ለቅዱሳን የተደረገ የገንዘብ መዋጮ እና የሐዋርያው ጳውሎስ ዕቅድ (1ኛ ቆሮ. 16፡1-24)

የቆሮንቶስ ክርስቲያኖች አይተዋቸው ለማያውቋቸውና በኢየሩሳሌም ለሚኖሩ አይሁዳውያን ክርስቲያኖች ገንዘብ መስጠት ያለባቸው ለምንድን ነው? (1ኛ ቆሮ. 6፡1-4)

የቆሮንቶስ ክርስቲያኖች የጠየቁት የመጨረሻው ጉዳይ በኢየሩሳሌም ለሚገኙ አይሁዳውያን አማኞች ገንዘብ መዋጣትን የሚመለከት ነበር። ጳውሎስ በቅርቡ ክርስቲያኖች በድህነት ወደሚሠቃዩባት ወደ ኢየሩሳሌም እንደሚሄድ ለአሕዛብ አብያተ ክርስቲያናት ሁሉ የተናገረ ይመስላል። ስለሆነም የአሕዛብ ክርስቲያኖች ለአይሁድ ክርስቲያኖች ፍቅራቸውንና ወንጌሉን ለማካፈላቸው ምስጋናቸውን የሚገልጹበትን ዕድል ሰጣቸው። ጳውሎስ አሕዛብ ክርስቲያኖች በየሳምንቱ ምጽዋት እንዲሰበስቡና እርሱ በሚመጣበት ጊዜ በተወሰኑ የቤተ ክርስቲያን መሪዎች አማካኝነት ገንዘቡን ወደ ኢየሩሳሌም እንዲልኩ መከራቸው። (ጳውሎስ እንደገና በ2ኛ ቆሮ. 8-9 ስለዚህ ጉዳይ ያነሣል።)

ከዚህ ክፍል አያሌ ጠቃሚ እውነቶችን ልንማር እንችላለን።

ሀ. ክርስቲያኖች ሁሉ ሁልጊዜም ለእግዚአብሔር ሥራና ለእግዚአብሔር ሕዝብ ገንዘባቸውን መስጠት አለባቸው። ጳውሎስ በየእሑዱ ምጽዋት እንዲሰበስቡ ነግሯቸዋል።

ለ. አማኞች ለራሳቸውና ለማኅበረ ምእመኖቻቸው ብቻ ሳይሆን በዓለም ሁሉ ለተበተኑት ወንድሞችና እኅቶች ፍላጎት ሊያስቡ ይገባል።

ሐ. ክርስቲያን መሪዎች ከገንዘብ ጋር በተያያዘ ዝናቸው እንዳይጎድፍ መጠንቀቅ አለባቸው። ጳውሎስ ገንዘቡን ለማድረስ ሌሎች የቤተ ክርስቲያኒቱ መሪዎች አብረውት እንዲሄዱ ጠይቋል። ጳውሎስ ይህን ያደረገው በራሱ ታማኝነት ላይ ጥርጣሬ ስላደረበት ሳይሆን፥ ታማኝነቱን የሚጠራጠሩ ሰዎች ወሬ እንዳያዛምቱበት ነበር። የመሪዎች ስም ከሚጎድፍባቸው ዐበይት መንገዶች አንዱ የተሳሳተ የገንዘብ አያያዝ ወይም ሌሎች ሰዎች የሚጠራጠሩበትን በር መክፈት ነው።

የውይይት ጥያቄ፡– ሀ) የተሳሳተ የገንዘብ አጠቃቀም የአንድን ቤተ ክርስቲያን መሪ ስም ሲያጎድፍ ያየኸው እንዴት ነው? መሪዎች ስማቸውን ለመጠበቅ ምን የተለየ ነገር ማድረግ አለባቸው? ለ) ብዙ ክርስቲያኖች አሥራትን የሚሰጡ ይመስልሃል? ካልሆነ ለምን? ሐ) የአንድ ቤተ ክርስቲያን የገንዘብ አጠቃቀም፤ የራስን ጥቅም ከመፈለግና ከራስ ወዳድነት ወይም ደግሞ ከቤተ ክርስቲያን ውጪ ክርስቲያን ያልሆኑትን ለመርዳት እንደዋለ የሚታወቀው እንዴት ነው?

መደምደሚያ (1ኛ ቆሮ. 16፡5-24)

ጳውሎስ ተጨማሪ ግላዊ መረጃ በመስጠት ይህን መልእክት ደምድሟል። በኤፌሶን ለጥቂት ወራት ከተቀመጠ በኋላ በመቄዶንያ በኩል ወደ ቆሮንቶስ ተጉዞ አያሌ ወራት እንደሚቆይ ይነግራቸዋል። ጢሞቴዎስ ሊጎበኛቸው ስለሚመጣ መልካም አቀባበል እንዲያደርጉለት ያሳስባቸዋል። በተጨማሪም፥ ጳውሎስ አጵሎስ ሄዶ እንዲያገለግላቸው መፈለጉንና አጵሎስ ግን በወቅቱ ይህንኑ ሊያደርግ አለመቻሉን ገልጾአል። አጵሎስ ከጳውሎስ የበለጠ የመናገር ስጦታ የነበረው ቢመስልም ጳውሎስ አልቀናበትም ነበር። ጳውሎስ የቆሮንቶስ ክርስቲያኖች በመንፈሳዊ ሕይወታቸው እንዲያድጉ ስለሚፈልግ፥ አጵሎስ ከመንፈሳዊ ለጋነታቸውና ከችግሮቻቸው አልፈው እንዲሄዱ ይረዳቸው ዘንድ ወደደ፡፡

ጳውሎስ ለቆሮንቶስ አማኞች ሰላምታንና በሦስት ተወካዮቻቸው (እስጢፋኖስ፥ ፈርዶናጥስና አካይቆስ) አማካኝነት ስለላኩለት ስጦታ ምስጋና በማቅረብ መልእክቱን ደምድሟል። ከእስያ ክርስቲያኖች በተለይም ከአቂላና ከጵርስቅላ ሰላምታ አቅርቦላቸዋል። አቂላና ጵርስቅላ በቆሮንቶስ ከተማ ስለኖሩ የአገሪቱ ክርስቲያኖች ያውቋቸው ነበር።

ምሁራን ጳውሎስ የዓይን ሕመም ስለነበረበት መልእክቱን ራሱ ለመጻፍ ሳይሳነው እንዳልቀረ ያስባሉ። በመሆኑም፥ ለሮሜ መጽሐፍ እንዳደረገው በሌላ ጸሐፊ ተጠቅሟል (ሮሜ 16፡22)። ነገር ግን መልእክቱ የሌላ ሰው ሳይሆን የራሱ እንደሆነ ለማሳየት በደብዳቤው ላይ ፈርሞበታል።

ጳውሎስ ይህንን መልእክት የፈጸመው ክርስቶስን የማይወዱትን በማስጠንቀቅ ነበር። ጳውሎስ የክርስቶስን ምጽአት ቢናፍቅም፥ ምጽአቱ ክርስቶስን በሕይወታቸው ባላከበሩት ሰዎች ላይ ፍርድን እንደሚያስከትል አልዘነጋም። እኛም ልባችንን ሁልጊዜ ልንመረምር ይገባል። ልባችን «ማራናታ» ወይም «ጌታ ኢየሱስ ሆይ ና» እያለ ቢጮህ፥ ለፍርዱ በፊቱ ለመቆም ልባችንን መመርመር አለብን። ለክርስቶስ ምጽአት ዝግጁዎች ነን?

የውይይት ጥያቄ፡- ከ1ኛ ቆሮንቶስ ጥናታችን የተማርሃቸው አንዳንድ ቁልፍ ትምህርቶች ምን ምንድን ናቸው?

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading