ክርስቶስን ለመከተል እምነት ወሳኝ ነው (ዕብ. 11፡1-39)

ብዙውን ጊዜ በክርስቶስ ማመን ምን ማለት እንደሆነ ሰዎች የተሳሳተ አመለካከት አላቸው። ብዙዎቻችን ስለ እውነታው ትክክለኛነት በሚያስረዳው እእምሮአዊ እውቀት ላይ እናተኩራለን። ስለሆነም አንድ ሰው በክርስቶስ እንዲያምን በምንጠይቅበት ጊዜ፥ «ክርስቶስ ለኃጢአትህ እንደ ሞተ እመን» ማለታችን ነው። ነገር ግን በክርስቶስ ማመን እርሱ በሚፈልገው መንገድ መጓዝን እንደሚጠይቅ አንገነዘብም። ከዚህም የተነሣ፥ ብዙ ሰዎች በክርስቶስ እናምናለን ቢሉም፥ ሕይወታቸው ግን አይለወጥም። ብዙ ሰዎች በአእምሮአቸው የሚረዱትን ወይም እሑድ እሑድ ወደ ቤተ ክርስቲያን ሲሄዱ የሚናገሩትን ነገር በአኗኗራቸው አያንጸባርቁም። አይሁዳውያን አማኞች ይኸው ተመሳሳይ ችግር ገጥሟቸው ነበር። አንዳንዶቹ አምልኮአቸውን፥ ከአሕዛብ አማኞች ጋር የነበራቸውን ግንኙነት ሳይቀይሩ፥ ክርስቶስ ለኃጢአታቸው እንደ ሞተ ይናገሩ ነበር። በመሆኑም የዕብራውያን መልእክት ጸሐፊ በምዕራፍ 11 ውስጥ እውነተኛ እምነት ሁልጊዜም በሰዎች አኗኗር ላይ ለውጥ እንደሚያስከትል ከብሉይ ኪዳን ምሳሌዎችን ጠቅሶ ያብራራል። የሚያድን እምነት እንዲኖረን ከተፈለገ አእምሮአዊው እውቀት ወደ ተግባር መለወጥ አለበት።

ሀ) የእውነተኛ እምነት ገለጻ፡ “እምነትም ተስፋ ስለምናደርገው ነገር የሚያስረግጥ፥ የማናየውንም ነገር የሚያስረዳ ነው።” እምነት እንዲኖር ከተፈለገ፥ ሦስት ነገሮች መኖር አለባቸው። በመጀመሪያ፥ እግዚአብሔር ስለዚሁ ነገር የተስፋ ቃል መስጠት አለበት። እግዚአብሔር አንድ ነገር እንደሚከሰት እስካልተነገረ ድረስ፥ በዚህ ጉዳይ ላይ እምነት ሊኖረን አይችልም። እግዚአብሔር ይህንን ነገር እንደሚያደርግልን ተስፋ ልናደርግ ወይም ልንመኝ እንችላለን። ለምሳሌ፥ እግዚአብሔር መንግሥተ ሰማይ እንዳለች ስለተናገረ መንግሥተ ሰማይ እንዳለች እናምናለን። በመሆኑም ለምድራዊ ጥቅማ ጥቅሞች ብቻ ሳይሆን ለመንግሥተ ሰማይ ሕይወት በመዘጋጀት የዕለት ተዕለት ኑሮአችንን እንገፋለን።

(ማስታወሻ፡ አንዳንድ ሰዎች ይህንን የእምነት ገጽታ በመሳት እግዚአብሔር በግልጽ ተስፋ ያልሰጠው ነገር እንደሚፈጸም ማመናቸው እውነተኛ እምነት እንዳላቸው የሚያሳይ መሆኑን ይናገራሉ። ለምሳሌ፥ የቤተ ክርስቲያኒቱ ሽማግሌዎች እግዚአብሔር ትልቅ የቤተ ክርስቲያን ሕንጻ ለመገንባት የሚያስችል ገንዘብ እንደሚሰጣቸው በማመን ከእግዚአብሔር ግልጽ ማረጋገጫ ሳይቀበሉ ሥራውን ይጀምራሉ። በሥራው ሂደት የነበራቸው ገንዘብ ሕንጻው ከመጠናቀቁ በፊት ያልቃል። በዚህም ጊዜ በጅምር የቀረውን ሕንጻ እየተመለከተ ኅብረተሰቡ ያላግጥባቸዋል፤ ይሳለቅባቸዋል። እነርሱም ምንተ እፍረታቸውን ወደ ተለያዩ ሰዎች በመሯሯጥ ገንዘብ ይለምናሉ። ይህ አጉል ድፍረት እንጂ እምነት አይደለም። በመሆኑም እኛ እምነት ነው በምንለውና የእግዚአብሔርን ምሪት ባልተቀበልንበት ተግባር ሳቢያ የእግዚአብሔርን ስም እናሰድባለን። እግዚአብሔር ለአንድ ነገር ያለውን ምሪት በተለያዩ መንገዶች ሊገልጽ ይችላል። እርሱ በልባችን ውስጥ አንድን ነገር ለማከናወን መፍቀዱን ሊናገር ይችላል። ሌላ ጊዜ ደግሞ በቃሉ አማካኝነት ሊደርስ ይችላል። ለጠቅላላይቱ ቤተ ክርስቲያን ኃላፊነት የተጣለብን ሽማግሌዎች ከሆንን፥ እግዚአብሔር ፈቃዱ የሆነውን ነገር መንፈሳውያን ለሆኑት ሽማግሌዎች ሊናገር ይችላል። እነርሱም ፈቃዱን በመሻት በውሳኔው ይስማማሉ።)

ሁለተኛ፥ እምነት አለ የሚባለው እምነት የተጣለበት ነገር ሳይታይ ሲቀር ነው። ማንም ሰው ከበሽታው ከተፈወሰ በኋላ እግዚአብሔር ያድነኛል ብሎ ማመን አያስፈልገውም። እምነቱ የሚያስፈልገው ፈውሱ ከመምጣቱ በፊት ነው። መንግሥተ ሰማይ ከደረስን በኋላ ስለ መንግሥተ ሰማይ መኖር ማመን አያስፈልገንም። ምክንያቱም በገዛ ዓይኖቻችን እናያታለንና። ስለ መንግሥተ ሰማይ እምነት የሚያስፈልገው አሁን ነው። ምክንያቱም እኛ ባናያትም፥ እግዚአብሔር መንግሥተ ሰማይ እንዳለች ነግሮናልና።

ሦስተኛ፥ እምነት ሊኖር የሚችለው እግዚአብሔር በሰጠን የተስፋ ቃሎች ላይ በእርግጠኝነት በመመሥረት አኗኗራችንን ልንለውጥ ነው። ጸሐፊው በዚህ ምዕራፍ ውስጥ አጽንኦት ሰጥቶ የሚናገረው ስለዚሁ እምነት ነው።

የውይትት ጥያቄ፡- ሀ) እግዚአብሔር የአንተን እምነት ተጠቅሞ ያልተጠበቀ ተግባር የፈጸመበትን ሁኔታ በምሳሌነት ጥቀስ። በዚህ ጊዜ እነዚህ የእምነት ክፍሎች የታዩት እንዴት ነው? ለ) አንዳንድ ክርስቲያኖች እምነት አለን በሚል የሞኝነት ተግባራትን በምሳሌነት ግለጽ። በዚህ ሁኔታ ውስጥ የተፈጸመው ስሕተት ምንድን ነው? ከእነዚህ ሦስት የእምነት አላባውያን የጎደለው ምንድን ነው?

ለ) የድል ነሺ እምነት ምሳሌዎች (ማስታወሻ፡ የዕብራውያን መልእክት ጸሐፊ፥ እምነት ምን እንደሆነና በሕይወታችን ውስጥ እንዴት መታየት እንዳለበት በአይሁዶች ዘንድ ታላቅ ግምት የሚሰጣቸውን አብርሃምንና ሙሴን ለማብራሪያነት ይጠቀማል።)

ጸሐፊው በብሉይ ኪዳን የነበሩ ሰዎች እምነታቸውን እንዴት እንደ ገለጹና እግዚአብሔርም እንደ ሸለማቸው ሲገልጽ፥ ሀ) ምን ዓይነት እውነታ እንዳመኑ፥ ለ) ከዚሁ እምነት የተነሣ ምን ዓይነት ኑሮ እንደ ኖሩ፥ እና ሐ) የእምነታቸው ውጤት ምን እንደሆነ ያብራራል።

  1. በፍጥረት ማመን፡- ማናችንም እግዚአብሔር ዓለምን ሲፈጥር ስላልተመለከትን፥ ይህንን እውነት በእምነት መቀበል አለብን። ምክንያቱም እግዚአብሔር ዓለምን እንደ ፈጠረ፥ በዙሪያችን ያለውን ሁሉ በትእዛዙ ካለመኖር ወደ መኖር እንዳመጣ ይናገራል። ዓለም የዝግመተ ለውጥ (ኢቮሉሽን) ውጤት ናት የሚሉ ብዙ ሳይንቲስቶች ቢኖሩም፥ በእግዚአብሔር ቃል ላይ ያለን እምነት የሳይንቲስቶችን አሳብ በመቃወም መጽሐፍ ቅዱስን እንድናምን ይገፋፋናል።
  2. አቤል፡- እምነት አቤል እግዚአብሔርን እንዲታዘዝና በእርሱ ዘንድ ተቀባይነት ያለውን መሥዋዕት እንዲያቀርብ አድርጎታል። ይህም እግዚአብሔርን ባለመታዘዝ እምነት እንደሌለው ከገለጸው ከወንድሙ ቃየን የተለየ ነበር።
  3. ሄኖክ፡- እንደ ጎረቤቶቹ ላለመኖር በመወሰኑና ከእግዚአብሔር ጋር የግል ኅብረት በመፍጠሩ እምነቱን አሳይቷል። ከዚህም የተነሣ፥ እግዚአብሔር ሳይሞት በፊት ወደ መንግሥተ ሰማይ ወስዶታል።
  4. ኖኅ፡- እግዚአብሔር የጥፋት ውኃ እንደሚመጣ የነገረውን የተስፋ ቃል በማመን (ምንም እንኳን ዝናብ ባይታይም) መርከብ ሠርቶ እምነቱን አሳይቷል። ከዚያም የተነሣ፥ የተቀረው የሰው ልጅ በሙሉ ሲጠፋ እርሱና ቤተሰቡ ሊድኑ ችለዋል።
  5. አብርሃም፡- በተለያዩ መንገዶች እምነቱን አሳይቷል።

ሀ) ወደ አገሩ ወደ ዑር ሳይመለስ እንደ ዘላንና እንግዳ በመኖር። ምንም እንኳን እግዚአብሔር የከነዓንን ምድር እንደሚሰጠው የተስፋ ቃል ቢገባለትም፥ እርሱም ሆነ ልጁ ወይም የልጅ ልጁ ወደ ከነዓን አልገቡም። ነገር ግን እምነት እግዚአብሔር ተስፋ የገባላቸው የተሻለች የመንግሥተ ሰማይ ከተማ እንዲመለከቱ ዓይኖቻቸውን አቅንቶላቸው ነበር።

ለ) ምንም እንኳን የእርሱ እና የሣራ እድሜ ከማርጀቱ የተነሣ ልጅ የሚወልድበት ጊዜ ቢያልፍም፥ እግዚአብሔር ልጅ እንደሚሰጠው በማመን።

ሐ) የተስፋ ቃል ልጅ የነበረውን ይስሐቅን በመሠዋት። አብርሃም ይህንን ሊያደርግ የቻለው እግዚአብሔር ይስሐቅ የቤተሰቡን ዘር እንደሚቀጥል የሰጠውን የተስፋ ቃል እንደሚጠብቅና በቃሉም መሠረት እግዚአብሔር ለአብርሃም የገባቸውን የተስፋ ቃሎች እንደሚወርስ በመተማመን ነበር። በመሆኑም እግዚአብሔር ከሙታን እንደሚያስነሣው እርግጠኛ ነበር።

  1. ይስሐቅና ያዕቆብ፡- ከአብርሃምና ከእግዚአብሔር የተቀበሏቸውን በረከቶች በማስተላለፍ እምነታቸውን አሳይተዋል።
  2. ዮሴፍ፡- ከግብጽ ይልቅ ከነዓን የበረከት አገር መሆኗን በማመንና ሥጋው ከግብጽ ይልቅ ከነዓን እንዲቀበር በመጠየቅ እምነቱን አሳይቷል።
  3. የሙሴ ወላጆች፡- የፈርዖንን ትእዛዝ ጥሰው ሙሴን ባለመግደላቸው እና የገዛ ሕይወታቸውን ከአደጋ ላይ በመጣላቸው፥ እግዚአብሔር ልዩ የሆነ ልጅ እንደ ሰጣቸው ማመናቸውን ገልጸዋል።
  4. ሙሴ፡- በተለያዩ መንገዶች በእግዚአብሔር ላይ የነበረውን እምነት ገልጾአል።

ሀ) ካሳደጉት ግብጻውያን ገዢዎች ይልቅ የአይሁዳውያን ባሮች ወገን መሆኑን በመግለጽ እምነቱን አሳይቷል። የዕብራውያን መልእክት ጸሐፊ ይህ ሙሴ ከምድራዊ ምቾት ይልቅ እግዚአብሔርን (ክርስቶስ) እና የእግዚአብሔርን ሽልማት መምረጡን ያሳየበት መንገድ እንደሆነ ገልጾአል።

ለ) ሙሴ በኃያሉ አምላክ ላይ እምነት ስለነበረው ታላቁ ፈርዖንን ሊጋፈጠው መረጠ።

ሐ) ሙሴ የእግዚአብሔርን የሞት መልአክም ሆነ ቀደም ሲል በተመሳሳይ ሁኔት የተፈጸመ ተአምር ባያይም፥ በዕለተ ፋሲካ የእግዚአብሔርን ትእዛዛት ተግባራዊ ለማድረግ ወስኗል።

  1. የእስራኤልም ልጆች በሚከተሉት መንገዶች እምነታቸውን ገልጸዋል።

ሀ) እግዚአብሔርን ታዝዘው ቀይ ባህር ውስጥ በመግባታቸው። በዚህ ጊዜ እነርሱ በደረቅ መሬት ላይ ሲጓዙ፥ ግብጾቹ ግን በባህሩ ውስጥ ሰጥመዋል።

ለ) የሞኝነት ትእዛዝ የሚመስለውን የእግዚአብሔርን ቃል ተቀብለው በኢያሪኮ ዙሪያ ዞረዋል። እግዚአብሔርም የኢያሪኮን ቅጥር በማፍረስ የተስፋ ቃሉን ፈጽሞላቸዋል።

  1. ረዐብ፡– ይህች ሴት ጋለሞታ ብትሆንም፥ ስለ እግዚአብሔር የነበራትን እውቀት በመታመን ሕይወቷን አድናለች። ይህም ሊሆን የቻለው ከአይሁዶች ጋር በመተባበር ሰላዮቹን በመደበቅ ነው።
  2. ማጠቃለያ፡– ጸሐፊው በዕብ. 11፡32-35 በብሉይ ኪዳን ታሪክ ውስጥ እያሌ ክስተቶችንና ሰዎችን ይዘረዝራል። ይህም ታሪክ እግዚአብሔር በተለያዩ ሰዎች እምነትና ተግባራት ሳቢያ ተአምራት መሥራቱን የሚያመለክት ታሪክ ነው። ጸሐፊው ይህንን ያደረገው ለአይሁዳውያን ክርስቲያኖች የብሉይ ኪዳን ጀግኖቻቸው ሁሉ ታላቅነታቸውን ያገኙት ከእምነታቸ የተነሣ መሆኑን ለማስገንዘብ ነው። ለእግዚአብሔር ታላላቅ ሥራዎች እንዲሠሩ ያስቻላቸውም ይኸው እምነታቸው ነበር። እግዚአብሔር የሰጠውን የተስፋ ቃል ተቀብለው ተግባራዊ ማድረጋቸው ተአምራዊ ውጤቶችን አስገኝቶላቸዋል።

የውይይት ጥያቄ፡– ከራስህ ገጠመኝ፥ በእግዚአብሔር ላይ የጣልከው እምነት ታላቅ ውጤት ያስገኘበትን ሁኔታ ግለጽ።

ሐ) በምድር ላይ እምነት ስደትንና መከራን እንጂ ድል እንደማያስገኝ የሚያመለክቱ ማብራሪያዎች። ብዙውን ጊዜ ስለ እምነት በምናስብበት ወቅት፥ አእምሮአችን እምነት በሚያስገኛቸው ተአምራት ላይ ያተኩራል። በመሆኑም በዕብራውያን ምዕራፍ 11 የመጀመሪያው ክፍል ላይ አጽንኦት እንሰጣለን። ነገር ግን እምነት ሁልጊዜ የምንፈልገውን ተአምር ላያመጣልን ይችላል። በአብዛኛው እዚህ ምድር ላይ ጊዜያዊ ሥቃይንና መከራን ወይም ሞትን እንድንጋፈጥ ያደርገናል።

ጸሐፊው ይህንን ያልተሟላ የእምነት ገጽታ ለማሳየት፥ ከብሉይ ኪዳን ታሪክ፥ እንዲሁም በብሉይ ኪዳን መጨረሻና በአዲስ ኪዳን መጀመሪያ አካባቢ አይሁዶች ነጻነታቸውን ለማግኘት ጦርነትን ባደረጉባቸው ጊዜያት የተከሰቱትን ሁኔታዎች ይዘረዝራል። (በዚህ ወቅት የተፈጸሙትን አንዳንዶቹን ነገሮች ለመመልከት በአዲስ ኪዳን ቅኝት ክፍል አንድ፥ ትምህርት አንድ ላይ የተሰጠውን ትምህርት አንብብ።) እምነትና ታዛዥነት በእግዚአብሔር ልጆች ላይ ያስከተሏቸው አንዳንድ ችግሮች ምን ምን ነበሩ?

  1. ሥቃይ፥ እምነታቸውን በመካድ ከዚህ ሥቃይ ሊያመልጡ ይችሉ ነበር።
  2. የጓደኞቻቸውና የጎረቤቶቻቸው መሳለቂያ መሆን
  3. እስራት፥
  4. ሞት፣
  5. ድህነት፥ ይህም ቤቶቻቸውና ንብረቶቻቸውን ተነጥቀው በዋሻዎች ውስጥ እንዲኖሩ አድርጓቸዋል።

ጸሐፊው የእግዚአብሔር ሰው ማለት ምን ማለት እንደሆነ በመግለጽ ይህንን ክፍል የሚያጠቃልልበትን ሁኔታ መመልከት ጠቃሚ ነው። እግዚአብሔር በሚመርጥበት ጊዜ እምነት ተአምርን ወይም ታላቅን ድል ሊያስገኝ ይችላል። ብዙውን ጊዜ ግን ስደትንና መከራን ያስከትላል። በዚህም ጊዜ፥ ድል የሚገኘው ከትንሣኤ በኋላ በመንሥተ ሰማይ ይሆናል። በዕብራውያን 11 ውስጥ የተጠቀሱት ሁለቱም ወገኖች እምነት ነበራቸው። ልዩነቱ የእግዚአብሔር ምርጫ ነበር። እርሱ አንዳንዶችን ሲያድን (እንደ ጴጥሮስ፥ የሐዋ. 12፡3–13)፥ ሌሎች ደግሞ መከራን እንዲጋፈጡ ፈቅዷል። (እንደ ያዕቆብ፥ የሐዋ. 12፡2)። ብዙም ሳይቆይ የእነዚህ አይሁዳውያን ክርስቲያኖች እምነት የሚፈተንበት ሰዓት ይመጣ ነበር። አይሁዳውያን ወገኖቻቸው ስደትን በሚያበዙባቸው ወቅት በክርስቶስ ላይ የነበራቸውን እምነት ይተዉ ይሆን? ወይስ እምነታቸውን ከመካድ ይልቅ ለጊዜው በማይታያቸው የመንግሥተ ሰማይ ተስፋ ላይ ዓይኖቻቸውን ተክለው ስደትን ለመቀበል የመረጡትን ጀግኖች ምሳሌነት ይከተሉ ይሆን? እግዚአብሔር ዓለም አልተገባኝም ብለው በስደት የጸኑትን ሰዎች በከፍተኛ ደረጃ አክብሮአቸዋል። እኛስ በእምነታችን የእነዚህ የእምነት ጀግኖች ቡድን አባላት ነን?

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) የእምነት ሕይወት አሁን ስደትን በኋላ ደግሞ ድልን እንደሚያስገኝ ከማሰብ ይልቅ፥ ብዙውን ጊዜ አሁን ድል እንዲያስገኝልን የምንፈልገው ለምንድን ነው? ለእንዲህ ዓይነቱ የሚዛናዊነት መጓደል ከርስቲያኖች የጠበቁት ነገር በማይሳካበት ወቅት (ከበሽታ ወይም ከስደት ሊተርፉ በማይችሉበት ወቅት) እምነታቸው እንዲናጋ የሚያደርገው እንዴት ነው? ሐ) እግዚአብሔር እምነታችንን በማክበር ነፃ የሚያወጣን ጊዜ ይልቅ ነገሮች እንደጠበቅን በማይሆኑበት ጊዜ (በሽታ፥ የቤተሰብ ሞት፥ ስደት) በታማኝነት መጽናቱ እንዴት የበለጠ እምነትን እንደሚጠይቅ ግለጽ።

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading