ኢያሱ 13-24

ክርስቲያን በሕይወቱ ከሚያጋጥሙት አደገኛ ነገሮች አንዱ ሰላምና በረከትን በሚያገኝ ጊዜ እግዚአብሔርን መርሳት ነው። ሙሴ ስለዚህ ጉዳይ በዘዳ. 8፡7-20 ባለው ክፍል እስራኤላውያንን አስጠንቅቆአቸዋል። የከነዓን ምድር በሙሉ ለእስራኤላውያን (ለአሥራ ሁለቱም ነገዶች) ከተከፋፈለ በኋላ እያንዳንዱ ሰው በተሰጠው ምድር አርፎ ሲኖር ሕዝቡ በዕለታዊ ተግባራቸው እየተጠመዱ በመፈተናቸው እግዚአብሔርን የመርሳት ከፍተኛ ዝንባሌ ታይቶባቸው ነበር፤ ስለዚህ ኢያሱ ሕዝቡን ሁሉ ወደ ሴኬም ጠራና ቃል ኪዳኑን አደሰ። እግዚአብሔርን ወይም ሌላን ነገር እንዲመርጡ፥ በቃል ኪዳኑ ስምምነት እንዲኖሩ ወይም በእግዚአብሔር ላይ እንዲያምፁ ምርጫ ማድረግ እንዳለባቸው አስገነዘባቸው። እኛም ልክ እንደ እስራኤላውያን ሁሉ ራሳችንን ለእግዚአብሔር ለመስጠት የገባነው ቃል ኪዳን ያለማቋረጥ መታደስ አለበት። በመጀመሪያ እንዳመንን ወይም ራሳችንን ለእግዚአብሔር እንደሰጠን የገባነው ቃል ኪዳን ያለማቋረጥ መታደስ አለበት፤ አለበለዚያ መንፈሳዊ ሕይወታችን እየቀዘቀዘ ይሄድና እግዚአብሔርን እንረሳለን።

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ሰላምና በረከት በሞላበት ጊዜ እግዚአብሔርን መርሳት በጣም ቀላል የሚሆነው ለምንድን ነው? ለ) ስለ ራስህ ሕይወት አስብ። በሙሉ ልብህ እግዚአብሔርን እንደምትወደውና እንደምትከተለው የገባኸውን ቃል ኪዳን ለመጨረሻ ጊዜ ያደስከው መቼ ነው? ሐ) እግዚአብሔር ስለ ሰጠህ በረከት ሁሉ እስቲ ለጥቂት ጊዜ አስብ። መ) ስለ እነዚህ ጉዳዮች ለአንድ አፍታ እርሱን አመስግን። ሠ) እግዚአብሔርን ለመከተል፥ እርሱን ሁልጊዜ ለማገልገል፥ በፊቱ በፍጹም ንጽሕና ለመመላለስ ወዘተ. የገባኸውን ቃል ኪዳን አድስ። 

የውይይት ጥያቄ፥ ኢያሱ 13-24 አንብብ። ሀ) ለካሌብ የተሰጠው ምን ነበር? ለ) የስድስቱ መማፀኛ ከተሞች ዓላማ ምን ነበር? ሐ) ለሌዋውያን ስንት ከተሞች ተሰጡአቸው? መ) የጎሣ ጦርነት ሊያስከትል የነበረ በምሥራቅ በሚገኙ ጎሣዎች የተፈጸመ ተግባር ምን ነበር? ሠ) ኢያሱ ከመሞቱ በፊት ለእስራኤላውያን የሰጠው ማስጠንቀቂያ ምን ነበር?

  1. የከነዓን ምድር ለእስራኤላውያን መደልደል (ኢያሱ 13-21)። አብዛኛው የከነዓን ምድር እንደተያዘ፥ እግዚአብሔር ለኢያሱ ምድሪቱን ለ12 ነገዶች እንዲያከፋፍል አዘዘው። እስካሁን ድረስ ያልተወረሩና ያልተያዙ ከተሞች በምድሪቱ ክፍል እንዲወርሱ የተደለደሉ ነገዶች የማስለቀቅ ኃላፊነት ነበረባቸው።

ሀ. ከዮርዳኖስ በስተ ምሥራቅ የሚገኙ ነገዶች፡- እንደምታስታውሰው፥ ሙሴ ከዮርዳኖስ በስተምሥራቅ የሚገኘውን ስፍራ ለሮቤል ለጋድ ነገዶችና ለምናሴ ነገድ እኩሌታ ሰጥቶ ነበር። አሁን ክልላቸው ተወስኗል።

ለ. ከዮርዳኖስ በስተምዕራብ የተደለደሉ ነገዶች፡- ለቀሩት ዘጠኝ ተኩል (9 የ2) ነገዶች ከዮርዳኖስ በስተምዕራብ የሚገኘው ክፍል ተሰጣቸው። በእግዚአብሔር ላይ ለነበረው እምነትና ጥንካሬ የይሁዳ መሪ ለነበረው ለካሌብ ልዩ ትኩረት ተሰጠውና የኬብሮንን ምድር አገኘ። ኢያሱ ለነገዶቹ ሁሉ የሚሆነውን ምድር ደለደለ፤ ክልላቸውን ወሰነ፤ በክልላቸው ውስጥ ያሉትንም ከተሞች ነገራቸው። ከዚህ በኋላ በክልላቸው ውስጥ የሚገኙትን ከተሞች ሁሉ የመያዝ ኃላፊነት የእነርሱ ነበር። እያንዳንዱ ነገድ ገና ወርሮና አሸንፎ የሚይዘው ክልል ነበረው። ከአሥራ ሁለቱ ነገዶች ዋና ዋና ለሆኑት፥ ለይሁዳ፥ ለኤፍሬምና ለምናሴ ነገዶች ስለተሰጠው ምድር ሰፊና ጥልቀት ያለው ትንተና ቀርቦአል።

ሐ. የመማፀኛ ከተሞች፡- በዮርዳኖስ በስተምሥራቅ ሦስት፡- በስተምዕራብ ሦስት፥ በአጠቃላይ ስድስት ከተሞችን እግዚአብሔር የስደተኛች ከተሞች ይሆኑ ዘንድ ለየ። የእነዚህ ከተሞች ዋና ዓላማ አንድን ሰው በስሕተት ለገደለ ሰው የጥበቃ ስፍራ ለመስጠት ነበር። ከሟቹ ሰው ዘመዶች ሊደርስበት ከሚችል ብቀላ ለመዳን ከእነዚህ ከተሞች ወደ አንዱ መሸሽ ነበረበት። የዚህ ዓይነቱ የፍትሕ ሥርዓት በእስራኤል ነገዶች መካከል በቤተሰባቸው ውስጥ በሞተ ሰው ምክንያት ሊፈጠር የሚችለውን በቀልና የእርስ በርስ ግጭት ለመከላከል ነበር። 

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ይህ መንገድ በምድሪቱ ሰላምን ለማስፈን መልካም የሆነው ለምንድን ነው? ለ) በቀል ፍለጋ ወደበለጠ ጦርነትና ጥፋት የሚመራው እንዴት ነው? ሐ ሮሜ 12፡17-21 አንብብ። ብዙ ክርስቲያኖች ይህንን ትእዛዝ የማይከተሉት ለምንድን ነው? መ) ክርስቲያኖች ብዙ ጊዜ እርስ በርስ በቀልን የሚፈላለጉት እንዴት እንደሆነ ምሳሌዎችን ስጥ። ሠ) ለእግዚአብሔር ቤተሰቦች ይህንን የማድረግ ውጤት ምንድን ነው?

መ. ምንም ምድር ያልተሰጣቸው ሌዋዊያን በ12 ነገዶች የመሬት ድልድል ውስጥ ተሰራጭተው ያሉ 48 ከተሞች ተሰጧቸው። በተጨማሪ ከተሞቹን የሚከቡ ለሰብልና ለከብቶቻቸው ግጦሽ የሚሆን መሬት ተሰጣቸው። 

  1. ምሥራቃዊ ነገዶች ወደ አገራቸው ተመለሱ (ኢያሱ 22)። ከዮርዳኖስ በስተምሥራቅ የሚገኘውን ሥፍራ የወረሱት ነገዶች በስተምዕራብ የሚገኘውን ምድር ለመውረስ ያሉትን 9 ½ ነገዶች ለመርዳት፥ እንደ እነርሱ ምድራቸውን እስኪወርሱ ድረስ ለመዋጋት ቃል ገብተው ነበር። ቃላቸውንም ጠብቀዋል። አብዛኛው የጦርነቱ ክፍል ተጠናቆ ስለነበር፥ ወደ ምድራቸው ለመመለስ ፈቃድ አገኙ። ወደ ስፍራቸውም ለመመለስ፥ ወደ ዮርዳኖስ ወንዝ በደረሱ ጊዜ የምሥራቁና የምዕራቡ ክልል ድንበር በሆነው ስፍራ ላይ ትልቅ መሠዊያን ሠሩ። የቀሩት እስራኤላውያን ግን፡- ይህን መሠዊያ የሠሩት 2 1/2 ነገዶች ጣዖታትን ለማምለክ ሲሉ ነው ብለው ገመቱ። ስለዚህ ቅዱስ በሆነ ቁጣ ወንድሞቻቸውን ለመውጋት ተነሡ። የትኛውም ነገድ ለዚህ ቃል ኪዳን የማይታዘዝ ቢሆን ፍርዱ የሚመጣው በሁላቸውም ላይ እንደሆነ ተገንዝበው ነበር። ነገር ግን የተሠራው መሠዊያ ዋናው ዓላማ፡- እነዚህ 2 1/2 የሚሆኑ ነገዶች የእግዚአብሔር ሕዝብ አካል ለመሆናቸው የቀሩቱ 9 1/2 ነገዶች፥ እንዲያውቁላቸው፥ ለማስታወሻ የተሠራ እንጂ ለጣዖት አምልኮ እንዳልሆነ ገለጡላቸው። እዚህ 2 1/2 ነገዶች በዮርዳኖስ ወንዝ አማካይነት ከሌሎቹ ነገዶች የተለያዩ ስለነበሩ እስራኤላውያን እንደ መሆናቸው መጠን ወደ እስራኤል ገብተው እግዚአብሔርን እንዲያመልኩ፥ እንደ ባዕዳን እንዳይቆጠሩ ቋሚ የሆነ ምልክት እንዲኖር ለማድረግ በመፈለጋቸው ነበር መሠዊያውን የሠሩት።

የውይይት ጥያቄ፥ እስራኤላውያን የተሳሳተ አምልኮ ወደ መካከላቸው እንዳይገባ ከነበራቸው ፍላጎት ምን እንማራለን?

  1. ኢያሱ ለእስራኤላውያን ያደረገው የስንብት ንግግር (ኢያሱ 23-24) ኢያሱ የመሞቻው ጊዜ እንደተቃረበ በማወቁ፥ ቃል ኪዳናቸውን እንዲያድሱ የእስራኤልን ነገዶች በሙሉ በአንድነት ጠራቸው። ለእግዚአብሔር ሕግ መታዘዝ እንዳለባቸው ለሕዝቡ ለማስታወስ ፈልጎ ነበር። ሕዝቡም ቃል ኪዳናቸውን በሴሎ አደሱ። ይህ ስፍራ እስከ ዳዊት ዘመን ድረስ የእስራኤል ሕዝብ ሃይማኖታዊ ማዕከል ሆነ። የመገናኛው ድንኳን ያረፈውና እስራኤላውያን ለአምልኮ ይመጡ የነበረው ወደዚህ ስፍራ ነበር።

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading