ክርስቲያን ለጣዖት የተሠዋ ሥጋ መብላት አለበት? (1ኛ ቆሮ. 8፡1-11፡1)

የውይይት ጥያቄ፡- 1ኛ ቆሮ. 8-10 አንብብ። ሀ) የቆሮንቶስ ክርስቲያኖች ያሳሰባቸው ጉዳይ ምን ነበር? ለ) ጳውሎስ ለጣዖት የተሠዋን ሥጋ ስለ መብላት ወይም ስላለመብላት የሰጣቸውን መርሆች ዘርዝር። ሐ) ዛሬ ክርስቲያኖች በአመለካከት የሚለያዩባቸውንና በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በግልጽ ያልተጠቀሱትን ልምምዶች ዘርዝር። የጳውሎስ መርሆች ከእነዚህ የተለያዩ ግንዛቤዎች ጋር የሚዛመዱት እንዴት ነው?

ሁልጊዜም ክርስቲያኖች በአመለካከት የሚለያዩባቸው የተለያዩ ልምምዶች አሉ። ክርስቲያኖች አልኮል ሊጠጡ፥ ከንፈራቸውንና ጥፍራቸውን ቀለም ሊቀቡ፥ የፋሽን ልብስ ሊለብሱ፥ ፊልም ሊያዩ፥ የዓሣማ ሥጋ ሊበሉ፥ ወዘተ.. ይችላሉ? ከኦርቶዶክስ እምነት የመጡ ክርስቲያኖች አንገታቸው ላይ የነበረውን ክር ሊበጥሱ ይገባል? ክርስቲያኖች በእነዚህ ጉዳዮች በአሳብ አይስማሙም። እንግዲህ፥ ክርስቲያኖች መጽሐፍ ቅዱስ በግልጽ በማይከለክላቸው ጉዳዮች ላይ በአሳብ በሚለያዩበት ጊዜ ምን ማድረግ ይኖርብናል? በእነዚህ ምዕራፎች ውስጥ በእግዚአብሔር ቤተሰብ ውስጥ ልዩነቶችን አቻችሎ ስለመኖር ጠቃሚ መርሆዎች ቀርበዋል።

ሀ. በቆሮንቶስ የነበረው ሁኔታ፤ በቆሮንቶስ ከተማ ብዙ ጣዖታትና ጥቂት ክርስቲያኖች እንደነበሩ ቀደም ብለን ተመልክተናል። በቆሮንቶስ ከተማ ከጣዖት አምልኮ ጋር የሚዛመዱ ብዙ ነገሮች ነበሩ። የቆሮንቶስ ሰዎች በክርስቶስ ካመኑ በኋላ፥ «ከቀድሞ ሕይወታችን ልንተወውና ይዘን ልንቀጥል የሚገባን ምንድን ነው? እያሉ ይጠይቁ ነበር። ሁለተኛው ጥያቄ ደግሞ፥ «ቀደም ሲል ሃይማኖታዊ አስከትሎቶችን ያስተናገዱትንና በራሳቸው ክፉዎች ያልሆኑትን ነገሮች እንዴት ልናስተናግዳቸው ይገባል?» የሚል ነበር። በቆሮንቶስ ክርስቲያን በገበያ ላይ የሚሸጥ ሥጋ ሊበላ ይገባል ወይ? በሚለው ጥያቄ ዙሪያ የተጧጧፈ ክርክር ይካሄድ ነበር። አንድ ሰው ለጣዖት ለመሠዋት በሚፈልግበት ጊዜ እንስሳውን ወደ ቤተ ጣዖት ይወስዳል። እንስሳው ታርዶ ከፊሉ ለጣዖት ከተሠዋ በኋላ፥ ከቀረው ሥጋ የተወሰነውን ለካህኑ ሲሰጥ፥ የተወሰነውን ደግሞ ቤቱ ወስዶ ከወዳጆቹ ጋር ሊመገብ ወይም ገበያ ላይ ሊሸጥ ይችል ነበር። ገበያ ላይ የሚሸጠው ሥጋ በአብዛኛው ለጣዖት የተሠዋ ነበር። ስለሆነም፥ የቆሮንቶስ አማኞች፥ «ክርስቲያኖች ከገበያ ላይ ሥጋ ገዝተው ሊበሉ ይችላሉ? ከዓለማዊ ሰው ቤት ሲጋበዙስ የሚቀርብላቸውን ሥጋ ሊበሉ ይገባል? ይህ ሥጋ ለጣዖት የተሠዋ ሊሆን ይችላልና» የሚል ጥያቄ አነሡ። ይህ እንዳንድ ክርስቲያኖች ከሙስሊም ሉካንዳ ወይም በተገቢው የኦርቶዶክስ ክርስቲያን ያልታረደ ሥጋ ለመብላት ከሚቸገሩበት ሁኔታ ጋር ተመሳሳይ ሊሆን ይችላል። ጳውሎስ ለዚህ ጥያቄ «እንዲህ አድርጉ/ እንዲህ አታድርጉ» የሚል ቀላል ምላሽ አልሰጠም። እንደነዚህ ዓይነት ጥያቄዎች ሁልጊዜም ሥር የሰደዱ ጉዳዮችን እንደሚያካትቱ ተገንዝቦ ነበር።

መርሆዎች፡- ጳውሎስ ለቆሮንቶስ ክርስቲያኖች ከሰጣቸው መልሶች ለሁላችንም ጠቃሚ የሆኑትን መርሆዎች እናገኛለን። እንደሚከተለው ቀርበዋል።

ሀ. አንድ ነገር ስሕተት አለመሆኑን ማወቃችን በፍቅርና ለሌሎች ከማሰባችን ጋር ሊጣጣም ይገባል (1ኛ ቆሮ. 8፡1-3)። ፍቅር ያልታከለበት እውቀት ኩሩና አጥፊ ነው። ለምሳሌ፥ ወደ ፊልም ቤት መሄድ ስሕተት አለመሆኑን ባውቅና ሌሎች ክርስቲያኖች ግን ስሕተት ነው ብለው ቢያስቡ፥ የእኔ ወደ ፊልም ቤት መሄድ የእነርሱን እምነት ከመጉዳትና የእኔን ምስክርነት ከማበላሸት የተሻለ ጥቅም አይኖረውም። ‹እውቀቴን ጉዳትን እንጂ ጥቅምን አላስከተለም። ሰዎች ተጨማሪ ትምህርት ከተከታተሉ በኋላ ተመልሰው የቤተ ክርስቲያናቸው መሪ በሚሆኑበት ጊዜ ይኩራራሉ። እውቀታቸው ከሌሎች ሰዎች የሚያስበልጣቸው ይመስላቸዋል። ይህ የኩራት እውቀት እነዚህ ሰዎች ስለ መንፈሳዊ ነገሮች ብዙም እንደማያውቁ ያሳያል።

ለ. ከእውቀት አንጻር፥ ሰብአዊ ጣዖት (ወይም ሌላ ሃይማኖት) ሰው ሠራሽ እንጂ አምላክ እንዳልሆነ በሳል ክርስቲያኖች ያውቃሉ (1ኛ ቆሮ. 8፡4-7)። አንዱ እውነተኛ አምላክ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የተገለጠው ብቻ ነው። ብቸኛው አምላክና ጌታ በዓለም ውስጥ ሁሉንም ነገር የፈጠረው እግዚአብሔር አብ፥ የፍጥረት ሥራ ሁሉ ወኪል የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስና ሕይወት ሰጭ የሆነው መንፈስ ቅዱስ ነው። ስለሆነም፥ ሕይወትና ኃይል ለሌላቸው ሰው ሠራሽና ሙት ጣዖታት የተሠዋን ሥጋ መብላት ምንም ማለት እንዳልሆነና ሊበላ እንደሚችል በሳል (ጠንካራ) ክርስቲያኖች ይገነዘባሉ።

ሒ. ሌሎች ቢያደርጉትም እንኳ ትክክል ነው ብለህ ያላመንኸውን ነገር ማድረጉ ኃጢአት ነው። ጣዖት ሲያመልኩ የኖሩና በእምነታቸው ያልበሰሉ አንዳንድ ክርስቲያኖች ሥጋውን መብላት በጣዖት አምልኮ ውስጥ መሳተፍ ነው ከሚል ድምዳሜ ላይ ደረሱ። ይህም ድነትን (ደኅንነትን) ባገኙ ጊዜ የተዉት ልምምድ ነበር። ስለሆነም፥ ሌሎች ክርስቲያኖች ይህን ሥጋ ሲበሉ አይተው ከኃፍረት የተነሣ አብረው በሚበሉበት ጊዜ፥ ሕሊናቸው ስለሚቆሽሽ ኃጢአትን ይሠራሉ። የሚያደርጉት ነገር በእግዚአብሔር የተፈቀደ ነው ብለው እስካላመኑ ድረስ (ጳውሎስ «በእምነት ካልሆነ» እንዳለው)፥ ሌሎች የሚያደርጉትን መከተል አያስፈልጋቸውም ነበር።

መ. ለጣዖት የተሠዋ ሥጋ መብላትም ሆነ አለመብላት ምንም ዓይነት መንፈሳዊ እሴት የለውም። አንድን ሰው ወደ እግዚአብሔር አያቀርበውም ወይም ከእግዚአብሔር አያርቀውም (1ኛ ቆሮ. 8፡8)። አዲስ ኪዳን ሁሉም ነገር በጸሎት የተባረከ ስለሆነ ልንበላ እንደምንችል ያስረዳል። በእምነት እስካደረግነው ድረስ በእግዚአብሔር የተፈቀደ ነው (ማር. 7፡14-19፤ የሐዋ 10፡9-16)።

ሠ. አንድ ተግባር በእግዚአብሔር የተፈቀደ ነው ብለን ብናምን እንኳ ፍቅር ከግለሰባዊ ነጻነት ይልቃል (1ኛ ቆሮ. 8፡9–9፡27)። ስለሆነም፥ ሥጋን መብላት ምንም ችግር የለውም የሚል እምነት ያላቸው (ወይም በመጽሐፍ ቅዱስ ያልተከለከለውን ተግባር የሚፈጽሙ) ሰዎች የተለየ አመለካከት የሚከተሉትን ወገኖች ላለመጉዳት ሲሉ ነጻነታቸውን መገደብ አለባቸው። (ጳውሎስ «ደካማ» እና «ጠንካራ» ክርስቲያኖች እንዳሉ ገልጾአል። ጳውሎስ ይህን ሲል ስለ መንፈሳዊ ብስለት ወይም መንፈሳዊነት መናገሩ አይደለም። እርሱ ያተኮረው አንድ ሰው በያዘው የግንዛቤ ደረጃ ላይ ነው። ስለሆነም፥ አንድ ክርስቲያን የዓሣማ ሥጋ በመብላቱ በኩል «ጠንካራ» ሊሆንና የፋሽን ልብስ በመልበሱ ረገድ «ደካማ» ሊሆን ይችላል። ሌላው ክርስቲያን ደግሞ ሥጋ ለመብላት ሊቸገርና የፋሽን ልብስ ለመልበስ ሊደፍር ይችላል።) ጠንካራ ክርስቲያኖች ደካማ ክርስቲያኖችን ላለማሰናከል ሲሉ ተግባሮቻቸውንና ነጻነቶቻቸውን መገደብ አለባቸው። ከሁሉም የሚበልጠው ፍቅር ነው። ፍቅር ደግሞ ሥጋን መብላት ወይም የተወሰኑ ልብሶችን መልበስ ሌላውን ክርስቲያን የሚጎዳው ከሆነ፥ ከዚህ ተግባር መቆጠብ እንዳለብን ይመክረናል።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ክርስቲያኖች የተለያዩ አመለካከቶችን ስለሚይዙባቸው ነገሮች ያቀረብኸውን ዝርዝር ከልስ። ወይም ሌሎች ምሳሌዎችን ጨምርበት። ጠንካራውና ደካማው የትኛው እርምጃ እንደሆነ ግለጽ። ለ) ፍቅር አልባ እውቀት ያለው ሰው በእነዚህ ልምምዶች ሁሉ ወቅት ምን እንደሚያደርግ ግለጽ። ሐ) ፍቅር ያለው ሰው በእነዚህ ልምምዶች ወቅት ምን እንደሚያደርግ ግለጽ።

ማብራሪያ፡ ለሌሎች ባለን ፍቅር የግል መብቶችንና ነጻነቶችን ስለመተው ጳውሎስ ከራሱ ሕይወት ምሳሌ ሰጥቷል (1ኛ ቆሮ. 9)። ጳውሎስ ሐዋርያ ቢሆንም፥ ለወንጌሉ ሲል ብዙ ጊዜ መብቶቹን ትቷል። ለምሳሌ፥

ሀ. ጳውሎስ የማግባት መብት ቢኖረውም ለወንጌሉ ሲል አላደረገውም።

ለ. ጳውሎስ ለሐዋርያዊ አገልግሎቱ ገንዘብ የመቀበል መብት ቢኖረውም፥ ሰዎች ለራስ ወዳድነት ምክንያቶች ያስተምረናል ብለው እንዳያስቡ ትቷል። ቆሮንቶሶችና አዳዲስ ክርስቲያኖች ለወንጌል ስርጭቱ ዓላማ ጥርጣሬ እንዳይኖራቸው በማሰብ፥ ጳውሎስ ክፍያ ላለመቀበል ወስኗል። ስለሆነም፥ ከበሳል አብያተ ክርስቲያናት በሚያገኘው ስጦታ ወይም ራሱ ሠርቶ በሚያገኘው ገንዘብ (በቆሮንቶስ ሳለ ድንኳን ይሰፋ እንደነበረ የሐዋ. 18፡3 አንብብ።) ራሱን ይደግፍ ነበር። በፊልጵስዩስ 1፡5 እና 4፡14–18 ጳውሎስ የፊልጵስዩስ ቤተ ክርስቲያን እንዴት አገልግሎቱን በገንዘብ እንደደገፈች ገልጾአል። ስለሆነም፥ ጳውሎስ ከወንጌል ስብከት ገንዘብ ለማግኘት ካልፈለገ ምን ይሆን የፈለገው? ጳውሎስ ገንዘብ ቢከፈለውም ሳይከፈለውም ከእግዚአብሔር ዘንድ ወንጌልን የመስበክ ግዴታ እንደተጣለበት ያውቅ ነበር። በግሉ የተሸላሚነት ስሜት የሚሰማው ገንዘብ ሳይጠይቅ ለጠፉት ወንጌልን በሚሰብክበት ጊዜ ነበር። (ጳውሎስ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ የሚያገለግሉ፥ በተለይም ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ብለው የገቢ ማግኛቸውን የሚተዉ ሰዎች ደመወዝ ሊከፈላቸው እንደሚገባ የሚያስረዳውን የመጽሐፍ ቅዱስ መርህ አጽንዖት ሰጥቶ ገልጾአል። ለሚያገለግሏት ሰዎች የማትከፍል ወይም ነፃ የውጭ ወንጌላውያን ሥራዎቿን እንዲያካሄዱላት የምትፈልግ ቤተ ክርስቲያን ከእግዚአብሔር ፈቃድ እንዳፈነገጠች ግልጽ ነው።)

ሐ. ከመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል እስካልወጣ ድረስ ጳውሎስ እንደፈለገ የመኖርና የመሥራት ነጻነት ነበረው። ነገር ግን በተቻለ መጠን ብዙዎችን ያድን ዘንድ ነጻነቱን ገድቦታል። አይሁዶችን በሚያገለግልበት ጊዜ ወንጌሉን ሊያካፍላቸው እንዲችል የተወሰኑ ምግቦችን የመመገብ፥ በተወሰኑ መንገዶች የመልበስና የማምለክ ነጻነቱን በመገደብ ባሕሉን ቀይሯል። አሕዛብን በሚያገለግልበት ጊዜ የቋንቋ አጠቃቀሙን፥ የአለባበስና የአምልኮ ሁኔታውን በመቀየር ከባሕላቸው ጋር ተግባብቶ ወንጌሉን ሰብኮላቸዋል። ጳውሎስ በእምነታቸው ደካሞች ሆነው እግዚአብሔር እንዳልከለከለ የሚያውቃቸውን ነገሮች ለማድረግ የማይፈልጉ ሰዎች በሚያጋጥሙት ጊዜ፥ እንደነርሱው «ደካማ» ሆኗል። ጳውሎስ ለግል ነጻነቱና መብቱ ብዙም ትኩረት አይሰጥም ነበር። ለጳውሎስ ዋናው የሰዎች መዳን ነበር። ስለሆነም፥ ሰዎች እንዳይድኑ የሚያደናቅፉትን ነገሮች ሁሉ ከማከናወን ይታቀብ ነበር።

የውይይት ጥያቄ፡– ) በኢትዮጵያ የተለያዩ አብያተ ክርስቲያናትና ባሕሎች በሃሳብ የሚለያዩባቸውን አንዳንድ ነገሮች ዘርዝር። ለ) የተወሰኑ ሕዝቦች (ለምሳሌ፥ ኦርቶዶክሶች ወይም ሙስሊሞች) በሚበዙበት አካባቢ የምታገለግል ወንጌላዊ ብትሆን፥ ወንጌሉን ለመስማት የበለጠ ፈቃደኞች ይሆኑ ዘንድ ነጻነትህን የምትወስንባቸውን መንገዶች ዘርዝር።

መ. ለጳውሎስ መንፈሳዊ ሩጫውን በሚገባ ሮጦ እግዚአብሔር የሰጠውን አገልግሎት በታማኝነት መፈጸምና መንግሥተ ሰማይ መድረስ ወሳኝ ነበር። ስለሆነም፥ የሚወዳቸውንና የሚጠላቸውን ነገሮች፥ አነሣሽ ምክንያቶቹን፥ ተግባራቱንና ሥጋዊ ፍላጎቶቹን በመቆጣጠር ራሱን ገዝቷል። (ጳውሎስ ይህንን ሥጋን መጎሰም ይለዋል።) ይህም የግል ነጻነቱን እየተወ ማንንም ሳያስቀይም ለሰዎች ሁሉ ወንጌልን እንዲሰብክና እግዚአብሔርን እንዲያገለግል ይረዳዋል። (ቆሮንቶስ ከጥንት የስፖርት ከተሞች አንዷ ነበረች። ለዚህ ነበር ጳውሎስ ስለ ክርስትና ለማስተማር ስፖርታዊ ምሳሌዎችን የጠቃቀሰው።)

ከብሉይ ኪዳን የተወሰደ ምሳሌ (1ኛ ቆሮ. 10፡1-13)፡- አንዳንድ ጊዜ በመንፈሳዊ ሕይወታችንና አገልግሎታችን ሳናድግ፥ ሁለንተናችንን ለእግዚአብሔር አሳልፈን ሳንሰጥና ሌሎችን በትሕትና ሳናገለግል በራስ ወዳድነት እየተሯሯጥን እንዋዥቃለን። ጳውሎስ ይህ አደገኛ አመለካከት መሆኑን ገልጾአል። ለእርሱ መንፈሳዊ ሕይወት እንደ ማራቶን ወይም እንደ ቦክስ ውድድር ነበር። ይህም ፍላጎታችንንና ሥጋችንን መቆጣጠርን የሚጠይቅ ከፍተኛ ራስን የመግዛት ተግባር ነው። ይህ ካልሆነ፥ ጳውሎስ ለመንፈሳዊ ሩጫው ብቁ እንደማይሆን አመልክቷል። ይህንንም እውነት ለማብራራት ብሉይ ኪዳንን፥ በተለይም የእስራኤላውያንን የምድረ በዳ ጉዞ በምሳሌነት ጠቅሷል። እነዚህ ታሪኮች ለመንፈሳዊ ሕይወታችን ጠቃሚ ትምህርቶችን ከመስጠታቸውም በላይ፥ ለክርስቲያኖች ሁሉ ማስጠንቀቂያዎችን ያስተላልፋሉ።

ሀ. እስራኤላውያን በክብር ደመና እየተመሩ ይጓዙ ነበር። (ቀን ቀን የክብር ደመና፥ ማታ ማታ የእሳት ዓምድ ይመራቸው ነበር።)

ለ. እስራኤላውያን ሁሉ የእግዚአብሔርን ኃይል ተመልክተዋል፤ ቀይ ባሕር ተከፍሎ ተሻግረዋል።

ሒ ሁሉም “በሙሴ ተጠምቀዋል”። ጳውሎስ ይህን ሲል ሙሴ ከእግዚአብሔር ጋር ከነበረው ግንኙነት በመነጩት መንፈሳዊ በረከቶች እየተደሰቱ በእርሱ አመራር ሥር ይኖሩ እንደነበር መግለጹ ነበር።

መ. ሁሉም መንፈሳዊውን የመና ምግብ በልተዋል። መናው ከእግዚአብሔር እንጂ ከምድር ስላልተገኘ መንፈሳዊ ተብሏል።

ሠ. ሁሉም አንድ ዓይነት መንፈሳዊ መጠጥ ጠጥተዋል። ይህም ከዓለቱ የፈለቀውን ውኃ ያመለክት ነበር። የብሉይ ኪዳን እስራኤላውያን በውኃውና በመናው እንደተደሰቱ ሁሉ፥ እኛም የሕይወት እንጀራችንና የሕይወት ውኃችን በሆነው በክርስቶስ ደስ እየተሰኘን ነው። (ዮሐ 6፡30-35፤ 7፥37-39 አንብብ።) መናውና የዓለቱ ውኃ ክርስቶስ ለተከታዮቹ የሚሰጣቸውን በረከት ያመለክታሉ።

ምንም እንኳ ሁሉም እስራኤላውያን ወደ ተስፋዪቱ ምድር ለመግባት በረሃውን እያቋረጡ መንፈሳዊ ሩጫ ቢሮጡም፥ ሩጫውን የጨረሱት ኢያሱና ካሌብ ብቻ ነበሩ። የተቀሩት የከነዓንን በረከት ሳይቀበሉ በምድረ በዳ ውስጥ ሞተዋል። በወሲብ ኃጢአት፥ በጣዖት አምልኮ፥ እንዲሁም በመሪዎቻቸውና በእግዚአብሔር ላይ በማመፃቸው ሩጫውን በሚገባ ሊሮጡ አልቻሉም። ስለሆነም፥ ጳውሎስ በመንፈሳዊ ሩጫቸው በመዘናጋት ላይ የነበሩት የቆሮንቶስ አማኞች ዋናው ሩጫውን መጀመር ወይም ለአጭር ጊዜ መሮጥ ሳይሆን ከፍጻሜ ላይ መድረስ እንደሆነ እንዲያስታውሱ አስጠንቅቋቸዋል።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ብዙ ክርስቲያኖች እስከ መጨረሻው ለመሮጥ ይችሉ ዘንድ ሕይወታቸውን ለመቆጣጠር ከመጣር ይልቅ በድነታቸውና (በደኅንነታቸው) ጊዜያዊ በረከቶች ላይ የሚያተኩሩት እንዴት ነው? ለ) 2ኛ ጢሞ 4፡6-8 እንብብ። ጳውሎስ ለእምነቱ ሊሞት ሲል ስለዚህ ሩጫ ምን አለ?

ጳውሎስ እውነተኛውን የሕይወት አቅጣጫ የሚከተል ሰው ስለነበር፥ በሩጫ ውስጥ መንፈሳዊ ፈተናዎች መኖራቸውን ለክርስቲያኖች አስጠንቅቋል። ስለሆነም ጸንተው ለመቆም ሊቆርጡ ይገባል። ብዙ ክርስቲያኖች በ1ኛ ቆሮንቶስ 10፡13 የተገለጸውን አሳብ በተሳሳተ መንገድ ይረዳሉ። እግዚአብሔር ከፈተና እንደሚጠብቀን ወይም ፈተና ገጥሞን በምንጸልይበት ጊዜ እግዚአብሔር ከፈተና ያድነናል ብለው ያስባሉ። ጳውሎስ የሚለው ይህን አልነበረም። ጳውሎስ ስለ ፈተና የተለያየ እውነቶችን ገልጾአል።

በመጀመሪያ፥ ክርስቲያኖች ሁሉ ፈተና እንደሚገጥማቸው ገልጾአል። ብዙውን ጊዜ ፈተና በሚገጥመን ጊዜ እኛ ላይ ብቻ የደረሰ ይመስለናል። ጳውሎስ ግን ክርስቲያኖች ሁሉ በፈተና ውስጥ እንደሚያልፉ ገልጾአል።

ሁለተኛ፡ ጳውሎስ ታማኙ አምላካችን ከእኛ ጋር ስላለ ወደ ፈተና የምንገባው ብቻችንን እንዳልሆነ አስረድቷል።

ሦስተኛ፥ ታማኙ አምላካችን ከአቅማችን በላይ የሆነ ፈተና እንደማይገጥመን የተስፋ ቃል ገብቶልናል። እግዚአብሔር ምን ዓይነት ፈተናዎች እንደሚገጥሙን በመወሰን በመንፈሳዊ እድገት ደረጃችን የምንቋቋማቸውን ብቻ እንድንጋፈጥ ይፈቅዳል።

አራተኛ፥ ሁልጊዜም ፈተናን ለመቋቋምና ለመጽናት የሚያስችል መንገድ አለ። ለእግዚአብሔር የሚከብድ ባይሆንም፥ ጳውሎስ ያተኮረው ከፈተና ስለመትረፍ አልነበረም። ጳውሎስ አጽንኦት የሰጠው በመንፈስ ቅዱስ አማካኝነት በመንፈሳዊ ጉዟችን ድል ነሺዎች ሆነን እስከ መጨረሻው በመጽናታችን ላይ ነው።

ጳውሎስ ስለ ሰዎች በፈተና መውደቅ ሰይጣንን እንደማይወቅስ አስተውል። ሰይጣን ዓለምንና ሥጋችንን ተጠቅሞ በኃጢአት ሊፈትነን ቢችልም፥ ኃጢአትን እንድንሠራ ለያስገድደን ግን አይችልም። እግዚአብሔር የማንችለውን ፈተና አመጣብን ብለንም ልናማርር አንችልም። ሌላ ሰው ለኃጢአት እንደገፋፋን በመግለጽም አንወቅሰውም። ሁልጊዜም ኃጢአትን የምንፈጽመው እግዚአብሔርን ከመታዘዝ ይልቅ የሥጋችንን ፍላጎት ለማሟላት ስለምንመርጥ ነው። ተግባሮቻችን የምርጫዎቻችን ውጤቶች በመሆናቸው ተጠያቂዎች ራሳችን ነን።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) አንዳንድ ክርስቲያኖች እውነተኛ ክርስቲያኖች ፈተና እንደማይገጥማቸው ወይም በመጸለይና ሰይጣንን በማሰር ፈተናው ትቷቸው እንዲሄድ እንደሚያደርጉ ሲናገሩ የሰማህበትን ሁኔታ አብራራ። ለ) አንዳንድ ክርስቲያኖች ራሳቸው ለፈጸሙት ኃጢአት ሰይጣንን ወይም ሌሎች ሰዎች ተጠያቂ የሚያደርጉት እንዴት ነው?

ስለ አምልኮተ ጣዖት የተሰጠ ማስጠንቀቂያ (1ኛ ቆሮ. 10፡14-22)። ጣዖታት አማልክት ላለመሆናቸው የነበራቸውን እውቀት በተሳሳተ መንገድ የተገነዘቡ አንዳንድ የቆሮንቶስ ክርስቲያኖች ነበሩ። «ጣዖታት አማልክት እስካልሆኑ ድረስ ጎረቤቶቻችንን ለማክበር ስንል ሄደን መሥዋዕት ልናቀርብላቸው እንችላለን። ከጎረቤቶቻችን ጋር ያለን ግንኙነት አስፈላጊ ነው። እንደ ድንጋይ ጣዖት ላለ እውነተኛ ያልሆነ ነገር መሠዋቱ ሊጎዳን አይችልም» ብለው አሰቡ። ምናልባትም ጣዖትን በማምላካቸው ምንም ሊጎዱ እንደማይችሉ በማሰብ በዚሁ ተግባራቸው የቀጠሉ ክርስቲያኖች የእግዚአብሔር ልጆች እንደ መሆናቸው ይህንኑ ተግባር ሊፈጽሙ የማችይሉባቸውን አያሌ ምክንያቶች ጳውሎስ ዘርዝሯል።

ሀ. ለጣዖት የተሠዋውን ምግብና መጠጥ እየበሉ እየጠጡ ከሌሎች ጋር ለጣዖት በሚሠዉበት ጊዜ የጣዖት አምልኮው ተካፋዮች መሆናቸውን እየገለጹ ነበር። አንድ ክርስቲያን ሙሉ ለሙሉ ከእግዚአብሔር ጋር የሚቃረን ተግባር ከሚፈጽሙ ሰዎች ጋር እንዴት በዚህ መንገድ ኅብረት ሊያደርግ ይችላል?

ለ. ጣዖታት በራሳቸው አማልክት ባይሆኑም፥ አጋንንት ከጣዖት ጋር ይሠሩ ነበር። ሰዎቹ አምልኮተ ጣዖትን በሚያካሂዱበት ጊዜ በትክክል አጋንንትን ማምለካቸው ነበር። ይህም ለሰይጣንና ለአጋንንት ሕይወታቸውን እንዲያጠቁ በር ይከፍታል። ክርስቲያኖች ደግሞ ከሰይጣን ጋር ለመዋጋት የሚያስችል ኃይል እንደሌላቸው ማወቅ አለባቸው። ማንም ሰው በቅዱስ ቁርባን ተምሳሌትነት እንደተገለጸው ክርስቶስን እያመለከ በጣዖት አምልኮ ውስጥ ሊካፈል አይችልም። ይህንን ማድረግ የእግዚአብሔርን ቅጣት ያስከትላል።

የውይይት ጥያቄ፡- ዛሬ ክርስቲያኖች እግዚአብሔርን እናመልካለን እያሉ ከሰይጣን ኃይል ሥር ያሉትን ነገሮች በማምለክ እግዚአብሔርን ሊያሳዝኑ የሚችሉባቸውን መንገዶች ዘርዝር።

ለጣዖት ስለተሠዋ ምግብ የተሰጡ ዝርዝር ትእዛዛት (1ኛ ቆሮ. 10፡23-11፡1)

ሀ. ጳውሎስ ቀደም ሲል ስለ ዝሙት በሚያስተምርበት ጊዜ ወዳነሣው መሠረታዊ መርህ ይመለሳል (1ኛ ቆሮ. 6፡12)። (የምንፈልገውን የማድረግ ነጻነት አለን ብለን ልናስብ ብንችልም፥ ዋናው ጥያቄ፥ «ጠቃሚ ነው ወይ?» የሚለው ነው። ይህ ለግለሰቡ ጠቃሚ ነው? ከሁሉም በላይ፥ ይህ ለሌሎች ጉዳዩ ለሚመለከታቸው ሰዎች ጠቃሚ ነው? ስለሆነም፥ በአንድ ልምምድ ላይ ሰዎች የተለያዩ አመለካከቶችን በሚያቀርቡበት ጊዜ፥ ልምምዱ ምንም ችግር ሊያስከትል እንደማይችል የሚያስበው ሰው ስለ ራሱ ነጻነት ብቻ ሳይሆን በሌሎች ላይ ስለሚያስከትለው ተጽዕኖም ማሰብ አለበት። ይህ ልምምድ በማያምኑ ሰዎች ፊት ምስክርነቱን ስለመጉዳቱና በሌሎች ክርስቲያኖች ላይ ስለሚያደርሰው ተጽዕኖ ማሰብ ይኖርበታል (1ኛ ቆሮ. 10፡23-24)።

ለ. ከገበያ የተገዛን ሥጋ መብላት። ለጣዖት ስለ መሠዋት አለመሠዋቱ አትጨነቅ። ለጣዖት ተሠውቷል ወይ? ብለህ የምትጠይቅ ከሆነ፥ ሕሊናህ እንዳትበላው እየነገርህ ነው ማለት ነው። ሥጋው መሠዋት አለመሠዋቱን አለማወቁ የተሻለ ነው። ሁሉም ነገር የእግዚአብሔር እንደሆነና እርሱም ደስ እንድንሰኝበት እንደሰጠን አስታውስ።

ሐ አንድ ዓለማዊ ምግብ ቢጋብዝህ፥ ለጣዖት ተሠውቶ ይሆን? ብለህ ሳትጠራጠር የቀረበልህን ብላ።

መ. አንድ ሰው (ዓለማዊውም ሆነ ጉዳዩ የሚያሳስበው ክርስቲያን) ለጣዖት የተሠዋ መሆኑን ከነገረህ አትብላው። ለምን? የማትበላው ሕይወት ለሌለው ጣዖት የተሠዋ ምግብ እንደማይጎዳህ እስካመንህ (እስካወቅህ) ድረስ መንፈሳዊ ችግር ስለሚያስከትልብህ አይደለም። የማትበላው ዓለማዊው የጣዖት አምልኮውን እየደገፍህለት እንደሆነ እንዳያስብ ነው። በደካማ ክርስቲያኖችም ፊት መብላት አይኖርብህም። ምክንያቱም ተግባርህ ሕሊናቸው የማይቀበለውን ነገር እንዲያደርጉ ያበረታታቸዋል። ሌሎች ሰዎች ምን ልናደርግ እንደምንችል ሊናገሩ አይችሉም። ሕሊናችን ከእግዚአብሔር ጋር ባለን ግንኙነት ላይ ይወሰናል። ነገር ግን ለሌሎችና ለወንጌሉ ባለን ፍቅር ምክንያት ተግባራችንን እንገድባለን።

ሠ. ተግባሮችህን የምትፈጽመው ስለፈለግህ ብቻ ሳይሆን ለእግዚአብሔር ክብርን ለማምጣት ጭምር እንደሆነ አረጋግጥ። ተግባሮችህ ለእግዚአብሔር የበለጠ ክብርን የሚያመጡት ክርስቲያናዊ ነጻነትህን እንዳሻህ ስትጠቀም ላይሆን ክርስቲያኖችንም ሆነ ዓለማውያንን ላለማሰናከል ጥረት ስታደርግ ነው።

የውይይት ጥያቄ፡- ክርስቲያኖች ስለማይስማሙባቸው ልምምዶች የጻፍኸውን ዝርዝር ተመልከት። ጳውሎስ በዚህ ክፍል ውስጥ ያቀረባቸውን መርሆዎች በመመልከት ጠንካራ ክርስቲያን ብትሆን ምን ዓይነት ምላሽ እንደምትሰጥ ግለጽ።

ምንም እንኳን ጳውሎስ ባያትተውም፥ «ደካማ» ክርስቲያኖች የተባሉት በደካማነታቸው መጽናት የለባቸውም። የሚያስቀይማቸውን ወይም ከሌሎች የሚለያያቸውን ተግባር መመርመር ያስፈልጋቸዋል። ደካማ ክርስቲያን ያንን ተግባር ለመፈጸም ባይፈልግም እንኳ፥ ሌሎች ክርስቲያኖች ሌላ አቋም ሲይዙና ቀደም ሲል ይጠላው የነበረውን ተግባር ሲፈጽሙ በሚመለከትበት ጊዜ ለመታገሥ እንዲችል ወደ «ጠንካራ» ክርስቲያንነት መሸጋገር ይኖርበታል። ወደ ጠንካራ ክርስቲያንነት መሸጋገር እንጂ በደካማነቱ መጽናት የለብንም። (ማስታወሻ፡- የምንነጋገረው መጽሐፍ ቅዱስ በግልጽ ስለጠቀሳቸው ኃጢአቶች ሳይሆን መጽሐፍ ቅዱስ ስለማይናገርሳቸው ነገሮች መሆኑን አስተውል።)

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading