥ ሞትም ጥቅም ነውና።» (1፡21)።  ምንጭ፣ ጽሑፍ በ ዋረን ደብልዩ ዌርዝቢ፣ ትርጉም በመስፍን ታዬ፣ እርማት በ ዓብይ ደምሴ

እጸልይላችኋለሁ (ፊል 1፡9-11)  Read More »

በልቤ ውስጥ ትኖራላችሁ (ፊል 1፡7-8) 

በልቤ ውስጥ ትኖራላችሁ (ፊል 1፡7-8)  “በልቤ ስላላችሁ፣ ስለ ሁላችሁ እንዲህ ማሰቤ ተገቢ ነው፤ በእስራቴም ሆነ ለወንጌል ስመክትና ሳጸናው ሁላችሁም ከእኔ ጋር የእግዚአብሔር ጸጋ ተካፋዮች ናችሁና። በክርስቶስ ኢየሱስ ፍቅር ሁላችሁንም ምን ያህል እንደምናፍቃችሁ እግዚአብሔር ምስክሬ ነው።” አሁን ደግሞ ትንሽ ጠለቅ ወዳለ አስተሳሰብ እንተላለፍ፤ ሌሎችን በአእምሮአችን ልናስታውሳቸው ብንችልም እንደ እውነቱ ግን በልባችን ውስጥ ላይኖሩ ይችላሉ። (አንድ ሰው እንደ ታዘበው፥ በዛሬው ጊዜ ብዙ ሰዎች፥ «አንጄቴን ቆርጠኃል!» በሚለው ገለጻ መጠቀማቸው የተለመደ ሆኗል።) ጳውሎስ ለጓደኞቹ ያለው ቅን የሆነ ፍቅር ግን የተሰወረ ወይም እንዳስመሳይ አልነበረም።  የክርስቲያን ፍቅር «የሚያስተሳስር» ነው። ፍቅር ተድነታችን (የደኅንነታችን) ማስረጃ ነው «እኛ ወንድሞችን የምንወድ ስለሆንን ከሞት ወደ ሕይወት እንደተሸጋገርን እናውቃለን» (1ኛ ዮሐ. 3፡14)። ጨው አልጫ ውስጥ ቢገባ ወጡን እንደሚያጣፍጠው ሁሉ ፍቅር የማኅበራዊ ጉዳዮችን የኑሮ እንቅስቃሴ ያለምንም እንቅፋት በሰላማዊ መንገድ እንዲጓዝ ይረዳል። ጳውሎስ ሲጽፍ «ሁላችሁም» የሚለውን ሐረግ ብዙ ጊዜ እንደተጠቀመበት አስተውላችኋል? በዚህ መልእክት ቢያንስ ቢያንስ ዘጠኝ ጊዜ ጠቅሶት ነበር። ስለሁሉም ሰው በማሰብ አንድም ሰው እንኳን ቢሆን እንዲገለልበት አይፈልግም (አንዳንድ ትርጉሞች «እኔ በልብህ ውስጥ አለሁ» ይላሉ። ለምሳሌ በቁጥር 7 ውስጥ ተመልከት፤ ሆኖም ግን መሠረታዊው እውነት ኣንድ መሆኑን ልብ በል።)  ጳውሎስ ፍቅሩን እንዴት ነበር ያሳያቸው? አንዱ ነገር፥ እርሱ ስለ እነርሱ መከራ ይቀበል ነበር። እስራቱም ፍቅሩን ያረጋግጣል። እርሱ «አሕዛብ ስለሆናችሁ ስለእናንተ የክርስቶስ እስረኛ ነበር» የተባለለት ሰው ነው (ኤፌ. 3፡1)። ጳውሎስ ለፍርድ በመቅረቡ ምክንያት፥ ክርስትና በሮም ባለሥልጣኖች ፊት በአግባቡ መታየት ጀመረ። ፊልጵስዩስ በሮም ቅኝ ግዛት ሥር ስለነበረች፥ በዚያ ያሉትን አማኞች ውሳኔው ጎድቷቸዋል። የጳውሎስ ፍቅር እንደው ለአፍ ያህል የሚናገረው ሳይሆን የተለማመደው ነገር ነበር። ለእርሱ አስቸጋሪ ሁኔታዎች ቢያጋጥሙትም፥ ዳሩ ግን ያንን አጋጣሚ ወንጌልን ለመጠበቅና እውነት መሆኑን ለማስረዳት ጥሩ ዕድል አድርጎ ቆጥሮታል። በዚህም በየቦታው ያሉት ወንድሞቹ ተጠቅመውበታል።  ታዲያ ይህን ዓይነቱን ፍቅር ለመለማመድ ክርስቲያኖች እንዴት መማር ይችላሉ? «እኔ ካልዳኑት ዘመዶቼ ይልቅ ከዳኑት ጎረቤቶቼ ጋራ መኖር የበለጠ ይቀለኛል» ብሎ አንድ ሰው ለመጋቢው አጫወተውና በመቀጠልም «ምናልባትም አንድ ቢላዋ ስለት እንዲያወጣ በሌላ ቢላዋ መሞረድ ያሻዋል እንደሚሉት ዓይነት ለእኔም ተመሳሳይ እርዳታ ሳያስፈልገኝ አይቀርም» ሲል አከለበት። የክርስቲያን ፍቅር እኛ የምንሠራው ነገር ሳይሆን እግዚአብሔር በእኛ ውስጥ እና በእኛም አማካይነት ለሌሉች የሚሠራው ነገር ነው። ጳውሎስ ከጓደኞቹ ተለያይቶ በመቆየቱ «በክርስቶስ ኢየሱስ እንደምናፍቃችሁ» ሲል ጽፏል (ቁ. 8)። ይህም ማለት የጳውሎስ ፍቅር በክርስቶስ አማካይነት ተገልጿል ማለት ሳይሆን፥ በዚያ ምትክ ግን የክርስቶስ ፍቅር በጳውሎስ አማካይነት ተላለፈ ማለት ነው። «በተሰጠን በመንፈስ ቅዱስ አማካይነት የእግዚአብሔር ፍቅር በልባችን ስለ ሞላ ተስፋው አያሳፍረንም» (ሮሜ 5፡5 አዲስ ትርጉም)። እግዚአብሔር «መልካሙን ሥራ» በእኛ ውስጥ እንዲያከናውን ስንፈቅድ፥ እርስ በርሳችን በፍቅር እናድጋለን።  በእውነት ከሌላው ክርስቲያን ጋር በፍቅር መተሳሰራችንን እንዴት መናገር እንችላለን? አንደኛ ነገር፥ እኛ ለሌሎች ማሰባችን ነው። በፊልጵስዩስ ያሉ አማኞች ለጳውሎስ ስለሚያስቡ አፍሮዲጡን እንዲያገለግለው ላኩለት። ጳውሎስም ደግሞ በተለይ አፍሮዲጡን በህመሙ ምክንያት መልሶ ለመላክ ባቃተው ጊዜ (2፡25-28) በፊልጵስዩስ (ስላሉት) ወዳጆቹ በጣም ያስብ ነበር። «ልጆቼ ሆይ፥ በሥራና በእውነት እንጂ በቃልና በአንደበት አንዋደድ» (1ኛ ዮሐ. 3፡18)።  እርስ በርስ ይቅር ለመባባል ፈቃደኛ መሆን ሌላው የክርስቲያን ፍቅር መግለጫ ነው። «ፍቅር የኃጢአትን ብዛት ይሸፍናልና ከሁሉም በፊት እርስ በርሳችሁ አጥብቃችሁ ተዋደዱ(1ኛ ጴጥ. 4፡8)።  ከዕለታት አንድ ቀን የሬዲዮ ፕሮግራም አዘጋጅ ለአንድ ሰው ቃለ መጠይቅ አቀረበለት፤ ያም ቃለ መጠይቅ እንዲህ የሚል ነበር፡- «ባለቤትህ የፈጸመችውን አንዳንድ ስሕተቶችን ልትነገረን ትችላለህን?» ብሉ ጠየቀው።  «ምንም ነገር ማስታወስ አልችልም» ሲል ሰውየው መለሰለት።  «ታዲያ፣ አንዳንዱን እንኳን ማስታወስ አያቅትህም» አለው የፕሮግራሙ አዘጋጅ።  «አይ፥ በእውነቱ ማስታወስ አልችልም» አለ መልስ ሰጪው። «ባለቤቴን በጣም ስለምወዳት እንደዚህ ያለውን ነገር በትክክል አላስታውስም»። በ1ኛ ቆሮ. 13፡5 ውስጥ «ፍቅር በደልን አይቆጥርም» ተብሎ ተጠቅሷል።  በፍቅር የሚሠሩ ክርስቲያኖች ሁልጊዜ ደስታን ይለማመዳሉ፥ ሁለቱም የአንድ መንፈስ መገኘት ውጤት ነው። «የመንፈስ ፍሬ ፍቅር፥ ደስታ … ነው» (ገላ. 5፡22)። ምንጭ፣ ጽሑፍ በ ዋረን ደብልዩ ዌርዝቢ፣ ትርጉም በመስፍን ታዬ፣ እርማት በ ዓብይ ደምሴ

በልቤ ውስጥ ትኖራላችሁ (ፊል 1፡7-8)  Read More »

እናንተን ባስታወስሁ ቍጥር አምላኬን አመሰግናለሁ (ፊል 1፡3-6) 

“እናንተን ባስታወስሁ ቍጥር አምላኬን አመሰግናለሁ። ዘወትር ስለ ሁላችሁ ስጸልይ፣ በደስታ እጸልያለሁ፤ ከመጀመሪያው ቀን አንሥቶ እስካሁን ድረስ በወንጌል አገልግሎት ተካፋይ ሆናችኋልና። በእናንተ መልካምን ሥራ የጀመረው እርሱ እስከ ክርስቶስ ኢየሱስ ቀን ድረስ ከፍጻሜው እንደሚያደርሰው ርግጠኛ ነኝ።” ጳውሎስ ስለራሱ ማሰብ ትቶ ለሌሎች ማሰቡ የሚያስደንቅ አይደለምን? ጳውሎስ በሮም ፍርዱን እየጠበቀ አሳቡን በፊልጵስዩስ ወዳሉት አማኞች በመመለስ እያንዳንዱ የሚያስታውሰው ነገር ደስታን ይሰጠው ነበር። የሐዋርያት ሥራ 16ን አንብቡ፤ ይህንን ስታነቡ ጳውሎስ በፊልጵስዩስ ከተማ ስለደረሰበት በደል ማወቅ ትችላላችሁ፥ ይህ ትውስታ ሐዘንን የሚፈጥር ነው። አግባብ ያልሆነ እስራትና ድብደባ ደረሰበት፥ ከግንድ ጋር አጣብቀው አስረውት ነበር፥ በሰዎችም ፊት ተዋርዶ ነበር፤ ነገር ግን እነዚህን ሲያስታውስ እንኳን ለጳውሎስ ደስታ ይሰጠዋል፥ ምክንያቱም በዚህ መከራ ውስጥ በማለፍ ነበር የወህኒ ጠባቂው ክርስቶስን ለማግኘት የቻለው! ጳውሎስ ሊዲያንና ቤተሰቧን ያስታውሳል፥ በአጋንንት ተይዛ የነበረችውን ድሀ ልጅ፥ እንዲሁም በፊልጵስዩስ ያሉ ውድ ክርስቲያኖችን እና ሌሎችም የሚያስታውሳቸው ነገሮች የደስታው ምንጭ ነበሩ። (እንዲህ ብለን እራሳችን መጠየቅ የሚገባን ነው «ለመሆኑ መጋቢዩ ስለእኔ በሚያስብበት ጊዜ እውነተኛ ደስታን የማስገኝለት ዓይነት ክርስቲያን ነኝን?»)።  ቁጥር 5 እነርሱ (የፊልጵስዩስ ሰዎች) ከጳውሎስ ጋር ስለነበራቸው ገንዘብ-ነክ ኅብረት ሊያወራ ይችላል፥ ይህን አርእስት በድጋሚ በ4:14-19 አንስቶታል። የፊልጵስዩስ ቤተ ክርስቲያን የጳውሎስን አገልግሎት ለማገዝ ከጳውሎስ ጋር ኅብረት ያደረገች ብቸኛ ቤተ ክርስቲያን ነበረች። በቁጥር 6 ላይ «መልካም ሥራ» ብለን የምንመለከተው ያላቸውን ነገር እንደሚከፋፈሉ ነው፤ ይህም የተጀመረው በጌታ እንደመሆኑ ጳውሉስም ጌታ በዚሁ እንደሚቀጥልና ከፍጻሜ እንደሚያደርሰው እርግጠኛ ነበር።  ነገር ግን እነዚህን ጥቅሶች ለድነታችንና (ለደኅንነታችንና) ለክርስቲያናዊ ኑሮአችን ዋስትና እንደሚያስገኙልን አድርገን መውሰዱ ወደ ስህተት ሊያመራን አይችልም። እኛ የዳንነው በመልካም ሥራችን አይደለም (ኤፌ. 2፡8-9)። ድነት (ደኅንነት) ማለት በልጁ ስናምን እግዚአብሔር በእኛ የሚሠራው መልካም ሥራ ነው። በፊል. 2፡12-13 እንደሚናገረን እግዚኣብሔር በእኛ የጀመረውን ሥራ በመንፈሱ በኩል ይቀጥላል በሌላ አነጋገር፥ ድነት በአጠቃላይ ሦስት አቅጣጫ ያለው ነው።  – እግዚአብሔር ለእኛ የሠራው – መዋጀት  – እግዚአብሔር በእኛ ውስጥ የሚሠራው – መቀደስ  – እግዚአብሔር በእኛ አማካኝነት የሚሠራው – አገልግሎት  ይህ ሥራ ክርስቶስን እስከምናየው ድረስ የሚቀጥል ሲሆን ከዚያ በኋላ ግን ሥራው ይፈጸማል «ቢገለጥ እርሱ እንዳለ እናየዋለንና እርሱን እንድንመስል እናውቃለን» (1ኛ ዮሐ. 3፡2)።  እግዚአብሔር በፊልጵስዩስ ባሉ አማኝ ጓደኞቹ ሕይወት ውስጥ እስካሁን መሥራቱን ማወቅ ለጳውሎስ የደስታው ምንጭ ነበር። በእርግጥም እውነተኛ መሠረት ያለው ደስተኛ የክርስቲያን ኅብረት አለ ለማለት የምንችለው እግዚአብሔር በየቀኑ ኑሮአችን ውስጥ ሲሠራ ነው።  ምንጭ፣ ጽሑፍ በ ዋረን ደብልዩ ዌርዝቢ፣ ትርጉም በመስፍን ታዬ፣ እርማት በ ዓብይ ደምሴ

እናንተን ባስታወስሁ ቍጥር አምላኬን አመሰግናለሁ (ፊል 1፡3-6)  Read More »

ጳውሎስ አንድነትንና ለክርስቶስ መኖርን ማበረታታቱ እና አማኞች ስላበረከቱት ስጦታ ምስጋናውን ማቅረቡ (ፊልጵ. 4፡1-23)

፩. ጳውሎስ አንድነትንና ለክርስቶስ መኖርን ያበረታታል (ፊልጵ. 4፡1-9) አንድን ሰው በምትወድበት ጊዜ ከሁሉም የሚሻለውን እንዲያገኝ ትፈልጋለህ። ከሁሉም የሚሻለው ሁልጊዜም እነርሱ ከሁሉም ይሻላል የሚሉት ሳይሆን በዘላለማዊ መንግሥት ብርሃን የላቀው ነው። ጳውሎስ የፊልጵስዩስ አማኞችን ከልቡ ስለሚወድ የተባረከ ሕይወት ያገኙ ዘንድ ሊያከናውኗቸው የሚገቧቸውን ነገሮች ያስታውሳቸዋል። ሀ. አንድ መሆን ይኖርባቸዋል። ቤተ ክርስቲያኒቱን በደንብ ስለሚያውቅ፥ ጳውሎስ የሚጣሉትን ሁለት ሰዎች በማገዝ እንዲያስታርቋቸውና በሰላም እንዲኖሩ እንዲያግዟቸው ይጠይቃል። በቤተ ክርስቲያን ውስጥ አንድነትን መፍጠሩ የሁሉም ሰው ሥራ ስለሆነ፥ ከሐሜትና ቲፎዞነት ይልቅ እነዚህን ሴቶች ለማስማማት እንዲጥሩ ተጠይቀዋል። ለ. የፊልጵስዩስ አማኞች ሁኔታቸውን አሸንፈው እንዲኖሩ ተበረታተዋል። ስደት በጳውሎስ ላይ እንደ ደረሰ ሁሉ በእነርሱም ላይ ይደርሳል። ሌሎች አሳዛኝ ነገሮችም ሊከሰቱ ይችላሉ። በዚህ ጊዜ ከማጉረምረምና እግዚአብሔርን ከመጠራጠር ወይም መራር ከመሆን ይልቅ መደሰት ይኖርባቸዋል። የምንደሰተው አስቸጋሪውን ሁኔታ ስለምንወደው ሳይሆን እግዚአብሔር ከእኛ ጋር እንዲሆንና ፍጻሜው ማለትም ዘላለማዊው የመንግሥተ ሰማይ ሕይወት መልካም እንደሆነ ስለምናውቅ ነው። እግዚአብሔር ሁኔታዎችን ስለሚቆጣጠርና ክርስቶስ ዳግም ስለሚመጣ፥ ሳንጨነቅ በልበ ሙሉነት እየተመላለስን በእግዚአብሔር ላይ ያለንን እምነት ማጽናት ይኖርብናል። በምንጸልይበት ጊዜ፥ እግዚአብሔር መልስ ከመስጠቱም በላይ ጥርጣሬያችንንና ጭንቀታችንን በማስወገድ በህልውናው እንድንተማመን ያደርገናል። ጳውሎስ በወታደሮች ተጠብቆ የሚኖር እሥረኛ ቢሆንም፥ በልቡ ውስጥ ትልቅ ነጻነት ነበር። በሚያስጨንቁን አስቸጋሪ ጊዜያት ወደ እግዚአብሔር ብንመለስ ደስታችንንና በእርሱ ላይ ያለንን መተማመን ይዘን እንጸና ዘንድ ልባችንንና አእምሯችንን የሚጠብቅ ወታደር ይልክልናል። ካለንበት ሁኔታ ባሻገር ዓለም የማይረዳው ሰላም ልባችንን ይሞላዋል። ሐ. የፊልጵስዩስ ክርስቲያኖች አሳባቸውን እንዲቆጣጠሩ ተነግሯቸዋል። የምናስበው ተግባራችንን ከመወሰኑም በላይ፥ ስሜታችንንም ይመራዋል። ባለማቋረጥ ስለሚያሸንፉን አሳቦች የምናስብ ከሆነ፥ ብዙም ሳይቆይ በጭንቀት እንረታለን። ወይም ደግሞ ከእግዚአብሔር ስለሚያርቁን ነገሮች የምናስብ ከሆነ፥ አእምሮን የሚያልፍ ሰላም ሊኖረን አይችልም። እነዚህ እንደ ምኞት፥ ክፋት፥ ወይም ገንዘብ ያሉ አሳቦችም ወደ ኃጢአት ይመሩናል። ነገር ግን «እውነት፥ ጭምት፥ ጽድቅ፥ ንጹሕ፥ ፍቅር፥ መልካም፥ በጎነትንና ምስጋናን» የምናስብ ከሆነ፥ እግዚአብሔርን የሚያስከብር ተግባር በመፈጸም፥ በእምነታችን ልናድግና ልባዊ ደስታን ልናገኝ እንችላለን። የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ያስጨነቁህን ነገሮች ዘርዝር። የተጨነቅኸው ለምን ነበር? ለ) የምናስባቸው ነገሮች ከእግዚአብሔር ጋር ያለንን ግንኙነትና ለሁኔታዎች ያለንን ስሜት የሚወስኑት እንዴት ነው? ሐ) ጸሎት ሁልጊዜም የምንፈልገውን ምላሽ ባያመጣም እንኳን ተገቢውን ሰላማዊ አመለካከት እንድንይዝ እንዴት እንደሚያግዘን ግለጽ። ፪. ጳውሎስ የፊልጵስዩስን አማኞች ለስጦታቸው ያመሰግናቸዋል (ፊልጵ. 4፡10-20) የሙሉ ጊዜ ክርስቲያን አገልጋዮች ለመማር የሚቸገሩባቸው ነገሮች አንዱ ለገንዘብ መንፈሳዊ አመለካከትን ማዳበር ነው። አብዛኛው ክርስቲያን አገልጋዮች ብዙ ደመወዝ ስለማያገኙ ፍላጎቶቻቸውን ለማሟላት ይቸገራሉ። ከዚህም የተነሣ አንዳንዶች ገንዘብን የሚቀላውጡ «ለማኞች» ወይም ስጦታ ለመቀበል ሲሉ በየሰዉ ቤት የሚዞሩ ሆነዋል። ሌሎች ደግሞ ኩሩዎች ስለሆኑ እግዚአብሔር የሚረዳቸውን ሰው ሲያመጣላቸው ስጦታውን ለመቀበል አይፈልጉም። የጳውሎስና የፊልጵስዩስ ቤተ ክርስቲያን ግንኙነት አገልጋዮች ለገንዘብ እንዴት ሚዛናዊ አመለካከት ሊኖራቸው እንደሚገባ ያሳያል። በሌላ በኩል ለአገልጋይ ከማሰቧ የተነሣ ሳትጠየቅ የገንዘብ ድጋፍ የምታደርግ ቤተ ክርስቲያን ማግኘቱ አስቸጋሪ ነው። የፊልጵስዩስ ቤተ ክርስቲያን ጊዜያቸውን ለአገልግሎት ለሚሰጡ ወገኖች የፍቅር እንክብካቤ በማድረጓ በአርአያነት የምትጠቀስ ነች። ጳውሎስ ሠርቶ ለመተዳደር በማይችልበት ሁኔታ ማንንም በማያውቅበት የባዕድ አገር መታሠሩን ሲሰሙ፥ ወዲያውኑ ገንዘብ ላኩለት። ነገር ግን እንዲህ ዓይነቱ ልገሳ ለእነርሱ አዲስ አልነበረም። ገና ወንጌሉን በተቀበሉ ጊዜ ጳውሎስና ሲላስ በፍጥነት ወደ ተሰሎንቄ ሄደው ወንጌልን መስበክ ነበረባቸው። በዚህም ጊዜ ለጳውሎስ የገንዘብ ዕርዳታ አድርገውለታል። ምንኛ ለጋስ ቤተ ክርስቲያን ነበረች! የሙሉ ጊዜ አገልጋዮቻቸውን እንዲህ የሚንከባከቡ የፊልጵስዩስ ዓይነት ቤተ ክርስቲያኖች ቢበዙልን ምንኛ መልካም ነው። ጳውሎስ ግን ሳይለምን ወይም ስጦታን ሳይጠይቅ አመለካከቱን በጥንቃቄ ጠብቋል። እግዚአብሔር ይረዱት ዘንድ ልባቸውን እንዲያነሣሣ ነበር የጠበቀው። በመሆኑም፥ ጳውሎስ ስለ አገልግሎቱና ስለ መስጠት የተማራቸውን አራት ነገሮች ያጋራናል። እግዚአብሔር ልጆቹን የመንከባከብን ኃላፊነት ይወሰዳል። ስለሆነም፥ ልጆቹ ዓይኖቻቸውን በእግዚአብሔር ላይ በመጣል ከሌሎች መለመንን ማቆም አለባቸው። እግዚአብሔር ብዙ ገንዘብ በሚሰጠን ጊዜ በምስጋና ልንቀበለው ይገባል። ትንሽም ቢሰጠን በዚያው መርካት ይኖርብናል። በብዙም ሆነ በጥቂቱ ፍላጎታችንን በሚሞላው እምላክ ልንረካ ይገባል። እግዚአብሔር እንደ ድህነትና ረሃብ ያሉትን ሁኔታዎች ለማለፍ የሚያስችሉትን ልገሳዎች ያደርጋል። ተጨማሪ ገንዘብ ከመፈለግ ይልቅ እርሱ በሚሰጠን መርካት አለብን። ጳውሎስ መስጠት በሰዎች ልብ ውስጥ ክርስቲያናዊ ዕድገትን እንደሚያበረታታና ሽልማትን እንደሚያስገኝላቸው ተረድቶ ነበር። እግዚአብሔር ከሰጠን ነገር ላይ በልግስናና በደስታ መስጠት አንዱ እግዚአብሔርን የምናመልክበት መንገድ ነው። እግዚአብሔር ሰዎችን እንዲሰጡ አነሣሥቷቸው ኢየሱስን ሲታዘዙ ይሸልማቸዋል። ብዙውን ጊዜ፥ «ለእግዚአብሔር ምስጋናችንን እንጂ ምን እንሰጠዋለን?» ሲባል እንሰማለን። እግዚአብሔር ለሰጠን ሁሉ ወሮታ ልንከፍል እንደማንችል እውነት ነው። ነገር ግን ለእግዚአብሔር ብዙ ነገሮችን ልንሰጥ እንደምንችል መጽሐፍ ቅዱስ ይናገራል። ለእግዚአብሔር ራሳችንን እንደ ቅዱስ መሥዋዕት ልንሰጥ እንችላለን (ሮሜ 12፡1-2)። ገንዘብ፥ ቁሳቁሶችንና ጊዜያችንን ለእግዚአብሔር ልንሰጥ እንችላለን። ይህም ራሱ እግዚአብሔርን ደስ የሚያሰኝ መሥዋዕት ነው። አምልኮ መዝሙር መዘመር ብቻ አይደለም። የአምልኮ መሠረቱ ራሳችንን ለእግዚአብሔር መስጠት ነው። ራሳችንን ለእግዚአብሔር ከሰጠን በኋላ ልንዘምርና እግዚአብሔር የሰጠንን ቁሳዊ በረከት ሌሎችን በመርዳት መልሰን ልንሰጠው እንችላለን። ገንዘባችንንም (ከብቶች፥ እህልና የመሳሰሉትን) ሆነ ሕይወታችንን ለእግዚአብሔር በመስጠታችን ምክንያት አንደኸይም። እግዚአብሔር የሚያስፈልገንን ሁሉ እንደሚሰጠን ቃል ገብቶልናል። እግዚአብሔር ከበረከት ግምጃ ቤቱ (በክርስቶስ ያለ ባለጠግነት) ለእርሱ በልግስና የሚሰጡትን ይባርካል። ይህ በረከት ዛሬ ፍላጎታችንን ማሟላት ሊሆን ቢችልም፥ በተለይ በመንግሥተ ሰማይ በሚሰጠን ሽልማት የሚገለጥ ነው። የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) በሁኔታዎች ሁሉ መርካት አስቸጋሪ የሚሆነው ለምንድን ነው? ለ) መርካት ተስኖህ ከእግዚአብሔር ጋር የተጣላህበትን ሁኔታ አስታውስ። ሐ) በችግር ውስጥ በመስጠትና በወንጌል ማኅበርተኝነት ለእግዚአብሔር መስጠት ክብር የሚሆነው እንዴት ነው? ፫. ማጠቃለያ (ፊልጵ. 4፡21-23) ጳውሎስ አብረውት ከነበሩት ሰዎች ሰላምታ በመላክ ይህንን መልእክት ይደመድማል። እነዚህ ሰዎች እነማን መሆናቸውን አናውቅም። ምናልባትም ሉቃስና ጢሞቴዎስ አብረውት ይሆኑ ይሆናል። ነገር ግን ጳውሎስ የቄሣርን ቤተ ሰዎች ነጥሎ ጠቅሷል። ምናልባት ይህ የቄሣርን ቤተሰብ አያመለክትም ይሆናል። ነገር ግን ወንጌል ቄሣር እስከሚያድርበት ቤት ድረስ መዝለቁን ያስረዳል። ጳውሎስ የቄሣር ሠራተኞች ለሆኑት ወታደሮች ወንጌሉን ለማካፈል ችሎ ነበር። ኔሮ የወንጌሉ ጠላት ሊሆን ቢችልም፥ ኃይልን የተሞላው ወንጌል እስከ ፊቱ ዘልቆ የጠላትን ግዛት ወሯል፡፡ ይህ የሆነው ጳውሎስ በመታሠሩ ነው፡፡ እግዚአብሔር እኛ በማንረዳው መንገድ የሚሠራ ምንኛ ድንቅ አምላክ ነው። በተለይም ወደ ሕይወታችን የሚመጣውን ሁኔታ ሁሉ በመቀበል ለመርካትና ለመደሰት በምንችልበት ጊዜ እንዲህ ዓይነት ተግባራትን ያከናውናል። (ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

ጳውሎስ አንድነትንና ለክርስቶስ መኖርን ማበረታታቱ እና አማኞች ስላበረከቱት ስጦታ ምስጋናውን ማቅረቡ (ፊልጵ. 4፡1-23) Read More »

ጳውሎስ ከሐሰተኛ አስተማሪዎች እንዲጠበቁ ያስጠነቅቃቸዋል (ፊልጵ. 3፡1-21)

ዘሪሁን ከታወቀ የሥነ መለኮት ኮሌጅ በማስትሬት ዲግሪ ተመረቀ። መጽሐፍ ቅዱሳዊ እውነቶችን ለመረዳት ለብዙ ጊዜያት ሲያጠና ነበር የሰነበተው። ዲግሪውን ከተቀበለ በኋላ ወደ አገሩ ተመለሰ። ሰዎች ጴጥሮስን «ሊቅ» አድርገው ቆጠሩት። እርሱም የሚያነሡአቸውን ጥያቄዎች ሁሉ በልበ ሙሉነት መለሰ። በቤተ ክርስቲያንም ውስጥ የሥልጣን ስፍራ ተሰጠው። ሥራው ፋታ ስለነሣው የእግዚአብሔርን ቃል ለማጥናት ጊዜ አላገኘም። «ሁሉም የማውቀው ነው» ሲልም አሰበ። ብዙም ሳይቆይ መንፈሳዊ ሕይወቱ ባለበት በመርገጡ በወሲብ ኃጢአት ወድቆ ከቤተ ክርስቲያን መሪነቱ ለቀቀ። የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) በተለይ ልዩ የመጽሐፍ ቅዱስ ሥልጠና ከወሰድን በኋላ በቀላሉ በመንፈሳዊ ሕይወታችን ማደግን የምናቆመው ለምን ይመስልሃል? ለ) ፊልጵስዩስ 3፡12-15 አንብብ። ጳውሎስ ስለ ሕይወቱና መንፈሳዊ ዕድገቱን ስለቀጠለበት ሁኔታ ምን ይላል? ሐ) አንድ ሰው በእምነቱ ሳያቋርጥ ለማደግ ምን ሊያደርግ ይችላል? መ) መንፈሳዊ፥ ማኅበራዊ፥ የእውቀት፥ ወዘተ… ዕድገት ለማግኘት በግልህ ምን እያደረግህ ነው? ሠ) ፊልጵስዩስ 3-4 አንብብ። ጳውሎስ እግዚአብሔርን በሚያስደስት መንገድ ስለመኖር ያስተማራቸውን ጠቃሚ እውነቶች ዘርዝር። እንዳለመታደል ሆኖ ብዙ የቤተ ክርስቲያን መሪዎች መንፈሳዊ እድገታቸውን ያቋርጣሉ። መጽሐፍ ቅዱስን እያጠኑ በእግዚአብሔር ቃል እውቀት አያድጉም። እንደ መጾም፥ መጸለይ፥ መስጠት፥ ቃሉን ማካፈል፥ ባሉት መንፈሳዊ ነገሮች አያድጉም። ስላገኘናቸው ዲግሪዎች ብዙ ማውራቱ ቀላል ነው። ነገር ግን የክርስትና ሕይወት በሁሉም የሕይወት ክፍሎች የማያቋርጥ ዕድገት የሚከሠትበት ሊሆን ይገባል። አዳዲስ ነገሮችን እየሞከርን ሥራችንን በበለጠ ልናውቅ ይገባል። በመንፈሳዊ ልምምድ የጸሎትና የጾም ሕይወታችንም ማደግ አለብን። ወደ መንግሥተ ሰማይ እስክንደርስ ድረስ ዕድገታችን መቋረጥ የለበትም። ጳውሎስ ይህንን ስለተገነዘበ፥ እግዚአብሔር በከፍተኛ ደረጃ እየተጠቀመበት ቢሆንም ወደ ኋላ እየተመለከተ ገድሉን ለመተረክ አልፈለገም። ይልቁንም ለማደግ መጣሩን ቀጠለ። ጳውሎስ በሕይወት እስካለ ድረስ ሁልጊዜም ለመሻሻልና ለማደግ ስፍራ እንዳለው ያውቅ ነበር። ስለሆነም፥ ወደፊት መጓዙን ቀጠለ። ጳውሎስ እንዳለው፥ በእምነታቸው ለመብሰል የሚፈልጉ ሰዎች ዕድገታቸው እንዳይቋረጥም መሻት አለባቸው። ጳውሎስ በፊልጵስዩስ ክርስቲያኖች ላይ የብሉይ ኪዳን ሕግጋትን የሚጭኑትን አይሁዳውያን ክርስቲያኖች ያስጠነቅቃቸዋል። ጳውሎስ እነዚህን አይሁዶች አስመልክቶ ሲናገር የፊልጵስዩስን አማኞች፥ «ከውሾች ተጠበቁ ከሐሰተኛም መገረዝ ተጠበቁ» ይላቸዋል። አይሁዶች በራሳቸውና የእግዚአብሔር ምርጥ ሕዝብ በመሆናቸው ይመኩ ነበር። አሕዛብን «ውሾች» እያሉ ይጠሩ ነበር። ጳውሎስ ግን ራሳቸውን ውሾች ይላቸዋል። በእግዚአብሔር ዓይን እውነተኞቹ የእግዚአብሔር ምርጥ ሕዝብ በክርስቶስ የሚያምኑት ሲሆኑ፥ ውሾቹ ደግሞ እነርሱ ነበሩ። በግርዘታቸው የተመኩት አይሁዶች ያልተገረዙ ሲሆኑ፥ ክርስቲያኖች ግን የተገረዙ ሆኑ። እግዚአብሔር የሚመለከተው የብልትን መቆረጥ ሳይሆን፥ በክርስቶስ የሚያምነውን ውስጣዊ ልብ ነውና። ከዚያም ጳውሎስ እንደ አይሁዳውያን ያሉ ሰዎች ስለሚመኩባቸው ውጫዊ ነገሮች የተረዳውን ያካፍላል። አይሁዶች የእግዚአብሔር ምርጥ ሕዝብ፥ የአብርሃም ልጆች፥ የብሉይ ኪዳንና ፈሪሳውያን የሚከተሏቸውን ልማዶች በመከተላቸው ይመኩ ነበር። ጳውሎስ ከክርስቶስ ጋር ከመገናኘቱ በፊት እነዚህ ነገሮች ሁሉ እንደነበሩት ይናገራል። እርሱ ከቢንያም ነገድ የተወለደ አይሁዳዊ ነበር። የቢንያም ነገድ በጣም ከተከበሩት ነገዶች አንዱ ነበር። በዚህ ጊዜ ብዙ አይሁዶች ከየትኛው ነገድ እንደተወለዱ ባያውቁም፥ ጳውሎስ ግን ያውቅ ነበር።) እርሱ ከዕብራዊም ዕብራዊ ነበር። ይህም ጳውሎስ የግሪክን ባሕልና ቋንቋ ለመከተል ያልፈለገ አይሁዳዊ መሆኑን ያሳያል። ጳውሎስ ከብሉይ ኪዳን ሕግጋት በተጨማሪ የሃይማኖት መሪዎች ያወጡትን ሕግጋት ጠንቅቆ የጠበቀ ፈሪሳዊ ነበር። በአይሁዶችም እንከን እንደሌለው ሰው ይቆጠር ነበር። ጳውሎስ ቀጥተኛ አይሁዳዊ በመሆኑ ቤተ ክርስቲያንን ያሳድድ ነበር። ጳውሎስ ከክርስቶስ ጋር ከመገናኘቱ በፊት ተወዳዳሪ የሌለው ቆፍጣና አይሁዳዊ ነበር። (ይህ በእኛ ዘመን ከተከበረ ጎሳ እንደ መወለድ፥ የታዋቂ ወንጌላዊ ልጅ እንደ መሆን፥ የታላቅ ቤተ ክርስቲያን አባል እንደ መሆንና ከዝነኛ የምዕራባውያን ሴሚናሪ የሥነ መለኮት ዲግሪ እንደ ማግኘት ነበር።) ከእነዚህ ነገሮች የትኞቹም ለጳውሎስ ድነት (ደኅንነትን) አላስገኙለትም። በዘላለሙ መንግሥት፥ የተወለደበት ጎሳም ሆነ ሌሎች ውጫዊ ነገሮች ምንም ጥቅም አይኖራቸውም። ዋናው ነገር ከክርስቶስ ጋር ያለው ግንኙነት ነበር። ስለሆነም ጳውሎስ በክርስቶስ እውቀት በማደግ፥ በመዳኑ ደስ በመሰኘትና በክርስቶስ ከማመን ባገኘው ጽድቅ መርካትን መረጠ። ጳውሎስ ክርስቶስን ከሙታን ያስነሣውን ኃይል ለመለማመድ፥ ለወንጌል በመሠቃየት ክርስቶስን ለመምሰል፥ በእምነት ለመጽናትና እንደ ክርስቶስ ከሞት ለመነሣት ነበር የፈለገው። የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) መንፈሳዊ ጠቀሜታ የሌሏቸውና አንዳንድ ጊዜ ክርስቲያኖች የሚመኩባቸው ሥጋዊ ነገሮች ምን ምንድን ናቸው? ለ) ጳውሎስ ያተኮረባቸው ነገሮች ለዘላለማዊ ሕይወት እጅግ ጠቃሚዎች የሚሆኑት እንዴት ነው? ሐ) የተመካህባቸው አንዳንድ ውጫዊ ነገሮች ምን ምንድን ናቸው? መ) እነዚህ ነገሮች በሕይወትህ እውን ይሆኑ ዘንድ ምን ልታደርግ ትችላለህ? እንደ ጳውሎስ ያሉ ታላላቅ መሪዎች ፍጹማን ናቸው ማለት ሊዳዳን ይችላል። እኛ ምን ያህል ደካሞች እንደሆንን እናውቃለን። የኃጢአት ተፈጥሯችን እንደ ጎሳችን፥ ቤተሰባዊ ውርሳችን፥ ትምህርታችን፥ ሀብታችን፥ ወዘተ… ካሉት ውጫዊ ነገሮች ክብርን ሊያገኝ እንደሚሻ እንረዳለን። ሁኔታዎች በማይመቻቹበት ጊዜ እድገታችንን ለማቋረጥም እንፈቅዳለን። ስለሆነም ጳውሎስ እርሱም እንደ እነርሱው መሆኑን ለፊልጵስዩስ ክርስቲያኖች ገልጾላቸዋል። ፍጹም ባይሆንም እድገቱን ለመቀጠል ይጥር ነበር። የሕይወቱን ዓላማ አካፍሏቸዋል። ባለው መንፈሳዊ ይዞታ ሳይረካ ለማደግ የሚፈልግ ሰው ነበር። ጳውሎስ የግሪክን የአትሌቲክስ ውድድሮች ምሳሌነት በመጠቀም የሕይወቱን ውስጣዊ ፍላጎት ገልጾላቸዋል። ይህ ለጳውሎስ ቀላል ባይሆንም ሩጫውን ለማሸነፍ እንደሚፈልግ ተወዳዳሪ ወደ ፊት ሊገሰግስ ፈለገ። «ስለ እርሱ በክርስቶስ ኢየሱስ የተያዝሁትን ያን ደግሞ እይዛለሁ ብዬ እፈጥናለሁ።» ይህን ሲል ጳውሎስ ክርስቶስ የሚፈልግብኝን ሁሉ እሆናለሁ ማለቱ ነበር። ጳውሎስ ቀደም ሲል ብዙ አብያተ ክርስቲያናትን በተከለባቸው ድሎቹና ከመዳኑ በፊት ብዙ ክርስቲያኖችን በገደለባቸው ጸጸቶች ላይ ከማተኮር ይልቅ ወደፊት አሻግሮ በመመልከት ክርስቶስ እንዲሆን የሚፈልገውን ስለመሆን ያልማል። ይህም «መዘርጋት» እና «መፍጠን» ሲል የገለጻቸውን ታላላቅ ጥረቶች ጠይቆታል። ጳውሎስ የፈለገው የሕይወትን ሩጫ በሚገባ ለመሮጥና በመንግሥተ ሰማይ ክርስቶስ የሚሰጠውን ሽልማት ለመቀበል ነበር። ጳውሎስ በሕይወቱ መጨረሻ ላይ፥ «መልካሙን ገድል ተጋድዬአለሁ፤ ሩጫውን ጨርሼአለሁ፤ ሃይማኖትን ጠብቄአለሁ። ወደፊት የጽድቅ አክሊል ተዘጋጅቶልኛል። ይህንም ጻድቅ ፈራጅ የሆነው ጌታ ያን ቀን ለእኔ ያስረክባል። ደግሞም መገለጡን ለሚወዱ ሁሉ እንጂ ለእኔ ብቻ አይደለም» ሊል ችሏል (2ኛ ጢሞ. 4፡7-8)። የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) እግዚአብሔር የሕይወትህ ዓላማ ምን እንደሆነ እንዲያሳይህ በጸሎት ጠይቅ። በልብህ ከምንም ነገር በላይ የምትፈልገው ምንድን ነው? ያንተ የሕይወት ዓላማ ከጳውሎስ ጋር ሲነጻጸር ምን ይመስላል? ለ) የሕይወትህ ዓላማ ምን እንዲሆን እንደምትፈልግ በጥቂት ዓረፍተ ነገሮች ግለጽ። (ለመሆንና ለማድረግ የምትፈልጋቸው ነገሮች ምን ምንድን ናቸው?) ሐ) ከዚያ ግብ ላይ ለመድረስ ልትወስዳቸው የሚገቡ ዝርዝር እርምጃዎች ምን ምንድን ናቸው? መ) ግብህ ተግባራዊ ይሆን ዘንድ በሕይወትህ ውስጥ ልታካሂዳቸው የሚገቡህ ለውጦች ምን ምንድን ናቸው? ሰዎች ምሳሌዎችን (ሞዴሎችን) ይፈልጋሉ። ወጣቶች የስፖርት፥ የፊልም ወይም የሙዚቃ ከዋክብትን ያዩና እንደ እነርሱው ለመሆን ይፈልጋሉ። የእነዚህ ወጣቶች እሴቶች በሚያደንቋቸው ሰዎች ተጽዕኖ ሥር ይወድቃሉ። እግዚአብሔር የሚፈልገን ዓይነት ሰዎች ሆነን ለማደግ የሕይወትን ሩጫ ለማካሄድ መልካም ምሳሌዎች የሚሆኑንን ሰዎች መከተል ይኖርብናል። እዚህ ላይ መልካም ምሳሌዎችን መምረጡ አስፈላጊ ነው። የፊልጵስዩስ አማኞች ክርስቲያኖች ነን የሚሉትን አይሁዳውያን ለምሳሌነት ቢመርጧቸው ኖሮ ጠቀሜታ በሌላቸው ውጫዊ ጉዳዮች ላይ ያተኩሩ ነበር። ነገር ግን ትክክለኛ ምሳሌዎችን ከመረጡ ክርስቶስን እንዴት ሊከተሉ እንደሚችሉ በተግባራዊ መንገድ ያያሉ። ስለሆነም ጳውሎስ ራሱንና ውድድሩን በጥሩ ሁኔታ የሚሮጡትን ሌሎች የቤተ ክርስቲያን መሪዎች እንዲከተሉ አበረታቷቸዋል። ጳውሎስ ብዙ ክርስቲያኖች በጥሩ ሁኔታ ጀምረው በሚያሳዝን መልኩ የመስቀሉ ጠላቶች እንደሚሆኑ ያውቅ ነበር። እንደ መንፈሳዊ ባሕርይ፥ ክርስቶስን ማገልገል፥ በሕይወታቸው፥ በባሕሪያቸውና በተግባራቸው ለሚያስከብሩት ሰዎች ክርስቶስ በሚሰጣቸው ሽልማቶች ላይ እንደ ማተኮር፥ ዓለም እንደ መልካምና ስኬት አድርጋ የምትመለከታቸውን ነገሮች ይከተላሉ። ብዙ ሰዎች እንደ ዓለማዊ ዝና፥ ጥሩ ምግብ፥ ሀብት፥ ጥሩ ቤት ባሉና ለኃጢአት ተፈጥሯቸው በሚመቹ ነገሮች ይሳባሉ። ነገር ግን ፍጻሜያቸው ጥፋት ነው። ጳውሎስ የፊልጵስዩስ አማኞች የእግዚአብሔር ልጆች እንደ መሆናቸው፥ ቀዳሚው ዜግነታቸውና ዘላለማዊው ቤታቸው መንግሥተ ሰማይ እንደሆነ ያስታውሳቸዋል። የሮም ዜግነት ሊኖራቸውና በሮም ከተማ ውስጥ ሊኖሩ ቢችሉም፥ ይህ ምድራዊ ሕይወት ጊዜያዊ በመሆኑ የሰማያዊ መንግሥት ዜግነትን ያህል ጠቃሚ አልነበረም። በዚህ ምድራዊ ሕይወት የኢትዮጵያ ዜጎች ሆነን ስንኖር፥ ሰውነታችን ቀስ በቀስ ይዳዳከምና ይሞታል።

ጳውሎስ ከሐሰተኛ አስተማሪዎች እንዲጠበቁ ያስጠነቅቃቸዋል (ፊልጵ. 3፡1-21) Read More »

ጳውሎስ ስለ አፍሮዲጡ መመለስና የጢሞቴዎስ መምጣት ይናገራል (ፊልጵ. 2፡19-30)

ጳውሎስ በምርመራው መሃል የሚገኝ ይመስላል። በቅርቡ በነፃ እንደሚያሰናብቱትና የፊልጵስዩስን ሰዎች እንደሚጎበኝ ተስፋ ያደርጋል። ነገር ግን ከቤተ ክርስቲያኒቱ ጋር ግንኙነት ለማድረግ ስለፈለገ፥ የቅርብ ጓደኛውና ረዳቱ የነበረውን ጢሞቴዎስን እንደሚልክላቸው ይናገራል። ጢሞቴዎስ ለቤተ ክርስቲያን ምሥረታና ለወንጌል መስፋፋት የበኩሉን አስተዋጽኦ በማድረግ ከ12 ዓመታት በላይ ከጳውሎስ ጋር ሠርቷል። ጳውሎስ የፊልጵስዩስን ቤተ ክርስቲያን ሁኔታ ለማወቅ ስለፈለገ ጢሞቴዎስ አይቷቸው እንዲመጣና እንዲነግረው ፈለገ። ጳውሎስ የፊልጵስዩስን መልእክት ከጻፈባቸው ምክንያቶች አንዱ አፍሮዲጡ ነበር። አፍሮዲጡ የፊልጵስዩስ አማኝ ሲሆን፥ ቤተ ክርስቲያኒቱ የጳውሎስን መታሠር በሰማች ጊዜ ይህንኑ ወንድም ነበረ መጀመሪያ ወደ ሮም የላከችው። እፍሮዲጡ ሮም ተቀምጦ ጳውሎስን በሚገባ አገለገለው። ብዙም ሳይቆይ ግን ለሞት እስኪያሰጋው ድረስ በጠና ታመመ። ጳውሎስም የፊልጵስዩስን ክርስቲያኖች ጭንቀት ለማርገብ ሲል ወደዚያው መልሶ ሰደደው። አፍሮዲጡ ባይታሠርም፥ ከጳውሎስ ጋር ሆኖ እሥራቱን ለመካፈል ፈቅዶ ነበር። ጳውሎስን ለማበረታታት ሲል የደረሰበትንም በሽታ ታግሦአል። «ስለሆነም፥ ጳውሎስ ክርስቲያኖች አፍሮዲጡንና ለወንጌሉ ሲል ራሳቸውን ለአደጋ የሚያጋልጡትን ሁሉ እንዲያከብሩ ጠይቋቸው ነበር። ይህ አጋጣሚ ስለ ፈውስ አንድ ጠቃሚ ትምህርት ያስተላልፋል። እግዚአብሔር ብዙ ሰዎችን ለመፈወስ በጳውሎስ ተጠቅሟል (የሐዋ. 20፡712፥ 28፡8-10)። ይህ ማለት ግን ሁልጊዜም የመፈወስ ኃይል አለው ማለት አይደለም። ራሱን እንኳን ለማዳን አልቻለም ነበር (2ኛ ቆሮ. 12፡7-10፤ ገላ. 4፡13-14)። በዚህ ስፍራ አፍሮዲጡ ሊሞት ሲቃረብም፥ ጳውሎስ ሊያድነው አልቻለም። አፍሮዲጡ ለረዥም ጊዜያት ታሞ የሰነበተ ይመስላል። ምክንያቱም ከሮም ወደ ፊልጵስዩስ ተጉዞ ስለ ሕመሙ ለመናገር ቢያንስ አንድ ወር ይፈጃል። ይህ ፈውስ በእግዚአብሔር እንጂ በሰው ፈቃድ ብቻ እንደማይመጣ ያስረዳል። እግዚአብሔር አንድ ሰው ሌላውን ለመፈወስ መሣሪያው እንደሚሆን በሚናገርበት ጊዜ ፈውሱ በጸሎት አማካኝነት ተግባራዊ ይሆናል። ነገር ግን እግዚአብሔርን ፈቃዱን ባልገለጠ ጊዜ እግዚአብሔር እንዲፈውሰው ብንጠይቅም ውጤቱን የሚያውቀው እርሱ ብቻ ነው። ከዚያ በኋላ እግዚአብሔር የሚያደርገውን እንጠብቃለን። እንዳንድ ጊዜ እግዚአብሔር ፈውስን ያወርዳል። ሌላ ጊዜ ደግሞ ታማሚውን ወደ ራሱ ይወስዳል። እግዚአብሔር አንድን ነገር እንዲያደርግ ልናዝዘው አንችልም። እግዚአብሔር ሰዎችን ለመፈወስ የተጠቀመባቸው ወገኖች ሁልጊዜም የታመሙትን እንደሚፈውሱ ወይም የጸለዩለትን ሰው ሁሉ እንደሚፈወስ ማሰብ የለባቸውም። እግዚአብሔር በግልጽ እስካልነገረን ድረስ ለምንጸልይለት ሰው «ጌታ ይፈውስሃል» ማለት የለብንም። ይህ ካልሆነ፥ እግዚአብሔር ሳይነግረን የውሸት መልእክት በማስተላለፍ የዚያን ግለሰብ ተስፋ በከንቱ እናለመልማለን። የውይይት ጥያቄ፡– ሀ) እግዚአብሔር ጳውሎስ አፍሮዲጡን እንዲፈውስ ያልፈቀደለት ለምን ይመስልሃል? ለ) ከዚህ ስለ ፈውስ አገልግሎትና አገልጋዮች ምን እንማራለን? (ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

ጳውሎስ ስለ አፍሮዲጡ መመለስና የጢሞቴዎስ መምጣት ይናገራል (ፊልጵ. 2፡19-30) Read More »