የ2ኛ ጢሞቴዎስ ዓላማ እና ልዩ ባሕሪያት

የ2ኛ ጢሞቴዎስ ዓላማ

የመጀመሪያው ዓላማ፡- ጢሞቴዎስ ከሚጋፈጠው ስደት ባሻገር በእምነቱ እንዲበረታ ለማሳሰብ። በመጨረሻዎቹ ጥቂት ወራት ጳውሎስ ብቸኝነት ተጫጭኖት ነበር። ከጽሑፎቹ እንደምንመለከተው፥ ጳውሎስም እንደኛ ሰው በመሆኑ በአንዳንድ አማኞች ተግባራት ጥልቅ ስሜት ጉዳት ደርሶበት ነበር። ስደትን ከመፍራታቸው የተነሣ ይመስላል ብዙዎቹ የጳውሎስ የግል ጓደኞችና የአገልግሎት ተባባሪዎች ብቻውን ጥለውት ወደየቤቶቻቸው ገቡ። ጳውሎስ ከእስያ አውራጃ ሁሉም ሰው እንደ ተወው ይናገራል። ይህም በኤፌሶን አካባቢ የሚገኝ ስፍራ ሲሆን፥ ጳውሎስ ለረጅም ጊዜያት ያገለገለበት ቦታ ነበር (2ኛ ጢሞ. 1፡15)። አብሮት ያገለግል የነበረው ዴማስ ትቶት ሄደ (2ኛ ጢሞ. 4፡10)። እነዚህ ሰዎች በክርስቶስ ማመናቸውን ይተዉ አይተዉ የታወቀ ነገር የለም። ነገር ግን ጳውሎስ እጅግ በሚፈልጋቸው ጊዜ ትተውት መሸሻቸው በጥልቀት ጎዳው። ነገር ኝ እንደ ሉቃስ ያሉ ጥቂቶች አብረውት እስከ መጨረሻው ቆይተዋል (2ኛ ጢሞ. 4፡11)። የቅርብ ወዳጁ ጢሞቴዎስ እንኳን ከጳውሎስ ጋር ለመተባበር በመፍራቱ ምክንያት እምነቱን ለመደበቅ የሞከረ ይመስላል። ስለሆነም ጳውሎስ ለጢሞቴዎስ ስደትን እንዳይፈራና በእስራቱ ወይም የእስራቱና የሞቱ ምክንያት በሆነው ወንጌል እንዳያፍር ይነግረዋል (2ኛ ጢሞ. 1፡8)።

ሁለተኛ ዓላማ፡- ጳውሎስ በኤፌሶን ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ስለነበሩት ችግሮች ከሰማ በኋላ፥ ኔሮ ስደቱን እያጠናከረ ሲሄድና የሐሰት ትምህርቶች ሲስፋፉ ብዙ ሰዎች በክርስቶስ ላይ ያላቸውን እምነት እንዳይተዉ ሰግቷል። በመሆኑም ጳውሎስ ጢሞቴዎስ የወንጌልን እውነት እንዲጠብቅ (2ኛ ጢሞ. 1፡14)፣ ተጨማሪ ስደት የሚያስከትልባቸው ቢሆንም (2ኛ ጢሞ. 1፡8፤ 2፡3) በአስቸጋሪ ጊዜያት ወንጌሉን መመስከራቸውን እንዲቀጥሉ (2ኛ ጢሞ. 4፡2) ለማሳሰብ ይፈልጋል። ይህ መልእክት የተጻፈው ለጢሞቴዎስ ብቻ ሳይሆን ለቤተ ክርስቲያን ሁሉ ነበር። ለዚህም ነው ጳውሎስ በ2ኛ ጢሞቴዎስ 4፡22 ላይ ጸጋ ከመንፈሳችሁ ጋር ይሁን ያለው፤ ይህም የኤፌሶንን ቤተ ክርስቲያን የሚያመለክት ነው።

ሦስተኛ ዓላማ፡- ጢሞቴዎስ በጥንቃቄ ሊይዘው በሚገባው የእግዚአብሔር ቃል ላይ አገልግሎቱን በመመሥረት በእምነቱ እንዲጸና ለማበረታታት (2ኛ ጢሞ. 2፡15)።

4ኛ ጥያቄ፡- በዘመናችን ያሉት ክርስቲያኖች እነዚህን እውነቶች በማስታወስ ተግባራዊ ማድረጋቸው አስፈላጊ የሚሆነው ለምንድን ነው?

የ2ኛ ጢሞቴዎስ መልእክት ልዩ ባሕርያት

  1. ጳውሎስ እውነትን ወይም ከሐዋርያት የተላለፈውን የእውነት አካል በመጠበቅ ላይ ያተኩራል። እዚህ ላይ አጽንኦት የተሰጠው አዲስን እውነት በማብራራት ወይም ሌሎች አስደሳች እውነቶችን በመፈለግ ላይ ሳይሆን፥ ጢሞቴዎስ ትክክል መሆኑን በሚያውቁት እውነት ላይ ነው። ብዙውን ጊዜ ከታላላቅ ሰባኪዎች የሚመጡትን አዳዲስና አስደሳች እውነቶች እንፈልጋለን ከታወቁ አብያተ ክርስቲያናት፥ ልዩ ስጦታ ያላቸውን ሰባኪዎች ወይም በምዕራቡ-ዓለም ከአጽናፍ እስከ አጽናፍ የናኘ ዝና ያላቸውን አገልጋዮች ለመጋበዝ እንሽቀዳደማለን። ይህ ግን አደገኛ ነገር ነው። ምክንያቱም ጳውሎስ አስተምህሯዊ ግራ መጋባት በሚኖርበት ጊዜ ወሳኙ ነገር የእምነታችንን መሠረት መያዝና በእነዚያ እውነቶች ላይ መጽናት እንደሆነ ያስተምራል። ከጳውሎስ የተነሣው የእውነት መሥመር ለእኛና ከእኛም በኋላ ለሚመጡት ትውልዶች ይደርስ ዘንድ ተግተን ልንጠብቀው ይገባል።
  2. ይህ ደብዳቤ አንድ ሸምገል ያለ ሰው ሊሞት ሲል በዕድሜው ወጣት ለሆነ ሌላ ሰው የሚያስተላልፈውን የመጨረሻ ምስክርነት ወይም ምክር ይመስላል። ጳውሎስ በዚህች አጭር ደብዳቤ ውስጥ ከሕይወት የተማራቸውን ዐበይት እውነቶች ጠቅለል አድርጎ አስቀምጧል። ከሞት ጋር ፊት ለፊት በሚጋፈጡበት ጊዜ፥ ለክርስቲያኖች ጠቀሜታ የሌላቸው እውነቶች አስፈላጊዎች አይሆኑም። የሚያስፈልጓቸው እጅግ ወሳኝ የሆኑ እውነቶች ናቸው። ለዚህም ነው ጳውሎስ ይህንን በደብዳቤው ውስጥ ያካተተው።
  3. ጳውሎስ አለማፈር የሚለውን ቃል አጽንኦት ሰጥቶ ጠቅሷል። ጳውሎስ ጢሞቴዎስ ሀ) ስለ እግዚአብሔር ለመመስከር፥ እስረኛ በሆነው በጳውሎስ (2ኛ ጢሞ. 1፡8)፥ ሐ) በወንጌል (2ኛ ጢሞ. 1፡12) እንዳያፍርና መ) ክርስቶስ በሚመለስበት ጊዜ እንዳያፍር ታማኝ አገልጋይ ሆኖ እንዲሠራ ያስጠነቅቀዋል (2ኛ ጢሞ. 2፡15)። ጳውሎስ በኔሮ ፊት በተመረመረበት ወቅት ለእግዚአብሔር ታማኝ በመሆኑ ለኀፍረት እንደማይጋለጥ ይናገራል (2ኛ ጢሞ. 4፡16-17)።

4 ጳውሎስ አማኞችን ከተለያዩ ነገሮች ጋር በማነጻጸር የታማኝ አገልጋዮችን ሚና ያብራራል። አማኞች እንደ ልጅ (2ኛ ጢሞ. 2፡1)፣ እንደ ወታደር (2ኛ ጢሞ. 2፡3-4)፥ እንደ አትሌት (2ኛ ጢሞ. 2፡5)፥ እንደ ገበሬ (2ኛ ጢሞ. 2፡6)፥ እንደ ሠራተኛ (2ኛ ጢሞ. 2፡15)፥ እንደ ዕቃ (2ኛ ጢሞ. 2፡20-21) እና እንደ ባሪያ (2ኛ ጢሞ. 2፡24) ተገልጸዋል።

  1. ጳውሎስ አማኝ በክርስቶስ ኢየሱስ ላለው እምነቱ እስራትንና ሞትን እንዴት በእርጋታ እንደሚቀበል ያብራራል። ጳውሎስ ለወንጌሉ መከራን ስለ መቀበል በተደጋጋሚ ጠቅሷል። ይህም የክርስቲያኖች ተለምዷዊ አኗኗር መሆኑን በመግለጽ፥ ክርስቲያኖች መከራ በሚገጥማቸው ጊዜ ከመሸሽ ይልቅ በትዕግሥት እንዲወጡት አሳስቧል (2ኛ ጢሞ. 1፡8፥ 2፡3፥ 8-13)። ጳውሎስ ታላቅ ጀግና መሆኑን ለማሳየት አልፈለገም። ነገር ግን እግዚአብሔር ሁኔታዎችን በመቆጣጠር ላይ መሆኑንና ክርስቲያን የመንግሥተ ሰማይና የእግዚአብሔር ክብር የሚጠብቁት መሆኑን በእርጋታ ያስረዳል።

በዘመናችን፥ ስለ ስደትና ለክርስቶስ ስለ መሞት ለመነጋገር አንፈልግም። ነገር ግን በየዓመቱ 330,000 ሺህ ክርስቲያኖች ለእምነታቸው እንደሚሞቱ ጥናቶች ይጠቁማሉ። ይህ በክርስቲያኖች ላይ የሚሰነዘር ጥላቻ እየጨመረ መሄዱን የሚያሳይ ሲሆን፥ እኛም አንድ ቀን ለእምነታችን ለመሞት እንገደድ ይሆናል። እንዲህ ዓይነት ሁኔታ ከገጠመን፥ እሥራትንና ሞትን ክርስቶስን በሚያስከብር መንገድ እንዴት መቀበል እንዳለብን የጳውሎስ ምሳሌነት ያስተምራል።

የውይይት ጥያቄ፡- ስደትና መከራ በሚገጥመን ጊዜ ስለ መንግሥተ ሰማይ የሚኖረን ግንዛቤና እውነት እንዴት ሊረዳን ይችላል?

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading