ሉቃስ 22፡39-23፡56

  1. እግዚአብሔር ከመስቀሉ እንዲያድነው ኢየሱስ ጸለየ (ሉቃስ 22፡39-46)

ሉቃስ ብዙውን ጊዜ የኢየሱስን ፍጹም ሰው መሆን አጉልቶ ያሳያል። ኢየሱስ መስቀሉን የተሸከመው ኃይሉን ሁሉ እንደተላበሰ አምላክ ሳይሆን፤ በሁላችንም ላይ በሚያንዣብብ የፍርሃት ስሜት ነበር፡፡ ደቀ መዛሙርት በዘመናት ሁሉ በኢየሱስ በማመናቸው ምክንያት ለሞት በሚዳረጉበት ጊዜ ሁሉ ሲያስጨንቃቸው ይኖራል። ስለሆነም ፍርሃት ተፈጥሯዊ የሰው ልጆች ስሜት ነው። ዋናው ነገር ፍርሃትን የምንቋቋምበት መንገድ ነው ኢየሱስ ከመስቀል ሞት ለመዳን እንደ ጸለየው እኛም ይህንኑ ልናደርግ እንችላለን። ነገር ግን ኢየሱስ ራሱን ለእግዚአብሔር ፈቃድ አሳልፎ እንደ ሰጠ ሁሉ፥ እኛም ይህንኑ ልናደርግ ይገባናል። አንዳንድ ጊዜ በዚህ መንገድ ልንተርፍ እንችላለን። ሌላ ጊዜ ደግሞ ልንሞት እንችላለን። እግዚአብሔር ለልጁ የ«አይሆንም» መልስ እንደ ሰጠው ሁሉ፣ ለእኛም ይህንኑ ሊያደርግ ይችላል። ነገር ግን እግዚአብሔር መልአኩን በመላክ፥ (ሉቃስ እንደ ጠቀሰው) ኢየሱስን እንዳበረታታው፣ እኛንም በጨለማው ሰዓት እንደሚያበረታታን እርግጠኞች ልንሆን እንችላለን።

ሉቃስ የኢየሱስን ሥቃይ ለማሳየት ሲል፥ ላቡ እንደ ደም መውረዱን ገልጿል። ይህም ጣታችንን በምንቆረጥበት ጊዜ ደም በፍጥነት እንደሚወርድ ሁሉ፣ ኢየሱስም ከፍተኛ ሥቃይ ላይ ላለነበረ ብዙ ላብ እንደ ወረደው የሚያመለክት ሊሆን ይችላል። ነገር ግን አንዳንድ ምሑራን ሉቃስ ሊያስተላለፍ የፈለገው መልእክት ከዚህ በላይ እንደሆነ ያስባሉ። በሰዎች ላይ ከፍተኛ ሥቃይ በሚደርስበት ጊዜ አነስተኛ የደም ሥሮች የሚበጠሱበት ሁኔታ ያጋጥማል። ስለሆነም ኢየሱስ በሚጸልይበት ጊዜ ደሙ ከላቡ ጋር አብሮ ይወርድ እንደነበር ይገልጻሉ።

ሉቃስ በተለይ በስደት ጊዜ ወደ ኋላ መመለስ እንደሌለብን ያስጠነቅቀናል። ጸሎት እጅግ የሚያስፈልገን በዚህ ጊዜ ነው። በጸሎት ጊዜ የተጋረጠብንን ፈተና የምናሸንፍበትን ኃይል እናገኛለን።

  1. የኢየሱስ መታሰር፣ መመርመር፣ መሰቀልና መሞት ሉቃስ 22፡47-23፡56)

ሉቃስ ስለ ኢየሱስ መሰቀል ያቀረበው ታሪክ ከሌሎቹ ተመሳሳይ ወንጌላት ጋር ተመሳሳይ ነው። ቀደም ሲል በማቴዎስ ወንጌል ውስጥ የተሟላ ማብራሪያ ስላቀረብን፣ በዚህ ክፍል ክስተቶቹን ጠቅለል አድርጎ ከማቅረብ ያለፈ ነገር አናደርግም። ሉቃስ ስለ ኢየሱስ ሞት እንዳንድ ጠቃሚ እውነቶችን ይገልጻል።

ሀ. ሉቃስ በኢየሱስ ሞት በተፈጸመው የእግዚአብሔር ፈቃድ ላይ ያተኩራል። ሉቃስ ሰባት ጊዜ ኢየሱስ “ሊሞት ይገባ ነበርና” የሚል ዐረፍተ ነገር ጠቅሷል (ሉቃስ 9፡22፤ 13፡33፤ 17፡25፤ 22፡37)።

ለ. ሉቃስ በተጨማሪም ኢየሱስ መስቀል ከፊቱ ሆኖ እየታየው እያለ እንኳ ሁልጊዜ ለሌሎች የሚያስብ አዳኝ እንደሆነ አመልክቷል። ወደ መስቀል በሚወስደው መንገድ ላይ ሲያለቅሱ ለነበሩት ሴቶች አዝኖ ነበር። በመስቀሉ ላይ ለነበረው ሌባ ራርቶ ነበር። ለሰቀሉት ሰዎችም ስለራራ፣ እግዚአብሔር ይቅር እንዲላቸው ጸልዮአል። የሃይማኖት መሪዎች፣ «ሌሎችን አዳነ፡ እስኪ አሁን ራሱን ያድን» እያሉ ተሳለቁበት። ይህ ኢየሱስ ሁልጊዜ እንዴት ራሱን ለሌሎች አሳልፎ እንደሚሰጥ ያመለክታል። እነርሱ ያልተረዱት ነገር ቢኖር ኢየሱስ በሞት ራሱን አሳልፎ በመስጠት የሰዎች ዋንኛ አዳኝ ለመሆን እንደ በቃ ነው።

ሐ. ሉቃስ ኢየሱስ ምንም ኃጢአት እንዳልሠራ ገልጾአል። ሉቃስ ሦስት ጊዜ ኢየሱስ ንጹሕ መሆኑን መስክሯል፡፡ ሄሮድስ፣ በመስቀል ላይ ተሰቅለው ከነበሩት ወንበዴዎች አንዱ፤ እንዲሁም የሮሙ የመቶ አለቃ ኢየሱስ ኃጢአት የሌለበት ሰው መሆኑን መስክረዋል። እርሱ ሞት የሚገባው ወንጀለኛ አልነበረም፡፡

መ. ሉቃስ የሀብታሞችንና የሃይማኖት መሪዎችን አመለካከት ከተራ ሰዎች ጋር ያነጻጽራል። ሉቃስ ለኢየሱስ ሞት በዋነኛነት ተጠያቂ ያደረገው የአይሁድ አለቆችን፣ ሀብታሞችና ኀይል ያላቸውን ሰዎች ነው። ይህም በመጽሐፉ ውስጥ ሀብታሞች ምን ያህል የክፋት ምንጭ እንደሆኑ ከሚያሳይበት ሁኔታ ጋር ይመሳሰላል። ኢየሱስ እንዲሞት የገፋፉት የሃይማኖት መሪዎች ናቸው። በመስቀል ላይ በነበረ ጊዜ ኢየሱስን ይሳደቡ የነበሩትም እርሱው ናቸው። በአንጻሩም ኢየሱስ ወደ መስቀል ሞት በወሰድበት ጊዜ ሴቶች ያለቅሱለት ነበር። ሌሎችም ሰዎች የመስቀል ላይ ሥቃዩን ቆመው ከተመለከቱ በኋላ፥ በኀዘን ደረታቸውን እየመቱ ወደ ቤታቸው ተመለሱ።

ሠ. ሉቃስ እንደ ማቴዎስና ማርቆስ ደቀ መዛሙርቱን ብዙም አላብጠለጠላቸውም። ደቀ መዛሙርቱ በኅዘን ምክንያት መተኛታቸውን እንጂ ጴጥሮስ፣ ያዕቆብና ዮሐንስ ሦስት ጊዜ በእንቅልፍ መሸነፋቸውን አልገለጸም። ሉቃስ ደቀ መዛሙርቱ እንዴት ከኢየሱስ እንደ ራቁ አልገለጸም። ነገር ግን ከሴቶች ጋር ሆነው በርቀት ስቅለቱን ይመለከቱ እንደ ነበር ጽፎአል።

  1. የኢየሱስ አልፎ መሰጠትና መታሰር (ሉቃስ 22፡47-53)።

ኢየሱስ ይህንን የመታሰርና የመሰቀል ጊዜ ጨለማ የሚነግሥስበት ጊዜ ሲል ጠርቶታል። እግዚአብሔር ሰይጣን ኢየሱስን ለሞት አሳልፎ እንዲሰጠው ፈቀደለት፡፡ ሰይጣን ለጊዜው የሥልጣኑን በትር የጨበጠ ይመስላል። ሰዎች ሁሉ የከፋ ተግባር እንዲያደርጉ በማነሣሣት፣ ደቀ መዛሙርቱ እንዲሸሹ፣ የሃይማኖት መሪዎችና አይሁዶች ኢየሱስን አንቀበልም በማለት እንዲወስኑና ኢየሱስ አልፎ እንዲሰቀል እንዲጠይቁ፣ ጲላጦስ ድፍረቱን እንዲያጣ የበኩሉን ድርሻ ተወጥቷል። ነገር ግን ሰይጣን ክርስቶስን አሸንፍሁበት ባለው መስቀል አማካይነት፥ እግዚአብሔር ዓለምን አድኗል። ሰይጣን ከሁሉም የከፋ የጭካኔ ተግባር ሊፈጽምብን ቢችልም፣ ሊያደርግ የሚችለው ነገር ቢኖር የእግዚአብሔርን ሥራ ማፋጠን ነው! አምላካችን ምንኛ አስደናቂ ነው!

የውይይት ጥያቄ፡- ) ሰይጣን በአንተ ወይም በቤተ ክርስቲያን ላይ የጨለማን ጊዜ ሲያመጣ የተመለከትከው እንዴት ነው? ለ) እነዚህ የጨለማ ጊዜዎች የእግዚአብሔርን ዕቅዶች እንደ ማፍረስ የበለጠ የሚያጠናክሩ ሆነው የተገኙት እንዴት ነው? ሐ) ይህ ስለ እግዚአብሔር ሉዓላዊነት ምን ዐይነት ልበ ሙሉነትን ይሰጠናል?

  1. ጴጥሮስ ኢየሱስን ካደ (ሉቃስ 22፡54-65)።

ጴጥሮስ ለኢየሱስ ሰይፍ ይዞ ሊዋጋና ሊሞት መድፈሩ ይታወሳል። በኋላ ግን አንዲት ሴት ባደረገችው ጥቆማ እጅግ ፈራ። አንዳንድ ጊዜ በሌሎች ፊት ምስክርነታችንን ከመስጠት ይልቅ ለእምነታችን መሞቱ ቀላል ነው። ሉቃስ ሁለቱም ማለትም ጴጥሮስና ኢየሱስ በአንድ ግቢ ውስጥ እንደ ነበሩ ገልጾአል። ጴጥሮስ ለሦስተኛ ጊዜ ሲክደው ኢየሱስ ዘወር ብሎ ተመለከተው። ኢየሱስ ምን እያሰበ ይሆን? ኀዘን? ይቅርታ? ኩሩው ጴጥሮስ ደካማነቱን በመገንዘብ ልቡ ተሰበረ። እግዚአብሔር ጴጥሮስን ለቤተ ክርስቲያኑ መታነጽ መሠረት አድርጎ የሚጠቀመው በራሱ ላይ የነበረው ልበ ሙሉነት ከተወገደ በኋላ ነበር።

  1. ኢየሱስ በአይሁዶች ፊት ተመረመረ (ሉቃስ 22፡66-71)።

ከሌሎች ወንጌሎች በተቃራኒው፣ ሉቃስ በአይሁዶች ፊት ስለተደረገው ምርመራ ብዙም የገለጸው አሳብ የለም። ሉቃስ ታሪኩን ያጠቃለለው ኢየሱስ በክብር በእግዚአብሔር ቀኝ የሚቀመጥ መለኮታዊ «የሰው ልጅ» እንደሆነ በመግለጽ ነው። ይህ አሳብና ኢየሱስ በግልጽ የእግዚአብሔር ልጅ ነኝ ማለቱ አይሁዶች በኢየሱስ ላይ የስቅላት ጥያቄ እንዲያቀርቡ አነሣሥቷቸዋል። ፍትሐዊ ባልሆነ ምርመራ፣ ወንጀለኛ ተብሎ ተከሰሰ።

  1. ኢየሱስ በጲላጦስ ፊት (ሉቃስ 23፡1-25)።

ሉቃስ በጲላጦስ ፊት ስለተደረገው ምርመራ ትኩረት ሰጥቷል። ለአንድ ሰው፥ ኢየሱስ እንዳደረገው፥ እኔ የአይሁድ ንጉሥ ነኝ ብሎ ማለቱ፥ የሮም መንግሥትን እንደ መክዳት ይቆጠርበታል። ጲላጦስ ግን የሃይማኖት መሪዎቹን ቅንዓት ከተመለከተ በኋላ፥ የኢየሱስ መንግሥት መንፈሳዊ እንደሆነ ተገነዘበ። ስለዚህም ጲላጦስ ኢየሱስ ምንም ጥፋት እንደሌለበት ተናገረ። ቢሆንም ግን ጲላጦስ ፈርቶ ነበር። ኢየሱስን ወደ ሄሮድስ ለፍርድ በመላክ አስቸጋሪውን ሁኔታ ለማለፍ ሞከረ። ኢየሱስ ሄሮድስ አንቲጳስ ይገዛ በነበረው የገሊላ አውራጃ ውስጥ ይኖር ነበር። ሉቃስ ቀደም ሲል ሄሮድስ በተደጋጋሚ ከኢየሱስ ጋር ለመገናኘት ጥረት ሲያደርግ እንደ ነበር ገልጾአል። በዚህ ጊዜ ተከሶ እፊቱ ሊቀርብ ንጉሡ የተመኘውን አገኘ። ኢየሱስ ግን መልስ ሊሰጠው አልፈለገም። ሄሮድስ ያደረገው ነገር ቢኖር ኢየሱስን፥ ንጉሥ እያለ ጠርቶ በእርሱ ላይ መሳለቅ ነበር። ከዚያም ኢየሱስን ወደ ጲላጦስ መልሶ ሰደደው። እርሱም ኢየሱስን ፈራው። ጲላጦስና ሄሮድስ ሁለቱም ኢየሱስን ስለፈሩት በአንድ ወቅት ባላንጦች የነበሩት ገዥዎች ፍርሃቱ በመታቸው ሁኔታ ወዳጅነትን መሠረቱ። ኢየሱስ ዓለማዊ ንጉሥ ከሆነ ሥልጣኔን ይነጥቀኛል ብሎ ይፈራ የነበረው ሄሮድስ እንኳ የኢየሱስን ንጽሕ እንደሆነ ተገንዝቧል (ሉቃስ 23፡5)።

ኢየሱስ ተመልሶ ሲመጣ ጲላጦስ ኢየሱስን ነፃ ለማድረግ ሌላ አማራጭ ፈለገ። አይሁዶች በርባን የተባለውን ወንጀለኛ እንደሚጠሉት ያውቅ ነበር። ስለሆነም ከበርባን ይልቅ ኢየሱስ እንዲለቀቅ እንደሚፈልጉ አልተጠራጠረም። አይሁዶች ኢየሱስ እንዲሞትና በርባን እንዲለቀቅ በጠየቁ ጊዜ ሳይደነቅ አልቀረም። ከዚያም ጲላጦስ ሌላ ነገር አሰበ። ኢየሱስ ከፊታቸው ሲገረፍ ቢያዩ ልባቸው ይራራ ይሆናል የሚል ግምት አደረበት። እንዳሰበው ግን አልሆነም። ቢያንስ ሦስት ጊዜ ጲላጦስ ኢየሱስ በደል የሌለበት ንጹሕ ሰው መሆኑን ደጋግሞ ቢያውጅም፣ በመጨረሻ ፍርሃቱ ስላሸነፈው ለኢ-ፍትሐዊ ፍርድ አሳልፎ ሰጠው። ከዚያም ኢየሱስ ይሰቀል ዘንድ ተስማማ።

ብዙውን ጊዜ የመንግሥትና የቤተ ክርስቲያን መሪዎች ጲላጦስ በተያዘበት ወጥመድ ውስጥ ይያዛሉ። ሰዎችን በመፍራት ለፍትሕ አልባ አመራር ስፍራ ይለቅቃሉ። ይህም የእግዚአብሔር የጽድቅ መሣሪያ እንደ መሆን፥ የሰይጣን የኃጢአት መሣሪያ እንዲሆኑ ያደርጋቸዋል። ጳውሎስ እንደገለጸው ሰዎችን ፈርቶ ለፍትሕ አልባ አመራር ስፍራ መልቀቅ የሰዎች ባሪያ መሆን ነው (ገላ. 1፡10)።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) አንድ የመንግሥት ባለሥልጣን ሰዎችን በመፍራቱ እንዴት ለፍትሕ አልባ አመራር ፈቃዱን እንደ ሰጠ ከገጠመህ ሁኔታ በመነሣት አብራራ። ለ) አንድ የቤተ ክርስቲያን መሪ ሰዎችን በመፍራቱ ኃጢአት እንዲራባ የፈቀደው እንዴት ነው?

  1. የኢየሱስ መሰቀል፣ መሞትና መቀበር (ሉቃስ 23፡26-56)።

አይሁዶች ሁሉ በኢየሱስ መሰቀል ተስማምተው ነበር? አልነበረም። ሉቃስ ሴቶች ለኢየሱስ ራርተው እንዳለቀሱለት ገልጾአል። ኢየሱስ በዚህ ጊዜ ሮማውያን ከ40 ዓመት በኋላ ኢየሩሳሌምን በሚደመስሱበት ጊዜ ስለሚሆነው መከራ አስጠንቅቋቸዋል።

ሉቃስ ሌሎች የወንጌላት ጸሐፊዎች ያልተጠቀሙባቸውንና ኢየሱስ በመስቀል ላይ ሆኖ የተናገራቸውን አያሌ ቃላት በመጽሐፉ ውስጥ አስፍሯል። ኢየሱስ በመስቀል ላይ የቁጣ፣ የጥላቻ ወይም የዕርዳታ ጥሪ አላቀረበም። በከፍተኛ ሥቃይ ውስጥ ሆኖ እየማቀቀ ሳለ እግዚአብሔር ሕዝቡን ይቅር እንዲል ነበር የጠየቀው። ብዙም ሳይቆይ ሌላው ሰማዕት እስጢፋኖስም ተመሳሳይ የይቅርታ ጥያቄ አቅርቧል (የሐዋ. 7፡60)። በእግዚአብሔር ሕዝብ ላይ በደል እየፈጸሙ ሳለ እንኳ ለሰዎች የይቅርታ ጸሎት እንድናቀርብ ኢየሱስ ምሳሌ ትቶልናል።

ሉቃስ በመስቀል ላይ በነበሩት ሁለት ሌቦችም ላይ ትኩረት ሰጥቷል። ከሁለቱ ወንበዴዎች አንደኛው ከሕዝቡ ጋር አብሮ በኢየሱስ ላይ ሲሳለቅ፣ ሌላው ግን ገሥጾታል። ሁለተኛው ወንበዴ ወንጀለኛ በመሆኑ የሞት ፍርድ እንደሚገባው ተገንዝቧል። ነገር ግን ከኢየሱስ መስቀል ባሻገር ሊመለከትና ኢየሱስ ንጹሕ የእግዚአብሔር ልጅ እንደሆነ ለመረዳት ችሏል። ወደ ኢየሱስ ፊቱን መልሶ በመንፈሳዊ መንግሥቱ አብሮት ለመሆን መፈለጉን አስታውቋል። ኢየሱስ በመስቀል ላይ የተናገረው ሁለተኛው ቃል ለወንበዴው በገነት አብረው እንደሚሆኑ ተስፋ መስጠት ነበር። ገነት የጻድቃን ነፍስ ማደሪያ ናት።

ሉቃስ ከ6 እስከ 9 ሰዓት ድረስ ፀሐይ እንደ ጨለመች ይነግረናል። ይህ ምናልባትም የፀሐይ ግርዶሽ ሊሆን ይችላል። ኢየሱስ መንፈሱን ለእግዚአብሔር ሰጥቶ ሲሞት፣ የቤተ መቅደስ መጋረጃ ለሁለት ተቀደደ። ስቅለቱን ሲያስፈጽም የነበረው የመቶ አለቃ ይህንን ሁሉ ድንቅ ሁኔታ ከተመለከተ በኋላ፣ ኢየሱስ «ጻድቅ ሰው» እንደ ነበር ተናግሯል።

ሉቃስ ከገሊላ ጀምሮ ከኢየሱስ ጋር በነበሩት ሴት ደቀ መዛሙርት ላይም እትኩሯል። እነዚህ ሴቶች የጌታቸውን ሞት ለመመልከት በመስቀሉ አካባቢ ሲጠባበቁ ቆዩ። ኢየሱስ ወደ ተቀበረበት ስፍራ የአርማትያሱን ዮሴፍ ተከትለው የሄዱት እነዚህ ሴቶች ነበሩ። ሉቃስ፥ ዮሴፍን የገለጸው እጥር ምጥን ባለ መንገድ ነበር። ዮሴፍ በኢየሱስ ላይ የሞትን ፍርድ የፈረደው የአይሁድ ሸንጎ አባል ቢሆንም እንኳ፥ በውሳኔው አልተስማማም ነበር። ዮሴፍ እግዚአብሔርን የሚወድና በምሥጢር ኢየሱስን የሚከተል እውነተኛ ሰው ነበር።

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading