የመጽሐፈ ኢያሱ ዋና ትምህርቶች

የውይይት ጥያቄ፥ ከመጽሐፈ ኢያሱ ጥናት ከሕይወትህ ጋር ልታዛምድና በቤተ ክርስቲያንህ ላሉ ሰዎች ልታስተምር የምትችላቸውን መንፈሳዊ ትምህርቶች ዘርዝር።

  1. የከነዓንን ምድር ለአብርሃምና ለዘሩ ለመስጠት ቃል ኪዳን የገባው እግዚአብሔር የሰጠውን የተስፋ ቃል ኪዳን ፈጸመ፤ (ዘፍ. 12፡7፤ 15፡7፥ 18-21)። እግዚአብሔር ለእስራኤላውያን በከነዓን ምድር በሚኖሩ ሰዎች ላይ ድልንና የከነዓንን ምድር ርስት አድርጎ ሰጣቸው። እኛ አይሁድ ስላልሆንን እነርሱ ለከነዓን ምድር የነበራቸውን በስሜት የተሞላ ቅርበት ልንረዳ አንችልም። የተስፋይቱ ምድር እግዚአብሔር ከአብርሃም ጋር ደግሞም በሲና ተራራ ከገባው ቃል ኪዳን ጋር በቅርብ የተያያዘች ናት። እንዲያውም እስራኤል ከምድሪቱ ጋር ያላት ግንኙነት ለቃል ኪዳኑ ምን ያህል ታዛዥ ናት በሚለው ነገር ላይ የተመሠረተ ነበር። ለቃል ኪዳኑ አለመታዘዝ ማለት በነገሥታት ዘመን እንደሆንው ከምድሪቱ ተባርረው ይወጣሉ ማለት ነው። በንስሐ መመለስና ለቃል ኪዳኑ መታዘዝ ማለት እግዚአብሔር ወደ ሰጣቸው የተስፋ ምድር ይመለሳሉ ማለት ነው። አይሁድ በ1948 ዓ.ም. ወደ ከነዓን የመመለሳቸው ነገር እግዚአብሔር እስካሁንም ድረስ ለአይሁድ ቃል ኪዳኑን እየጠበቀ መሆኑን የሚያሳይ ምልክት ነው።

የክርስቲያን ርስት ከሚታይ መሬት ርስት ወይም ምድራዊ ተስፋ ጋር የተያያዘ አይደለም። የእኛ የተስፋ ምድር መንግሥተ ሰማያት ነው። እኛ የሰማያዊ አገር ዜጎች ነን። ቤታችን በዚያ ነው፤ የምንጓዘውም ወደዚያው ነው። አንድ ክርስቲያን ስለምድራዊ መሬት ወይም በምድር ስላለው ቤት ከሚገባ በላይ ትኩረት ሲሰጥ፥ በምድር ላይ የሚኖረው ለጊዜው እንደሆነና እውነተኛ ቤቱ በሰማይ እንዳለ ረስቷል ማለት ነው።

የውይይት ጥያቄ፥ የሚከተሉትን ጥቅሶች ተመልከት። ስለ ዘላለማዊ ቤታችን የሚናገሩት ነገር ምንድን ነው? ዮሐ. 14፡1-4፤ ዕብ. 11፡10፥ 16፤ ፊል. 3፡20።

  1. የእምነት ሕይወት የጦርነት ሕይወት ነው። ድል መንሣት ያለባቸው በርካታ ጠላቶች አሉ። ለአይሁድ ጠላቶቻቸው በአካል የሚታዩ አገሮች ወይም ነገዶች ሲሆኑ፥ ሊሸነፉ ያስፈልግ ነበር። ለክርስቲያን ሦስት ጠላቶች አሉት፤ እነርሱም፡- ሰይጣን፥ የዓለም ክፉ ሥርዓትና በሁላችንም ዘንድ ያለው የቀድሞው (አሮጌው) የኃጢአት ባሕርይ ናቸው። እነዚህን ጠላቶች የምናሸንፍበት ብቸኛው መንገድ የእግዚአብሔር ኃይል ነው። ይህንን ኃይል የምናገኘው በውስጣችን እንደሚሠራ ስናምን፥ ለእግዚአብሔር ሕግጋት ስንታዘዝና በቅድስና በመንፈስ ቅዱስ ኃይል ስንራመድ ነው።

እግዚአብሔር ለአይሁድ የሠራዊታቸውና የሰማይ ሠራዊትም አዛዥ እንደሆነ አስተምሮአቸዋል። ለሕዝቡ ለመዋጋት እንደተዘጋጀ መለኮታዊ ተዋጊ ሆኖ እንመለከተዋለን፤ (ኢያሱ 10፡14)። በነቢያትና በቅኔ መጻሕፍት ውስጥ ሁሉ እግዚአብሔር ታላቅ ተዋጊ ሆኖ እናየዋለን። እስራኤላውያን በእግዚአብሔር ትእዛዝ ያካሄዱት ማንኛውም ዓይነት ጦርነት ቅዱስ ጦርነት ነበር።

ክርስቲያኖች እንደመሆናችን መጠን በአካል የሚታይ ሥጋዊ ጦርነት የለብንም። ክርስቲያኖች መብታቸውን ለማግኘት ኃይልን መጠቀም ስሕተት ነው። ጦርነታችን መንፈሳዊ ነው፤ (ኤፈ. 6፡12)። ክርስቶስ እኛ ያለንበት መንፈሳዊ ጦር መሪ ነው፤ ስለዚህ ለእርሱ ትእዛዝ መገዛት አለብን። ለእርሱ በመታዘዝ በእርሱ ርዳታ ብቻ የሚያጋጥሙንን መንፈሳዊ ጠላቶች ለማሸነፍ እንደምንችል መገንዘብ አለብን።

የውይይት ጥያቄ፥ ኤፌ. 6፡12። ሀ) ጳውሎስ የሚናገረው ስለማን ነው? ለ) እነዚህን ጠላቶቻችንን የምንዋጋውና የምናሸንፈው እንዴት ነው? ሐ) ለጦርነቱ ማረጋገጫ የሚሆኑ አንዳንድ ነገሮች ከሕይወትህ ጥቀስ።

  1. ድል ለማግኘት በሚኖረን ብቃት ውስጥ የእግዚአብሔር ቃል ዕከላዊ ነው። በመጽሐፈ ኢያሱ ውስጥ በእግዚአብሔር ቃል ላይ ከፍተኛ ትኩረት ተሰጥቷል። የእግዚአብሔርን ቃል፥ በቃል ልናጠና፥ ልንረዳውና ልንታዘዘው ያስፈልጋል፤ (ኢያሱ 1፡7-8፤ 23፡6 ተመልከት)።
  2. በመንፈሳዊ ሕይወት ውስጥ ድል፥ በሦስት ነገሮች ላይ የተመረኮዘ ነው፡- 

ሀ. ነገሮችን በራሳችን ጥበብና ብርታት ከማድረግ ይልቅ ኃይል እንዲሰጠን በጌታ ላይ መታመን አለብን። 

ለ. የእግዚአብሔርን ቃል ልንረዳውና ልንታዘዘው ያስፈልጋል።

ሐ. በእግዚአብሔር ፊት የተቀደሰ ሕይወት መኖር አለብን። 

የውይይት ጥያቄ፥ ከእነዚህ ሦስት ነገሮች ክርስቲያኖች ብዙ ጊዜ የማይጠብቋቸውና በዚህም ምክንያት በመንፈሳዊ ሕይወታቸው የሚሸነፉባቸው የትኞቹ ናቸው?

  1. እግዚአብሔር ከሁሉ የባሱ ኃጢአተኞችን ይቅር ይላል። ከዚያም በእርሱ ዕቅድ ውስጥ እጅግ ጠቃሚ ሚና እንዲጫወቱ ያደርጋል። ምንም ስፍራ የለውም የምንለው ሰው እንኳ በእግዚአብሔር ዕቅድ ውስጥ እጅግ ጠቃሚ ቦታ አለው። ረዓብ ጋለሞታና አሕዛብ ነበረች። ምንም ተስፋ የሌላት ሴት ነበረች። በእግዚአብሔር ከጥፋት ዳነች። ከይሁዳ ቤት የሆነውን ሰው አገባችና በሥጋ ኢየሱስ ከመጣበት ከዳዊት የዘር ሐረግ ውስጥ ተቆጠረች። ከአዳም ጀምሮ በአብርሃም፥ በዳዊት፥ ከዚያም በኢየሱስ ክርስቶስ የተዘረጋው የድነት (ደኅንነት) መስመር ውስጥ ገባች።
  2. የጌታ ሠራዊት አዛዥ የነበረው ያለምንም ጥርጥር ኢየሱስ ክርስቶስ ነበር። እርሱ የነገሥታት ንጉሥ የጌቶችም ጌታ ነው። አንድ ቀን ከሰማይ ሠራዊት ሁሉ ጋር ይገለጥና የእግዚአብሔርን ጠላቶች ሁሉ ያሸንፋል፤ ራእይ 19፡11-21 ተመልከት)።

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) መጽሐፈ ኢያሱ በድል ስለመመላለስ ለማስተማር ክርስቲያኖችን እንዴት ይጠቅማቸዋል? ለ) ለቤተ ክርስቲያንህ አባሉች ይህን መጽሐፍ እንዴት እንደምታስተምር ዕቅድ አውጣ።

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

1 thought on “የመጽሐፈ ኢያሱ ዋና ትምህርቶች”

Leave a Reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading