መጽሐፍ ቅዱስን ለመተርጎም የሚጠቅሙ አጠቃላይ ሕጎች

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) እግዚአብሔር ለአንተ የተናገረባቸውን የተለያዩ መንገዶች ዘርዝር። ለ) በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ እግዚአብሔር ለሰዎች የተናገረባቸውን የተለያዩ መንገዶች ዘርዝር (ዕብ. 1፡1-2 ተመልከት)።

በዘመናት ሁሉ እግዚአብሔር ራሱንና ፈቃዱን ለሰዎች በተለያዩ መንገዶች ገልጿል። ለአንዳንዶች እግዚአብሔር በቀጥታ በሚሰማ ድምፅ ተናግሯል። ለሌሎች በሕልምና በራእይ ተናግሯቸዋል። አንዳንዶች የእግዚአብሔር ግፊት በልባቸው ይሰማቸዋል። እግዚአብሔር እስካሁንም ድረስ ራሱንና ፈቃዱን በእነዚህ መንገዶች የሚገልጽ ቢሆንም፥ ዛሬ ራሱንና ፈቃዱን የሚገልጥበት ዋና መንገድ መጽሐፍ ቅዱስ ነው። ይህ እውነት በጣም አስፈላጊ የሆኑ ሁለት ጭብጦችን ያስተምረናል፡

  1. እያንዳንዱ ክርስቲያን እግዚአብሔርን በጥልቀት ለማወቅ ብቻ ሳይሆን፥ የእግዚአብሔርን ፈቃድ ለማወቅና ለመታዘዝ ቃሉን የማንበብና የማጥናት ኃላፊነት አለበት። ክርስቲያን የእግዚአብሔርን ቃል ማንበብ ስለሚችል እግዚአብሔርን ላለመታዘዝ ምንም ምክንያት ማቅረብ አይችልም። ማንበብና መጻፍ የማይችሉ ክርስቲያኖች እንዲማሩ የሚያነቃቃቸው አንዱ ነገር የእግዚአብሔርን ቃል ለማንበብ እንዲችሉ ነው። መጽሐፍ ቅዱስ በእያንዳንዱ ነገድ ቋንቋ እንዲተረጎም የሚያስፈልግበት አንዱ ዋና ምክንያት ይህ ነው። እግዚአብሔር ፈቃዱ ከእኛ እንዲሰወር አይሻም፤ ይልቁንም እርሱን እንድናውቀውና በፈቃዱ እንድንኖር ይፈልጋል። መጽሐፍ ቅዱስ በእያንዳንዱ ሰው ቋንቋ ሊጻፍ ይገባዋል፤ ምክንያቱም ይህ ሲሆን ሰዎች ያነበቡትን ነገር በግልጥ ይረዱታል። በዚህ መንገድ ከእግዚአብሔር ጋር ኅብረት ማድረግና እርሱን የበለጠ በማወቅ ለፈቃዱ ታዛዥ መሆን ይቻላል።

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ለመጽሐፍ ቅዱስ ትርጓሜ ሥራ ድጋፍ ለማድረግ ስለ ቤተ ክርስቲያን መሪዎች ኃላፊነት ይህ ምን ሊያስተምረን ይገባል? ለ) የቤተ ክርስቲያን አባላት በግላቸው መጽሐፍ ቅዱስን ያጠኑ ዘንድ ለማበረታታት ስለ መሪዎች ኃላፊነት ይህ ምን ያስተምረናል? 

  1. እግዚአብሔር ከእኛ ጋር ግንኙነት ማድረግ የሚችልባቸው የተለያዩ መንገዶች በመጽሐፍ ቅዱስ ዳኝነት መመዘን አለባቸው። ብዙ ሐሰተኞች አስተማሪዎች ብድግ እያሉ እግዚአብሔር ተናግሮአል ይላሉ፤ ነገር ግን ተናግሮናል የሚሉት ነገር እግዚአብሔር በቃሉ በግልጥ ከተናገረው ነገር ጋር የሚቃረን ነው። ሰይጣንም ሕልምን መስጠት ይችላል። ሰይጣንም አንዳንድ ነገሮችን እንድናደርግ በልባችን ሊያነሣሣን ይችላል። እውነትን ከውሸት ለመለየት የምንችለው ሐሰተኛ አስተማሪዎች የሚናገሩትን ነገር ከእግዚአብሔር ቃል ጋር በማወዳደር ብቻ ነው። እግዚአብሔር የማይዋሽና የማይለወጥ ስለሆነ ዛሬ ለእኛ የሚገለጥልን ነገር ሁሉ በመጽሐፍ ቅዱስ ከገለጠው ነገር ጋር የግድ መስማማት አለበት። 

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) አንዳንድ ሰዎች እግዚአብሔር ተናገረን የሚሉበትን መንገድ ለመግለጥ የሚያስችሉ መግለጫዎችን ዘርዝር። ለ) ከመጽሐፍ ቅዱስ ጋር ስታወዳድረው እነዚህ ሰዎች የሚሉት ነገር ከእግዚአብሔር ጋር ይስማማል ወይስ ይቃረናል? ሐ) ሐሰተኛ አስተማሪዎች እግዚአብሔር ተናገረን ሲሉ ሰምተህ ታውቃለህን? መ) እግዚአብሔር በቃሉ እንዴት እንደተናገረህ የሚያስረዱ ምሳሌዎችን ጥቀስ።

መጽሐፍ ቅዱስ እግዚአብሔር ራሱንና ፈቃዱን ለሰው ልጆች የገለጠበትና ዛሬም የሚገልጥበት መንገድ ነው ካልን፥ ልጆቹ እንደ መሆናችን ቃሉን ማጥናት ተቀዳሚ ተግባራችን መሆን አለበት። እግዚአብሔር መጽሐፍ ቅዱስን የሰጠን ከእርሱ ጋር የግል ግንኙነት ለመመሥረት እንድንችል ነው፤ ስለዚህ ከእግዚአብሔር ጋር በጸሎት ብቻ ሳይሆን ያለማቋረጥ መጽሐፍ ቅዱስን በማንበብ ካልተገናኘን እግዚአብሔር እንድናውቀው የሚፈልገውን ያህል እርሱን አናውቀውም። 

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ብዙ ክርስቲያኖች የእግዚአብሔርን ቃል ለማንበብ በጣም ጥቂት ጊዜ የሚሰጡት ለምንድነው? ለ) የእግዚአብሔርን ቃል ከማንበብና ከመጸለይ በጣም አስፈላጊ የሆነው የትኛው ይመስልሃል? ለምን?

ከእግዚአብሔር ጋር ባለን ግንኙነት ያለማቋረጥ ልንከተላቸው የሚገባን ሁለት መንፈሳዊ ሥርዓቶች አሉ። ከእነዚህም አንዱ ጸሎት ነው። ብዙ ሰዎች በጸሎት ጊዜያቸውን ማሳለፍ ይወዳሉ። ለመጸለይ በማለዳ ይነቃሉ። ስለብዙ ነገር ይጸልያሉ። አንዳንድ ጊዜ ለእግዚአብሔር የልመና ጸሎት ብቻ ስለሚያቀርቡ ጸሎታቸው የስስታምነት ይሆናል። በጸሎታቸው እግዚአብሔርን ለማምለክና ለማመስገን ጥቂት ጊዜ ብቻ ይሰጣሉ። በጸሎት ከእግዚአብሔር ጋር እንነጋገራለን፥ እናመልከዋለንም። ደግሞም የከበደንን ነገር ወደ እርሱ ዘንድ በማምጣት እርሱ እንዲያቃልለው እንለምነዋለን፤ ነገር ግን እግዚአብሔር ለእኛ ሊናገረንና እርሱን ልናደምጠውም ይገባል። ሁለተኛው መንፈሳዊ ሥርዓት የእግዚአብሔርን ቃል ማንበብ ነው። የእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ እኛን የሚናገረን፥ የሚያበረታታን፥ የሚመራን፥ ራሱንና ፈቃዱን ለእኛ የሚገልጠው ወዘተ በቃሉ ነው። ክርስቲያን በመንፈሳዊ ሕይወቱ እንዲያድግ መጸለይና መጽሐፍ ቅዱስን ማንበብ ሚዛናዊ በሆነ መንገድ ሊከናወኑ ይገባል። ሁለቱም እኩል አስፈላጊዎች ናቸው።

የውይይት ጥያቄ፥ የዚህ ሳምንት የጸሎት ጊዜህን መርምር። ሀ) የእግዚአብሔርን ቃል ለማንበብ ምን ያህል ጊዜ እንደወሰድክ ተከታተል። ል) ለመጸለይ ምን ያህል ጊዜ እንደወሰድህ ጻፍ። ሐ አንተ ልታደርገው ቀለል የሚልህ የትኛውን ነው? ለምን? መ) በሕይወትህ ውስጥ ጸሎትንና የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናትን እንዴት የማያቋርጥ ልምምድ ማድረግ ትችላለህ? 

ብዙ ሰዎች መጽሐፍ ቅዱስን በተለይም ብሉይ ኪዳንን ለመረዳት በጣም አስቸጋሪ እንደሆነ አድርገው ይገምታሉ፤ ስለዚህ የሚወዱአቸውንና የሚረዱአችውን ክፍሎች ያነብባሉ። ለመረዳት የሚከብዱትንና አስቸጋሪ የሆኑትን ክፍሎች አያነብቧቸውም።

የውይይት ጥያቄ፥ ብዙ ጊዜ የማታነብባቸውንና ለመረዳት አስቸጋሪ የሚሆኑብህ ክፍሎች ያሉባቸውን የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት ዘርዝር።

ነገር ግን መጽሐፍ ቅዱስ በሙሉ የእግዚአብሔር ቃል ከሆነ፥ እግዚአብሔር ለእያንዳንዱ መጽሐፍና ምንባብ ዓላማ አለው፤ ስለዚህ መጽሐፍ ቅዱስን በሙሉ ማንበብና መረዳት ለሁላችንም ጠቃሚ ነው። በጣም አስቸጋሪ የሆኑ የብሉይ ኪዳን ክፍሎች እንኳ ስለ እግዚአብሔርና ስለ ፈቃዱ የሚገልጡት ነገር አላቸው። እጅግ ከባድ የምንላቸው ክፍሎች ሁሉ «ለትምህርት፥ ለተግሣጽ፥ ልብን ለማቅናትና ጻድቅ ለሆነ ምክር» የሚጠቅሙ ናቸው (2ኛ ጢሞ. 3፡16)፤ ስለዚህ እግዚአብሔር በቃሉ በሚገኙ የተለያዩ ክፍሎች በኩል ለእኛ ሊገልጥ የፈለገውን ፈቃዱን መረዳት ጠቃሚ ነው። ብሉይ ኪዳንን በምናጠናበት ጊዜ በጣም አስቸጋሪ በሆኑ መጻሕፍት ውስጥ እንኳ የእግዚአብሔር ዓላማና መልእክት ምን እንደሆነ ለመረዳት እንጥራለን። መጽሐፍ ቅዱስን ለመረዳትና በትክክል ለመተርጎም ስንፈልግ ልናስታውሳቸው የሚገቡ ሦስት መሠረታዊ እውነቶች አሉ፡-

  1. የመጽሐፍ ቅዱስ መሠረታዊ ትምህርት (መልእክት) ግልጥ ነው፤ ማንኛውም ክርስቲያን ሊያነበውና ሊረዳው ይችላል።

እግዚአብሔር የጻፈው የተደበቀ መልእክት አይደለም። ፈቃዱ እንዲታወቅና ልጆቹ ሁሉ እንዲከተሉት ይፈልጋል። እኛ ልጆቻችን በሚገባቸው መንገድ አንድን ነገር እንዲያደርጉ ትእዛዝ እንደምንሰጣቸው ሁሉ እግዚአብሔርም በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ትእዛዛቱን የሰጠው ክርስቲያኖች ሁሉ እርሱ የገለጠውን ነገር መረዳት በሚችሉበት መንገድ ነው። የእግዚአብሔርን ቃል በማስተዋል የሚያነብ ማንኛውም ክርስቲያን እግዚአብሔር ማን እንደሆነ፥ ሰዎች ኃጢአተኞች እንደሆኑና ክርስቶስ ለሰዎች ኃጢአት ሁሉ በመስቀል ላይ እንዴት እንደሞተ በቂ ግንዛቤ ያገኛል። የእግዚአብሔር ቃል መረዳት የተሰጠው «ለተማሩ» ወይም «በመጽሐፍ ቅዱስ» ወይም በሥነ መለኮት ትምህርት ዲግሪ ላላቸው ብቻ አይደለም። የእግዚአብሔርን ቃል ለማጥናት ሰፊ ጊዜ የሰጡና የብሉይ ኪዳንን ዘመንና ባሕል በከፍተኛ ሁኔታ የተገነዘቡ ሰዎች የበለጠ ሊረዱአቸው የሚችሉአቸው አስቸጋሪ የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርቶች ቢኖሩም፥ መሪዎች እንደመሆናችን መጠን መጽሐፍ ቅዱስ እኛ ብቻ ልንረዳው የምንችልና ለእነርሱ ግን በጣም ከባድ ነው ብለን ለቤተ ክርስቲያናችን ምእመናን በፍጹም መናገር የለብንም። በመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት መሠረት ክርስቲያኖች ሁሉ የእግዚአብሔር ካህናት ስለሆኑ፥ የእግዚአብሔርን ቃል በመንፈስ ቅዱስ እርዳታ ሊያጠኑና ሊተረጉሙት ይችላሉ (1ኛ ጴጥ. 2፡4-10፤ 1ኛ ዮሐ. 2፡27 ተመልከት)።

የውይይት ጥያቄ፥ ክርስቲያኖች መጽሐፍ ቅዱስን መረዳት የሚችሉት ልዩ መሪዎች ብቻ እንደሆኑ በማሰብ መጽሐፍ ቅዱሳቸውን ለራሳቸው ማጥናት በሚያቆሙበት ጊዜ አደገኛ የሚሆነው ለምንድነው?

  1. እግዚአብሔር ራሱንና ፈቃዱን ለሰው ልጆች ሁሉ በግልጽ ገልጧል። የጻፈው የተደበቀ መልእክት አይደለም።

ብዙ ክርስቲያኖች እግዚአብሔር መጽሐፍ ቅዱስን የጻፈው «በሰምና ወርቅ» ነው ብለው ያስባሉ። እግዚአብሔር መጽሐፍ ቅዱስ እንዲጻፍ በሚያደርግብት ጊዜ የተጻፈውን ነገር እውነተኛ ትርጉም ከቃላቱ በስተጀርባ ሰውሮታል ብለው ይገምታሉ። ስለዚህ መጽሐፍ ቅዱስን ለመተርጎም በሚሞክሩበት ጊዜ ዘወትር የተሰወረ ትርጉምን ይፈልጋሉ። የምናመልከው አምላክ ግን ራሱንና ፈቃዱን በምሥጢራዊ ቃላት የሚሰውር አይደለም። እግዚአብሔር እኛን በቀጥታ ይናገረናል፤ እንድናውቀውና እንድንታዘዘውም ይፈልጋል።

ጓደኛችን ስለ ሕይወት በማንሣት አንድ ነገር እንድናደርግለት በመጠየቅ ደብዳቤ ቢጽፍልን የተሰወረ ትርጉም ከደብዳቤው መፈለግ የተለመደ አይደለም። የጻፈውን መልእክት እንዳለ እንቀበለዋለን። የእግዚአብሔርም ቃል ከዚህ ጋር ተመሳሳይ ነው። በአንድ በኩል ስናየው እግዚአብሔር ለእኛ የጻፈው ደብዳቤ ነው። እግዚአብሔር ስለ ራሱ ይነግረናል። ደግሞም እስካሁን ምን ሲያደርግ እንደነበረና እኛ ምን እንድናደርግ እንደሚፈልግ ይነግረናል። እግዚአብሔር ራሱንና ፈቃዱን ምሥጢራዊ ትርጉም ያላቸውን ቃላት በመጠቀም መደበቅ ልማዱ አይደለም።

  1. ብዙ ጊዜ መጽሐፍ ቅዱስን ለመረዳት አስቸጋሪ የሆነው ከእኛ የተለየ ቋንቋ ለሚናገሩና በተለየ ባሕል ውስጥ ለሚኖሩ ሰዎች የተጻፈ በመሆኑ ነው።

ሁላችንም ብንሆን አንድን ነገር በምንሠራበት ወይም በምንናገርበት ጊዜ ሰዎች በተሳሳተ መንገድ ይረዱን ይሆንን? የሚል ፍርሃት ያደረብን ጊዜ ነበር። የራሳችንን ቋንቋ የሚናገሩና ከሁሉ በተሻለ ሁኔታ የሚያውቁን ቤተሰቦቻችን እንኳ አንዳንድ ጊዜ በተሳሳተ መንገድ ይረዱናል። በዕድሜ የገፉ አዛውንት ወጣቶችን፥ ወጣቶች ደግሞ አዛውንትን በተሳሳተ መንገድ ይረዷቸዋል። ይህ ደግሞ የተለያየ ቋንቋ በሚናገሩና የተለያየ ባሕል ባላችው ሰዎች መካከል ያለ ነው። በርካታ ያለመግባባቶች ሊፈጠሩ ይችላሉ። በተለይም በተሳሳተ መንገድ መረዳት ሊኖር የሚችልባቸው ሁለት ሁኔታዎች አሉ፡-

ሀ. የሰዎችን ቋንቋ በተሳሳተ መንገድ መረዳት፥ የእንግሊዝኛ ቋንቋ የምታውቁ ሰዎች ከአፍ መፍቻ ቋንቋችሁ ጋር አንድ ዓይነት ወይም ፍጹም ተመሳሳይ የሆነ ትርጉም የሌላቸው በርካታ የእንግሊዝኛ ቃላት እንዳሉ ትገነዘባላችሁ። በቋንቋችሁ ሁለት ዓይነት ትርጉም የሚሰጡ ቃላት ከእንግሊዝኛው ትርጉም የተለዩ ናቸው። ብሉይ ኪዳን የአይሁድ ቋንቋ በሆነው ዕብራይስጥ ተጻፈ። ወደ አማርኛ፥ ወደ ኦሮምኛ፥ ወይም ወደ እንግሊዝኛ በሚተረጎምበት ጊዜ መጀመሪያ በተጻፈበት በዕብራይስጥ የነበረውን ዓይነት ትርጉም እንዲሰጥ ማድረግ ከባድ ነው፤ ስለዚህ ነው ለአንድ ቃል የተለያዩ ትርጉሞች የሚሰጡት። የግዕዝን ቋንቋ የማያውቁ ወይም አማርኛ የመጀመሪያ ቋንቋቸው ያልሆነ ብዙ ኢትዮጵያውያን በቀድሞው የአማርኛ ትርጉም ውስጥ ያሉ አንዳንድ ቃላት ምንም ስሜት አይሰጧቸውም፤ ስለዚህ እግዚአብሔር ሊለው የፈለገውን ነገር በተሳሳተ መንገድ ሊረዱ ወይም የእግዚአብሔርን ቃል መረዳት ከባድ ሊሆንባችው ይችላል።

ለ. የሌሎችን ብሔረሰቦች ባሕል በተሳሳተ መንገድ መረዳት፥ ሁላችንም የምንኖረው በኢትዮጵያ ውስጥ ቢሆንም በአገሪቱ ውስጥ የተለያዩ ብሔረሰቦች መኖራቸው እርግጥ ነው። እያንዳንዱ ብሔረሰብ የራሱ የሆነ ባሕል ስላለው ከተለያዩ ብሔረሰቦች የሆኑ ሰዎች በአንድ ላይ ሲሆኑ፥ ብዙ ጊዜ አንዱ ሌላውን በተሳሳተ መንገድ ይረዳዋል፤ ለምሳሌ በአንዳንድ ባሕሎች ለአንድ ሰው አንድን ነገር በግራ እጅ መስጠት ነውር ነው። በሌሉች ባሕሎች ደግሞ በግራም ሆነ በቀኝ መስጠት ምንም ልዩነት አያመጣም። ለአንድ ባሕል ነውር የሆነው ነገር ለሌላው ባሕል ምንም አይደለም። ነገር ግን እንዲህ ዓይነት ቀላል ነገር ሳይቀር በሰዎች መካከል ያለመግባባትን ሊያመጣ ይችላል። በተመሳሳይ መንገድ ብሉይ ኪዳን የተጻፈው የራሳቸው ባሕል ላላቸው አይሁድ ነው። በኢትዮጵያ ውስጥ ለምንኖረው ለእኛ ወይም በተለይ ላለንበት ብሔረሰብ የተጻፈ አይደለም። ይህም ማለት አንዳንድ ጊዜ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ያሉትን አንዳንድ ክስተቶች በተሳሳተ መንገድ ልንረዳ እንችላለን ማለት ነው። ወይም ደግሞ አንድን ተግባር ላንረዳው ስለምንችል የብሉይ ኪዳንን አንዳንድ ክፍሎች ከሕይወታችን ጋር ለማዛመድ በጣም ልንቸገር እንችላለን።

በእነዚህ ሁለት መንገዶች መጽሐፍ ቅዱስን በተሳሳተ መንገድ መረዳት በጣም ቀላል ስለሆነ ሁለት ነገሮችን በማድረግ በተሻለ መንገድ ለመረዳት መሞከር አለብን፡- የመጀመሪያው በዚያ ስፍራ በሥራ ላይ የዋሉትን ቃላት ትክክለኛ ትርጉም መረዳታችንን ማረጋገጥ አለብን። ለእግዚአብሔር ቃል ያለንን ትክክለኛ መረዳት ያዛቡብናል ብለን የምናስባቸውን ቃላት በትክክል ለመረዳት የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላትና ሌሎች የማብራሪያ መጻሕፍትን መጠቀም ይኖርብናል። ለምሳሌ፡- ድነት (ደኅንነት)፥ መዋጀት፥ ቅድስናና ጽድቅ የሚሉት ቃላት ለአይሁዳውያን የሚሰጡትን ትርጉም መረዳት አለብን። ሁለተኛው ነገር፥ የእግዚአብሔርን ቃል በትክክል መተርጎም እንችል ዘንድና የአይሁዳውያንን ባሕል በትከክል ለመረዳት በመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላትና በሌሉች የማብራሪያ መጻሕፍት መጠቀሙ አስፈላጊ ነው። 

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) መጽሐፍ ቅዱስን በምናጠናበትና በምንተረጉምበት ጊዜ ከላይ የተጠቀሱትን ሦስት እውነቶች ልናስተውሳቸው የሚገባን ለምንድን ነው ብለህ ታስባለህ? ለ) እነዚህን መመሪያዎች የማይከተሉ ሰዎች በቤተ ክርስቲያን ውስጥ እንዴት የእግዚአብሔርን ቃል በተሰሳተ መንገድ እንደተረጎሙት ግለጥ።

ሰዎች የእግዚአብሔርን ቃል በተሻለ ሁኔታ እንዲረዱና እንዲተረጉሙት ለመርዳት የመጽሐፍ ቅዱስ ምሁራን ልንከተላቸው የሚገባን አንዳንድ መመሪያዎችን አዘጋጅተዋል። ዋናውና ጠቃሚው የእግዚአብሔር ቃል ምን እንደሚል እኛ የምናስበው ሳይሆን የእግዚአብሔር ሥልጣን ያለው፣ እርሱ በቃሉ የሚለውና የተናገረው እንደሆነ ልብ ማለት ያሻል። የራሳችንን መረዳት ከመጽሐፍ ቅዱስ እንደተገኘ ከመቁጠር ይልቅ፥ እግዚአብሔር በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በእርግጥ የሚለውን ነገር ለመረዳት መሻት በጣም አስፈላጊ ነው። የሚከተሉት ነገሮች ለእነዚህ ሕግጋት መግቢያ ብቻ ናቸው፡-

  1. የመተርጎም ሂደት በትክክለኛ ቅደም ተከተላችው ልናሟላቸው የሚገቡን የሁለት ጥያቄዎችን ቅርፅ የሚይዝ ነው። መጀመሪያ፥ የእግዚአብሔርን ቃል ለመተርጎም የሚፈልግ ሰው:- «መጀመሪያ ለጻፈው ሰውና መጀመሪያ ደርሶት ለሚያነበው ማለትም ለተጻፈለት ሰው የሚሰጠው ትርጉም ምንድነው?» ብሎ መጠየቅ አለበት። ብዙ ጊዜ ክርስቲያኖች የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሉ ምን እንደሚል ከመወሰናቸው በፊት፥ ከግል ሕይወታቸው ጋር ሊያዛምዱት ይሞክራሉ፤ ዳሩ ግን እግዚአብሔር ከአንድ ክፍል ውስጥ ምን እንደሚያስተምረን ከመወሰናችን በፊት በውስጡ ባስቀመጠው መልእክት አማካይነት ለተጻፈላቸው ለመጀመሪያዎቹ ሰዎች ምን ለማለት እንደፈለገ መረዳታችንን ማረጋገጥ አለብን። ይህንን ካደረግን ብቻ ክፍሉን ከራሳችን ሕይወት ጋር እግዚአብሔር እንድናዛምደው በሚፈልገው መንገድ ልናዛምደው እንችላለን። 

በሁለተኛ ደረጃ፥ «ይህ ክፍል ዛሬ ለእኛ ምን ማለት ነው?» የሚለውን ጥያቄ ለእራሳችን ማቅረብ አለብን ይህ ጥያቄ ሁልጊዜ ከመጀመሪያው ጥያቄ ቀጥሎ ሊመጣና ከእርሱም መልስ ጋር አብሮ ሊሄድ ይገባል። መጽሐፉ መጀመሪያ ሲጻፍ ምን ማለቱ እንደነበር በትክክል ለመወሰን ከቻልን ብቻ፥ ይህ ቃል ለዚህም ዘመን የሚሆን የእግዚአብሔር ቃል ነው ብለን በእርግጠኝነት ከሕይወታችን ጋር ልናዛምደው እንችላለን።

ብዙ ሰባኪዎችና አስተማሪዎች በዚህ ይሳሳታሉ። ብዙ ጊዜ ሊሰብኩት የሚፈልጉት ርእስ ይኖራቸዋል። ያንን ርእስ በአእምሮአቸው ይዘው ከርእሱ ጋር በአንድ ወይም በሌላ መንገድ የሚያያዙትን የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅሶች ይፈልጋሉ። የጥቅሶቹን ዓውደ-ንባብ በማጥናት መልእክቱ የተጻፈላቸው የመጀመሪያዎቹ ሰዎች የተረዱት ነገር ምን እንደሆነ ለማረጋገጥ ብዙም አይጥሩም።

እንዲሁም ቀድሞ ለነበሩት ሰዎች የተጻፈውን ብቻ በማጥናት፥ ዛሬ ከሕይወታችን ጋር በማዛመድ ልናገኘው የምንችለውን ትምህርት መተውም ስሕተት ነው። በክርስትና ሕይወት ውስጥ ሊያጋጥሙ ከሚችሉ አደጋዎች አንዱ የእግዚአብሔርን ቃል እንደታሪክ፥ ሒሳብ፥ ወይም ሳይንስ ለእውቀት ብቻ ማጥናት ነው። የእግዚአብሔር ቃል ሕይወታችንን ለመለወጥ የተሰጠ ነው። ሊለውጠን እንዲችል ካልፈቀድንለት፥ መንፈሳዊ ሕይወታችን ወዲያውኑ ይደርቃል። 

  1. ክፍሉን መጀመሪያ እንደተጻፈላቸው ሰዎች ለመረዳት እንድንችል የሚከተሉትን ነገሮች ማድረግ ያስፈልገናል፡-

ሀ. የምናጠናው የሥነ-ጽሑፍ ዓይነት ምን እንደሆነ በመወሰን በተጻፈበት የሥነ ጽሑፍ ዓይነት የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሉን ለመተርጎም መሞከር አለብን። 

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) በጽሑፋችን ወይም በስብከታችን የምንጠቀምባቸውን የተለያዩ የሥነ ጽሑፍ ዓይነቶች ዘርዝር። ለ) ከግልጋሎት ላይ የዋለው የሥነ -ጽሑፍ ወይም የንግግር ዓይነት ምን እንደሆነ መወሰን ለምን ይጠቅማል?

በየዕለቱ በምንገለገልበት ቋንቋ የተለያዩ ዓይነት የንግግር ዘዴዎችን እንጠቀማለን። በየዕለቱ ከምንጠቀምባቸው እነዚህን ከመሰሉ የንግግር ዓይነቶች በጣም ስለተላመድን የንግግሩን ዓይነት መሠረት በማድረግ በምናስብበት ጊዜ እንኳ መረዳትንና ትርጉሙን በሚመለከት እንለያያለን። ለምሳሌ፡- «እንቁላል ቀስ በቀስ በእግሩ ይሄዳል» የሚለውን ምሳሌ ስንሰማ ወዲያውኑ በዚህ ምሳሌ ውስጥ በጣም አስፈላጊው ነገር ቀጥተኞቹ ቃላት ሳይሆኑ ከምሳሌው በስተጀርባ ያሉ የሥነ-ምግባር ትምህርቶች እንደሆኑ እንረዳለን። በተጨማሪም «ሰምና ወርቅ»፥ ግጥሞች ታሪኮች ደብዳቤዎችና ልብ ወለድ ታሪኮች ወዘተ እንጠቀማለን።

በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ አራት ዋና ዋና የሥነ – ጽሑፍ ዓይነቶች አሉ። መጀመሪያ፥ በዘጸአት፥ በዘሌዋውያንና በዘዳግም እንዳሉት ዓይነት ሕጎች አሉ። በሁለተኛ ደረጃ፥ የታሪክ መጻሕፍት አሉ። እነዚህ የታሪክ የአጻጻፍ ስልቶች እንደ መጽሐፈ ኢያሱና መሳፍንት ባሉ በአብዛኛዎቹ የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት ውስጥ ይገኛሉ። ሦስተኛ፥ የግጥም መጻሕፍት ናቸው። አብዛኛው የብሉይ ኪዳን ክፍሎችና በተለይም መዝሙረ ዳዊት በግጥም የተጻፉ ሲሆን መልእክቱንም ለመግለጥ በተለያዩ ሥዕላዊ አገላለጾች ይጠቀማሉ። (ለምሳሌ፡- ዛፎች ሲዘምሩ እናያለን፤ (መዝ. [96]፡ 12)። አራተኛ፥ የነቢያት ቋንቋ ነው። እንደ ኢሳይያስና ኤርምያስ ባሉ አብዛኛዎቹ የትንቢት መጻሕፍት እንደሚታየው የነቢያት ቋንቋ የታሪክና የግጥም ድብልቆች ናቸው። ይህም የነቢያትን መልእክት ትክክለኛ አተረጓጎም የበለጠ ከባድ ያደርገዋል። ከእነዚህ አራት የሥነ ጽሑፍ ዓይነቶች የትኛውንም በምናጠናበት ጊዜ ልንጠቀምባችው የሚገባን የትርጉም ሕግጋት አሉ። ጥቂት ቆይተን የተለያዩ የሥነ ጽሑፍ ዓይነቶችን እንዴት እንደምንተረጉም የበለጠ እናጠናለን።

ለ. በክፍሉ የሚገኙ ቃላት መጀመሪያ መልእክቱን ለጻፈው ሰውና ለመጀመሪያዎቹ የመልእክቱ አንባቢዎች ምን መልእክት እንደሚያስተላልፍ አስቀድመን መረዳት አለብን። ይህም በተለይ በጣም አስፈላጊ የሚሆነው እንደ ጽድቅ፥ ቅድስና፥ ወዘተ ያሉ የሥነ መለኮት ትምህርት ቃላትን ስናጠና ነው። ደግሞም «የተቀደሰ እጃችሁን አንሡ፤ በጠንካራው የቀኝ ክንዱ፥ በተቀደሰ መሳሳም ሰላምታ ተሰጣጡ፤» ወዘተ ያሉትን ሥዕላዊ አነጋገሮች መጠቀም በሚመለከትም ረገድ ትክክለኛ ግንዛቤ መጨበጡ አስፈላጊ ነው። 

ሐ. መልእክቱ በተጻፈበት ጊዜ ስለነበረው ባሕልና የመጽሐፍ ቅዱስ ዘመን ሰዎች የቻልነውን ያህል ለመረዳት መጣር አለብን። መልእክቱ የተጻፈው አይሁድ በምርኮ በነበሩ ጊዜ ነው ወይስ በነፃነትና በብልጽግና ሳሉ ነው? በባርነት አገር ነበሩ ወይስ በራሳቸው ምድር? ገበሬዎች ነበሩ ወይስ የከተማ ነዋሪዎች? «እግዚአብሔር እረኛዬ ነው፤ እግዚአብሔር ዓለቴ ነው፤» ወዘተ የሚሉትን ቁልፍ አሳቦች ለመረዳት እነዚህ አስፈላጊዎች ናቸው። ለእግዚአብሔር የተሰጡት እነዚህ ስሞች የወጡት ከእስራኤላውያን የሕይወት ዘይቤ ሲሆን፥ በዚህ ዘመን ያላቸው መልእክት አንድ ላይሆን ይችላል። 

የውይይት ጥያቄ፥ መዝ. (18)፡2 ተመልከት። የብሉይ ኪዳን ጸሐፊ «እግዚአብሔር ዓለቴ፥ አምባዬ፥ መሸሸጊያ፥ ጋሻዬ፥ የደኅንነቴ ቀንድና መጠጊያዬ ነው» ሲል ምን ማለቱ ይመስልሃል?

የአይሁድን ባሕል ማወቅም በጣም አስፈላጊ ነው። ለምሳሌ አህያ ስለማንነዳ፥ የአይሁድ አህያን የመንዳት ሥዕላዊ ገለጻ አይገባንም። የአይሁድ ነገሥታት የመጡት በሰላም እንጂ እንደ ወራሪ ንጉሥ አለመሆኑን በአህያ ላይ ተቀምጠው በመሄድ ያሳዩ ነበር። ኢየሱስ በአህያ ተቀምጦ ወደ ኢየሩሳሌም በገባ ጊዜ እንደ ድል ነሺ ሳይሆን እንደ ሰላም ንጉሥ መምጣቱን ያመለክት ነበር።

መ. የምናጠናውን ክፍል ዓውደ ንባብ መመልከት አለብን። የምንመለከተው አንድ ቁጥርን ብቻ ከሆነ፥ ቁጥሩ ባለበት ክፍል የሚገኘውን ምዕራፍ በሙሉ ማጥናት አለብን። ከምናጠናው ክፍል ፊትና ኋላ ስላሉት ምዕራፎችም ማወቅ አለብን። ደግሞም ጸሐፍቱ ያንን መጽሐፍ በሚጽፉበት ጊዜ የነበራቸውን ዓላማ ማወቅ ይገባናል። ይህን የብሉይ ኪዳን ጥናት የምናጠናበት አንዱ ምክንያት የጸሐፊውን አጠቃላይ ዓላማ በተሻለ ሁኔታ እንድንረዳና ከዚያም የየክፍሎቹን ትርጉሞች ማስተዋል እንድንችል ነው።

አንድ ቃልና አንድ ቁጥር ትርጉም የሚያገኙት ባሉበት አንቀጽ ውስጥ ነው። ለምሳሌ በ1ኛ ቆሮ. 7፡2 ጳውሎስ ሲጽፍ፥ «ከሴት ጋር አለመገናኘት (አለማግባት) ለሰው መልካም ነው» ብሏል። ይህንን ጥቅስ ብቻ ብንመለከት፥ ማንም ሰው ማግባት የለበትም የሚል ትምህርት ልናስተምር ነው። ክርስቲያኖች ሁሉ ያላገቡ መሆን አለባቸው ልንል ነው፤ ነገር ግን አንቀጹን በጥንቃቄ ብንመረምረው ጳውሎስ ሳያገቡ እንዲኖሩ ሰዎችን የሚመክረው እግዚአብሔርን በተሻለ መንገድ ለማገልገል ዓላማ እንደሆነ እንመለከታለን። ጳውሎስ ስለ ዝሙት ጠንቅ ለእያንዳንዱ ለራሱ ሚስት እንድትኖረውም ይመክራል።

እንደ ይሖዋ ምስክሮች፥ ኢየሱስ ብቻ፥ ወዘተ ያሉ በርካታ የሐሰት መምህራን ትምህርታቸው የተመሠረተው ዓውደ ንባቡን በጥንቃቄ ባልተመራመሩባቸው አንድ ወይም ሁለት ጥቅሶች ላይ ነው።

ሠ. አንድን ጥቅስ ወይም ንባብ መተርጎም ያለብን በቀረው የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት መሠረት ነው። እግዚአብሔር መጽሐፍ ቅዱስን ለማስጻፍ ብዙ የተለያዩ ሰዎችን ቢጠቀምም፥ ጸሐፊው ራሱ ስለሆነ፥ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ያሉ አሳቦች በሙሉ እርስ በርስ መስማማት አለባቸው። እግዚአብሔር አይዋሽም፤ ደግሞም አይለወጥም፤ ስለዚህ በዘፍጥረት ያስተማራቸው ትምህርቶች ከሐዋርያት ሥራና ከራእይ ጋር የሚስማሙ መሆን አለባቸው። የአንድን ጥቅስ ትምህርት በማንረዳበት ጊዜ የቀረውን የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል በመመልከት መሠረታዊ ትምህርቱን ልንረዳ እንችላለን።

ረ. መጽሐፍ ቅዱስ አንዳች ስሕተት የሌለበት ቢሆንም፥ የእኛ ማስተዋልና ለመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርቶች የምንሰጠው ትርጉም ከስሕተት የጠራ ሊሆን አይችልም። መረዳታችን ውሱን የሆነ የሰው ልጆች እስከሆንን ድረስ፥ የመጽሐፍ ቅዱስን አጠቃላይ ትምህርት በሙላት ልንረዳ አንችልም። የእግዚአብሔርን ቃል ምን እንደሚል ለመረዳት የምንችለውን ያህል መጣር አለብን፤ ነገር ግን በአተረጓጎማቸው ከሌሎች ሰዎች ጋር ሳንስማማ ስንቀር ትሑታን ልንሆንና ልዩነቶችን ልናስተናግድ ይገባል። ይህም ማለት የትኛውም የጥናት መጽሐፍ ወይም የመጽሐፍ ቅዱስ ማብራሪያ መቶ በመቶ ትክክል ሊሆን አይችልም ማለት ነው። ጸሐፊዎቹ ስሕተትን ላለማስገባት የሞከሩ ቢሆንም፥ ውሱን መረዳት ያላቸው ሰዎች ናቸውና መሳሳታቸው አይቀሬ ነው። ይኸውም ሰባኪዎችና የቤተ ክርስቲያን መሪዎችም ሳይቀሩ ስሕተት ሊሠሩ ይችላሉ ማለት ነው።

የውይይት ጥያቄ፥ የሐዋ. 17፡11 ተመልከት። ሀ) የቤርያ ሰዎች የተመሰገኑባችው ነገሮች ምን ነበሩ? ለ) ሰባኪዎችን በምናዳምጥበት ወይም የመጽሐፍ ቅዱስ ማብራሪያዎችን በምናነብበት ጊዜ የቤርያ ሰዎችን ምሳሌነት መከተል ያለብን ለምንድነው?

ነገር ግን ልዩነቶች እንዲኖሩ በምንፈቅድበት ጊዜ ከመጠን በላይ ቻይና ታጋሽ (አቋም የሌለን) እንዳንሆን መጠንቀቅ አለብን። በመጽሐፍ ቅዱሳችን ውስጥ መሠረታዊ ትምህርቶች ላይ የአመለካከት ልዩነት ቢኖርም ትምህርቶችን በቀጥታ የሚቃወም ትርጉም ሊኖር አይችልም። ለምሳሌ «ኢየሱስ ብቻ» የሚባለው የሐሰት ትምህርት በተመረጡ ጥቂት ጥቅሶች ላይ ተመሥርቶ ሥላሴ እንደሌለ በመናገር መጽሐፍ ቅዱስ በግልጥ ያቀረበውን ትምህርት ይቃረናል፤ ስለዚህ ለተከታዮቹ ትክክል አለመሆናቸው ሊነገራቸው ይገባል።

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ሰዎች በቤተ ክርስቲያንህ ውስጥ በሚሰብኩበት ጊዜ ከእነዚህ ውስጥ በሚገባ ያልተጠቀሙባቸው ሕግጋት የትኞቹ ናቸው? ለ) የምንባብ አተረጓጎምን ለማረጋገጥ የሚረዱ፥ የምታውቃቸውን መጻሕፍት ዝርዝር ጻፍ። ሐ) የአንዳንድ ቃላትን ትርጉም ለመረዳት የሚጠቅሙ መጻሕፍትን ዝርዝር ጻፍ። መ) የብሉይ ኪዳንና የአዲስ ኪዳን ባሕል ለመረዳት የሚያስፈልጉ መጻሕፍትን ዘርዝር።

ለትክክለኛ ትርጉም ቁልፉ ምንድነው? በተቻለን መጠን የመጀመሪያው የመልእክቱ ተቀባይ አካል ለመሆን መጣር አለብን። አንድ ጊዜ የጸሐፊውን ዓላማ፥ የተጻፈላቸው ሰዎች የነበሩበትን ሁኔታ፥ ጸሐፊው የተጠቀመበትን የሥነ-ጽሑፍ ዓይነት ከተረዳን፥ እግዚአብሔር ለመጀመሪያ ተቀባዮች ያስተላለፈውን የመልእክት ትርጉም ለመረዳት እንችላለን። በዚህ ጊዜ ብቻ ከዘመናችን ጋር በትክክል እናዛምደዋለን። የእግዚአብሔር ቃል በታሪካዊ ዓውደ ንባቡ መሠረት ስንመለከተውና ስንረዳው በሥልጣን ልንሰብክና ልናስተምር፥ እንደ ብሉይ ኪዳን ነቢያትም «እግዚአብሔር እንዲህ ይላል» ልንል እንችላለን።

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

1 thought on “መጽሐፍ ቅዱስን ለመተርጎም የሚጠቅሙ አጠቃላይ ሕጎች”

  1. From Mulat Eticha
    Mathewes 28:1-8
    Jesus Has Risen
    After the Sabbath, at dawn on the first day of the week, Mary Magdalene and the other Mary went to look at the tomb. 2There was a violent earthquake, for an angel of the Lord came down from heaven and, going to the tomb, rolled back the stone and sat on it. 3His appearance was like lightning, and his clothes were white as snow. 4The guards were so afraid of him that they shook and became like dead men. 5The angel said to the women, “Do not be afraid, for I know that you are looking for Jesus, who was crucified. 6He is not here; he has risen, just as he said. Come and see the place where he lay. 7Then go quickly and tell his disciples: ‘He has risen from the dead and is going ahead of you into Galilee. There you will see him.’ Now I have told you.” 8So the women hurried away from the tomb, afraid yet filled with joy, and ran to tell his disciples.

Leave a Reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading